እንዴት እንተማመን?

ሰሞኑን ከባቡር መንገድ ስራው ጋር በተያያዘ የአቡነ ጴጥሮስና የአፄ ምኒልክ ሀውልቶች ይነሳሉ፡፡ የሚል ያልጠራ ወሬ ይዘን ብዙ ስንልና ስንባል ነበር የከረምነው፡፡ እግዜር ይስጣቸው፣ ብስጭቱ ስኳር ደማችንን ከፍ አርጎት ሳይደፋን በፊት ብቅ አሉና… የአንዳንድ ፀረ ልማት ሀይሎች አሉባልታ ወሬ ነው፡፡ ለደህንነቱ ሲባል መንገዱ እስኪያልቅ ድረስ የአቡነ ጴጥሮስ ሀውልት ይነሳና፣ መንገዱ ሲያልቅ ይመለሳል፡፡ የእምዬ ምኒሊክ ሀውልት ግን ጭራሽ አይነካም፡፡ ምናምን… ብለው አረጋጉን፡፡

ከዚያም በኋላ ቃላቸውን እንደሚጠብቁ እንዴት እናውቃለንና እንመናቸው? የሚለው የብዙ ሰው ስጋት አዘል ጥያቄ ሆነ፡፡ እኔም ደገምኩ! – እንዴት ነው የምናምናቸው? ማንም ጤናማ አዕምሮ ያለው ኢትዮጵያዊ መንገድ በመሰራቱ፣ አገር በመልማቱ፣ ብልፅግና በመምጣቱ…ቅር አይለውም ብዬ አስባለሁ፡፡ እኛው ኗሪዎቹ ነን በመንገዱ የምንሸልልበት፡፡ እነሱ እንደው አንዴ ተሸፋፍነው ከመረቁት ወዲያ፣ ሞተው (የሰይጣን ጆሮ ይደፈን) አስከሬናቸው ካልሆነ በአዲስ አበባ መንገድ አይምነሸነሹም፡፡

ምናልባት አንዳንዴ መውጫና መግቢያ መንገድ ሲሆን (እንደ ቦሌ) በዝጉ ላስ ላስ የሚሉበት ሁኔታ ይኖር ይሆናል እንጂ፡፡… መንገድ ማዘጋታቸውም ቢሆን አመል ሆኖባቸው ክባድ ሲፈጥሩ እንጂ፣ ኑሮና እነሱ ተባብረው ዐይናችንን ጋርደውት፣ የአገሩ መንግስት ይለፍ የእድሩ ዳኛ መንግስቱ መች እንለይና? – መሰለኝ!

ያም ሆነ ይህ ግን በአቡነ ጴጥሮስ ሀውልት ተነስቶ መመለስ ጉዳይ ዙሪያ፣ እንዴት እንመናቸው? ነው ጥያቄው፡፡ ሲጀምር የሰዉ አፀፋ ምን ሊሆን እንደሚችል በመገመት (አሉባልታም ሆን ምን ከመስማታችን አሊያም ከመፍጠራችን በፊት) አካሄዱን የተመለከተ ነገር በዚያ ቆርቆሮ ወቆረቆራም ቲቢ በኩል ሰው ወክለው ሊያሳውቁን ይገባ ነበር፡፡ የነሱ ዝምታ ነው እኛን ያስቀባጠረን፡፡ በዝምታቸውም አሸበሩን! ቅሉ ንጉስ አይከሰሰ….

ሲቀጥል ደግሞ ከዚህ በፊት ብዙ ቁማሮች ላይ ያፈሩብን እፍርታሞች ናቸው፡፡ ሌላ ሌላውን ብተወው እንኳን ሁለት ነገሮችን አይረሱኝም፡፡ ያኔ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ስንትና ስንት ወንድምና እህቶቻችን ደማቸውን ካፈሰሱ በኋላ (እኛም ሆ….ብለን በነቂስ ወጥተን፣ በሞራልና በወኔ ሞልተን ሸኝተን ለፈሰሰው ደም ከተባበርን በኋላ)፣ ጦርነቱንም ማሸነፋችንም ታውቆ ድህረ ድልም (post victory) ሸልለን … ‘ባድመ እኮ belongs to ‘em’ ብለው አረዱን፡፡

የኢትዮጵያችንን የሰው ዘር መገኛነት ጮክ ብላ የምታቀነቅነው ሉሲም (ሰላም መጥታ እስክትቀናቀናት ድረስ) አሜሪካ ለስድስት ዓመታት ጉብኝት ፈታ ብላ ትምጣ ተብሎ ከሄደችበት መመለሷን አልሰማንም፡፡ ጥገኝነት ጠይቃ ነው መሰል በዚያው የውሀ ሽታ ሆና ቀረች፡፡ ስድስት ዓመቱ ባለፈው ጥቅምት ደፍኗል፡፡ እንዲያውም ‘አሜሪካ ሄደሽ፣ አወቅሽ፣ ነቃሽ…ሀሳቤን የመግለፅ መብቴን ምናምን አልሽ…’ ተብሎ የአሸባሪ መዝገብ ምናምን ሊከፈትላትም ይችላል፡፡

እንግዲህ ጎብኚዎች እንዳይጉላሉ በማሰብ ተጎብኚውን ቦታቸው ድረስ በማድረስና የተቀላጠፈ አገልግሎት በመስጠት ረገድ እኛን ማን አህሎን?…. ደግሞስ ማን ያውቃል? – አቡነ ጴጥሮስ ሰማዕትነትን በጭካኔውና በላዩ ላይ፣ በታላቅ ኩራት የተቀዳጁበትን ፋሽስት ጣልያን ሄደው ይሸልሉበት፣ ህዝቡንም ይቅርታ እያስጠየቁ ያስገብሩት (ያባት እዳ ለልጅም አይደል?) ምናምን ተብሎ መንገዱ እስከሚያልቅ ድረስ ደርሰው ይመለሱ ቢባልስ ምን እናውቃለን?

እኛና ጣልያን እንደው ድንጋይ በመወራወር ስር የሰደደና ዓለምን ያስናቀ ልምድና ታሪክ ነው ያለን፡፡ ያኔ…አያቶቻችን በዘመናዊ ጦር የታጠቀውን ቡርቂ ጡርቂ የጣሊያን ሠራዊት በድንጋይ፣ በጦርና በጎራዴ ቂጥ ቂጡን እያሉ አባረሩት፡፡ ጣሊያንም ድል ማድረግ አልሆን ሲለው፣ አገሩ ሲመለስ ባዶ እጁን እንዳይሆን ብሎ…የከበረና ታሪካዊ ድንጋይ ይዞ ፈረጠጠ፡፡ ወደ ሮም፡፡

(እዚህ ጋር የአክሱም ሀውልትን ክብርና ዋጋ በማሳነስ ሳይሆን የተቀረፀበት ቁስ ድንጋይ መሆኑን በማሰብ ብቻ ያልኩት መሆኑ ይታወቅልኝ፡፡ የጨዋ ልጆች ነን፡፡ ሀውልትን – ‘ድንጋይ’፣ ባንዲራን – ‘ጨርቅ’ አንልም፡፡)

‘ከቅንፍ ስንወጣ’ – አለ አቤ ቶኪቻው፣….ከቅንፍ ወጥተን ሌላ ቅንፍ ውስጥ ብንገባስ? – መብታችን ነው፡፡ ህገ – መንግስታዊ መብታችን፡፡ እናም ሌላ ቅንፍ ውስጥ ገባን… ምሽግ መሆኑ ነው፡፡ (ያኔ የጣሊያን ሰራዊት መጀመሪያ ከጀግኖች አርበኞቻችን የተዘነዘረበትን ጥቃት ለመመከት፣ እንደ ጦር መሳሪያ ሊጠቀምበት አስቦ ነበር… ከቦታው የነቀለውና ይዞ መሮጥ የጀመረው፡፡ ኋላ ላይ ግን ነገሩ ከግምቱና ከአቅሙ በላይ ሆኖበት በእኛው አንበሶች ቀኝ ኋላ ዙር ሲባል ጊዜ፣ በዚያው ይዞት ሮም ገባ፡፡ (በደመነፍስ ሮጦ…) ከዚያም የቅሌትና ልክን የማወቅ ዘመኑን ያስተውሰው ዘንድ አደባባይ ላይ ተከለው፡፡ ምናምን ብለን እናሽሟጥ እንዴ፡፡

ከዚያም በኋላ….ኢትዮጵያውያን በተለያዩ ምክንያቶች ሮም ሲሄዱ ሀውልቱን ተደግፈው ፎቶ ሲነሱ ኖረው ኖረው…. ከዕለታት በአንዱ ቀን በፀሀዩ መንግስታችን የአክሱም ሀውልት አስመላሽ ብሔራዊ ኮሚቴ ተዋቀረና አክሱማችን ወደ ጦቢያችን ተመልሳ ዳግም ከመንበሯ ላይ ተሰየመች፡፡ ደስም አለን፡፡ በልባችን ዘንባባ ዘንጥፈን እንደ አዲስ ጨፈርን፡፡ በልጅነት ቀልባችንም፣ ይሄ የድንጋይ ቅብብል (ቅልብልቦሽ ልንለውም እንችላለን፡፡) ቢያስገርመንና ቢረቅብን ጊዜ…. በኩልትፍና እንዲህ ብለን ነበር….

የስልጣኔ ጥግ…
ድንጋይ ከአገር አገር
ያግዝ ያንሸራሽር፣
ያወራውር ጀመር፡፡

/ዮሐንስ ሞላ/

ተሽከርክረን ወደ ዋናው ጉዳይ ስመለስ…በበኩሌ፣ ጉዳዩ መንገድ አይሰራ ሳይሆን፣ እንድናምናቸው አድርገው አላሳደጉንምና እንዴት እንመናቸው? የሚለው ነው፡፡

ያልተዘመረለት – ‘የተረገመው ባለቅኔ’!!

ሁሉም ቢያገኘው፣ሁሉም ቢያነበው፣ ሁሉም ቢረሰርስበት፣ ሁሉም ቢማርበት፣ ሁሉም ቢያውቀው፣ ሁሉም ቢደመምበት፣ ሁሉም ቢያከብረው፣ ሁሉም ቢዘምርለት…ብዬ ብጓጓ፤ምድር በጥበቡ ከመረስረሷ ባሻገር፣ ነፍሱ ባለችበት ሀሴት ታደርጋለች፣….ብዬ ባስብ…. ከትናንት በስትያ (ወዳጄ አብዲ ሰይድ “ወፍዬ”ን ለጥፎ ቢቆሰቁሰኝ) ያልተዘመረለትና በወጉ ሳይታወቅ ያለፈው ታላቅ ገጣሚ ሙሉጌታ ተስፋዬ የባለቅኔ ምህላ መፅሀፍ ድጋሚ ይታተም ዘንድ ስንዱ አበበን ስጠይቃት፣ (ኮፒው በእጄ ቢኖርም፣ ቢያንስ የህትመት ወጪዋን አንባቢው ይጋራ ዘንድ፣ የርሷን (የአሳታሚዋን) ፈቃድና መብት እንዳልጋፋ በመፍራትና… መፍራቴን በመግለፅ…)

(እዚህ ጋር አብዲ በአበበ ተካ ወፍዬ ተቆስቁሶ…የተዘነጋ ገፅ በሚል ርዕስ የከተባት ማስታወሻ ብዙ ትጨምራለች፡፡ እኔም ይህችን እከትብ ዘንድ በእጅጉ ወስውሳኛለች፡፡)

በመጀመሪያ ህትመቱ ብዙ ብር በመክሰሯ ድጋሚ እንደማታሳትመው፣ ሶፍት ኮፒውን ግን ለኢትዮጵያ ህዝብ ነፃ ስጦታ ይሆንላት ዘንድ በመሻት ለወዳጆቼ ባካፍልላት ደስታዋ መሆኑን ገለፀችልኝ፡፡  በፊት ከነበራት በሚጠልቅ ደግነት፡፡ ቀድሞ በአሳታሚ ድርጅቷ በኩል ካሳየችን በሚልቅ ርህራሄ፣ ፍቅርና ቅርበት፡፡ለነገሩ ወትሮም የርሷ ጉዳይ ጥበቡን መዝራት፣ ተሸጦ ገቢ ቢኖረው በትርፉ ሌላ ያልተዘመረለትን አንስታ ለማዘመር እንጂ መች ሌላ ሆኖ….፡፡

መቼም ጉኖዬን (ሙሌክስ እንደሚጠራት) አለማመስገን በብዙ ፍቅር አለማክበርና ስለርሷም  አለመዘመር አጉል ስስት ነው የሚሆነው፡፡ አድሮ የሚቆጠቁጥስስት፡፡ ከሄዱ በኋላም የሚያሸማቅቅ፡፡ እነሆ የመፅሀፉን ኮፒ ከዚህ ጋር ተያይዞ ይገኛልና ረስርሱበት፡፡ ፍቅርና ክብራችሁን ለፀሀፊው ለሙሉጌታ ተስፋዬ እና ለአሳታሚዋ (እንዲሁም አሳታሚዋ አመስግኑልኝ ላለቻቸው) እያበረከታችሁ አንብቡት፡፡ አንብባችሁ ስትወዱት ደግሞ ባላችሁበት ዘምሩለት፡፡ ሌሎችም ይዘምሩለት ዘንድ አስተላልፉት፡፡

Yebaleqine-Mehela

እኔ ሙሌን ሳስበው እንባ ይቀድመኛል፡፡ ሳላውቀው የቆየሁበት (በዘፈን ግጥሞቹ ተወስኜ) ጊዜ ይቆጨኛል፡፡ መሀላችን አለመኖሩ ያንገበግበኛል፡፡ በኖረና ብዙ በፃፈ….በኖረና ቋጠሮዎቹን በፈታ…. እያልኩ፡፡ እንደ አዲስ ዳስ ጥሎ፣ ንፍሮ ቀቅሎ ለቅሶ መቀመጥ ያምረኛል፡፡ ግና መፅሀፉን ከመደርደሪያዬ ላይ አንስቼ ጠረግ ጠረግ አድርጌ ማንበብ ስጀምር እንባዬ ይታበሳል፡፡ ብዙ መኖሩ ይሰማኛልና ቁጭቴን ሁሉ በደፈናው “ከንቱ” እለዋለሁ፡፡ ከንቱ ሀዘን፡፡ ደርሶ በጥበቡ የሚበርድ፡፡አንዳንድ ጊዜ ስቃዥ ደግሞ ቆሪጡን ማግኘትና ማናዘዝ ያሰኘኛል፡፡

የግጥምቆሪጡን፡፡  የቅኔዛሩን፡፡ ማስለፍለፍ….ማስቀባጠር…ማናዘዝ… ከስር ከስሩ እየተከተሉ መቃረም…. ወደኗሪውማጋባት… አይ ሙሌክስ፣ …እርሱን ሳስብና ሳገኝ(እድሜ ለስንዱ) እንዲህ ብቻ አይደለም የምሆነው፡፡ የቃላትን ስንፍና የሚያሳይ ብዙ የማይገለፅ ነገር፡፡ በቃላት ለመጫወት መፍጨርጨሬን (ግጥም መፃፍ መሞከሬን)ማ ስንት ጊዜ እንደሚኮረኩመው፡፡ ስንት ጊዜ እንደሚያሸማቅቀው…. የተረገመ!! ዛሩንባገኘው ኖሮ ግን ስንት ነገር አናዝዘው ነበር…. ስንት ነገርስ እቃርም ነበር…. እግሮቹ ስር ቁጭ ብዬ፣ ቢፈቅድ ፀጉሬን እየደባበሰ…. ቲሽ! አጉል ቅዠት!!

በመግቢያው ላይ ስብሀት ገ/እግዚአብሔር (ነፍሱን ይማረውና) እንዲህ ብሎ ነበር… (አቤት…ከሙሌክስ ጋር ሲገናኙ ግን እንዴት ሆነው ይሆን? … ምናልባት ለስንዱ ደብዳቤ ከላኩላት ታስነብበናለች፡፡ እርሷ እንደው ደግነቷ ብዛቱ…፡፡)

ሙሉጌታ ግን ከቅዳሴ እስከ ቅኔ፣ ከዛም ተሻግሮ ቁርአን፣ ሀዲስንና መንዙማን የሚያውቅ ምሁር ነው፡፡ ይህም ባንዳንዶቹ ግጥሞቹ ውስጥ ይታያል፡፡ እግዜርንም ሸይጣንንም በእኩል ንቀት እየገረመመ ሲያናግራቸው እንደ ዳኛ ነው፡፡ ምንም ምክንያት ሳላገኝለት እውስጤ የሰረፀ ጥርጣሬ አለኝ፡፡ በሞተበት ቦታና ሰዓት ከሰይጣን ጋር እየተፋጠጠ፣ እየተናነቀ ነበር ይሆን…

እዝጌርም ሰይጣንም የለም የሚሉ አንባብያን ሁሉ፣ እዝጌርም ሰይጣኑም የመለሱለት የራሱ ህሊና የፈጠረቻቸው ህልም ወይም ቅዠት ናት በሉ፡፡ ሌላ ማለት ብትፈልጉም መብታችሁ በህገ-መንግስቱ የተጠበቀ ነው፡፡

ስንዱዬ ደግሞ በምናቧ ከሙሌ ያስላከቸው ደብዳቤ ደግሞ እንዲህ ይቀነጨባል፡፡….

በምድር ስኖር ለግሌ ብዬ ያከማቸሁት ምንም ነገር አልነበረም፡፡ እንግዲያውስ በእርዳታ ድርጅት ውስጥ ከመስራት እስከ ኢህዴን – ብአዴን – ኢህአዴግ ድረስ ታገልኩ! በግሌ ያገኘሁት ነገር፣ መናቅ፣ መዋረድ፣ ለዐይን አለመሙላት ሆነ፡፡ ዋጋና ችሎታዬን ያወቁና የተረዱ ‹‹ጓዶች›› እንኳን የሚፈልጉኝና የሚያስፈልጉኝ ‹‹የድል በዓል›› በሚል ሰበብ ቅኔ እንድቀኝ፣ ግጥም እድገጥም፣ በአጭሩ የድግሳቸው አድማቂ፣ ተራ ‹‹አዝማሪ›› የሆንኩ እስኪመስለኝ መጎሳቆል ተሰማኝ፡፡

ይህንን ይሁን ብዬ ጓዶቼን ፈትቼ፣ ህዝቤንም አምኜ፣ ችሎታዬን ለዘፋኞች ልሰጥ አልኩና ተነሳሁ፡፡ ገበያው እጅግ የደራ ከመሆኑ የተነሳ እንኳን ሌላ ነገርሽን ከዐይንሽ ላይ ኩልሽን ሊሰርቁሽ የሚችሉ ሰዎች የበዙበት ሆነ፡፡ ይህን ትልቅ የገበያ ስፍራ ለመቀላቀል ስንት አሳር እንደቆጠርኩ ዛሬም ሳስበው ይዘገንነኛል፡፡ በቃ የስልጣናቸው የመጨረሻ ዳር ድንበር አሁን ትዝ አለኝ! ‹‹የኢኮኖሚው ባለቤት የፖለቲካውም ዋና ባለቤት›› እንደሆነው ሁሉ የስራው ባለቤቶች ነጋዴዎች ብቻ ሆኑ፡፡

‹‹እኔ እበላ – እኔ እበላ›› እያሉ ከሚሻሙት ጋር ለጨው፣ ለበርበሬ፣ ለውሎ ለአዳሩ እንኳ ብዬ አብሬያቸው ለመቆየት አቃተኝ፡፡ ይልቅ ጠጋ ያሉኝ ጋር በማርያም መንገድ፣ በማተብ፣ በክርስትና ለየግል ተነጋግረን፣ ቀኑን አሳምረንን ዱአ እያደረግን፣ ተፈጥሮንና ፈጣሪን ሳይቀር እየተፋጠጥን አብረን ጎጆ ልንወጣ ሰርተን ፈረንካው ሲገኝ ዐይኔን ለማየት እንኳ ይፀየፋሉ፡፡ አልፈው ተርፈው ብኩርናዬን ሳይቀር እንድሸጥላቻ ሁሉ ጠየቁኝ፡፡

ጉኖዬ – እንጂማ እኔ ወንድምሽ፣ ጥንቅቅ፣ ጥንፍፍ ያልኩ ጀግና ነኝ፡፡ ቅሱስም ንጉስም እሆናሁ አላልኩሽም ነበር… ካልሆንኩ ኋላ ትታዘቢኛለሽ፡፡ ለጊዜው ‹‹ብርዕ በደም ዕንባ››፣ ‹‹አንተሙሽር››፣ ‹‹ከመንበርህ የለህማ››፣ ‹‹ከነዓን ነው ዘንድሮን›› ግጥሞቼን ብቻ እንኳ ልጥቀስልሽ፡፡ እያደር እንደምትሰሙኝ ተስፋ አለኝ፣ ታዲያ እኔ እንዴት አባቴ አድርጌ ብኩርናየን ልሽጥ?!

ወደ ሁለት ሺህ የሚጠጉ ግጥሞችን፣ ሁለት ቲያትሮችን (ደጀ ሰላምንና ግምሻን) እና በርካታ ዘፈኖች ሰርቻለሁ፡፡ ውድነሽ በጣሙ፣ አማራ ነኝ ያውም ደሜ አረንጓዴ (ራዲዮ ፋና ሰነበው ቀድቶኛል፣ ጠይቀሽ ስናፈቅሽ ደግመሽ ስሚው፡፡ ‹‹ከመንበርህ የለህማ›› ኢትዮጵያ ሬድዮ ነበር፡፡ …እና ታዲያ ጉኖዬ አንቺ ግን ‹‹ጉዳዬ ሞተብኝ!›› ብለሽ በጣም ያዘንሽው ለእኔ ነው?

ይልቅስ ለሁሉም ሰው ይቅርታ መድረጌንና ይህ አካሄድ በእኔ ቢያበቃ ደስ እንደሚለኝ ንገሪልኝ፡፡ የሰራሁትን፣ ሀቄን፣ ገንዘቤን አንድጄ ብሞቀው እንኳ የሚያገባው እንዳልነበረ ደሞ መንገር እንዳትረሺብኝ!!

ቀብሬን ለማከናወን በእጅጉ የተባበሩሽን ጓዶቼን፣ መላ ጓደኞቼንና ቀባሪዎቼን አመስግኝልኝ፡፡ በምድር ሳለሁ አብረን የተሽከረከርናቸው ሰፈሮች የማስታውሳቸውን የምድር ጀለሶቼን አለምገናዎችን፣ ተረት ሰፈርን፣ ፈረንሳይ ለጋሲዎኖችንና ስድስት ኪሎዎችን፣ ቅድስት ማርያሞችን፣ ዶሮ ማነቂያዎችን፣ ሀብተጊዮርጊስ ድልድዮችን፣ አጠና ተራዎችን፣ ሰንጋ ተራዎችን….መላውን ወዳጆቼን ‘እንገናኛለን እኔ አልቆርጥም ተስፋ!’ ብሏል በይልኝ፡፡

ከልጆቼ ቀጥሎ የወለድኳቸውን ስራዎቼን እያስታወሳችሁ ‹‹አደራ ልጄን አደራ›› የሚለውን የብፅዓት ስዩምን ዘፈን እንድትሰሙልኝም ጋብዘዤያችኋለሁ፡፡ ጉኖዬ – ሆድ ሲብስሽ ደግሞ የሀና ሸንቁጤን ‹‹ሆዴ ባለአብሾ››ን ስሚ፡፡ በጣም ደግሞ የአበበ ተካን ‹‹ወፍዬ››ንም ስሚ!

ስሚ እንጂ …አንድ ቀን ‹‹ያንተን የተለያዩ ዘፈኖች መደዳውን ዛሬ አራት በኤፍ ኤም ሰማሁ›› ብለሽ በልብሽ ያጨበጨብሽልኝን ዕለት አስታውሼ ምን ትዝ አለኝ መሰለሽ… ያወጣሁላቸው ስሞች! ታምራት ‹‹ሀኪሜ ነሽ››፣ መሰረት ‹‹ጉም ጉም››፣ ፀደንያ ‹‹ገዴ››፣ ብፅአት ‹‹ገዳዬ››፣ ሸህ አብዱ ‹‹ሀዋብስል›› ኸረ ስንቱን አድምቄዋለሁ አያ!…ምንስ ቢሆን ሙሉጌታ ተስፋዬ ወዲ ሀለቃይ! ተጋዳላይ ነኝ እኮ!…

ከመፅሀፉ ላይ አሟልታችሁ ድገሙት፡፡ (ገፅ 133 – 135)

እስኪ ‘እውነት ከመንበርህ የለህማ’ን ፣ ቀንጭቤ ነገሬን ልቋጭ፡፡ወትሮም ለአመሌ ነው መቀባጠሬ እንጂ፣ መፅሀፉንካ ወረደ በኋላ ማን ይሰማኛልና?!

ምነዋ መንግስተ ሰማይ! የምህረትሽ ቀን ራቀ?
ምነው ትንግርትሽ ረቀቀ?
ምነው ኪዳንሽ ታጠፈ….ወዝሽ ወዘናሽ ነጠፈ?
እንደ ዳጉሳ ድፍድፍ….ላቦትሽ ተንጠፈጠፈ
አሳርሽ ጠሎ አሰፈፈ

ምነው እርሾው ተሟጠጠ….ጎታው ጎተራው ታጠጠ
ረሀብ ላንቃው ፈጠጠ….ያዳም ልጅ አፅሙ ገጠጠ
ምነው ጭር አለ ቀየው! ሀሩር ነዲዱ በረታ
ኮርማው ጥማዱ ተረታ

ምነው ነበልባሉ አየለ! ማሳው ተንቀለቀለ?
ነቀለ ሞፈር ሰቀለ! ተገድራ ደቀለ
ምነው ምድር ጨነገፈች….ዝላ ተርገፈገፈች?
ካስማ እንደተደገፈች ምነው ሳታብብ ረገፈች፡፡

ምነው የናት ጡት ደረቀ…..አራስ ልጅ ተስረቀረቀ?
ምነው አንጀቱ ታለበ….በውኑ ተለበለበ?
ኮሶ ስንብቱን ለለበ
ምነው ወላድ ተነስለሰለ….ልሳነ ቃሉ ሰለለ
በቁሙ ቆስሎ ከሰለ፡፡

አቤት የርግማን ቁርሾ…
በንጣይ እርሾ መነሶ
ምነው ላይፀድቅ በቀለ
የሰው ልጅ ዋጋ ቀለቀለ
ትቢያ አፈር ተቀላቀለ፡፡
ሆድና ጀርባው ተጣብቆ
አንጀቱ በራብ ተሰብቆ
እንደፈረሰ ክራር ቅኝት
ሰርቅ እንዳነቀው ድብኝት….

ከመፅሀፉላይጨርሱት፡፡ (ገፅ 11)

ከዚህ ወዲያ ሽብር?!

አካላዊ ጥቃቶች (physical violences)

ባል ሚስቱን ደብድቦ ገደለ፣ ሚስት ባሏን ገደለች (የአቅምም ሁኔታ ታክሎበት ነው መሰል፥ ይሄ ብዙም አይሰማም። ሲሰማም ሞቱ እንኳን ለህብረተሰብ ጆሮ ወንጀሉን ለሚፈፅሙት ሴቶችም ድንገቴና አስደንጋጭ ነው የሚሆነው።) ፣ ልጅ አባቱን ገደለ፣ ልጅ እናቱን ገደለ፣ ባል ሚስቱን አቆሰለ፣ ሚስት ባሏን አቆሰለች፣ አሲድ ደፋባት፣ አሲድ ደፋችበት፣ ዐይኗን አጠፋት፣ ከፎቅ ወረወራት፣ በስለት ወጋችው….ሌላም ሌላም በተለያዩ  ምክንያቶች ተፈፀሙ የተባሉ የተለያዩ ዓይነት ጥቃቶችን በተለያዩ ጊዜያት ስንሰማ ኖረናልና፥ ነገሩን ጆሮአችን ለምዶታል። ያም ሆኖ እንዲህ ያሉትጥቃቶች ብዙ ጊዜ በደፈናው ይድበሰበሱና ‘ፆታዊ’ በሚል ስም ይጠቀለላሉ። ‘ህፃን ደፈረ’ማ ተነግሮንም ሳይነገረንም የሚገጥመንን የመብራት ፈረቃ ያህል እንኳን የማያስገርመን ነገር ሆኗል።

በወቅቱ ወሬውን ስንቀባበል፣ ስንሰበሰብ፣ ስናራግብ፣ስንፅፍ፣ ስናነብ፣ ነገሩን ስናወግዝ፣ “እግዚኦ” ስንባባል እንከርምና ወዲያው ወከባ በበዛበት የኑሮ ባህራችን ውስጥ እንደ አንዳች ነገር ጠብ ብሎ ይረሳል።ይደክመናል። ወይም ደግሞ ተከትሎ የሚመጣውን የፍርድ መጠን እንገምተውና ወሽመጣችን ቁርጥ ብሎ ጉልበታችንን ይወስነዋል። ያም ሆኖ… ድንጋጤና ሀዘኑ ባይሆን እንኳን ወሬ መቀባበልና ነገሩን ማውገዙም ቢሆን ብዙ ጊዜ በአድልዎና በቲፎዞ የሚደረግ ነው።ብቻ ግን የአንድ ሰሞን ጉድ ሆኖ ይከርማል። ወዲያው ደግሞ ይረሳል። ህይወት ትቀጥላለች።ምናልባት በሌላ የከፋ የወንጀል ዓይነት እየተተካና “የባሰ አታምጣ” እያስባለን።  – የሞተ ቀረበት!

እንዲህ ያለውን ነገር በፊት ፖሊስና ህብረተሰብ ፕሮግራም ላይ ሲተላለፍ እናቴ “ቅጣቱን አብረው ካልነገሩ ባያወሩት ይሻላል። ካልሆነ አዲስ ዘዴ ነው የሚያስተምሩብን።” ትል ነበር። እውነት ነው። አንድ ዓይነት የወንጀል ዘዴ በዜና ሰበብ ለህብረተሰቡ ከተዋወቀ በኋላ በቀጣይ ተመሳሳይ የወንጀል ዓይነቶች ሲፈፀሙ እንሰማለን። ለዚህ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነን አሲድ በመድፋት ጥቃት ማድረስ ነው። እንደ ቀልድ ተፈፅሞ (ምናልባት መጀመሪያ የደፋው ሰው ‘ይሁን’ ብሎም ሳይሆን በአቅራቢያው ስላገኘው ብቻም ሊሆን ይችላል።) እንደ ጉድ ተወራ፣ ከዚያም አሲድ መደፋፋት ተለመደ። ጆሮአችንም ለመወደው። እንዲህ ነን እኛ።

የቤት ሰራተኛዋ አሰሪዋንና ሁለት ልጆቻቸውን ገደለች

ዛሬ በጠዋቱ ከሸገር 102.1 የሬድዮ ጣቢያ የሰማሁት ጉድ ደግሞ ለጆሮዬ እንደመርግ የከበደ ነው። ምናልባት ከመሰል የሰራተኛ አሰሪ ጥቃቶች ጋር እስክንላመድ ድረስ። በርግጥ ሰራተኛ አሰሪን ሲበድል የመጀመሪያ አይደለም። ሆኖም ከዚህ በፊት የተለመደው ልጆችን ማጥቃት እንጂ እንዲህ ቤተሰብ መፍጀት አልነበረም። ወይም እኔ ስሰማ ይሄ የመጀመሪያዬ ነው። ፈፃሚና ተፈፃሚው ዞሮ ያው ሰው መሆኑ ከከዚህ በፊቶቹ ወንጀሎች ባይለየውም የጥቃት አድማሱ እንዴትና ወደየት እየሰፋ መሄዱን አጉልቶ ያሳየናል። ሸገር ላይ የተሰማው ወሬ “የቤት ሰራተኛ አንዲት ሴት ወይዘሮንና ሁለት ልጆቻቸውን ገደለች።” ብሎ ይጀምርና እንዲህ ያብራራል።…

“በሻሸመኔ ከተማ አንዲት የቤት ሰራተኛ በደመወዝ ጨምሩልኝ ሰበብ በተነሳ ጭቅጭቅ አሰሪ ወይዘሮዋንና ሁለት የአራት ዓመትና የሰባት ዓመት ልጆቻቸውን በተኙበት በመጥረቢያ ደብድባ ገደለቻቸው። ድርጊቱን ፈፅማ ለጊዜው ተሰውራ የነበረ ቢሆንም በፖሊሶችና በአካባቢው ነዋሪዎች ክትትል በወላይታ ሶዶ ከተማ ውስጥ ከተደበቀችበት ተገኝታለች።” (ቃል በቃል አልፃፍኩትም።)

የደቡብ ሰዎች (ወላይታዎች መሰሉኝ) እንዲህ ያለ፥ ለጆሮ ከባድ ነገር ሲገጥማቸው (ሲሰሙ) ‘ጎንዶሮ!’ ይላሉ። ‘አያድርስ’ እንደማለት ነው። አያድርስ ቢባልም ግን እነሆ ደርሶ የቤተሰቡ ህይወት ተቃርጧል። መቼስ ሁሉም በራስ ደርሶ ይታይ አይባል። ሆኖም… – ጎንዶሮ!

ምን ሰይጣን አሳታት?

መቼስይሄምድርጊት ማብራሪያ አያጣም ይሆናል። ምናልባት ወንጀለኛዋ የመክፈል አቅምና ፈቃድ ያለው የቅርብም ሆነ የሩቅ ቤተሰብ ካላት የሚቆምላት ጠበቃም አታጣም። ሰብአዊ ተቆርቋሪ ነን ባይ ኗሪዎችም ድርጊቱን በጓሮ መንገድ አዙረው ከሰራተኛ አያያዝና ከአሰሪዎች በደል ጋር አያይዘውት፥ ትንታኔ ሰጥተውበት ቢያንስ ለኗሪ ህሊና የወንጀለኛውን አጢሀት ሊያቀሉ ይሞክሩ ይሆናል። ወይ ደግሞ የወንጀለኛዋን የትምህርት ደረጃና የማሰላሰል ሁኔታ ተንትነው፣ ቢያንስ ልባቸውን አሳምነው በልባቸው ምህረት ያደርጉላትም ይሆናል። (ለነገሩ ይሄ በፍርድ ቤትም ቢሆን ዓይነተኛ የፍርድ ማቅለያ መሆኑን በተለያየ ጊዜ ታዝበናል።)

ከዚህ የሚተርፈው አብዛኛው የማህበረሰብ  ክፍል ግን እንዲህ ያለው ነገር ሲከብደው “ምን ሰይጣን አስቶት/ቷት ነው?” በሚል ቆራጣ አረፍተ ነገር ጠቅልሎት፥ አጢሀቱን ሁሉ ሰይጣን ላይ ነው የሚያላክከው። ይሄ ነቢይ መሆን ወይም ጥናት አያሻውም። ይልቅስ ያለፉ የወንጀል ታሪኮችንና ህብረተሰባዊ ትንታኔዎቻቸውን ማስታወስ በቂ ነው። ሰይጣን ግን ፈረደበት። የምር አንጀቴን ነው የሚበላኝ።

እዚህ ጋር ከዚህ በፊት የሰማሁትን ተረት (አፈታሪክ) ላንሳ…

የሆነ ገዳም ውስጥ ነው። የፆም ወቅት ላይ አንድ መነኩሴ እንቁላል ጥብስ ክፉኛ ያምራቸዋል። ሊያረሳሱት ቢሞክሩም ጭራሽ የሚባረር ዓይነት አምሮት አልሆነባቸውም። ከዚያም ዘየዱ። ሰብረው ቢጠብሱት አንድም እሳት የላቸውም ሌላም ደግሞ ሽታው በገዳሙ ቅፅር ውስጥ ተሰምቶ የሚያስቀጣቸው ይሆናልና እንቁላሉን ሳይሰብሩት ቅርፊቱን በጧፍ ለብልበው መጥበስ አሰቡ። ከዚያም ጧፉን ለኩሰው መጥበስ ጀመሩ። በመሀል ከየት መጡ ሳይባል የገዳሙ አበምኔት ወደመነኩሴው ማደሪያ ዘው ብለው ሲገቡ ድርጊቱን ተመልክተው ደነገጡ። ገሰፅዋቸውም። መነኩሴውም ጥፋታቸውን አጠር ባለች ማብራሪያ ይቅርታ ለመኑ። “ይቅር በሉኝ አባቴ። ሰይጣን አሳስቶኝ ነው።” ለካስ ቀድሞም አምሮቱን ሊያሳድርባቸው ቤት መጥቶ ኖሮ “ኧረ አባቴ ይህን ዘዴ፥ እኔም ካለዛሬም አላየሁት” ብሎ ሰይጣን ራሱ መልስ ሰጠ። ይባላል።

እንግዲህ ይሄ የሚያሳየን ነገሮችን በሰይጣን ላይ የማላከክ አባዜያችንን ጥልቀት ነው። ጥቅም የለውም እንጂ ብዙዎቻችን ሰይጣንን እንበልጠዋለን።

እናቱምገበያየሄደችበትእኩልየሚያለቅስበት’ –  የእኛ ፍርድ ቤት

በተለያዩ ጊዜያት፥ በዝርዝር የማላስታውሳቸውን ወንጀሎች፣ ጭራሽ ከማይመጣጠኑ ቅጣቶቻቸው ጋር ሰምቼ አንገቴን፥ ወንጀሉን በፈፀሙት ግለሰቦች ላይ ብቻ ሳይሆን በወንጀለኛ መቅጫ ህጋችንና በፍርድ ቤታችን ላይ ደፍቼያለሁ። ፊቴ ከማይጠፉት እንደምሳሌም፡-  ባንድ ጎን፥ የሚስቱን እጆች በመጥረቢያ የቆረጠው 19 ዓመት ተፈረደበት፡፡ ሲባል እንሰማና፤ በሌላ ደግሞ፥ የ6 ልጆቹን እናት (ሚስቱን) አንዱን ልጅ ከኔ እንዳልወለድሽው በራእይ ታይቶኛል ብሎ የገደላት 6ዓመት ተፈረደበት ሲባል እንሰማለን።

ይህ ገርሞን ሳያባራ፣ ሚስቱ ላይ ግልፅ የሆነ ጥቃት አድርሶ ልጆቹ እንዳይመሰክሩበት አባትነቱ አራራቸው የተባለለት አባወራ ደግሞ፣ በነፃ ተለቀቀ እንባላለን። ሁሉንም የሚያደርሱን ቴሌቪዥንና ሬዲዮዎቻችን ናቸው፡፡ እንግዲህ ይህ ነው የኛ ፍርድ ቤት። አመክሮው፣ ጉቦውና ዝምድናው ተደማምረው የፍርዱን መጠን የት ሊያደርሱት እንደሚችሉም መገመት ልብ ላላ ሰው ቀላል ሂሳብ ነው። ታዲያ የኛን ፍርድ ቤት፣ “እናቱም ገበያ የሄደችበት እኩል የሚያለቅስበት” ብለው አሳነስኩት እንጂ አበዛሁት ይባል ይሆን?

ከዚህ በላይ ሽብር ከወዴት ይገኛል?

ያም ሆነ ይህ ግን ወንጀሎች በብዛትና በዓይነት እየተፈፀሙ ዘወትርጆሮአችንን ይደርሳሉ። ሰጋት ላይም ይጥሉናል። ከትንንሽ የቀበሌ ትኩረት ከተነፈጋቸው ጥቃቶች እስከ ትልልቅ አገራዊ ሽፋን እስከሚሰጣቸው ጥቃቶች ድረስ ብዙ እንሰማለን። በሞባይል ቀፎ ቅሚያና ኪስ በማውለቅ ሳቢያ በየቅያሱ የሚነሱ አምባጓሮዎችና በሰላማዊ ኗሪዎች ላይ የሚደርሱ አሰቃቂ ጥቃቶች ብዙ ናቸው። ‘በሩ ላይ ተወጋ። በሩ ላይ ተዘረፈ። በሌሊት የቤተሰብ ቤት ተሰብሮ ተሰረቀ።…’ የሚሉ ወሬዎች በተለይ በአሁኑ ወቅት በየቀበሌው ገነዋል። ‘ሌባና ዱርዬም በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅቷል እንዴ?’ እስኪያስብል ድረስ። (ቢያንስ በእኛ ቀበሌ ውስጥ ታይቶም ተሰምቶም በማይታወቅ መልኩ ተበራክተውና ተጠናክረው እየተፈፀሙ ነው።)

ይህንንም ሽሽት ሰዉ ወደቤቱ ለመግባት የሚጣደፈው ገና ጀምበር ስታዘቀዝቅ ነው። የቤቱን አጥር ቢጠነክርልኝ ብሎ አጥር የሚያስቀይረውም ብዙ ነው። ሲሆን የስልክ ቀፎም ይቀየራል እንጂ፣ በወርቅማ ማን ያጌጣል? ዱላው ይቀራል እንጂ ዝርፊያና ንጥቂያው በጠራራ ፀሀይ፣ በፖሊሶች ምስክርነት ሳይቀር ይፈፀማል። በየታክሲ ቦታው፣ በየመንገዱ፣ በየካፌው፣ በየጎዳናው፣ በየጥጋጥቁ…. አሸባሪው ብዙ ነው። ሰዉም ጥላውን ሳይቀር ይጠራጠራል።

‘የአበራሽን ጠባሳ ያየ በእሳት አይጫወትም’ና የሰማውን አስታውሶ ራሱን ለመጠበቅ ይጨነቃል። በለመደውና ይሆናል ብሎ ባሰበው ሲጨነቅና ራሱን ለመጠበቅ ሲሞክር፥ ጭራሽ ያልሰማው ዓይነት ንጥቂያ ይገጥመዋል። ያልገመተው ዓይነት ጥቃት ይደርስበታል። ታስረው ሳይቆይ ስለሚፈቱ የከፋ ጥቃት ያደርሱብኛል ብሎ ስለሚፈራ ማንም ማንም ላይ መጠቆም አይፈልግም። ይፈራል። እንግዲህ ከዚህ በላይ ሽብር ከወዴት ይመጣል? (ለስንቱስ ነገር ይሆን ይሄን ሀረግ የምንመዘው?)

እንግዲህ በማንም ልገደል የምችልበት ሁኔታ እንዳለ ነው እና እየተማርኩ ያለሁት ከእንግዲህ አልፈራም። (ለነገሩ ድሮም አልፈራም ነበር።) እናም እላለሁ። የእኛ ፍርድ ቤት ነገሩን እንዴት ይመለከተው ይሆን? ‘አሸባሪ’ በሚል ታርጋ ቃሊቲ የታጎሩትና በስደት ያሉት የሚያማምሩ አዕምሮዎች በቴሌቪዥን፣ (ለዚያውም ክሱ ተጠናቅቆ ፍርዳቸው ሲነገር – በዜና ወይ በዶክመንተሪ) አደረጉ ተብሎ ከምንሰማው ነገር ባለፈ ምንም ሲያደርስብን አላየንም።

ማወቅ፣ መጠየቅ፣ መፃፍና ማንበብ በሚያሸብሩበት አገር እንደምን እንዲህ ያሉ ጥቃቶች ችላ ተባሉ? ነው ወይስ ወንበር እንዳይነቀንቁ አያሰጉምና?! ባትሰማንም ቅሉ እንላለን – ቃሊቲ ሆይ በርሽን ከፍተሽ ውስጥ ያሉትን ሰላማዊ ዜጎች አስወጪና የሚያሸብሩንን አስገቢልን።

ወይ ጂጂ…! (2)

ዛሬ እጅጋየሁ ሽባባው (ጂጂ) ስለ አባይ የተጫወተችውን ሙዚቃ አዳምጬ እንደ አዲስ ብገረምና የምለው ግራ ቢገባኝ…. ከዚህ በፊት በ ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አብርሀምና ሰርፀፍሬ ያዘጋጁት የነበረው የጣእም ልኬትፕሮግራም ላይ የሰጡት ትንታኔ ትዝ አለኝ፡፡ ከዚያም ቅጂው ያለበትን ፋይል ከማህደሬ በርብሬ አግኝቼ ወደ ፅሁፍ ገለበጥኩት፡፡ ያኔ በጣእም ልኬት ፕሮግራም መቋረጥ የተነሳ ከሸገር ሬድዮ ጋር የነበረኝን ቂም መርሳቴ ትዝ ቢለኝ ደግሞ፣ ወርቅ ላበደረ ጠጠር እንዲሉ ባለፈው ክረምት በደል ሳይቆጠር በደመቀ ሁኔታ የተፈፀመ የሆነ አገራዊ ክስተት ቢገርመኝ የጫርኳት ግጥም መሳይ ነገር እንዲህ ትዝ አለችኝ…

ሆደ ሻሽ ሀገሬ ቂም አለመያዙን ዛሬ ባየ ኖሮ፣
ያንገራገጨውን፣ የገላመጠውን የናቀውን ቆጥሮ፣
ከልቡ ባዘነ፣ ይቅር በሉኝ ባለ፣ በደሉን ዘርዝሮ፡፡

ሆ…. ‘ምን አገናኛቸው?!’ ኸረ ምንም! ግን እንደው ነገሩ ትንሽ ቢነካካ ለሸገርም ይሆን ነበር በማለት እንጂ፡፡ የምር ግን ሸገሮች ከልባቸው ተፀፅተውና በደላቸውን ዘርዝረው ይቅር ሊሉን በተገባ ነበር፡፡ ባወቁ…

ለማንቻውም እነሆ የጣእም ልኬት ትንታኔ በአባይ የዘፈን ግጥም ላይ….

ይህ ግጥም የአገራችንን ታላቅ ወንዝ አባይን በርዕሰ ጉዳይነት የሚያነሳ የዘፈን ግጥም ነው፡፡ ይህ የዘፈን ግጥም በእኔ እምነት እስከዛሬ ስለ አባይ ከተቀነቀኑት ዘፈኖች ሁሉ እጅግ የተለይ፣ ጥልቅና ምጡቅ ስራ ነው፡፡ አንዳንዶች በጓን ለማድነቅ ፍየሏን ማረድ አያስፈልግም ይላሉ፡፡ ይህ አባባል እውነትነት ያለው ነው፡፡ አተረጓጎም ላይ ችግር ካልተፈጠረ በስተቀር፡፡

አንዱን ለማድነቅ ሌላውን ማብጠልጠል መዝለፍና አንዱን ለሌላው ክብር መስዋዕት ማድረግ ፈፅሞ ያልተገባ ነገር እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ይህ ማለት ግን አንዱ ከሌላው በሆነ ጉዳይ መሻሉን፣ በሌላ ነገር ደግሞ መድከሙን መግለፅ አያስፈልግም ማለት ከሆነ እጅግ አደገኛ አነጋገር ይሆናል፡፡

በህይወት እጅግ በርካታ ነገሮች አንፃራዊ ከመሆናቸውም በላይ በበጎ እይታ የአንዱን ከአንዱ መሻል ማውሳት ለጥበቡ በእድገትና በመሻል ጎዳና በርትቶ መግፋት እጅግ ረብ ያለው ግብአት ነው፡፡ በመሆኑም ይህ አባይ የተሰኘው የእጅጋየው ሽባባው ግጥም ከእስከዛሬዎቹ አባይ ነክ ግጥሞች ሁሉ የረቀቀ ነው ስንል እንናገራለን፡፡ የስራዋን ግሩምነት ማስተጋባት ከገጣሚዋ ዋና አምሀዎች አንዱም ጭምር ነውና፡፡ ይህንን ለማለት ያስቻሉንን ምክንያቶች እንደሚከተለው እንጠቅሳለን፡፡

ግጥሙ ሲጀምር የሚያነሳው ስለ አባይ አፈጣጠርና አመጣጥ በመተረክ ነው፡፡ እናም የራሱን ምናባዊ ብየና ይሰጣል፡፡ ወደሚቀጥሉት የሀሳብ ድሮቿ ከመሸጋገሯ በፊት ገጣሚዋ መሰረቷን አጥብቃና አፅንታ ለመሄድ በመሻት ስለአባይ የመነሻ ቦታ አመጣጡን እና አፈጣጠሩን የምናብ ነፃነቷን ተጠቅማ ትበይናለች፡፡ ትተርካለችም፡፡ ስለታላቁ ወንዝ ስታወጋን ስለአመጣጡ ማውሳቷን እፁብ የሚያደርጉት አንዳንድ ምክንያቶች አሉ፡፡

አንደኛ የምታጫውተን ስለወንዝ ከወንዝም ከዓለም ረጅም ስለሆነው ስለአባይ ነውና፤ ወንዝን አንስቶ፣ ወራጅ ውሀን ጠቅሶ ስለመነሻና መድረሻ አለመናገር ግጥሙን ስነኩል ያደርገው ነበር፡፡ ስለዚህ ይህ ድንቅ ብየና ለግጥሙ ፅኑ መንደርደሪያና ልዩ ምልአት ሰጥቶታል፡፡ ሁለተኛ የገጣሚዋ ብየና የወንዙ መነሻ ያደረገው አንዱን ክፍለ አገር፣ አህጉር ወይም ግዛት በመጥራት አይደለም፡፡ የትኛውም ቀበሌና ጎጥም አልተጠቀሰም፡፡ ይልቅስ…

የሀሳብ አድማሷ ወዲያ ተመንጥቆ፣ ምድርን ተሸግሮ፣ ዓለምን ዘቅዝቆ እያየ….አባይ ህይወት እንድትቀጥል ለምድር ከገነት የተቸራት ቅዱስ የጠበል ውሀ መሆኑን ታበስረናለች፡፡ ባናውቅበት ነው እንጂ…የምትልም ይመስላል፡፡ እነኚህን ሀሳቦች ሁሉ የምናገኘው እንግዲህ በዘፈኑ የመጀመሪያ ክፍል ማለትም አዝማች ላይ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ይህንን ሁሉ ግዙፍ ፍልስፍና፣ እነኚህን ሁሉ አበይት ሀሳቦች የተሸከመ የስንኞች ህብር ሌሎች ተከታይ ስንኞችን ለማዝመት ብቁ በመሆኑና መንደርደሪያነቱም የጎላ በመሆኑ አዝማች የሚለው ስም ያንስበት ይሆናል እንጂ አይበዛበትም፡፡ አባይ ከ እንጂ እስከ እንደሌለው አበክረው ይሰብካሉ….

የማያረጅ ውበት…. የማያልቅ ቁንጅና…፣
የማይደርቅ፣ የማይነጥፍ፣ ለዘመን የፀና፣
ከጥንት ከፅንሰ አዳም….
ገና ከፍጥረት…
የፈሰሰ ውሀ… ፈልቆ ከገነት፡፡
ግርማ ሞገስ፣
የአገር ፀጋ፣ የአገር ልብስ…
ግርማ ሞገስ…አባይ፣
ግርማ ሞገስ፣
የአገር ፀጋ፣ የአገር ልብስ…
ግርማ ሞገስ….አባይ….
የበረሀው ሲሳይ፣ (4X)

ብነካው ተነኩ!…. አንቀጠቀጣቸው፣
መሆንህን ሳላውቅ፣ ስጋና ደማቸው፣
የሚበሉት ውሀ፣ የሚጠጡት ውሀ፣
አባይ ለጋሲ ነው… በዚያ በበረሀ…
አባይ… አባይ… አባይ… አባይ…
አባይ ወንዛወንዙ፣
ብዙ ነው መዘዙ…
አባይ… አባይ… አባይ… አባይ…
አባይ ወንዛወንዙ፣
ብዙ ነው መዘዙ…

አዝማች፡-

አባይ የወንዝ ውሀ፣ አትሆን እንደሰው!
‘ተራብን፣ ተጠማን…’ ተቸገርን ብለው፣
አንተን ወራጅ ውሀ….ቢጠሩህ አትሰማ፣
ምን አስቀምጠሀል ከግብፆች ከተማ?
አባይ…አባይ…አባይ…አባይ…
አባይ ወንዛወንዙ፣
ብዙ ነው መዘዙ…
የበረሀው ሲሳይ፣ (3X)

Oh, Gigi…!!

ጨዋታ ዘግንቦት

ክረምቱ ተገፋ፣ ፀሀዩ በረደ፣ ቀዘቀዘ ስንል… ወርሀ ፅጌ ከማለፉ፣ ፀሀዩ በህዳሩ እንደ ግንቦት ከርሮ ሲቀጠቅጠንና፣ ዝንቦቹም ሲፈለፈሉ ብናይ ጊዜ ባለፈው ያመጣናት ጨዋታ ትዝ ብላን ድጋሚ መዘዝናት፡፡  ግንቦት መጨረሻ ላይ እንዳለን ሁሉ በታሳቢ ይነበብ…

እሽሽ….ቆይ ….የት ትሄድ መስሎሃል? ….አገኝሃለሁ! …. (እዝዝዝ….እያለ ሄደ።…. ዝንብ መሰለኝ። በዝንብኛ እየሳቀባቸው። በዝንብኛ እያለመጠባቸው። በዝንብኛ ሙድ እየያዘባቸው….) ወቸው ጉድ! በግንቦት እንዲህ ተፈልፍለው መጫወቻቸው አረጉኝ እኮ።…. ወይስ እርጅና ይሆን?…. ኤድያ! ዝንብ ድሮ ቀረ እቴ! የዛሬ ዝንብ እንደው ዓይነ ደረቅ ነው። ሂድ ቢሉት አይሰማ፣ ቢያባርሩት ተመልሶ እዛው። አሳበዱኝ እኮ። ኧረ ጨርቄን ሊያስጥሉኝ ነው። እኔ ለነርሱ ስል ቆዳዬን አልገፍ ነገር፤ ምን ተሻለኝ ይሆን?…. (የልጅ እግር ሴት ልጅ ሳቅ ይሰማል)

ምን ያስቅሻል? ጥርስሽ ይርገፍ እቴ! ለነገሩ የዛሬ ልጅ ምን ቆዳ አለውና ምን ይሰማዋል ብለሽ? ቆዳ ድሮ ቀረ እቴ! ኧረ እንኳን ዝንብ አርፎብሽ ጅብ ግጦሽ እንኳን ህመሙ ከሰማሽ ልቀጣ! (ይሳሳቃሉ…) ተባብረው ሲበቀሉልሽማ ደስታሽ ነው። ሙች! እውነቴን እኮ ነው…እስኪ እያቸው አፈር ስሆን… ድሮ የበደልኳቸው ነገር እንዳለ ሁሉ ለበቀል የመጡ ነው የሚመስሉት። የማይሆኑት የለም እቴ…..እንደ ወይዘሮ – ኩሽና ነው….እንደ አባወራ – ሳሎን ነው…. እንደ ባለሞያ – ላብስል ነው…. እንደ ምኡር – ላንብብ ነው….እንደ ፈላስፋ – ልተንትን ነው…. እንደ ውሻ – ልንከስ ነው …እርጎው ሳይኖር በባዶ ሜዳ የማይጠልቁበት የለም …

እርጎስ በእኛ ጊዜ ቀረ እቴ። ወተቱ ከጓዳ… ልግዛህም ቢሉት የት ጠፍቶ? ሁሉ በእጅ ሁሉ በደጅ። አዪዪ….ይብላኝ ለዛሬ ልጅ፣ ለወተት ብርቁ!….ግን ዝም ብዬ ሳስበው እናንተ የምትወልዷቸው ልጆች ወተትን በአማርኛ ትምህርት ክፍለ ጊዜ ‘ለምሳሌ’ ቢያውቁት ነው። ኧረ ወዲያ…እርሱስ አማርኛው ከኖረ  አይደል? አማርኛ በእኛ ጊዜ ቀረ እቴ….! ነገሩን ሁሉ በምሳሌ እያወራርድን፣ ጠጁን ሁሉ በብርሌ እየኮመኮምን ባንድ ‘ዝም ባለ አፍ ዝንብ አይገባም!’ ምሳሌ ብቻ የስንቱን የጨዋ ልጅ አፍ እንዘጋው ነበረ መሰለሽ?! ቢሻን ደግሞ ‘ካለመናገር ደጃዝማችነት ይቀራል’ን መዝዘን እናናግረው ነበር፡፡ ዛሬ ግን ይኧው ዝንብ እንኳን ጊዜ ሰጥቶት፣ አፋችንን ፈልቅቆ ሊገባ ይጠብቃል… ደጃዝማችነቱንም ጠቅልለው ይዘውታል ስልሽ….

መቼስ ታምር አያልቅም!…. ‘ሰው ከጦጣ መጣ’ ሲባል ሰምተው፣ ምናልባት ከዝንብነት ወደ አውሬነት ለማደግ ሲታገሉ ይሆን እንዲህ ድርቅ የሚሉት? ሆሆሆ…. (ሳቅ ይሰማል…) ኡኡቴ….አሁን በእኔ ድንቁርና መሳቁ ነው? ወግ ነው!… የናንተ እውቀት እንደው ነገር ማጣመምና ቦታ ማገላባበጥ ነው። የዝንቡን ፍሊት ከኔ ደብቀሽ ለገላሽ ስታርከፈክፊ አንድ ቀን እዚያው እንዳትደፊ እንጂ….(‘ዶዶራንቱን ነው እኮ’ እያለች ትስቃለች) ድንቄም! ከፈረንጅ ሴጣን ጋር አማሽኝ ማለት ነው? አማርኛማ ዳገትሽ ነው… ነገሩን ሁሉ እያደባለቀሽ በእግሩ እያስኬድሽው…. የኔታው ብርቅ ሆኖ አስኳላ የማንም መጫወቻ ሆና ቀረች! ቱቱቱ….

(የረሱት ነገር ድንገት ትዝ እንዳላቸው ሁሉ መንጨቅ ብለው) እስኪ የዝንቡን ብዛት እዪማ! አቆናጠጣቸው ብትይስ? እንደ ሆነ ነገር አይደል ሚመዘልጉት እንዴ? ሆሆ… እኔማ ድንጋይ ይዞ ከነሱ ጋር መሯሯጥ ነው የቀረኝ። ዱላውንማ ቆየ ከጀመርኩት። ታዲያ ምን ያደርጋል?! እቃ ብሰባብር እንጂ ዝንቦቹ ከኔ ጋር አባሮሹን ለምደውታል። ‘የባሰ አታምጣ!’ ማለት ነው የሚሻለው….እንጂማ የመጪውን ማን ያውቃል?  ምናልባት ዝንብ መግደል ከጀግንነት ተቆጥሮ ያሸልም ይሆናል። (አሁንም ሳቅ ይሰማል…) ሙች ስልሽ… (ሳቁ ይቀጥላል…)

ኤድያ! ለነገሩ ጊዜ ሰጥቶሻል….በደንብ ሳቂ! ጊዜ እንጂ ብርቱ፣ ሰውማ ደካማ ነው። ምኑንም ችዬ አላሳይሽ። ጊዜ ያሳይሻል….አንሙት ብቻ! ሰው ዛሬ የያዘው የመሰለው ነገር ሁሉ ከእጁ እየተፈተለከበት ሰዶ ሊያሳድድ ይሰደድም ይሆናል።… ደግሞስ ማን ያውቃል? በዝንብ ተማርረን ጫካ የምንገባበት ጊዜም ይመጣ ይሆናል። (አሁንም ይሳቃል…) ሥራ መፍታት እንዲያ ነው! ታየኝ መቼስ…. ለዝንብ ቦምብ ሲጠመድ….. ለዝንብ ምሽግ ቆፍሮ ሰው ተሸሽጎ  ሲዋጋ…..ግን ምን ያተርፈኝ ተብሎ? ለነገሩ ሰውስ ምን ያተርፈኝ ብሎ ነው ከሰው ጦር የሚማዘዝ? እንዲያው ቢፈርድበት  እንጂ… ‘በዚህ ብላ! ላብ ይሁንህ’ ቢባል እንጂ!… ይሁና! ነገ ሰኔም አይደል?… የወቅቱስ ዝንብ ያልፋል!… ብቻ የባሰ አታምጣ! ተመስገን!….

ትናንት ጠዋት አልጋዬ ላይ ሆኜ በሰመመን የሰማሁት ነው። በህልሜ ይሁን በእውኔ እንጃ። ሴትዮዋም ማን እንደ ሆኑ በትክክል አልለይም። …አንድ ነገር ግን አውቃለሁ….ዛሬ ሰኔ ነው….ግንቦት አልፏል….ዝንቦቹም ቀስ እያሉ ይሄዳሉ። እኛን ለብርድና ለቁር አቀብለውን.። ዞምቢዎቹስ?

(ማስታወሻ፡ ሰኔ 1/2004 የተፃፈ)

አዪዪ…

☞ ORION BANANA ማስቲካ ከ1996 ዓ/ም ጀምሮ (በግምት) ጥቂት ከሚባሉ ጊዜያት በቀር ከኪሴ ተለይቶኝ አያውቅም ነበር። ተመሳስሎ ሲሰራም ከአስመጪው ከአልሳም ትሬዲንግ ሁሉ ቀድሜ የማውቀው እኔ ነኝ ብል ማጋነን አይሆንም። ሃሃሃ… ስንቱን እንደከተብኩለት ቢያውቅ ኖሮ ተቆራጭ ያስብልኝ ነበር። (ተቆራጭ ኬክ ነው? ብሎ መቀለድ አይቻልም። ሄሄሄ…) ባለፈው የሀዘኑ ጊዜ ‘በየመንገዱ ማስቲካ ማኘክ አይቻልም።’ የሚል ተባራሪ ወሬ ሰምቼ የተውኩት፥ ይሄው እስከዛሬ አፌ ገብቶ አያውቅም።

Oh my Orion, I missed u so much!:D

 

☞ በ1993 ዓ/ም የ11ኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ በ1 ብር ከስሙኒ (1:25) የገዛሁትን ጥፍር መቁረጫ ነው እስከዛሬ ድረስ የምጠቀመው። ውይ ደጉ ዘመን… ብር ከስሙኒ የሚባል…እቃ የሚገዛ ብር ነበረን። ምናምን ብለን እናማር እንዴ? ሃሃሃ… የምር ግን በየመሀሉ ለአፍታ ከዐይኔ እየተሰወረች ሳጣት ሌላ ብገዛም ሳይቆይ ይሰበርብኛል። ያኔም ጥንካሬና አለመሰልቸቷን ውለታ እየቆጠርኩ እወለውላታለሁ። ምናልባት ለልጄ አወርሳት ይሆናል እያልኩ።…ሃሃሃ (ሰው ጠብመንጃ ሲወለውል፣ ቤት ሲያወርስ አይተሀል።’ ብሎ መቀለድ አይቻልም።) ተመስገን! እነሆ እኛም ድሮ ቀረ እያልን ያለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡

Oh my nail cutter, I owed a lot to you! :p

 

☞ በ1997 ዓ/ም የ3ኛ ዓመት ተማሪ ሳለሁ በ35 ብር የገዛኋት አንዲት የምታምር ነጭ ቲሸርት አለችኝ። በጣም ስለምወዳት ብዙ ጊዜ እለብሳታለሁ። እርሷ ግን ለመጣል ፈቃደኛ አይደለችምና ዛሬም ያኔ በነበረችበት ይዞታ ላይ ሆና ታባብለኛለች። ሰሞኑን (ከ3 ወር ወዲህ) ባመጣሁት ክብደት የመጨመር ፕሮግራም መሰረት ያቀድኩትን ያህል በመጨመሬ ምክንያት እርሷም እንደሌሎቹ ልብሶቼ እየጠበበችኝ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። እንዴት ነው እናጫርታት? ወይስ መልሰን ክብደት የመቀነስ ስራ (z other way round) እንጀምር?:) (ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ’ ብሎ መተረት ከቅናት ይቆጠራል። ሄሄሄ…)

Oh my t-shirt, I don’t wanna lose you!;)

 

☞ በ1992 ዓ/ም የአስረኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ ጋሽ ዓለሙ የሚባሉ ባዮሎጂ መምህራችን (አዲስ ከተማ የተማሩ ያውቋቸዋል። ወይም ደግሞ በትርፍ ጊዜያቸው የመስመር ዳኝነት (አራጋቢነት) ስራ ስለሚሰሩ ምናልባት ስታዲየም የሚያዘወትሩ ወዳጆች ያውቋቸው ይሆናል።) በትምህርት መሀል ‘ጉንፋን ሊጀምር ሲል (ስሜቱ ሲመጣ) አፍንጫን በቀዝቃዛ ውሀ በመታጠብ ጉንፋኑን ሳይመጣ በፊት ድራሹን ማጥፋት ይቻላል፡፡ ያው ክትባት በሉት።’ ብለው ነገሩን። እነሆ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ እኔም ምክራቸውን ተግባር ላይ እያዋልኩ (ለሰውም እየመከርኩ) ጉንፋንን እከላከላለሁ።:) በመሆኑም ከዚያ ወዲህ ጉንፋን ይዞኝ የሚያውቀው በጣም ጥቂት ጊዜ ነው። እርሱም ክትባቴን ስረሳት! (‘ውሀ በመንደሩ ሲጠፋ ሲጠፋ…’ በል እንጂ ብሎ ማላገጥማ አይቻልም። ሃሃሃ…)

Oh common cold, where are you?:-/

ወይ ጂጂ…! (1)

To my everyday surprise, and every spot astonishment, the way she expresses things is the way I want them be expressed!…and mostly, she makes things way far from my imaginations (and even from their nature), before she shows me nailing them down.

Her exceptional ability of playing with words (specially as a music lyrics) is something I would die craving for more!, &would dare to try one:) …aww, she put everything a scale up, so that no one dare to try. She knows how to mesmerize and quench a thirsty and a demanding soul effortlessly.

Most importantly, she understands the music; knows what to work, whom to work with, and for whom she is working it; upgrade her knowledge in many regards! Though I didn’t get chance to see any of her paintings, I’ve heard that they are amazingly professional; even herself tell that she is more sure about her artistic qualities in the painting than the music. (Sheger FM 102.1, interview with Meaza Biru)

I push she should sing more! I push she should paint more! I push she should write more! I even push she write a book…just she trigger her mom’s spiral. YeY, her mom is publishing a historical novel, which Gigi has rated as wonderful. I can’t wait…

The track, my player is playing now is….

ምን ትጠብቃለህ?…አቦ ሽማኔ፣ አቦ…
እንዲያ ወዲያ ወዲህ ትንቆራጠጣለህ፣
በሰፋው ደረትህ…ባማረው ባትህ…
እስኪ ተለመነኝ፣ ባይን በጥርስህ
የሰው ስጋ እርም ነው፣ ይቅር መብላትህ
አቦ ሸማኔ…

አደራ ብሰጠው፣ አደራ ልቤን
በልቶት ተገኝ አሉ፣ በጣጥሶ አንጀቴን
የደከመን ገድሎ፣ ፉከራው ምንድን ነው፣
ቀን የጣለው ለታ እርሱም እንደ እኔ ነው፡፡
እርም የእናቴን ስጋ፣ እምልልሀለሁ
ፍቅርን ካልሰጠኸኝ እሞትብሀለሁ፡፡
ያን እምቢ ያን እምቢ…ስለመን ከርሜ፣
ይኸው ተጃጃልኩኝ ደግሜ! ደግሜ! ደግሜ…

ባቱ፣ ተረከዙ፣ ሲጋው ተነባብሮ፣
ወገቡስ የሱ አይደል አይበላም ወይ አብሮ
ልጁ የወይን ሀረግ፣ ጠይም ዓሳ መሳይ
እኔ እናቱን ብሆን፣ ለሰውም አላሳይ፡፡

አንተ ልጅ አንተ ልጅ ያሙሀል
ልብ ይበላል እንጂ አይሰጥም ይሉሀል፣
በዚህች በማተቤ እምልልሃለሁ፣
ፍቅርን ካልሰጠኸኝ እሞትብሀለሁ፡

አሻፈረኝ እምቢ አትናገሩኝ፣
ወስዳችሁ ቅበሩኝ የሰው ነው አትበሉኝ፡
እኔስ ያንን ጀግና፣ ተኝቼ አላልፈውም፣
አገር ጉድ ይበለኝ፣ የኔ ነው…የኔ ነው….የኔ ነው….

የኔ ናት…የኔ ናት…. የኔ ናት… የኔ ናት…. ))

I love Gigi ( Ejigayehu Shibabaw ) so much!!

ለአገር ጉዳይ ስብሰባ ላይ ነበርኩኝ….

መንደርደሪያ…

የመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርቴን ከጨርስኩኝ ጊዜ ጀምሮ በመምህርነት ሞያ አገልግያለሁ። (‘ሳይማር ያስተማረንን ማህበረሰብ ሳንማር እናስተምር’ በሚል ግነት መርህ ቢጤ ተደጋግፌ…) በመጀመሪያ መምህር ለመሆን ስወስን ስራ ስፈልግ አግኝቼው (ሌላ አጥቼ) ሳይሆን ለግልም ሆነ ለህብረተሰብ እድገት ጉልህ አስተዋፅኦ ለማድረግ ጥሩ ሞያ ነው ብዬ መርጬው ነበር። መምህርነት ሰው የማምረት ሞያ እንደመሆኑ የሰው ልጆችን የአስተሳሰብ አድማስ የማስተካከልም ትልቅ ሀላፊነትን ይሰጣልና ስራውን በፍፁም መነቃቃት እና ጉጉት ውስጥ ሆኜ ነበር የምሰራው።

አንዳንድ ጊዜም በሚጠበቀው መልኩ ችግሩን መርዳት አለመቻሌን ሳስብ ጥረቴ እና ጉጉቴ ከንቱ ይሆንብኛል። ስራው ከእኔ በተሻለ የእውቀትና የእድገት ደረጃ ላይ ያለ ሰው እንደሚያስፈልገው ሲሰማኝም ብዙ ጊዜ የስራ መልቀቂያ ደብዳቤ እፅፍና ስጨርስ፥ ከራሴ ጋር ተሟግቼ ሀሳቤን ቀይሬ ቀድጄ እጥለዋለሁ። ይህን የማደርገው ስራውን ላለመተው በመፈለግ አልነበረም። ይልቅስ ተማሪዎቹ ያሳዝኑኛል። ስራውን ብተወው በቦታው የሚተካው ሰው ማንነት ያስጨንቀኛል። ከንቱ ጭንቀት። ቢያንስ ችግሩን (ጉድለቴንም ጭምር) አውቀዋለሁና እስከ ጊዜው ድረስ መቆየቱን እመርጥና ሀሳቤን እለውጣለሁ። ፀዳ ያለ ትምክህት።

ያም ሆነ ይህ ግን እንደ መምህር የሞውን ደረጃና ክብር ለመጠበቅና ራሴን ከጊዜው ጋር እያደስኩና (update እያደረግኩ) ጎዶሎዬን ለመሙላት እየጣርኩ፣ ብቁ ለመሆን በመጓጓት ማድረግ የምችለውን ነገር ሁሉ አደርግ ነበር። እንደ ወጣት መምህርነቴም በዚህ ረገድ በብዙ ተሳክቶልኝ ነበር ማለት ይቻላል። ከተማሪዎቹ ጋር የነበረንም ግንኙነት እንደ እድሜያችን መቀራረብ ሳይሆን፣ በፍፁም ፍቅርና መከባበር ውስጥ የነበረ የአባትና የልጅ ዓይነት ነበር። ያም ማስተማሩን ይበልጥ ደስ እያለኝ እንድሰራው ረድቶኛል። – ያው በመማረርና በመመራመር  መሀል ውስጥ እየዳከርኩኝ

የእኔ ነገር… ልናገር ያሰብኩትን ረስቼ ነገር አበዛሁኝ። ለነገሩ ይሄን የምቀባጥረው የገጠመኝ (ከታች እንደሚነበበው) ከለመድኳቸው ወጣ ያለ ተማሪ መሆኑን ጠቆም ለማድረግም ነው፡፡ – ነገሩን ይበልጥ እንድትገነዘቡት፡፡ እነሆ ወደ ገደለው….

የገጠመኝ…

ከእለታት በአንዱ ቀን የተማሪዎች የሴሚስተር አጋማሽ ፈተና ወቅት ሆነ። እኔ የማስተምረው ትምህርትም ፈተና ጊዜ ደርሶ ተማሪዎቹን ፈትኜ፣ በመነጋው ቢሮ ቁጭ ብዬ የፈተና ወረቀታቸውን በማረም ስራ ላይ ተጠምጄ ነበር። አንድ ግድየለሽ ተማሪ ወደ ቢሮዬ ዘው ብሎ ይገባል። ፊቱ ላይ ፍፁም መረጋጋትና ኩራት ይታይበት ነበር። ስሙን ጠርቼ ሰላምታ ከሰጠሁት በኋላ ምን እንደፈለገ ጠየቅሁት።

እርሱ: “ትናንት ፈተና አልተፈተንኩምና እንድተፈትነኝ ነው።” አለኝ።

እኔ: (የምሬን አሳዝኖኝ እንዲሁም መረጋጋቱ ገርሞኝ) “ምነው በሰላም? አሞህ ነበር? አይዞህ! በቃ የሀኪም ማስረጃህን ታመጣና እፈትንሀለሁ።”

እርሱ: የትዝብት ፈገግ ብሎ “አይ ቲቸር አሞኝ አልነበረም።”

እኔ: “አሃ… ምነው? ሀዘን ምናምን?”….ስፈራ ስቸር። (ሟርተኛ ላለመሆንም፣ ላለመባልም)

እርሱ:  “ኧረ አይደለም።”….ሳቅ ብሎ ።

እኔ: “እንግዲያው በሀዘንና በህመም ምክንያት ያልተገኘ ተማሪ ብቻ…እርሱም መረጃ ሲያቀርብ ነው ድጋሚ የሚፈተነው።”

እርሱ: ምንም አልተረበሸም። በትኩረትና በትዝብት ተመልክቶኝ…ፀጉሩን እያሻሸ …በድጋሚ ፈገግ ብሎ… አስረግጦ – “ትፈትነኛለህ! ለአገር ጉዳይ ስብሰባ ላይ ነበርኩኝ።” አለኝ…

(እንግዲህ የተማሪ አባልነቱን ተጠርቶ  መሆኑ ነው)

😀 😀 😀

ያመናቸው ከደተውት (ወይም ከአቅማቸው በላይ ሆኖባቸው) አለመፈተኑ ግድ ሆኖ… ለተመሳሳይ ኮርስ በዓመቱ ክፍል ሲመጣ የመጀመሪያው ቀን ላይ አቀርቅሮ ነበር…

“ሰውን ከማመን እግዜርን መለመን” ~ እናቴ

😀 😀 😀

☞ እንግዲህ ይሄ  ፍንትው አድርጎ የሚያሳየው ትልቅ አገራዊ ጉዳይ መኖሩን ልብ ይሏል።

የግልብ ዘመን ግጥሞች…

‘ዓሳ ጎርጓሪ….’

በትዝታ ፈረስ ጭኖ፣ ወደኋላ አሳፍሮኝ ያለፈውን እያስቃኘኝ፣ ብቻዬን ሲያዝናናኝ የዋለ ደስ የሚል እሁድ። ‘ዓሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል።’ እንዲሉ የጠፋብኝን አስፈላጊ ወረቀት ፍለጋ ከማለዳው አንስቶ፥ ሳጥኔን ስበረብር ስንትና ስንት ወረቀቶች አግኝቼ ከራሴው ጋር ስጫወት፣ አንዳንዶቹን ለእህቶቼ እያነበብኩላቸው አብረን እየሳቅን፣ በየመሀሉ ደግሞ በዋናነት የምፈልገውን ነገር እየረሳሁት ስባዝን ዋልኩ። ወይ ጉድ! ምን ያላገኘሁት ነገር አለ? ደብዳቤ (የተፃፈልኝ፣ የፃፍኩት፣ ያልጨረስኩት፣ ያልላኩት…)፣ ግጥም፣ መጣጥፍ፣ ልብወለድ….መሳይ ነገሮች (ለአቅመ እነዚያ ስያሜዎች ያልደረሱ።)

ልጅነት እንዴት ደስ ይላል? በተለይ የ2ኛ ደረጃ ተማሪ ሳለሁና ከዚያ በፊት የፃፍኳቸውን ነገሮች ስመለከት የነገሮች ብስለትና የአገላለፅ ችሎታ ላይ የጊዜ ሚና ፍንትው ብሎ ታየኝ። በጣም የሚያስቁ አገላለፆች። ቤት ከቤት በመምታት ላይ ብቻ ያተኮሩ ዝም ብሎ ግጥሞች። እንደ ነገሩ የተደረደሩ የቃላት ትርምስ የተሞላባቸው አረፍተ ነገሮች። በሽቅድምድም የተፃፉ የሚመስሉ ያልበሰሉ ሀሳቦች። ቤት አመታታቸው በሳቅ የሚያፈርሱ መስመሮች። (ልክ ‘ነው። ነው።’ ወይም ደግሞ ‘እና፤ እና’ ብለው ሁለት መስመሮች በተከታታይ እንደሚዘጉ ዓይነት…) ዜማ የማይሰሩ ለዛ ቢስ ድርድሮች። ለዛ ባለው የቤት ምት የተሸፈኑ ተራ ሀሳቦች።… እያሳቁኝ። እያስገረሙኝ። በራሴው ፊት እያሸማቀቁኝ። (እንዲያው ጨዋታ እንጂ በጉርምስና ሀሳቤና ድርጊቴ በጉልምስናዬ እሸማቀቅ ዘንድስ ሀይማኖቴ አይፈቅድልኝም።:)) [ዛሬ መሀመድ ሰልማን ከልጅነት የግጥም ዝንባሌ ጋር በተያያዘ የፃፈውን status update ብንመለከትም በተያያዥ የሚነግረን ነገር አለው።]

ያኔ በልጅነት እንደሰዉ የልብ ልብ ተሰምቶኝ አሳትሜያቸው፣ ለሰው ጆሮ አድርሻቸው ቢሆን ኖሮ ምንስ ይውጠኝ ነበር? ሆ… ማርያም ተፍታኛለች አቦ! ማርያምን!:) በርግጥ እንዲህ ያሉ ተራ ፅሁፎች ተሰባስበው በመፅሀፍ ሲታተሙ እና ለአደባባይ ሲውሉ ማየት አዲስ አይደለም። ዛሬም ብዙ የምንታዘበው ሞልቷል። ከሙላቱ የተነሳም ነገሩን እየለመድነው ነው። መፅሀፍ እስኪሆኑ ድረስ ሳንጠብቅ እንኳን በየግድግዳዎቻችን ላይ የምንለጣጥፋቸው ግጥሞች በአብዛኛው የግጥምን ደረጃ አይጠብቁም። ቤት ከቤት ከማማታት፣ ቃላት ከመደርደር አይዘሉም። ከዚህም ጋር ተያይዞ ይመስላል የአገራችን የግጥም መፅሀፍ ገበያ በጣም ቀዝቃዛ ነው። እንደዚህ ምሽት ቀዝቃዛ።:) ግጥምን ብዙዎች ይፈልጉታል፥ ግን ደግሞ ብዙዎች አይገዙትም። (ብዙዎች አይፈልጉትም።) ለጨዋታው እጥረትና ቀጥተኛነት በዋናነት ስነ ግጥምን ይዘን እንዝለቅ…

‘ፍቅር ሲደቁሰው ሁሉም ሰው ገጣሚ ይሆናል…’

ሥነግጥም ለስሜት ቅርብ የሆነ የፅሁፍ ዓይነት በመሆኑ በተለያዩ ጊዜያት ብዙዎች ወደው ይሞክሩታል። በአንፃሩ ደግሞ ሥነግጥም በሥነፅሁፍ ስር ያለ አንድ ዘርፍ ነውና፥ የራሱ ህግጋቶች (ደንቦች) እንዲሁም ለዘርፉ የተሰጡ የራሱ አዋቂዎች አሉት። ማንም ሰው ተነስቶ ሱቅ ከፍቶ መነገድ ሊፈልግ ይችላል። መነገድ የፈለገ ሁሉ ግን ነግዶ ለማትረፍ የሚያበቃ የገበያ ገድ ወይም የንግድ ክህሎት ሊኖረው አይችልም። ለንግድ ስራው በጣም ፍቅርና የተወሰነ የንግድ ስራ ያለው ቢኖር ግን በልሂቃን ድጋፍና ምክር ሊሻሻልና የበቃ ነጋዴ ሊሆን ይችላል። ለዚህም ለኪሳራ ራሱ ሀላፊነቱን (risk) ወስዶ ነው። በእኔ መረዳት፥ ሥነግጥምም እንደዚሁ ነው።

ከዚህ ጋር በተያያዘም ታላቁ የግሪክ ፈላስፋ ፕላቶ at the touch of love everyone becomes a poet’ (‘ፍቅር ሲደቁሰው ሁሉም ሰው ገጣሚ ይሆናል…’) ይላል።  ፍቅር ሲደቁስ የጀመረ የመግጠም አባዜ ግን ለሁሉም ሰው እስከመጨረሻው ድረስ ዘልቆ መሄድ ስላለመቻሉ የብዙ ሰው ታሪክ ነውና የመግጠም ፍላጎት በሰዎች ህይወት ውስጥ የሆነ ቦታ ላይ ሊከሰት የሚችል ነገር መሆኑን እንረዳለን። ሆኖም በተለያየ ስሜት ውስጥ ሆነን የፃፍናቸውን ግጥሞች ለሚመለከታቸው (በቀጥታ ለጉዳዩ  ባለቤቶች) ካልሆነ በቀር ለሌሎች በትኩሱ አናጋራቸውም። አንድም ስሜታችንን በመደበቅ ሰበብ፣ ሌላም የግጥማችንን ደረጃ ማወቅ ባለመቻላችን፥ የፃፍናቸውን ለማንም ሳናሳይ በፊት እኛ ጋር ይቆያሉ። ከርሞ… ስሜቱ ሸሽቶን ከእኛ ጋር የቆዩት ግጥሞች ግን ጣእምና ውበታቸው ሲያብለጨልጭብን ጊዜ፥ የፃፍነውን ለሰዎች ስለማጋራት እናስባለን።

ስለሆነም ሀሳባችንን በግጥምም ሆነ በሌላ ዓይነት የስነፅሁፍ ዘርፍ ብንገልፅ ‘ይበል!’ የሚያሰኝ ነገር ነው። የፃፍነውን ነገር ለሰው ስለማካፈል (ስለማሳተም) ስናስብ ግን ራስ ጋር ከማቆየት ባሻገር ሞያዊ አስተያየትን መጠየቅ አግባብ ነው። እኛንም የተሻለ የእድገትና የመረዳት እርከን ላይ ያስቀምጠናል። – ቢያንስ መስመሩን በውል እስክንለየው ድረስ! ልክ ለወዳጅ ዘመድ የተፃፈ ደብዳቤ ሁሉ ተሰብስቦ እንደማይታተም፤ ነገር ግን ለወዳጅ ዘመድ ከተፃፉ ደብዳቼዎች መሀል ስነፅሁፋዊ ፋይዳቸው ተስተውሎ ሊታተሙ እንደሚችሉ ሁሉ ስሜትን ለመወጣት በማሰብ የሞከርነውን በሙሉ ሰብስበን ብናሳትም ግን ሀላፊነት የጎደለው ተግባር ነው የሚሆነው። ተራና ጊዜያዊ እርካታን ከማጎናፀፍ አያልፍም። ሲቆይም በራሳችን ፊት ሊያሸማቅቀን ይችላል።

ከዚህ ጋር ተያይዞ የባለሞያዎች (እንዲሁም የግጥም አንባቢዎች) ግድየለሽነትና ሀላፊነትን በአግባቡ ያለመወጣት ነገር ከግጥሞቹ ያለመመጠን ሁኔታ እኩል የሚያሳፍር የሚያሳስብ ነገር ነው።  ያም ሆነ ይህ ግን “ይህ ሌላ፣ ያ ሌላ” አሉ አፄ ቴዎድሮስ እንዲል ብርሀኑ ዘርይሁን (በታንጉት ምስጢር መፅሀፉ) ግጥም መግጠም ሌላ፣ የገጠሙትን ለሰፊው ህዝብ ማቅረብ (ማሳተም) ሌላ! መሆኑን ሁሉም ባለድርሻ (ገጣሚም አንባቢም) ሊያስተውለው የሚገባ ጉዳይ ነው።

ስነ ግጥምና የሂስ ባህል…

ሥነ ግጥም የሰው ልጅ በቋንቋ አማካይነት ስሜቱንና ሀሳቡን የሚገልፅበት የቋንቋ አጠቃቀም ስልት ነው። ደስታ፣ ሀዘን፣ ጥቃት፣ ብቸኝነት፣ በግጥም ይገለፃሉ። ፀሎት፣ ምህላና ምስጋና በግጥም ይደርሳሉ። እንጉርጉሯችን፣ ፀሎታችን፣ ዘፈናችን፣ ሆታችን፣ ቀረርቷችን፣ ምህላችን፣ ምርቃታችንና እርግማናችን፣ ግጥማዊ የንግግር ስልቶች ናቸው።  (ብርሀኑ ገበየሁ (1999), ‘የአማርኛ ስነግጥም’) በዚህም መሰረት ሀሳብን ከመግለፅ እና ከመግባባት አንፃር ከተመለከትናቸው የግጥሞች ጥራትና ደረጃቸውን መጠበቅ አለመጠበቅ ጉዳይ ገጣሚያኑን አያስወቅሳቸውም።

ሆኖም እርሱን ተከትሎ የሚግተለተሉ የአስተያየት ዓይነቶችና ገጣሚያኑ አስተያየቶቹን የሚመለከቱበት ዐይን ሁኔታ ግን፥ በጠቅላላው የጥበቡንና በተናጥል የገጣሚውን የነገ የብስለት ደረጃ የመወሰን አቅማቸው ብዙ ነው። በመሆኑም አስተያየት አሰጣጣችን ላይ ስሜት፣ እንክብካቤና ቸልተኝነት ካመዘነ ጉዳቱን ዘመን ተሻጋሪ (intergenrational) ያደርገዋል። ይህንን ሀሳብ ሲያጠነክርልንም ሌሊሴ ግርማ “ዘመን አልፎት የሚሄድ ጥበብ ጥልቅ አይደለም።” ይለናል። ግልፅ የሂስ ባህል ከሌለም ለመሻሻልና ለመለወጥ ማሰብ ብሎም ራስን ለማሳደግ መጣር የሚታሰብ ነገር አይሆንም።

“እውነተኛ የሂስ መንፈስ የሌለበት ቦታ የህዝቡ ሂስ የጥበብ ደረጃን ያወጣል። ያወጣው ይፀድቃል። ህዝብ የወደደው ሁሉ እውነተኛ ነው።” (ሌሊሴ ግርማ (2004), ‘አፍሮጋዳ’) ይሄ እየኖርን ያለንበት ግልብ ዘመን ሀቅ ነው። በተድበሰበሱ እውነቶች ተከብበን በብዥታ እንመላለሳለን። ብዥታንም እንፈጥራለን። ብዙ ነገር ስላየን ብዙ ነገር ያወቅን ይመስለናል። ብዙ ነገራችን የለብለብ ነው። የተጠበሰና የበሰለ ነገር አናውቅም። ብናውቅም ዙሩን ያጠነክርብናልና አንፈልግም። ሌሊሴ ዘመኑን በአንድ ቃል ሲጠቀልለውም “አፍሮጋዳ” ይለዋል። “ለእኛ የዘመኑ ታዋቂነት መንፈስ “አፍሮ” እና “ጋዳ” ተጠቃሽ ናቸው። የአፍሮጋዳ አስተሳሰብ የሚመነጨው ጥልቅነትን ከማለዘብ ነው።” በማለት እያብራራ….

ምናልባት ዛሬ የተመለከትናቸውን ችግሮች፣ በተሰማን መልኩ ነቅሰን በማውጣት ሂስ ብንሰጥ፥ ፀሀፊው ለሚሰራቸው ቀጣይ ስራዎች እናግዘዋለን እንጂ አንጎዳውም። ገጣሚውም የምሩን በጥበብ የተቃኘ ወይም የመቃኘት ፍላጎት ያለው ከሆነ እገዛችን ከምን ፍላጎት የመነጨ መሆኑን ቀድሞ ያውቀዋልና ስለምንፈጥርበት አሉታዊ ተፅህኖ ብንጨነቅ፥ – በእውነት በከንቱ ነው። የሰላ ሂስ መስጠትም የሚችለውን (ለዘርፉ የተሰጠውን) ሲያበረታው፥ የማይችለውን (ለዘርፉ ያልተሰጠውን) ሰው ደግሞ በማይሆን ነገር ላይ መድከሙን ትቶ መክሊቱን ፍለጋ ይተጋ ዘንድ ያነቃዋል።

መቅረዝ የኪነ ጥበባት አፍቃሪያን ህብረት

መቅረዝ የኪነ ጥበባት አፍቃሪያን ህብረት በቀድሞ ደቡብ ዩኒቨርስቲ (ዲላ፣ ወንዶገነትና ሀዋሳ ግቢዎች) ውስጥ የተመሰረተ እና እስካሁንም ያለ የስነፅሁፍ አፍቃርያን ስብስብ ነው። የቀድሞ የህብረቱ አባል መምህር ሆኖ ሰመራ ዩኒቨርስቲ በሄደበት አጋጣሚም መቅረዝን በሰመራም አቋቁሟል። ያው ከነሙሉ ክብሩና መታወቂያው – በተለይ የሂስ ባህሉ – ማለት ነው። የቀድሞ የህብረቱ አባላትም ከሁለት ዓመት በፊት በአዲስ አበባ ተሰባስው ፈቃድ በማውጣት ህብረቱን ወደ አገር አቀፍ ማህበርነት  አሳድገውት የነበረ ቢሆንም፥ በተለያዩ ምክንያቶች ለጊዜው ይህ ነው የሚባል እንቅስቃሴ እያደረገ አይደለም። በዩኒቨርስቲዎቹ (አሁን ለሁለት ተከፍለው ዲላ እና ሀዋሳ ተብለዋል) ውስጥ ግን አሁንም ድረስ የድሮ መልክና ቅርፁን እንደያዘ አለ። ወደፊትም እንደሚኖር እናምናለን።

ርእሱን ያነሳሁት ስለ ህብረቱ ልናገር አይደለም። ይልቅስ ያተረፍኩበትን አውቃለሁና ህብረቱ ስለሚታወቅበት ጠንካራ ባህርዩ – የሰላ ሂስ – ጥቂት ለማለት ነው። ይሄን የመቅረዝ መታወቂያ የሆነውን ሂስ አሁን ያሉት (ከእኛ ቀጥለው የመጡ) አባላት “ግጀራ” ይሉታል። ግጀራ፥ ገጀራ ከሚል የአማርኛ ስም የረባ ግስ ነው። የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማእከል (2001) ያዘጋጀው መዝገበ ቃላት ደግሞ “ገጀራ”ን “ቆንጨራ” ብሎ ይተረጉመዋል። እንግዲህ በዚህ መሰረት ግጀራ ማለት “በቆንጨራ ቆርጦ መጣል።” የሚል ትርጉም ይይዝልናል።

ካለምንም ማብራሪያ አዲስ የወጣለት ስያሜ የሂሱን ሂደትና ዓይነት የሚያሳይለት እንቅስቃሴ በመቅረዝ ይደረጋል። ከ “ይሄን ግጥም ብለህ ፃፍክ?!” እስከ ግጥሙን ለማሻሻል “እንዲህ አርገው፣ ይህን አውጣ…” ምናምን እያሉ ጣልቃ ገብቶ እስከማገዝ የሚደርስ ሂስ በውስጥ ስብሰባዎች ላይ ይደረጋል። – ጥበቡን አፍቅረዋልና ለገጣሚውም ይሳሱለታል። በመቅረዝ ባለቤቱ ጥበብ ነው። አባላቱ ግን አገልጋዮች ናቸው። ማንም ግጥም ቢፅፍ ለራሱ ብሎ ሳይሆን ጥበብን አፍቅሮ ፃፈ የሚል ያልተፃፈ ስምምነት አለ። ነገሩ የገባቸውና በስነፅሁፍ ፍቅር የተለከፉ አባላት ፀንተው ቆይተው፣ በብዙ አትርፈው፣ የካምፓስ ቆይታቸውን አድምቀው ይመረቃሉ።

መቅረዝ በዚህ በግልፅ የመነጋገር ባህሉ አባላቱን ፍፁም ስለሚያስተሳስብ የቤተሰብ ዓይነት ቅርርብ ይፈጥራል። የመቅረዝ አባል እስከሆነ ድረስ መቼም ይመረቅ መቼ ከሌላ የመቅረዝ አባል ጋር ዞሮ ሲገናኝ መግባባቱ የግድ ነው። ከሁኔታዎች አንፃር አለመገናኘት ቢኖር እንኳን በተገናኙ ጊዜ ያለው ፍቅር የሚገርምና ፍፁም ቤተሰባዊ ነው። የመቅረዝ አባላት ከግቢ ከወጡ ከብዙ ጊዜ በኋላም “ሀዋሳ” ወይም “ዲላ” ነበር የተማርኩት የሚል ወዳጅ ቢገጥማቸው ስለመቅረዝ መጫወታቸው አይቀርም። – ይገርመኛል። ምናልባት ሌሎችም እንዲህ ያሉ የስነፅሁፍ ክበቦች ይኖራሉ። እንዲህ ያለ የሂስ ባህል የሌላቸው እንደሆነ ግን ይህንን ባህል ከመቅረዝ ቢወርሱ ትርፋቸው የሁለት እዮሽ ነው። – የተሻለ የስነፅሁፍ እውቀትና ፍፁም ወዳጅነት!

ደረኮ (የመፅሀፍ የጀርባ አስተያየት) 

ብዙ ጊዜ ታዋቂ የስነፅሁፍ ባለሞያ ለማይመጥን የስነፅሁፍ ስራ፥ ደረኮ (የጀርባ አስተያየት) ሲፅፍ በይሉኝታና አግባብነት በሌለው መልኩ በከንቱ እያወደሰና እየመሰከረ መሆኑን እንታዘባለን። “እንዲህ ሲል አይደብረውም?!” ለሚል ታዛቢ ራሱንና ክብሩን፣ እንዲሁም እውቀቱንና ሞያውን አሳልፎ እየሰጠ። ግን የምር አይደብረውም?! ምናልባት እንዲህ ያለው ግድየለሽነትና ከንቱ ውዳሴ፥ ለፀሀፊዎቹ አጉል ከመሳሳትና ለስሜታቸው ከመጨነቅ የሚመጣ እንደሚሆን እገምታለሁ።

አንዳንዴ ነገሩ በጣም ሲመረኝ ደግሞ ነገሩን ከስግብግብነትና እነሱ ብቻ ጎልተው ለመታየት ካላቸው ፍላጎት ያመነጩት መሆኑን አስቤ እበሳጫለሁ። (እንዲያው በልጅነት ሀሳብ እንጂ የምሩን ለሞያው የተሰጡት ሰዎች ያንን ያደርጋሉ ብዬስ አይደለም።) በዚህ ላይ በ1996 ዓ/ም ገደማ ለማይረባ መድብል የተሰጠን ውዳሴ አምላክ የመሰለ ደረኮ አንብቤ ብበሳጭ እንዲህ መግጠሜ ትዝ አለኝ….

ምናምን ጫጭሬ፣ ሰብስቤ ብሰጠው፥ አርምልኝ ብዬ፣

አድጌ እንዳልበልጠው፣ ስህተቴን አርቄ፣ ሂሱን ተቀብዬ።

ሸንግሎ ሰደደኝ፣ ‘አባቴ’ ነው ያልኩት፣ ትልቁ ሰውዬ፣

/ዮሐንስ ሞላ/

የልብን እንደማይናገሩ በሚያውቁበት ጊዜ ግን ምንም አለመፃፍ እያለ እንዳልሰብረው በሚል ስስት በባዶ ሜዳ ማሞካሸትና በከንቱ ማወደሳቸው ራሳቸውን ከማስወቀሱም ባሻገር የግለሰቡንም የእድገት ደረጃ ይወስነዋል። ለስነፅሁፍ እድገት የሚኖረውንም አስተዋፅኦ ያቀጭጨዋል። ከባለሞያ ውጪ ያለ አንባቢም ችግሮቻችን በግልፅ አይነግረንም። እኛም የሚሰጡንን ሂሶች ለመቀበል ፈቃደኞች አንሆንም። (በግል ስራዎቻችን ይቅርና አንዳንዶቻችን የምንወደው ታዋቂ ሰው (ለምሳሌ ቴዲ አፍሮ) ተተቸ ብለን እሪ እምቧ በማለት ራሳችንን ለአደባባይ ትዝብት ከመጣላችን ባሻገር ከወዳጆቻችን ጋር እስከመቆራረጥ (block መደራረግ) ድረስም እንደርሳለን።) አንድ ጊዜ የሞከሩን ደጎች ቢኖሩ እንኳን ያለመቀበል ችግራችንንና ቆራጥ እርምጃችንን ሲመለከቱ ሂስ በመስጠት አይቀጥሉም። ይሄ ግን መለወጥ ያለበት ባህል ነው። ጥሩ ስራ ሲመለከቱ ማድነቅ እንዳለና አግባብ እንደሆነ ሁሉ፣ ጥሩ ያልሆነ ነገር ሲመለከቱም እርሱን መጠቆም፥ የቀደመውን አድናቆት ልባዊነት ይበልጥ ያሳያልና ወዳጅነትን ቢያጠነክር እንጂ አይጎዳም። በመሆኑም ሊዳብር ይገባዋል።

ሥነግጥም በዘመነ መፅሀፈ – ፊት (Facebook)

Facebook እንደማህበራዊ ግንኙነት መረብነቱ የዓለምን ማህበረሰብ በማቀራረብ ረገድ እየተጫወተ ያለው ሚና ትልቅነት ግልፅ ነው። ተጠቃሚዎቹም ሀሳባችንን በደግነትና በነፃነት እንድናካፍል ‘ረድቶናል። የማያቋርጠው የ’what is in your mind…?’ ጥያቄውን በመመለስ ሰበብም አህምሮአችንን ለመረዳት እና ሀሳባችንን ለመግለፅ የምንሞክር ብዙ ነን። ሰዎች በፃፉት ነገር ላይም ሀሳባችንን እንሰጣለን። ከዚህም ባሻገር አገርን፣ ባህልና ችሎታን ከማስተዋወቅና ለሌሎች ከማጋራት አንፃርም facebook ያለው አስተዋፅኦ ይህ ነው አይባልም።

በfacebook ብቻ የሚተዋወቁ ሰዎች ከfacebook ወዳጅነት አልፈው ብዙ ነገር ሲሰሩ፣ ወዳጅነታቸውን ሲያጠነክሩ ተመልክተናል። አሁንም ብዙ ነገሮች እየተሰሩ ነው። ከዚህም ሌላ የተለያዩ የስነፅሁፍ ስራዎችን በማዳረስ ረገድ facebook ትልቅ ስራ እየሰራ በመስራቱ በተለይ የስነፅሁፍ ፍቅር ያለንን ሰዎች ወደ አንድ ማእድ እያሰባሰበን ነው። እንደመሰባሰባችን ግን ስነፅሁፉን ለማሳደግ ጥረት ስናደርግ አንታይም። የስነፅሁፍ ስራዎችም እንደመብዛታቸው መለወጥና መንጠር አልቻሉም። በጎዶሎ ሀሳብ የምንዳክር ግልቦች እንበዛለን። ግልብነታችንም የሚፈጥረው ዘመን የማይሻገሩ ግልብ ስራዎችን ነው።

በርግጥ ፅሁፍ በመፃፍ ተግባር ውስጥ የፀሀፊው ዋናው ጉዳይ (ጭንቀት) የሚሆነው በወቅቱ ያለውን ሀሳቡን ከአህምሮው ጨምቆ  ማውጣቱ ነው። ከዚያ በኋላ ለሌሎች ማድረስ አለማድረሱ ደግሞ ከፀሀፊው ፈቃደኝነት በመቀጠል በሚኖረው የማዳረሻ መንገድ ምቹነት ይወሰናል። ፈቃደኛ ለሆኑ ፀሀፊዎች facebook ዓይነተኛ መንገድ ነው። ለአጠቃቀም ቀላል ከመሆኑ ባሻገር ብዙ ሰዎችን ለመድረስ ይረዳልና በተለይ ገጣሚያን ስራዎቻችንን ለሌሎች ለማጋራት እየተጠቀምንበት ነው። በቀላሉ መገኘት ከመቻሉ (accecibility) ጋር ተያይዞ ግን ግጥሞችን እንደፃፍናቸው (እንደወረዱ) እንድናጋራ ስለሚያረገን ቢያንስ እኛ ጋር ቆይተው እንዲበስሉ አንፈቅድላቸውም።

ከዚህም ሌላ ግጥሞቻችንን ስንለጥፋቸው የሚኖሩ አስተያየቶችም አንዳንዶቻችንን ወደኋላ ስለሚጎትቱን፥ ሁሉን ነገር ግጥም የማድረግና በግጥም የመግለፅ አባዜ ውስጥ እንወድቃለን። በመሀሉም መብሰልና መለወጥ ይጠፋል። ግልብ ሆነን ላይ ላዩን እንኖራለን። አካባቢያችንንም በአግባቡ እንዳንመለከትና ነገሮችን እንዳንመረምር እንጋረዳለን። በዚህም መሀል የምንፅፈው አብዛኛው ነገር ከአፍላፊ የማይተናነስ ግልብ ነው። ዝም ብሎ ቤት ለመምታት ብቻ እንፅፋለን። ለዚህም አፀፋው ከወዳጆቻችን በደግነት የሚቸሩን ልብን የሚያቀልጡ የአድናቆትና የውዳሴ ቃላቶች ብቻ መሆኑ ነገሩን ይበልጥ አሳሳቢ ያደርገዋል።

በርግጥ ፀሀፊው ነፃነቱን ተጠቅሞ የፃፈውን አንባቢውም ነፃነቱን ተጠቅሞ ባተረፈበት ልክ ቢያመሰግን፣ ቢያወድስና አስተያየቱን ቢሰጥ አግባብ ነው። ፀሀፊዎቹ የሚሰጠውን አስተያየት የሚመለከቱበት ዐይን ግን የራሳቸውን ብሎም የስነፅሁፍን እድገት ይወስነዋል። አንባቢውም ቢሆን በግልፅ የሚመለከተው ችግር እያለ፣ እየጎረበጠውና ቅር እያለው….ባለበት ሁኔታ ላይ ችግሩን ደፍሮ መጠቆም ባይችል እንኳን፥ ዝም ብሎ በከንቱ ቢያወድስ የተሻለ ማደግ የሚችል ወዳጁን ያቀጭጨዋልና ይሄ ባህል ሊለወጥ ይገባዋል። ቢያንስ የአድናቆት መጠናችንን ከግጥሙ የልቀት ሁኔታ ጋር አጣጥመን ከፍ ዝቅ ብናረገው ገጣሚውም ግጥሙን በተመለከተ፥ ‘ወተት ነጭ፣ ጨለማ ጥቁር’ ሳይባል በራሱ የሚረዳው ነገር ይኖራል። ልክ ባህርይውን በደንብ የምናውቅለት የቅርብ ወዳጃችን ዝም ስንል ምን ማለታችን፣ ለአድናቆት ቃላት ጠፍቶን ስንንተባተብ ምን ማለታችን እንደሚገባው ሁሉ፥ በfacebook ግጥሞቻችን ላይም ያንን የመግባባት ደረጃ እና ስምምነት መፍጠር  ብንችል የግልብ ዘመን ግጥሞቻችን በተሻለ የግልብነት ይዞታ ላይ እንዲገኙ ይረዳናል።

በተለይ ራሳችን ግጥም የምንሞክር ሰዎች ለሌሎች አስተያየት ስንሰጥ በሀላፊነት ሊሆን ይገባዋል። እርስ በርሳችን ብንተራረም (በአደባባይ ቢከብደን በውስጠ ሳጥን (inbox) ስነፅሁፍን ከማሳደግ በተጨማሪ ጥቅሙ ለራሳችን ነው። ማንኛውም ዓይነት ሂሶች ሲደርሱንም ከልብ አመስግነን በመቀበል ቆም ብለን ማሰብ ብንለምድ ለስነፅሁፍ እድገት ብሎም ለግል ስብእናችን ይረዳናልና ቢንለማመደው መልካም ነው ብዬ አምናለሁ። በዚህም የዘመንን ግልብነት መለወጥ ባይቻለን እንኳን ከህሊና ወቀሳ እንድናለን።

ሁሉም በእኔ እምነት ነው። እስኪ የእናንተን አክሉበትና እንጨዋወት።