ሰካራም ቀለም

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፥ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማእከል፥ በ2001 ዓ/ም ያዘጋቸው የአማርኛ መዝገበ ቃላት “ሰከረ”ን በግስነት — ‘በአልኮል መጠጥ፣ በዕፅ…ምክንያት ስሜቱን የሚሰራውን መቆጣጠር አቃተው።’ ይልና፤… ከሰከረ ለቅፅልነት የረባውን “ሰካራም” —
1. አልኮል መጠጥ አዘውትሮ የሚጠጣ፥ ጠጪ።
2. አልኮል መጠጥ ጠጥቶ የሰከረ።’ ብሎ ይተረጉመዋል።

የእኛ ቤት (የእህቶቼ) መዝገበ ቃላት ደግሞ “ሰካራምን” ከስካር (ስ) ከረባ ቅፅልነትstock-photo-paint-splashing-blotches-of-different-colors-105645551 ባሻገር በቀለም ዓይነትነት ያስቀምጠዋል።… ቃሉን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ ሳለሁ ነበር። [ትንሽና ትልቅነታቸው እርስበርሳቸው ሲተያዩ ሆኖ]… ትንሿ እህቴ ትልቋ እህቴን….
“እሙዬ ክሩን አቀብይኝ” አለቻት።
ትልቋ ቀልጠፍ ብላ ቀዩን ክር ብድግ ስታረገው …
ትንሿ: “አይ…ሰካራሙን አለቻት”… ሌላ ቀይራም አቀበለቻት። ደብለቅለቅ ያለ ቀለም ያለውን ቱባ ክር አንስታ አቀበለቻት። መግባባታቸው ገረመኝ። ልቤ ‘ጉድ’ አለ! (ብለን እናካብድ? ሃሃሃ…)

እነሆ ከዚያ በኋላ “ሰካራምን” በቀለም ዓይነትነት አወቅሁኝ። ሰካራም ማለት ብዙ ዓይነት ቀለማት በአንድነት ሲሰፍሩ (ካለመደባለቅ) የሚኖር መልክ መሆኑን ተማርኩኝ። ስሙን ከማወቄ (ከመማሬ) በፊት ሰካራሙ ክር ተቀምጦ ሳየው፣ በአቀላለሙ መልክና በቀለም አቀያየጡ ስርዓት እገረምና …‘ወይ ጉድ! እንዴት አቀለሙት?’ ብዬ ለራሴ እጠይቅ ነበር።… ከርሱ በፊት በስንቱ ተገርሜ ስጠይቅ እንዳልኖርኩ፤…. ከርሱ በኋላ በስንቱ ተደምሜ እንደማልጠይቅ፤… ላሊበላና ይምርሀነ ክርስቶስን አይኔ አይቼ የአድናቆት ጥግ ላይ እስክደርስ ድረስ…. (ውይ እርሱንም መፃፍ አለ ለካ?! :-/)

ከዚያ በኋላ በልጅ አእምሮዬ ሰካራም ሳይ ደስ ይለኝ ነበር። fክሩንም የሰከረውንም። እንደ ስምም እንደ ቅፅልም። (እንደ ስም – ቀለሙን፤ እንደ ቅፅል – ጠጥቶ ራሱን የሳተውን)። ከማንም በተሻለ ሰካራምን እንደተረዳሁ ይሰማኝና በልቤ እሸልል ነበር። የሰዉን ግድግዳ እየደበደበ (ሲያጠብቅ፣ ሲያላላ)፣ ያገኘውን እየጠለዘ፣ እየተሳደበ፣ እየተዘለፈ… ሲያልፍ፣ ህፃናቱ እየተከተሉትና ኮቱን እየጎተቱ : –

“ሰካራም ቤት አይሰራም፣
ቢሰራም ቶሎ አይገባም
ቢገባም ቶሎ አይተኛም
ቢተኛም ቶሎ አይነቃም…”

…ሲሉት እኔ በራሴ ሀሳብ እብሰለሰል ነበር። (ቃሉን በቀለምነት ካወቅሁ በኋላ ፀባዬ ተቀይሮ) ለእኩዮቼ ሰካራሙን ሰውዬ ከቀለሙ ጋር አነፃፅሬ እንዴት እንደማስረዳቸው አስብ ነበር። ሲሰክር ስለሚያየው የሚያምር ሰካራም ቀለም ዓይነት እንዴት እንደማስረዳቸው (ቢከራከሩኝ እንኳን ክሩን ከቤት አምጥቼ ማሳየት እንደምችል ሳይቀር እያሰብኩ) በልቤ አቀናብር ነበር። ቅንብሬን ሳልጨርስ ሰካራሙ ያልፍና ይረሳ ነበር። ሌላም ሰካራም ይመጣል… እርሱም እንደ አዲስ ሳቀናብር ያልፋል። ሌላም… ሌላም… ሌላ ቅንብርም… ሌላአአአ…

ሰካራም ቀለም እና ቅዳሜ

አሁን አሁን ግን ትንታኔውን ልብ አልለውም፡፡ እንዲያው imagesከሰካራም ቀለም አመሰራረትና ትንታኔ፣ እንዲሁም ከልጅነት ትዝታዬ ይልቅ የቀለሙ ዓይነት ተዋህዶኝ የቀለም ዓይነት ለመጥራት እጠቀመዋለሁ፡፡ የሚያምር ቀለም። ሁሉም ነገር ያለው። ሁሉም የሞላለት። ምንም ያልጎደለው። ቅዳሜ ለእኔ እንዲያ ነች። ቅዳሜ መጥቶ ምን ጠፍቶ? ሁሉ ነገር ሙሉ ነው…. ቀይ ቢሉ፣ አረንጓዴ ቢሉ፣ ሀምራዊ ቢሉ፣ ሰማያዊ ቢሉ…. የቀለም ዓይነት። የመልክ ዓይነት። ድርድርድርድርድር….ጥቁርም ሳይቀር!…
ግን ጥቁሯን የምታሳየው ከስንት አንዴ ነው። ምናልባት በዓመት አንድ ጊዜ? – “እንደ ባቲ መንገድ?” ውሸት ምን ይሰራል?… የባቲ መንገድ የመጣልኝ አሁን ነው። ልክ አሁን። የጂጂ ሙዚቃ ዞሮ ተዟዙሮ “ባቲ”ዋ ጋር ሲደርስ… ባቲን ስትጫወት… ባቲን ስታንቆረቁር…. ወይ ግጥምጥሞሽ! ብለን ተደመምንና እንደምንም ሰካናት! ሃሃሃ…

“♩ ♬ ኧረ ባቲ ባቲ፣ ባቲ ከተማው
ከሚበላ በቀር የሚጣል የለው፤
እንደ ባቲ መንገድ፣ እንደ ወዲያኛው፣
በዓመት አንድ ቀን ነው፣ የምትገኘው፤ ♪

♫ ጨረቃ ባትወጣ፣ ደምቃ ባትታይ፣
አንተ ትበቃለህ፣ ለአገሬ ሰማይ፣
አንተ ትበቃለህ፣ ለአገሬ ሰማይ። ♫”

ተኝተን ስንነሳ…

አዋሳ ገብርኤሏ ደርሷል። — ቅዱስ ገብርኤሏ! — መልአከ ገብርኤሏ! – ነገ ነው። በልጅነት አፍ 735219_299686156819091_45223971_n ደግሞ – ‘አንዴ ተኝተን ስንነሳ ገብርኤል ይሆናል።’ ቀጤማው፣ ዳቦው፣ ጠላው፣ ጠጁ….. – ፌሽታ!! — አንዴ ተኝተን ስንነሳ ሁሉም ይሆናል። (ልጅ እያለሁ ‘አንዴ ተኝተን ስንነሳ….’ ‘ሁለቴ ተኝተን ስንነሳ…. እንዲህ ይሆናል!….. እንዲህ ቀን ይመጣል።’ ምናምን ስንል ዛሬ ናፕ የምንለውን ዓይነት ቆራጣ እንቅልፍ ተኝቶ መነሳትና ቀኑን ጎትቶ ማምጣት ያምረኝ ነበር። የማልፈልገውን ቀን ለማራቅ ደግሞ (ለምሳሌ ትምህርት የሚጀመርበትን ቀን) ብዙ በማምሸት (ባለመተኛት) ቀኑን መግፋት ያምረኝ ነበር። — አይ ልጅነት!)

ገብርኤሏ ሲደርስ ከተማው ብቻ ሳይሆን የሰዉ ስሜትም ድብልቅልቅ ይላል። የልቡ ሁኔታም ድብልቅልቅ ይላል። [በልባቸውም ቢሆን]…. አማኙ – ይሸልላል!…. ሌላ አማኙ – ይቀናል! ….. ፈታ ያለው ኢ-አማኒ በፌስቲቫሉ ይደመማል! – የልቡ ዳሌ በደቡብ ስልት ይደንሳል!… ወግ አጥባቂው ኢ-አማኒ ደግሞ ይበሳጫል! – የርሱን ማወቅ (በራሱ የተረጋገጠውን፣ ባነበባቸው መፅሀፍት የፀደቀውን ማወቅ) እየተነተነ ለህዝቡ አዛኝ ይመስላል (ወይም ያዝናል)!… – ያም ሆነ ይህ ዓመት በዓል ነው – የሽለላ! የቅናት! የድማሜ! የብስጭት ዓመት በዓል! – ሁሉንም እንኳን አደረሰው!!

እመት አዋሳም ከዓመት በዓሎቿ አንዱ ደርሶባት ወገቧን አስራ ሽር ጉድ ትላለች። ሰው ተቀብላ ታሳርፍና ሌላ መምጣት አለመምጣቱን ለማየት ከአንገቷ ቀለስ በማለት ዓይኖቿን በጥቁር ውሀ በኩል ወርወር ታደርጋለች። (ሻሸመኔ ባለውለታዋ ነች።… የወዲያኛዎቹን ከየአቅጣቻው አሰባስባ ታሳልጥላታለች። ታስተናብርላታለች። ታስተላልፍላታለች።) ደግሞ ታያለች… መለስ ብላ በቱላ፣ በቦርቻ በኩል ወደ ይርጋለም – ዲላ — ይርጋ ጨፌ — ሀገረ ማርያም —- ያቤሎ —– (ጲጲጲጲ…) ተምዘግዝጋም፣ እንዴትም አባቷ ብላ ቢሆን ሞያሌ ድረስ መብቷ ነው… – ልብ ካለች፥ ለገብርኤሏ የሚሸክፍ እንግዳ አታጣም።

አመት በዓሏ ሲደርስ እንዲህ ነች።… መለስ ቀለስ ነው ስራዋ። እንግዶቿን ትቀበላለች። — ዳኤ532674_3168644382957_136314712_n ቡሹ! – አኒ ኬራ!! መኪኖቹ ምዕመኑን ሞልተው ከተለያየ ቦታ እያመጡ መናህሪያዋ ላይ ያራግፉላታል። ቤተስኪያኑ በራፍም ያራግፉላታል። መኪኖቹ ደርሰው ማራገፊያቸው እንደቆሙ…. ቤንዚን ጠብ እንዳለበት እሳት ቦግ ያለ የመራገፍ ትርምስ ይታያል። — ምዕመናን ከመኪኖቹ ሲወጡ…. ቀን በሌዎች፣ ተራ አስከባሪዎች፣ ሌቦች (ያው ግርግር ለሌባ ያመች የለ?) ወደ መኪኖቹ ሲሮጡ እኩል ይሆናል። — እቃ ለመያዝ….. እቃ ለማስያዝ…. — ትርምስ!

ቦግ ያለው የሰው ትርምስ (እንደ እሳት ያለው) ወዲያው ክስም ይላል። (የሰው ቤንዚን ሲደፋበት መልሶ ቦግ እስኪል ድረስ) … ደርሰው ሲበተኑ። ምዕመናኑ ወደ ማረፊያቸው…. ቀን ሰራተኞቹ ወደ ጥጋጥጋቸው…. — ፀሀይዋን ሽሽት! ውይ ፀሀይ…. ለነገሩ ለማያውቃት ጥቁር እንግዳ እንጂ ለኗሪዎቿ ብርቅ አይደለችም። ስትጠፋ ነው ብርቅ። — ‘ኡኡቴ…. ማን ሊሞት ይሆን?’ ይባልላታል። ማን ሲሞት ፀሀይ ጠልቆ እንደሚያውቅ… — ራሳቸው ኡኡቴ!

እንግዲህ ነገ ነው ቀኑ። ከየቦታው የተሰበሰቡት ምዕመናን ነጠላቸውን አንጠላፍተው ከተማው282820_299685563485817_469295871_n አስፓልት ላይ ከቤተክርስቲያኑ ወደ ሀይቅ — ወደ እርሻ ጣቢያ መንገድ — ወደ ማውንቴይን —- ወደ ሰፈረ ሰላም (አቶቴ) (አላሙራ) —- ወደ ቅያሶቹ —- ወደ…. ይሰመራሉ። ልክ መንገዱ ላይ የተደፋ እርጎ ሊመስሉ (በታላቁ Adam Reta ልጅ፣ የግራጫ ቃጭሉ መዝገቡ አገላለፅ)። ከቤተስኪያኑ የተደፋ እርጎ ግን አይመስልም።… መሀል ላይ፣ ከቤተስኪያኑ ፊት ለፊት የቆመው የሀውልት ደንቃራ ያደናቅፈዋል….

ኤፍ ዋይ አይ!

ዮሐንስ ረቡዕ ረቡዕ ጫት አይቅምም።
— ሀሙስ ሀሙስም….
— አርብ አርብም….
— ቅዳሜ ቅዳሜም…
— እሁድ እሁድም…
— ሰኞ ሰኞም…
— ማክሰኞ ማክሰኞም…!!
ይህን ብለን ጨዋታችንን እንቀጥላለን. . .
* * *
ድሮ (ወግ ነው መቼስ ዮሐንስም ድሮ አለው!) ሲባል ይሰማ ነበር… አሁን ግን ተምታቶበት በደንብ አይለየውም። ወይም ያኔ ሲነግሩት በደንብ አልሰማቸውም ነበር። ወይ ደ’ሞ በደንብ አልነገሩትም. . . (ምናልባት ነጋሪዎቹ ቃሚ ከነበሩ፥ ለመቃም ሲጣደፉ፣. . . ሊፈርሹ ሲዋከቡ. . . ወይም ደግሞ አጣርተው ስለማያውቁት. . . ወሬውን አጥርተው አልነገሩትም። ወይ ደግሞ በምርቃና አዛብተውታል። ወይ ደግሞ. . . ) የራሳቸው ጉዳይ! ብቻ ግን እንዲህ ነበር ያሉት. . .
             ‘ያልቃመ ተጠቀመ፣
የቃመ ተለቀመ?!’
ወይም. . .
‘የቃመ ተጠቀመ፣
ያልቃመ ተለቀመ?!’
እነሆ ዮሐንስ አለመለቀሙን ግን እናውቃለን። ቢቅም ኖሮ ግን ማን ነው የሚለቅመው?… ማለቴ ማን ነበር የሚለቅመው? ዱካክ በወፍ አምሳል? (ስለ ዱካክማ መዓት ያውቃል።) የምሩን፥ ይህቺ ለቀማ ግን ፌክ ሳትሆን አትቀርም። ይልቅስ የሆነ ነገር ትዝ አለው. . .
* * *
መርካቶ . . . መሀል ከተማ. . . እዛ የማይሸጥ የለ መቼስ. . .! ከእለታት በአንዱ ቀን. . .

ከሚሸጡ እቃዎች፣ አልባሳት፣ ሸቀጦች፣. . . መሀል ጥቅሶች ነበሩ። የሚሸጡ ጥቅሶች። የድሀን ቤት ማስዋቢያ። ቀዳዳን ሸፍነው እግረ መንገዳቸውን የሚነበቡ። ከምሁር ተርታ የሚያስሰልፉ። በተስፋ የሚሞሉ። ከሀይማኖታዊ እስከ ፆታዊ. . . –ልክ እንደ facebook status update የሚመስሉ ጥቅሶች. . . ጥቅማቸው የሁለት እዮሽ ነው። የልብን ቀዳዳ ባይደፍኑም ማባበል። እንዲሁም የቤት ግድግዳ ቡድርስ መሸፈን። (ብርድ ለመከላከል? ለዐይን ለመሙላት?)

ከ “የሚረዳኝ የለምና ከእኔ አትራቅ” (መዝሙረ ዳዊት 22፥11) እስከ. . . “አድርገህልኛልና ለዘለዓለም አመሰግንሀለሁ።” (መዝሙረ ዳዊት 52:9) ከ “rose is rose, sky is blue,/….and I love you!” እስከ “ሮዝ አበባ ላይ ታምሜ ተኝቼ/….ምናምን ምናምን….” በቀለም (በማርከር) ያበዱ ጥቅሶች። እነሱን የሚያጅቡ ምስሎች ተለጥፎባቸው። ሁሉም ነገር በእጅ ነበር የሚሰራው….

አቤት የጥቅሱ ገበያ: ከመጠቀሚያ. . . እስከ መጠባበቂያ. . . ጥቅስ ድረስ የተሟላለት። ከችግር ቀን ስሞታ (አቤቱታ) እስከ ምቾት ቀን የእፎይታ ድምፅ። የችግሩ — በችግር ቀን፣ የሚበላ ሲጠፋ፣ ወዳጅ ፊት ሲነሳ፣ ጎረቤት ደጁን ሲዘጋ፣ ፀሀይ በቤቱ ስትጠልቅ ይለጠፋል። (ወይ ደግሞ እንዲያ የሆነ ሰው ይገዛዋል። እንዲያ ነኝ ብሎ ያመነ። ራሱን የመዘነ ሰው – ደሀ ሰው. . . ) በቦታዋ ጥቅሷ ቦግ ትላለች። — ችጋር ወለድ ፀሎት፣ ልመና፣ ተስፋ፣ እምነት. . . ከዚያ ሁሉ በላይ ደሞ የቤትን ቀዳዳ የመድፈን ተልዕኮ የሰነቀ!

የእፎይታ ድምፃም ጥቅሱ፥ በተድላ ቀን ይወጣና ይለጠፋል። በአንፃራዊ ተድላ። በአንፃራዊ ጥጋብ. . . በአንፃራዊ ምቾት. . .ፀሀይ በቤቱ ብቅ ስትል። ኩራዞች ላምባ ሲሞሉ። ምድጃው እንጨት ሲነድበት። (ምናምን ውስጡ ያለው ድስት ሊጣድበት) ድስት ሲታጠብ. . . (ወይም እንዲያ ሆነልኝ ብሎ ያሰበ ይገዛዋል።) — ምስጋና፣ እፎይታ፣ እርካታ. . . ከዚያ ሁሉ በላይ ደግሞ ማንቆላለጭ! ማናፋት! ማቅራራት! (ሰው እግር ጥሎት ቤት ዘው ሲል ጥቅሱ ዘው እንዲልበትና እንዲማረር።)

ገጣሚዎቻቸው የማይታወቁ ግጥሞች። ከ2 እስከ 4 መስመር የሚሆኑ ድርድር መስመሮች። ደሀው፣ ያልተማረው፣ ጎረምሳው. . . እንደሙላቱና እንደጉድለቱ የሚገዛቸው። ከገዙበት ስሜት ውጭ ሆነው (ትንሽ ሲሻሻሉ) ቢያነቧቸው በሳቅ ባያፈርሱ እንኳን በፈገግታ ሊያፈኩ የሚችሉ ጥቅሶች….ግጥሞች….– ከዚያ ባሻገር ግን ብርድ የሚከላከሉ። የቤት ቀዳዳን የሚደፍኑ። (የኑሮው ቢቀር)

ሻጩ (የነቃው ነጋዴ) ‘እልል በል ሀበሻ….’ እያለ ለተራበ ሀበሻ ይሸጣል። መንገደኛውን ለመማረክም ጮክ እያለ በተራ በተራ እያነሳ ያነባቸዋል። ሀበሻውም በልቡ ‘እልል’ እያለ ይከባል. . . ገበያውን! የጥቅሱን ጥብስ ገበያ!

አንደኛው እንዲህ ይነበባል. . .
“በጠፍጣፋ ድንጋይ ከተዘጋ በሩ፣
እናት አትገኝም፣ እንደ ወፍ ቢበሩ።”

ሞያዊ ትንታኔ አያሻውም። መልእክቱ ደርሷል። ድንጋይ…በር…ምናምን… ምንም እንደማይሰሩ፣ በሩ ተከፈተ ተዘጋ ምንም እንደማይረባው….. ገጣሚውም፣ ሻጩም ገዢውም ግጥም አርገው ያውቁታል። ግን ግድ የላቸውም። (ለነገሩ ማን ይመረምረውና ቀድሞ?) በቃ እናት ወርቅ ናት ነው መልእክቱ። ናት! ናት! ናት!

ብዙ ሰው ለሚያምነውና ለሚያውቀው ነገር ማረጋገጫ ደስ ይለዋል። ምናልባት ለዚያ ይሆናል ግብይቱ—ማረጋገጫ መፈለግና፣ ማረጋገጫ መስጠት። ይሄም ማረጋገጫ ነው።…. ግን ደግሞ ንግድ! በምስኪን ኗሪ ስስ ጎን የታለመ ትርፍ! –ከዚያ ሁሉ በላይ ለሰሪውስራ!! ‘ስራ ለሰሪው፣ እሾ ላጣሪው!’ ለተሰሪው ደግሞ የግድግዳን ሽንቁር መድፈኛ ወሽመጥ! ግድግዳን ማሳመሪያ ቀለም!

ሌላው እንዲህ ይቀጥላል. . .
“አንድ ፍየል ነበር እንደ እኔ የከፋው፣
የሆዴን ብነግረው፣ ያ’ፉን ቅጠል ተፋው።”

ፍየሉ ይቅም ነበር? ፍየሉ ይሰማል? እርሱ ሞኝ ነው ለፍየል የሆዱን የሚነግረው? ምናምን ምናምን….ብዙ መጠየቅ ይቻላል። ግን ማንም አይጠይቅም። ዋናው መልእክቱ ነው። — ‘በሆዴ ብዙ አለ….ፍቶኛል’ ነው መልእክቱ!

ይቀጥላል. . .
“ሁለት ውሾች አሉኝ የማሳድጋቸው፣
ሰምቶ መቻልና ችሎ ማለፍ ናቸው።”
እዚህም መልእክቱ ደርሷል። ስለችሎ ማለፍና ስለሰምቶ መቻል (ህብተረሰባዊ ምርጥ ባህርያት) ይሰብካሉ።. . . ሌላም ብዙ ብዙ. . .

ከእነርሱ መሀልም ስለጫት የሚያወራው እንዲህ ይላል. . .
“የዓለም ሳይንቲስቶች በእውቀት የመጠቁ፣
ሁሉም ይቅማሉ እየተደበቁ።”

ይህኔ ጉድ ፈላ። ሲያዩት (በልጅ ወይም ባልበሰለ አእምሮ) ብስለቱ ይማርካል (ወይም በሳል ይመስላል)። ፍልስፍናው ይጠልቅለትና አንድ ብሯን መዠረጥ አርጎ መግዛት ነው (ያው ለተገለጠለት)። ግን ከዚያስ? አሃ….መልእክቱስ? ‘ቃሙ ችግር የለውም?!’ ‘እንኳን እናንተና የዓለም ሳይንቲስቶችም ይቅማሉ?!….ጫት ጀት ያደርጋል?!’…. ምናምን ምናምን….

መቼስ የእኛ ሰው ለሚያደርገው እያንዳንዱ ነገር ደጋፊና አረጋጋጭ አካል ሲያገኝ ደስ ይለዋል። ድጋፉ በግጥም ተገልፆ በወረቀት ሲሰፍርማ በቃ! ዮሐንስ ጥቅሱን (ግጥሙን) or whatever ባየበት ቅፅበት መደቡ ላይ አንድ ኮፒ ብቻ ነበረ። ኪሱ ውስጥ ደግሞ አንድ ብር። አናፍቶ ገዛሁት። ተከራክሮ። (ክርክሩ ለደንቡ ነው….ለገዥና ሻጭ ደንብ….)

ያኔ ጥቅሱን የገዛው ማርኮት አልነበረም። የዋህ ቃሚ (ከሰው ተደብቆ እየቃመ ለማቆም የሚታገል) አግኝቶት ሀሳቡን እንዳይለውጥ አሰቦ እንጂ።….የ6ኛ ክፍል ተማሪ ነበር… ፓ! ጀትነቱ!…. ቅሞ ነበር እንዴ? ሆሆሆ…..የምር ግን እንዲህ ዓይነት ተቆርቋሪነት ያስቀናል። እነሆ ዛሬ በ6ኛ ክፍሉ ዮሐንስ ቀና…. (ይሄ ነገር ለራሱም አስቆታል) የምር ግን 6ኛ ክፍሉ ናፍቆታል….ትናንት 6ኛ ክፍል ሲደርሱ የተለውን የሚወደውን ጓደኛውን ከ16 ዓመታት በኋላ በድምፅ ሲያወራው ባሰበት….

ከጥቅሱ መደብ ጥቅሶች ይሄም ጥቅስ ትዝ አለው. . .
“ታምሜ ብተኛ፣ ቆሜ ባንቀላፋ፣
እንገናኛለን እኔ አልቆርጥም ተስፋ።”
***

አሁን ልቡ እየዘመረ ነው….በደማቋ ጨረቃ ውበት ልቡ ጠፍቷል…. ኧረ እንዲህም አድርጋው አታውቅ… ልጆቹ ሲዘምሩ በሀሳቡ ይሰማዋል። የርሱም ድምፅ ይሰማዋል….መዝሙራቸውን እየሰማ በየመሀሉ ይጠይቃል….

“ጨረቃ ድምቡል ቦቃ
አጤ ቤት ገባች አውቃ፣
/እሿ ደግሞ ሾካካ ነች። ንጉስ ቤት መግባት ትወዳለች። ማለቴ ንጉስ ልብ…:)/

አጤ ቤት ያሉ ሰዎች
ፈተጉ ፈታተጉ
/ገብሱን? አጃውን?/

በቁልፊት አስቀመጡ
/ለምን?….ከዚያስ?/

ቁልፊቷ ስትሰበር፣
/ውይ….ማን ሰብሯት ይሆን?/

በዋንጫ ገለበጡ፣
/ቢራውን?…አሃ! ሊጠጡ?/

አጃ ቆሎ፣ ስንዴ ቆሎ
/ውይ…. ስንዴ ቆሎ ይምጣብኝ። በሱፍ ያበደ ስንዴ ቆሎ። አቆላሉ…አበላሉ… ኧረ ማቅረቢያ እንቅቡስ ቢሆን?! መብላት ግን ደስ አይለኝም። ሲቆላ ሳይና ሰዎች ሲበሉ ሳይ ግን ሰው ይናፍቀኛል። በክረምት. . . ስንዴ ቆሎ. . . ከሰል ተቀጣጥሎ. . . ጋቢ ተለብሶ. . . ሲበላ. . . ሲቆረጠም. . . ሲሞቅ. . . ፓ!/

ያቺን ትተህ፣ ይህቺን ቶሎ!”
/ወይ ጉድ…የቷን ትቼ? የቷን ቶሎ?/

በላይ በላዩ ይጠይቃል። ልጅነቱ ናፍቆታል. . .
***

ቀጠለ. . .
በሀሳቡ መጡበት — ልጅነቱ. . . ጓደኞቹ. . . የሚቀናበት (ጠብቆም ላልቶም ቢነበብ ግድ የለውም) ዮሐንስ. . . ዘፋኙ. . .

“ኧረ ልጆች ልጆች እንጫወት በጣም፣
ከእንግዲህ ልጅነት ተመልሶ አይመጣም።”
/ከ6ኛ ክፍል በታች የነበሩ ጓደኞቹ/

“…………………………………………………..
……………………………………………………
……………………………………………………
……………………………………………………”
/የሚቀናበት ዮሐንስ/

“ላይታረስ ጉም (?)፣ ኑግ እንደ ሱፍ ላይነጣ፣
ተመልሶ ናፈቀኝ፣ ተመልሶ ላይመጣ…”
/ዘፋኙ/

ወደ ጨረቃዋ ተመለሰ. . . አይፈረድበትም ኧረ! በጣም ታምራለች. . .
አሁን አይጠይቅም. . . ዝም ብሎ ይዘምራል. . .

“…ጨረቃ ድምቡል ቦቃ
አጤ ቤት ገባች አውቃ፣
አጤ ቤት ያሉ ሰዎች
ፈተጉ ፈታተጉ
በቁልፊት አስቀመጡ
ቁልፊቷ ስትሰበር፣
በዋንጫ ገለበጡ፣
አጃ ቆሎ፣ ስንዴ ቆሎ
ያቺን ትተህ፣ ይህቺን ቶሎ!…”

 

ተ.እ.ታ.

ከሳሁኝ፣ ጠቆርኩኝ፣ ጉልበት ደሜ ነጣ፣
አካሌ ‘ረገበ፣. . . ደም ስሬ ተቆጣ፣
ክብደቴ ቀነሰ፣. . . ቆዳዬ ገረጣ. . .
በአስራ አምስት በመቶ!

ኩም ኩርምት አለ፣ አጠረ ቁመቴ፣
ደም-ግባቴ ጠፋ፣ ከዳኝ ሰውነቴ፣
ወዜ ጠንጣፈፈ – ነጠፈ ከፊቴ፣
በአስራ አምስት በመቶ!

ለዛ ቢስ ሰው ሆንኩኝ፣ ከውካዋ ዘረጦ፣
አቅም ከድቶኝ ዛሬ፣ አጥም፣ አጥንቴ ገ’ጦ፣
ፀጉሬ ሸሽቶ፣ ሳስቶ. . . ቁመናዬ ጎብጦ፣
በአስራ አምስት በመቶ!

ችጋሩ ተጠጋኝ፣ ‘ራቀኝ ብልፅግና፣
ችሮታን ዘነጋሁ፣ ጠፋኝ ልግስና፣
ደጃፌ ተዘጋ፣. . . ቤቴ ሆነ ኦና፣
በአስራ አምስት በመቶ!

ንፉግ ሆንኩ፣ ስስታም፣ አጓጉል ቋጣሪ፣
እንኳንስ ከሌላው፣ ከአፍ ነጥቆ ቀባሪ፣
አጎብዳጅ፣ ተልከስካሽ፣ ተባራሪ ኗሪ፣
በአስራ አምስት በመቶ!

ያንንም. . . ያንንም፣. . . ብዙ ክፉ ክፉ፣
በአስራ አምስት መቶኛ፣ ምን ያልሆንኩት አለ?
ካየሁ፣ ከበላሁት፣ ካሸተትኩት ሁሉ
ካፌ እየነጠቀ – አንድ እሴት ሳይጨር – ‘ቀፈቱ እየዶለ።

/ዮሐንስ ሞላ/

ግን ምን ያጣድፈናል?

አንዳንዴ ነፍሴ ሽማግሌ ነገር ትሆንብኛለች። በዚህም ራሴን እታዘበውና ብቻዬን እስቃለሁ። በቀላሉ ሊማርከው ይችላል፣. . . አጓጉቶት ይመርጠዋል. . . ተብሎ የሚታሰብ ነገር ልክ ደጃፌ ሲደርስ ራሱን በዜሮ ያባዛል — አንዳንድ ጊዜ በልማድ (tradition). . . — አንዳንዴ ደግሞ እንዲያው በደመነፍስ (instintct)። ጎጂ ያልሆነ ልማድ ካለምንም አሳማኝ ነገር ሊቀየር ሲል (ወይም ሲቀየር) ይደብረኛል፤. . . ደመነፍሴን ደግሞ ህይወቴ ላይ እንዲወስንልኝ ፊትና እድል ባልሰጠውም በደንብ አምነዋለሁ። ችላ ስለውም በሙሉ ልቤ አይደለም።

ዘመናዊ እውቀትና የኑሮ ወከባ፣ እንዲሁም ትእቢትና ትምክህት ባይጋርዱንብ ኖሮ ደመነፍስ የሚነግረን ብዙ ነገር እንዳለ አስባለሁ። አንዳንዴም ደመነፍሳችን ጮሆብን. . . ሳንሰማው ቀርተን፣ የጠረጠርነው (ግን ደግሞ ችላ ያልነው) ነገር ሲደርስ — ‘ውይ! ታውቆኝ ነበረ. . . ፊቴ ላይ ነበር. . . እያሰብኩት. . .’ ምናምን ብለን የፀፀት ሀረጋትን እንደረድራለን። የራሳችንን ማሰላሰልና ማወቅ በማይጠይቁ ነገሮች ላይ ግን ደመነፍስን ማዳመጥ ሊያተርፍ የሚችል ነገር ይመስለኛል። በርግጥ የሚያከስርበት ጊዜ ሊኖርም ይችላል። – ማን አይቶት፥ ማን እቅጩን ያውቃል?

በአዲስ መስመር ወደ ጥድፊያው ስንመለስ ደግሞ . . . ቦታ ቀይሮ ፈታ ለማለት ረዥም መንገድ 801589መሄድ በጣም ያስደስተኛል። የጉዞ ጣጣዬን ቶሎ ጨርሼ፣ ካሰብኩበት ቦታ በጊዜ መድረሱንና እንዳሰብኩት መዝናናቱን ባልጠላውም፣ የመንገዱ መርዘምና መጎተት ብዙም አያስጠላኝም። ወይ ደግሞ ለምጄው ተስማምቶኛል። እንደውም ደስ ይለኛል። እንደ ጥሩ ትርፍ. . . ከመኪና መንቀራፈፍ ጋር በተያያዘ መንገድ ላይ የማንበብ ልምድ አዳብሬያለሁ። ብዙ ጊዜም መሄዴን ሳላውቀው ነው የምደርሰው።

በፍፁም ትኩረት፣ ርጋታና አለመሰልቸት ውስጥ ሆኜ ካነበብኩባቸው ቦታዎች መካከል የክ/አገር አውቶቢሶች ዋናዎቹ ናቸው። የምሄደው በአዲስ መንገድ ከሆነ ደግሞ በመስኮት በክል ግራ ቀኙን እያየሁ ተፈጥሮን አደንቃለሁ። በሀሳብ እነጉዳለሁ። ምናምን ምናምን . . . ካለምርጫና ካለማቋረጥ ማንበብ መቻሉ ቀድሞም ለነበረኝ የጉዞ ፍቅር ተጨማሪ ቅመም ሆኖልኛል። ስለሆነም ረጅም መንገድ ስጓዝ እንደ ሚኒባስ ያሉ ፈጣን የሚባሉ የትራንስፖርት አማራጮችን ለመጠቀም አላስብም።

አያዝናኑኝም። መፅሀፍት አያስገልጡኝም። ፊት ለፊቱን እንጂ ግራ ቀኙን በመስኮት እንዳይminibus-accident1 እድል አይሰጡኝም። ነፍሴን ካለአግባብ ያዋክቧታል። በጭንቀትና በስጋት ወጥረው ካለ ቅጥ ያርገበግቧታል። ያንገበግቧታል። መጨረሻዋ ለማይታወቅ እርሷ. . . መጨረሻዋን ለቅፅበት ያሳይዋታል። በፈጣሪ ስልጣን ገብተው፥ ወስደው ይመልሷታል። ካለልቧ ዥዋዥዌ ያጫውቷታል። ከዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ የብዙ ነፍሳት መጨረሻ በሚኒባስ ሲወሰን ተመልክቻለሁ። ‘ኧከሌ/ኧከሊት. . .’ ብዬ በስምና በግብር በቅርብ የማውቃቸው ሰዎች በሚኒባስ ተሰናብተዋል። ቅዳሜ ለመገናኘት ቀጠሮ የነበረኝ ሰው በዋዜማው አርብ በሚኒባስ ተፈፅሞ በጣም አዝኜ አውቃለሁ። በየቦታውም ብዙ ዓይነት ታሪክ አለ። ብዙ ሰው እንደወጣ መንገድ ላይ ቀርቷል። ቶሎ ለመድረስ ሲጣደፍ በአጣዳፊው ተሰናብቷል። – በሚኒባስ!

ብቻ ግን ረጅም መንገድ በሚኒባስ መጓዝ አልፈልግም። አልጓዝም። ከሚኒባስ ውጭ አማራጭ መጓጓዣ በማይገኝበት ቦታ ካልሆነ በቀር አማራጭም አላደርገውም። ይልቁንስ በጣም ትልቁን አውቶብስ ነው የምመርጠው። ጉዞው በህብረት ከሌሎች ወዳጆች ጋር በሚሆንበት ጊዜ ወይ ደግሞ ስለአካሄዴ ተናግሬ ሚኒባስ እንድጠቀም ሲያግባቡኝ አልሰማቸውም። እሞግታቸዋለሁ። ሲስማሙ – አብረን እየተጫወትን በትልቋ እንሄዳለን። ላይ ወርጄ ታች ወጥቼ በሀሳቤ አልስማማ ሲሉኝ ደግሞ እነሱም – በፈጣኗ፤ እኔም – በተምዘግዛጊዋ እንለያያለን። – ሰላም ከደረስን ለመገናኘት ተቀጣጥረን።

የምቀርበው ሰው መንገድ እንደሚሄድ ሳውቅም፥ የወጪ ስንቄ – ‘በናትህ/ሽ በሚኒባስ ethiopian-busrides09እንዳትሄድ/ጂ’ የምትል የጭንቀት ሀረግ ናት። ብዙዎች ይገርማቸዋል። ‘ነፍስህን አንተ ተብቀሃት አይሆንም። በትልቅ መኪናም ሄደህ አደጋ ካለ አይቀርልህም። ከቀንህ አታልፍም’ ምናምን ምናምን. . .። አይገባኝም። የእኔ ሃሳብ አደጋ ማስቀረት ሳይሆን አለመሳቀቅ ነው። ሞትማ ምናባቱ! በጉርሻ ትንታም ሲቀራርብ አይተን እናውቃለን። ቀኑ በተመደበበት ህይወት ነው የምመላለሰው ብዬ ግን አላስብም።

ረጅም ርቀት በሚኒባስ በተጓዝኩባቸው አምስት በማይሞሉ ጊዜያት ውስጥ ሳስታውሰው (አንዳንዴም በጉዞው መሀል) እስቅበት ዘንድ ራሴን የታዘብኩበት ነገር አለ። መኪናው ፍጥነቱን ሲጨምር መንፈሳዊነቴ ይጨምራል። አላግባብ ፀሎተኛ እሆናለሁ። ነጠላ ማንጠላፋትና የፀሎት መዝገብ መግለጥ ያምረኛል። (ያልያዝኩትን) የማውቀውን ፀሎት ሁሉ እደረድራለሁ። በተማፅኖ እቀባጥራለሁ። “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝና ወራት ፈጣሪህን አስብ።” (መፅሀፈ መክብብ 12፥1) የምትለዋ ትምህርት ነገርም ይበልጥ ይገለጥልኛል። በዚያም እስቃለሁ። በሰቀቀን። – እያነቡ እስክስታ!

ከዚህ በፊት ‘ሰላም መጣችሁ እንጂ ቶሎ መጣችሁ የሚለን የለምና ቀስ ብለን እንንዳ።’ የምትል የረሳኋትን ምንጭ ጠቅሶ የፃፋት መልእክት አንድ ወዳጄ ፅፏት አንብቤ ልቤ ሰርፃ ነበር። እናም ዛሬ ልደግማት ወደድኩ። — ‘ሰላም መጣችሁ እንጂ ቶሎ መጣችሁ የሚለን የለ’! ምን ያጣድፈናል? ታላቅ ወንድሜ ደግሞ ‘በአላስፈላጊ ጥድፊያ ውስጥ ሆነንና ቶሎ ለመድረስ ፍጥነት ጨምረን ተጉዘን የምናተርፋቸው ጊዜያት ተመዝግበው ቢደመሩ በዓመት አንድ ቀንም አይሞሉም። በዓመት አንድ ቀን ላላተርፍ አልሯሯጥም።’ ይላል።

ገበያን የሚያሰፋው የተጠቃሚ ፍላጎት ሁኔታ ነውና ተረጋግተን ሄደን በሰላም ለመግባት (ለመድረስ) በመፈለግ አደጋን እንቀንስ። ለፍላጎታችን የሚሆነውን መኪና መምረጥ ስንጀምር መጓጓዣዎቹ ፍላጎታችንን ለማርካትና ገበያ ለማግኘት በምንፈልገው መስመር ይገቡልናል። ‘እንደወጣ ቀረ’ ከመባል ያድነን።

የመጨረሻው ኑዛዜ

አድናን አሊ
e-mail: adnan2000free@yahoo.com

አሞራዎቹ ከበውናል። ነብሳችን ሳትወጣ ስጋችንን በጫጭቀው ሊበሉ አሰፍስፈዋል። ጉልበቶቻችን በጠኔ ዝለዋል፤ በረሃብ ደክመናል። ያረፈብንን ዝንብ እንኳ ‘እሽ’ ለማለት እጃችንን ማወናጨፍ አቅቶናል። ደክመናል። መንገዶቻችን ሁሉ ወደ አዘቅት ወስደውናል። አሁንስ የትኛው ተስፋ ቀረን? . . . . . . . . በአሞራዎቹ ከመሰልቀጥ በቀር።

እንዲህ ይሆናል ብለን እንዳንናገር አፋችን በሴራ ተተብትቦ ልሳን አልባ ሆነን ኖረናል። ከዝምታችን ብዛት አፋችን ላይ ሸረሪት ድሯን አድርታብናለች። በዚህች እንኳ የሞት ሽረት ትንቅንቅ ውስጥ ልሳናችን ተለጉሟል።
“ማን ያውጋ? . . . የነበረ
ማን ያርዳ? . . . የቀበረ” . . . ነበር ድሮ። የነበርነውም አላወራን፤ የቀበርነውም አላረዳን . . . . . ታዲያ ምን ይበጀን ይሆን? . . . . . ሞት በቀር። ‘በሞት አፋፍ ብሆን እንኳ ስለእውነት እመሰክራለሁ’ ያለው አንደበታችን ዛሬ ምን ዋጠው? ሳንናዘዝ አሞራዎቹ ሊቦጫጭቁን እኮ ነው። ለንሰሃ ጊዜ በሌለን ሰዓት . . . . . . ምነው ሐጥያታችን በኑዛዜ ቢቀልልን?

ማነህ? . . . . . . . . ፀሐፊ!
እስኪ ብዕርና ብራና ይዘህ የያንዳንዳችንን ጓዳ ጎድጓዳ እውነት ከትበህ አስቀረው። በአሞራዎቹ ከመበላታችን በፊት ኑዛዜያችንን አኑረው። በሞት አፋፍ ላይ ሆነው እውነት ይደብቃሉ ብለህ አትስጋ። ለመኖር ነው ሰው አድርባይ ውሸታም የሚሆነው።

አሁን ግን ደክመናል። በጠኔ፣ በረሃብ ደቀናል። እኛ የምንበላው ሳይኖረን የሰማይ አሞራዎች በኛ ስጋ ሊጠግቡ ነው። ይህ ነው እንግዲህ የሕይወት ሚዛን! Survival of the fittest!

ዓለም እኛን ከመመገብ ይልቅ የሰማይ አሞራዎቹን እና ጥንብአንሳዎቹን ለመመገብ መርጧል። “This Is Natural Selection!” እኛ አቅም አጥተናል። አቅም ያለው የኛን ስጋ ይበላል።

የወረወርናቸው ቀስቶች መልሰው እኛኑ ይወጉናል። የደማችን ዥረት ሆዳቸውን አሳብጧል፤ ልጆቻቸው እንደ ቅልብ ጫንቃቸው ወፍሯል። ይህ የዚች ዓለም ሚዛን ነው!

አሁን ደከመን የመጨረሻው እስትንፋሳችንን እየጠበቅን ነው። አሞራዎቹ ወደ መሬት ማዘቅዘቅ ጀምረዋል። ከቀይ መስቀል እርዳታ ቀድመው ይደርሱልናል።

አንተ ፀሐፊ!
ወረቀቶችህ በሌሉ የፍቅር ቃላት ውዳሴ እና በቅንዝረኞች ፈንጠዝያ ከሚሞሉ . . . ና . . . የኛን የሰቆቃ ኑዛዜያችንን ፃፍበት። ና! . . . አሞራዎቹ ስጋችንን እየቦጨቁ ሲሄዱ በካሜራህ ቅረጸን። የውዳቂ መጽሔትህ የፊት ሽፋን ባይሆን . . . ገጽ ማሟያ ወሬ ይሆንሃል። ሞዴሎቻችን በተጥለቀለቁበት የፊት ሽፋን ገጽ ጀርባ የኛን የጠኔ ክርፋት አትምበት።

እንዲህ ሆነው ነው የሞቱት ብለህ ዘግበን። አርሰው፣ ዘርተው፣ አጭደው መብላት አቅቷቸው በረሃብ ሞቱ ብለህ ዘግበን። አንተን ለሚሰሙ ጥራዝ ነጠቅ ሊቆች።

ካሜራዎች እያንዳንዷን ቅጽበት ያንሱ፤ እንዳንዷውን ቅጽበት ይቅረጹ።

አሁንስ ምን ቀረን? . . . ከገማው ስጋችን፤ ከከረፋው ማንነታችን በቀር። እንደ እባብ አፈር ልሶ መነሳት አልተማርን። የሌለንን ዛሬ ከየት እናምጣ?

አሞራዎቹም የሳር ጎጆዋችን ክዳን ላይ አርፈዋል። እኛን ለመቦጨቅ አሰፍስፈዋል። ከመሬት ተንጋለን ሰማዩን እናማትራለን። እግዜር ከሰማይ ወርዶ እንዲያስጥለን እንማጸናለን። ተማጽኖዋችን በበረታ ቁጥር አሞራዎቹም ወደኛ ይቀርባሉ።

ማናችሁ? . . . እናንት ፀሓፊያን!!!
የሕብረተሰቡ ችግር የኛ ችግር ነው ትሉ አልነበር? በስራዎቻችን ሕብረተሰቡን እናንፀባርቃለን ትሉ አልነበር? . . . ምነው ታዲያ የኛ ችግር ችግራችሁ አልሆነም?

************************************

ተቀበል አዝማሪ
ተቀበል ግጥሜን
ና ወዲህ ጠጋ በል

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የሚነጥቁ’

ብለህ አንጎራጉር
አንት አዝማሪ ዘምር
ጮክ አርገው ድምጽህን
ከጫፍ ጫፍ ይሰማ
ንጠቅ ከኔ ዜማ
ውሰድ የኔን ስንኝ
ድገመው እንደ ሞኝ

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የሚነጥቁ’

ድገመው አንድ ጊዜ
ማሲንቆህ ሳይበቃ
የፈዘዘች ነፍሴ፣ ባንተ ጩኸት ትንቃ።

ተቀበለኝ ግጥም
እንደማር እንደጠጅ
እንደወይን የሚጥም
ተቀበለኝ ግጥም
አንጎራጉር ዜማ
አለም ሁሉ ይስማ

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የነጠቁ’

ብለህ አሳምረው
አንተ ደሃ አዝማሪ፣ የምጮኽ ላንተው ነው።

‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የነጠቁ
ከረሃብ ጋር ታግለው ተረተው ወደቁ
በአሞራዎቹ፣ በጥንብ አንሳዎቹ፣ ተበልተው አለቁ’

 

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የሚነጥቁ’

ብለህ ዘምርልኝ
አንተ ቂል አንተ ሞኝ

* * *

ና አንተ ፀሐፊ. . .

አዝማሪው ከብዶታል
የኔን ስንኝ ማለት
እስኪ በብራናህ
ፃፈው የኔን ውድቀት

. . . . . . . . ‘ከተራሮቹ ጫፍ እስከ ሸለቆዎቹ
. . . . . . . . ምንም ማይበግረው፣ ጠንካራ ክንዶቹ
. . . . . . . . ዛሬ ከመንገድ ዳር
. . . . . . . . ወድቆ ይማፀናል
. . . . . . . . ወደ ሰማይ ያያል . . .’

ፃፈው የኔን ውድቀት
ሳትጨምር እብለት

አዝማሪው ደክሞታል
አዝማሪው ከብዶታል
አንተ ትጉህ ሰው ነህ
ፃፍልኝ እባክህ
እባክህ . . . እባክህ
ከመሞቴ በፊት
ክተብ ይሄን እውነት

****************************

አሁን አሞራዎቹም ወርደዋል። የሞት ሽረት ትግል ሊጀመር ነው። አሞራዎቹ ከኛ ስጋ የሚያገኙ መስሏቸዋል፤ ካገጠጡ አጥንቶቻችን በቀር። እስትንፋሳችን በቀጭኗ መውጫ ተወጥራለች። ቁስሎቻችን ላይ ዝንቦች ካረፉ ሰንብተዋል። እነሱን ለማባረር ክንዳችን ዝሏል።
አሁንስ ምን ቀረን? . . . ታፋችን ሲዘነጠል ከማየት በቀር። በመንቁራቸው የዓይኖቻችንን ብሌን ሲያፈርጡ ከምንሰማው የፃር ድምጽ በቀር።

ምነው ቶሎ ጀምረው በገላገሉን። የሞት መንገድ እንዲህ ይርቃል እንዴ? . . . ለምን ስቃያችንን ያራዝሙታል? . . . ለምን በድምፆቻቸው ያሸብሩናል?
ድምጽ!
ድምጽ!!
ድምጽ!!!
የአምቡላንስ ድምጽ!
ማነው ቀድሞ የሚደርስልን???

“ላነስተስልም! . . . ላነስተስልም! . . . ላነስተስልም!”

የ “በሚመጣው ሰንበት” እንቆቅልሾች?!

ከቀኑ ትርምስ መለስ ስል. . . ባለፈው ከአንድ ወዳጄ ጋር ምሳ ለመብላት ወጥቼ የገዛሁትን፣ በወቅቱ ከወዳጄ ከሰሚር ጋር ሆነን በጨዋታ መሀል ገረፍ ገረፍ አድርጌው፣ በሙሉ ትኩረት ለማንበብ በመሻት ጥሩ ሙድ ሳመቻችለት የነበርኩትን የታገል ሰይፉን “በሚመጣው ሰንበት” የግጥም መድብል. . . ቆይቼ ፉት አደረግኩት። እንዲያው እንደ እሳት ማራገቢያ ከፊፍ ጥራዝ በመሆኑ ሲነበብ ጊዜም አይፈጅ።

ከመደበኛ የምስጋና ገፅ ቀጥሎ፥ ፀሀፊው መፅሀፉን ለ3 ልጆች መታሰቢያ አድርጓል። እንዲህ ብሎ. . .
– አባታቸው ለሚወዳቸው ልጆቹ ፍቅር የሚሰጥበትን ጊዜ ያጣ ሙሉ ዕድሜውን ለህዝብ /ለሃገር/ የሰጠ ነበር
– መታሰቢያነቱም ለእነሱ : – ለሰምሃል፣ ለማርዳ፣ እና ለሠናይ ይሁን።
ስማቸውን አበጥሮ ማወቁም ይገርማል። በእውነት ለመደበኛ ኗሪ የተጠቀሱት ሰዎች ማንነት የሚገለጠው ምናልባት መፅሀፉን ከጨረሰው በኋላ ነው። እግርጌ ደርሶ መለስ ቀለስ ካለ በኋላ። ሃሃሃ. . .

በእኔ አመለካከት፥ የተካተቱት 27 ግጥሞች እንደ ግጥም ደህና የሚባሉ ናቸው። የታገልን ግጥም አዋቂነት ይናገራሉ። አወራረዳቸው፣ ምጣኔያቸው፣ ዜማ አጠባበቃቸው፣ የሀሳባቸው ጥልቀትና የሚቀመጡበት መንገድ. . . ከሞላ ጎደል ጥሩ የሚባሉ ናቸው። ምርጥ ግጥም ለተጠማ (በተለይ የኤፍሬም ስዩምን ‘ፍቅር እዚህ ቦታ ፈገግ ብሎ ነበር’ን በጉጉት ጠብቆ የሁለት እዮሽ ለተበሳጨ – በጥበቃው ዳፋና፣ የጠበቀውን በማጣት. . . ) ምስኪን የጥበብ አፍቃሪ. . . ከቁጥራቸው ማነስ የተነሳ (የቁጥራቸው ማነስ ከዋጋው ጋር ባለመመጣጠኑ) ‘ጥም ይቆርጣሉ’ ባይባልም እንኳን፥ ከጥራታቸው የተነሳ አፍ ማርጠቢያ ይሆኑ ዘንድ አያንሱም። — ያው በገለልተኛነት ቢነበቡ ማለት ነው። ቅሉ እርሱ እንደዚያ እንዲሆን አላደረጋቸውም።

ይህም ቢሆን ግን ከነድክመቱ ነው። ሌላ ሌላ ሞያዊ እክሎች ቢቀሩ እንኳን እንዲያው ማንም አንባቢ በወፍ በረር የሚታዘባቸው ስነፅሁፋዊ ሳንካዎችም አሉት። ለምሳሌ: – ምንም ሳልወጣ ሳልወርድ፣ ይህን ታይፕ በማድረግበት ቅፅበት፣ (ለማሰብ ጊዜ ሳልወስድ)… ያነበብኩትን በማስታወስ ብቻ ትዝ ከሚሉኝ መሀል. . . — ባለቤትን ለመጠቆም ‘ህ’ መጠቀም ሲገባው፥ ብዙ ቦታ ላይ ‘ክ’ ይጠቀማል። እንኳን ያልሆነና — ለነገሩ ቢሆን እንዲህ አይሆንም ነበር — ታገል የእኛ ቤት ልጅ ቢሆን ኖሮ፣ በዚህ ምክንያት ከአባቴ ጋር ሁሌ ይጣሉ ነበር።

አባቴ ‘በላክ?’. . . ‘ጠጣክ?’. . . ‘መጣክ’. . . ሲባል በጣም ይበሳጫል። ተበሳጭቶም ዝም አይልም። መልሶ ያበሳጫል። ስህተቱ በተፈፀመበት ቅፅበት ሁሉ ተከታትሎ ያርማል። ሲያርም እንደ ሰባኪ — “‘በላህ?’. . . ‘ጠጣህ?’. . . ‘መጣህ?’. . . ነው የሚባለው።” ብሎ አይናገርም። . . . ይልቅስ ‘በላክ?’. . . ‘ጠጣክ?’. . . ‘መጣክ’. . . ብሎ የመጨረሻዋን “ክ” አጥብቆ ንግግሩን ይደግማል። በዚያም የነሩንም አካሄድ ያስታጉላልና ያበሳጫል። መበሳጨቱ የከፋውም ስህተቱን አይደግመውም። – ቢያንስ የእኔ አባት ፊት።

ታገል ግን ይላል – ‘ተስፋክ’. . . ‘ዋሸክ’. . . ‘በሸሸክ’. . . የፅሁፍ ስህተት ነው እንዳይባል መደጋገሙ ያስፎግራል።. . . የፆታ አለመጣጣምም ሌላው ስነ – ፅሁፋዊ ችግር ነው። ለምሳሌ “አቤቱ ፀጋን የተመላሽ” ይለናል ስለአገር በፃፈው ግጥሙ ላይ። እንግዲህ “አቤቱ” የምንለው ለወንድ ሲሆን “ፀጋን የተሞላሽ” ደግሞ ለሴት ነው። ይሄም ዓይነቱ የፆታ መጣረስም የሚጠበቅ አይደለም። የገጣሚነት መብቱን (poetic license) ሲጠቀምም ትርጉም ማዛባት በሚያስችል መልኩ ቸልተኝነትም ይታይበታል። ብቻ እንዲህና እንዲያ ዓይነት ስህተቶች ተበታትነው አሉ። ከነርሱ ጭምር ግን፣ ከአንድ ግጥም እስኪወጡ ድረስ የግጥሞቹን ደረጃ አያሳንሳቸውም።

ከዚያ ሌላ ደግሞ ለ27ቱም ግጥሞች ሳይታክት የግርጌ ማብራሪያ ይሰጣል። “ለ ኧከሌ” እያለ። አንዱም ላይ ተቀባይ ሳይጠቅስ ባለመቅረቱ “ለምን በ27 ብር ከሚሸጥልኝ በየአድራሻቸው አይልክላቸውም?” ያስብላል። (በማሳዘንና በማበሳጨት መሀል ሆኖ) ከዚያም ሌላ ደግሞ የተወሰኑት ግጥሞች ‘ተቀባዮች’ ማንነት መታወቅ. . . ለሁሉም ተቀባይ ከመሰየሙ ባሻገር፣ የግጥሙንም አቅጣጫ ከአንድ በዘለለ እንዳይታይ ሳንካ ይሆናል። ይህም የገጣሚውን የመረዳት ነፃነት ይገፍፈዋል። በነፃነት (እንደልቡ) የገጠመ ሰው ይሄን ነፃነት ገፈፋ ካለምንም ፋታ ማድረጉ ይበልጥ ያበሳጫል። ከዚያም በነፃነት መፃፍ አለመፃፉ ጥያቄ ያጭራል። ይልቅስ በሆድ ተፅህኖ ስር መፃፋቸው ይታያል።

እንግዲህ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግጥሙን. . . ‘አገር አማን’ ብሎ ማንበብ የቀጠለ ሰው፥ ምርጥ የ27 ግጥሞች ስብስብ እያነበበ እንዳለ ይሰማውና በአቅራቢያው ላለ ለማንም “አንብቡት” ብሎ ሊጠቁም ይችላል። …በግማሽ ልብ ሆኖ። ገና መጨረሻው ሳይደርስ በተመለከተው. . . 27 ብቻ ናቸው። 1ግጥም በ1 ብር?! ተወደደ። 27ቱም ተቀባይ ግለሰቦች ተመድቦላቸዋል። የአጀብ መንኳተት ሊደብረው ይችላል። የግጥሞቹ ደህና መሆን ደግሞ ከአጀባው ጋር አልጣጣም ይለዋል። ማህበርን ወይም ፓርቲን አያወድሱም። ግለሰብን አያንቆላጵሱም። ታዲያ ለምን መደጎሻው በዛ? – ሊጠይቅ ይችላል። አሁንም የገጣሚው ሆድ ይታየዋል!

አንባቢው የእኔ ቢጤ (ነገር በሰልስቱ የሚገባው) ከሆነ ቆም ይልና ጥያቄውን ወደ ላይ ያወጣዋል። ሲገባ መታሰቢያ የተደረገላቸው ልጆች ትዝ ይሉታል. . . መለስ (ይላላልኝ። ሆሆሆ….) ብሎ ያነበውና ሊጠይቅ ይችላል።
– አባታቸው ማነው?
– እናታቸውስ? (ስሟ አለመጠቀሱን ልብ ይልና ሸፍጥ እንዳለ ያስባል። በልቡ – ‘ሆ . . . ኋላ እንዳያወቃቅሰው!. . . የለሁበትም!’ – ይልና ብቻውን ይስቃል። – ነገር እየበላ! 🙂 . . .)
– ለምን ከነአባታቸው ስም አልተጠቀሱም? ምናምን ምናምን. . .– ሌሎች ጥያቄዎች። ሌሎች ነገር መብላቶች። – ለዚያውም ችሎ ቆም ካለ ነው።

ለነገሩ ታገልን “ፍቅር” በሚለው የግጥም መድብሉ እና በአጭር ልብ ወለድ መፅሀፉ (ርእሱን ዘነጋሁት እንጂ. . . አፌ ላይ ነበር፣ ግን ጠፋኝ! ሃሃሃ. . . የምር ግን ያሁኑን መንግስትን ደህና አድርጎ የሚነቁር ነገር እንደነበረው አስታውሳለሁ። ወይም በጎረምሳ አዕምሮዬ እንደዚያ ነበር የገባኝ።. . . እስኪ የምታስታውሱት!) የሚያውቀው ሰው ግን የፈለገውንና ሊያነበው ወፍራም ቡና ከጥሩ ሙድ ጋር የሚገጥሙለትን ቀን የጠበቀ ሰው ግን የሆነ ነገር ፍለጋ ቆም ይል ዘንድ ግድ ነው። ቢያንስ ይሄን እያነበበ እነዚያ ይናፍቁታል። – እነዚያንም ቢሆን በተፅህኖ እንደፃፋቸው ፀሀፊው ራሱ ደጋግሞ ቢናገርም. . .

በቲቪ የሚያቀርባቸውን ቪዲኦዎች ግን እንኳን ዛሬ በልጅ አእምሮዬ እንኳን አልወዳቸውም። ጭራሽ ያስቁኝ ነበር። የሆነ የልጅ የጅል ነገር ሆነውብኝ። – ለራሴ ልጅ ሳለሁ። ሃሃሃ… ዝም ብሎ ቤት መምቻውን ድርግም፥ ድርግም እያደረገ ሲሄድ ያስቀኛል። እንዲያውም ቤት ለመምታት ብቻ የሚለቅማቸውን ቃላቶቹ በልጅ ቀልቤ እንኳን ነቄ እልበት ነበር።
ታ ታ ታ ታ ታ
ጄኪቻን ሲማታ
አምስቱን በተርታ
በእርግጫ፣ በቴስታ. . . ዓይነት ነገሮች።

ብቻ ግን እንደ እኔ ሙዴን ሰብስቤ እይዘውና የሚመጣውን ሰንበት ያጣብቀኛል ብሎ ያሰበ ሰው “በሚመጣው ሰንበት” ግጥሞች ወዲያው ተገፍተው 68ኛው ገፅ ላይ መጠናቀቃቸውን ሲረዳ ብሩ ያንገበግበዋል። (ከቻለ በ”ነይ ነይ ሰናድሬ” ዜማ “27 ብሬ፣ 27 ብሬ. . .” እያለ ያንጎራጉርና ሌላ መሳቂያ ያበጃል። ‘እዬዬም ሲደላ ነው’ እንዲሉ በራሱ ድምፅ ይስቃል። ሃሃሃ. . . ) በ27 ብሩ ምን ምን ሊያደርግ ይችል እንደነበር ያስባል። የግጥሞቹን ማለቅ የሚያረዳውም 69ኛው ገፅ ላይ ያለ ቀይ መብራት ነው። – “የግርጌ ምስጋና” ይላል።

(ቀን ከህይወት ባይሰማ ኖሮ) ገና ርዕሱን ሲመለከተው በእንግዳነት ግር ይለዋል። ግርታውን ውጦ ነገሩን ምርመራ ይዘልቃል. . . ለአፍታ መንገብገቡን ወደ ጎን እየገፋ። እንጂማ የጠፋበት ቀሪ ገንዘብ (ከ27 ብሩ ላይ) እንዳለ ተሰምቶት እርሱን ፍለጋ ወደኋላ ገፅ ያስስ ነበር። የገጣሚ ነገር — ምናልባት በሰምና ወርቅ ምናምን ጠፍሮ አስቀምጦት እንደሆነ። ሄሄሄ. . .

ከዚያ ተገጣሚው ይጠይቃል. . .
1. የእግርጌ ማስታወሻ ለምን አስፈለገ?
2. ለምን በረከት ስምኦን፣ ካፒቴን ሰለሞን ግዛው፣ ሻለቃ ኃይሌ ገ/ሥላሴ፣ አዋድ መሐመድ (አዲካ)፣ ኢንጂነር ተክለብርሀን አንባዬ (ልክ እዚህ ጋር ሲደርስ ኢንጂነር ተክለብርሀን ‘የአባቴ ስም አምባዬ ነው። ስሜን አጥፍተሀል’ ምናምን ብለው የሚወቅሱት ይመስለውና ፈገግ ይላል። ሄሄሄ…)፣ እስክንድር አሰፋ ከበደ (ሞኖ 2000)? ማመስገንስ መብቱ ነው። ግን ለምን የግርጌ ማስታወሻ ምናምን ማለት አስፈለገ? እንዲያውም ሲሆን “ልዩ ምስጋና” ምናምን መስጠት ነበር እንጂ። ብሎ በራሱ ፊት ገጣሚውን ከተመስጋኞቹ ጋር ለማቧቀስ ያብሰለስላል። ሃሃሃ. . . አሁን ሆዳምነቱ ይበልጥ ይታየዋል። በእነዚህ ሰዎች ታግዞ ከነበረ ምናለ ዋጋውን ቀነስ ቢያደርገው ኖሮ? የሚል ሌላ ጥያቄ ያነሳል።

ቀጥሎም ሊሆኑ ስለሚችሉ እንቆቅልሾች ያስባል. . .
1. መፅሀፉ ህዳር 11/2005 ይላል። ሆኖም ግን በተባለው ቀን መፅሀፉ ገበያ ላይ አልዋለም። ለምን የተለየ 1 ቀን ተጠቀሰ?

2. ቀን ሰምቶት አፍሯልና የምስጋናዎቹን ይዘት ችላ ቢለውም እንኳን. . . የግርጌ ምስጋና የተደረገላቸው ሰዎች በእውነትም የአብዛኞቹ ግጥሞች መፃፊያ ምክንያቶች ከነበሩ ስለምን የራስጌ ምስጋና አልተበረከተላቸውም? ከዚያም ለራሱ ለመመለስ ይሞክራል። – በግምት። ምናልባት ‘ከሁለት ያጣ ጎመን’ ሆኖ በአንባቢው እጠላለሁ። ብሎ ፈርቶ. . . ወይም አንባቢውን ከመግቢያው ላለመግፋት መጨረሻ ላይ ተቀምጦ መውጫ ይሁነው። ብሎ እንደሆነ ግራ በገባው መንፈስ ይገምታል። ወዲያው ነገሩ ያበሳጭቶት ያሳዝነውና፣ ባዶ ሆዱ ይታየውና ተመስጋኞቹ ‘ምናባህ ቆርጦህ እግርጌ ወስደህ አስቀመጥከን?’ ብለው በተጣሉት ብሎ ይመኛል። ሃሃሃ. . .

3. ከፊት ለፊት መታሰቢያ የተደረገላቸው ልጆች የቀድሞው ጠ/ሚው (አልሞቱም የምትሉ ውሸት ነው። ሞተዋል። ይልቅስ አፈሩን ገለባ ያርግላቸው በሉ። ይላል በልቡ። ሄሄሄ) ልጆች መሆናቸውን ይረዳና ይጠይቃል። እናታቸው ለምን አልተጠቀሱም? የአባታቸው ስምስ? ሆነ ተብሎ አንባቢን ላለማስደበር (ላለመግፋት) የተደረገ ነው? ከዚያ ደግሞ መላ ምቱን ይቀጥላል። ለብ ማለቱና አድር ባይ ላለመባል መፍራቱ ፍጥጥ ብሎ ይታየዋል።በዚያም ይበልጥ ይናደዳል። ባዶ ክፍል ውስጥ መፅሀፉን በሀይል ወርውሮ “ሆዳም” ብሎ ይሳደባል። ሆዳም ሰው እንደማይሰማ ዘንግቶት። 😉

4. የግጥሞቹ ይዘቶች ጋር ሲገባ ደግሞ ግጥሞቹ የተበረከቱት ለተለያዩ ሰዎች ነው። ለተለያዩ ማለት ስማቸው እንደ መብራት – በራስጌ እንደ ጫማም – በእግርጌ ከተቀመጡት ውጪ ላሉ ሰዎች። ይዘታቸውም ቢሆን በከፊል አቋም የያዙ እንዳልሆኑ ይረዳል። ከዚያም ነገር ማጋጋል ይፈልግና ይላሉ – እንዴት? ‘ሽልማት ምናምን’ እያለ ሲሸልል ከርሞ አንዳንድ ግጥም እንኳን አይፅፍላቸውም? በዚያውም እኮ ገፁ ይበዛለት ነበር። በዚያውም ይበልጥ ይወደድ ነበር። በዚያው ሆዱ ይዳጉስ ነበር። ሃሃሃ. . .

“እውል ብሎ ከሰው፣ አድር ብሎ ከሰው
ነብር ጉሮሮውን፣ ፍየል ገብቶ ላሰው።”ይላል የአገሬ ሰው ሆድ አደሮችን ሲታዘብ። እንቆቅልሹ ይቀጥላል። – ሀበሾች ነና።

ታገል በመፅሀፉ ውስጥ “በጨለማ የሚያበራው ትል” በሚል ርዕስ ያቀረባትን ግጥም ላካፍላችሁና ነገሬን ልቅጭ። በረከትነቷ //ሳያውቁ ለተደነቁ….ሳይሰሩ ለተከበሩ….እና ባይባረኩ ለሚመለኩ የዋሆች….// ይላል። ሳያውቀው ያረገው እንደሆን እንጃ፤ እኔ ግን ጅምላ ጨራሽ ሆና አገኘኋትና ለራሱም ጭምር አበረከትኳት። – በሰፈሩት ቁና መሰፈር እንዲህ ነው። ሃሃሃ…. ወይ ደግሞ ተንጋለው ቢያጎኑት ተመልሶ ካናት። ሄሄሄ…

በሺህ ዓይኖች የተከበብክ፣ ተከናንበህ የፅልመት ማቅ
እንደ ጠቢብ የተነበብክ፣ እንደ ብርሃን መልከ ደማቅ
ዓይን ሁሉ ከርቀት ያየህ፣ በራስህ ድምቀት የታጠርክ

“ብርሃን ነኝ!” ብትል ዋሸክ፣ ብርሀንማ ብትሆን ቅሉ፣
ጨለማው ጥሎ በሸሸክ፣ ካለህበት ስፍራ ሁሉ…
አንተ ግን ፅልመት ነው ተስፋክ፣ በጨለማ እሚያበራ ትል
ንጋታችን እስኪያጠፋ፣ አፈር አይንካኝ የምትል….

ክብርህ እንዴት ተከበረ? ጥሩ ተብለክ ስመ – ጥሩ
“መንገድ ነው” ብሎ ለደፈረ፣ ጉድጓዶች እንደነበሩ
“ጉድጓድ ነው” ብሎም ለቀረ፣ መንገዶች እንደተሰሩ
ካልገለፅክለት ገስግሰህ፣ ምን ሊፈይድ ጉንድሽ ጮራህ
ካናታቸው በላይ ነግሰህ፣ ከፍ ብለህ ስለበራህ. . .

ተመሳጥረህ ከፅልመቱ፣ ብትንጎማለል በግርማ፣
ብትብለጨለጭ በከንቱ፣ ውጧቸው ድቅድቅ ጨለማ፣
ገደል ገብተው ለሚሞቱ፣ ካልደረስክላቸውማ
ቅንጣት ብርሃን ካልተረፈህ፣ ከቁም ዳፍንት የሚያጠራ
ዋጋም የለህ ላይን ገዝፈን ሽቅብ ብትከንፍ እንዳሞራ. . . .

በጠፍ ጀምበር በቀን እጦት፣ ገደሉን ፅልመት ሸፍኖ፣
ጋራውን ጨለማ ውጦት፣ ያንተ ድምቀት ብቻ ገኖ፣
ከጋራው በላይ ደንድነህ፣ “ጋራው እኔ ነኝ” የምትል፣
አንተ እንደሆን ኢምንት ነህ፣ ራስህን የምትፈትል፣
ፅልመታችን ያገነነህ፣ በጨለማ ሚያበራ ትል. . .

/ታገል ሠይፉ/

የልደት ወግ: 125 vs. . .

አንተዬ በማለዳው ልቤን አንድ ነገር ቢያስጨንቀው ጊዜ፥ ልጠይቅህ ረፋዱ ላይ ብቅ አልኩኝ። እንዲያው የትናንት የልደት ሻማ ገበያ እንዴት አዋለህ? — ድካሙ? ዋጋው?… ‘እድሜ ሲገፋ ከኬኩ ዋጋ ይልቅ የሻማው ዋጋ ነው የሚወደደው’ ምናምን የሚባል ወሬ ሰምቼ እኮ. . . “ወይኔ ወንድሜን እንዴት ሆኖ ይሆን?” ብዬ ስጨነቅ ነው ያደርኩት። እንዴት አረገህ ባ’ያሌው? አዪዪ. . . የኬኩን ነገርማ ትናንት ጨረስነው እኮ። ቢረክስስ በምን ጥርስ ሊበላ?– ጥርስ ድሮ ቀርቶ! –አያ!. . . እድሜ በልቶት! ሀሀሀ. . .

እድሜው ለገፋበትና እርጅና ለተጫነውስ፥ ሻማው ሲረክስ ነበረ ጥሩ፤ እንዲያ ሲሆን የደከመ እይታንም ያግዛል ምናምን ይላሉ። መቼስ የእኛ ነገር በ‘ይላሉ’ ነው።. . . እንጂማ ምኑን አይተነው? ምኑን አውቀነው?. . . ብለህ?! — ስታየን! ሰታውቀው!… ኸረ ገና ብላቴኖች ነን!…ብቻ ግን ሻማው ቢረክስ ከሞት ወዲያ ሌጋሲውን አጠናክሮ ለማስቀጠልም ጠቃሚ ግብአት የሚሆንይመስለኛል። ህልምና ራዕይስ ቢሆን በሻማ ይበልጥ ደምቆ ይታይ የለ?!…መሰለኝ! ሁሁሁ. . .

ዝም ብዬ ሳስበውግን. . .“ኧከሌ. . . ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል በፀሀይና በሻማ ሲሰራ ኖሮ”…ምናምን ተብሎ፥ በሻማ የመድመቅ ታሪኩ ታክሎ ወሬ ቢጀመር ሌላ ነው የሚሆነው። ስንቱን ሰምተህ የለህ… ‘እንትን ተደግፎ መፅሀፍ ሲያነብ… ኖሮ… ኖሮ… ሞተ’ ተብሎ ገድሉ ሲወራ…. ሌላው ቀርቶ ሻማና ምግባሩን መዝዘን እንኳን. . . “እንደ ሻማ ቀልጦ” ብለን ጨዋታ ብንጀምር የስንቱን አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪ ጆሮ እንስበው ይሆን? አዪ. . . አዲስ አበባ ስል ደግሞ ልደቷ ብልጭ አይልብኝ መሰለህ?! – (ነገርን ነገርም አይደል የሚያነሳው?) ሙት! ከሆኑስ አይቀር ከተማ መሆን ነው ኧረ። ሂሂሂ. . .
ከዚያም ልደትን ዓመት ሙሉ ማስከበር። በዘልማዳዊ ዘይቤም ይባላልሀል — “የወዳጃችንን ልደት ለየት የሚያደርገው ከአዲስ አበባ ልደት ጋር አብሮ መዋሉ ነው።”. . . ልክ “የዘንድሮውን አዲስ ዓመት ለየት የሚያደርገው ከሚሊንየሙ ጋር አብሮ በመዋሉ ነው።” እንዳሉት. . . ሃሃሃ. . . ውይ አዲስ አበባ፣ ውይ አራዳ ሆይ… (ወይ አላልንም ልብ አርግ!) እንዲያው ጭርጭስ ብላ፣ በአልሞትባይነት ስትታገል – ስታታግል፣ ስታስወጣ – ስታስገባ፣ ስትወድቅ – ስትነሳ፣ ስትጥል – ስታነሳ፣ ስትፈርስ – ስትገነባ. . . 125 ዓመቷን ደፈነች። አይዞን አንተም እኮ ደርሰህባታል፣ ብዙም አልቀረህ! ሃሃሃ. . .

እንዴት መታደል ነው ግን አንተዬ?… 125 ዓመት ሙሉ በግንባታ ላይ።125 ሙሉ መቀባባት። 125 ዓመት ሙሉ መኳኳል። 125 ዓመት ሙሉ መጊያጊያጥ። 125 ዓመት ሙሉ መሽሞንሞን፡፡ 125! — ግን እንዲያው በብላሽ! – አንዴም ሳያምርባት! በስሜት “ኧረ እሷን ባረገኝ’ እልና. . . ደግሞ ወዲያው ታሳዝነኛለች። ስታገባ፣ ስትፈታ በወጉ ለደህና ባል ሳትዳር እድሜዋ እብስ ማለቱ ፊቴ ይደቀንና አንጀቴን ትበላዋለች። ውይ ወላጅ እናቷ ጣይቱና አባቷ ምንሊክ የዛሬን ባላይዋት። መቼስ ከሄዱበት መንገድ መመለስ ቢፈቀድ “ውይ እንዳስቀመጥናት” ምናምን ሳይሉ ይቀሩ ብለህ? ኧረ ወዲያ ህንፃው መች ሆነና ቁምነገሩ?!… የእኔ መኳንንት – በዓሉ እኮ ሁሉን ጨርሶታል —-

ከጎራው ዘልቄ እስኪ ልነጋገር፣
ያለሰው ቢወዱት ምን ያደርጋል አገር፣
ህንፃው መች ሆነና የድንጋይ ክምር፣
መንገድ መች ሆነና የድንጋይ አጥር፣
ህንፃው ምን ቢረዝም ምን ቢፀዳ ቤቱ፣
መንገዱ ቢሰፋ ቢንጣለል አስፓልቱ፣
ሰው ሰው ካልሸተተ ምንድነው ውበቱ
የኔ ውብ ከተማ የኔ ውብ አገር፣
የሰው ለጅ ልብ ነው. . .
. . . የሌለው ዳርቻ፣ የሌለው ድንበር፡፡
/በዓሉ ግርማ/

ብቻ እልሃለሁ 125 ዓመቷን ፉት አድርጋ ለማክበር ደፋ ቀና ስትል፥ የኬኩን ጉዳይ በአንድ አንድ ድፎ ዳቦ ስትሸውደው የሻማው ነገር ግን ኪሷን ሲንጠው ነበር የከረመው አሉ።125 ሻማዎች? ዓመቱን ሙሉ –እግዚአብሄር ያሳይህ… በዚያ ላይ በየቦታው ነው የሚበራው።እኔስ ቀድሞ ያሰብኩት. . . ዓመቱን ሙሉ ከተማዋ ላይ መብራት በማብራት (የኤሌክትሪክ አገልግሎት ባለማቋረጥ)፣ ኗሪዎቿን በሙሉም ዓመቱን ሙሉ ኬኩ ቀርቶ ሽልጦ በማብላት ይከበርላታል ብዬ ነበር። አይጠብቁትን ነገር ጠብቄ ተገረምክብኝ? ውይ እሱስ. . . የማይሆን ጠይቆ ሲቀርስ ድርብ በደል ነው። ይሁና . . .

ትዝ ትልህ ዬል ባለፈው በጨዋታ. . . ‘ሄዋን ገጣሚ’ ምናምን ብለን የጫርናት? አዳምሄዋን፣ ያው በለው! ጠይቆ መከልከሉ ነው ጉዳዩ. . .

ዋ… ሄዋን መበደሏ፣ ሄዋን መታለሏ፣
የማይሆን ጠይቃ፣ አልችልም መባሏ፣
የማይችል ጠይቃ፣ አይሆንም መባሏ፣
ስድ ፅሁፍ ሆኖባት ሰንካለው እድሏ፣
ገጣ ስትፈልግ፣ ፍቺኝ ሲላት ባሏ፣

/ዮሐንስ ሞላ/

ውይ ሳልነግርህ?! ባለፈው ከወደ መርካቶ ምናለሽ ተራ እሳት ተነስቶ ወደ 40 ሱቆችን ቢያወድም ጊዜ የአካባቢው ቧልተኞች. . . ‘ለሸገሪና የሚለኮሱ አሮጌ ሻማዎች ስለሌሉን 125 ቤቶችን ለማቃጠል እቅድ ይዘን ገና 40 ገደማው ከመቃጠሉ የከተማዋ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከል ሰራተኞች እንደ አሞራ መጥተው እሳቱን ተቆጣጥረው፣ ራዕያችንን አደናቀፉት’ ብለው ሲያስቁን ነበር።’ አሮጌ ተራም አይደል? ነገር ካላረጀ አገልግሎት ላይ አይውልም። ታዲያ ማን አሮጌ ሻማ አውጥቶ ይሸጥ ብለህ? – ማንም ካልሸጠስ፣ ማን ሊገዛ? የመብራቱ ብልጭ ድርግም መላ ካላገኘ ግን በቅርቡ ቆራሊያዎች — ‘ቆራሌዮ… አሮጌ ሻማ አሌዮ…’ ይሉ ይሆን?! ህህህ. . .

እውነት ግን. . . ይሄኔ ለሌላ ነገር (ለሌላ ዓላማ) ቢሆን እኮ የተቃጠለው ከርመው ነበር የሚመጡት። –ተዘንቦ! ተባርቆ! ነፋስ መጥቶ አመዱን ቡን ማድረግ ሲጀምር! ምቀኞች. . . ምናል ለእናት አዲስ አበባ ክብር እንኳን 125 ሺ ቤት ቢቃጠል? ደግሞ ለሚፈርሱ ቤቶች፤ ተቃጥለው እሳቱን መሞቅ ሳያተርፍ ይቀር ነበር ብለህ? ሄሄሄ. . . አንተዬ ‘ድንገተኛ አደጋ’ ስል ደግሞ እንትን ትዝ አይለኝ መሰለህ ‘አዲስ አበባ እኮ በዚህ እድሜዋ የግሏ መኪና ማንሻ – ክሬን – የላትም’ አሉ። አይገርምም?. . . (አይኔን ‘ባላየሁም’ ስብር አድርጌያለሁ፡፡)

ውይ ሳልነግርህ?! ባለፈው ከወደ መርካቶ ምናለሽ ተራ እሳት ተነስቶ ወደ 40 ሱቆችን ቢያወድም ጊዜ የአካባቢው ቧልተኞች. . . ‘ለሸገሪና የሚለኮሱ አሮጌ ሻማዎች ስለሌሉን 125 ቤቶችን ለማቃጠል እቅድ ይዘን ገና 40 ገደማው ከመቃጠሉ የከተማዋ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከል ሰራተኞች እንደ አሞራ መጥተው እሳቱን ተቆጣጥረው፣ ራዕያችንን አደናቀፉት’ ብለው ሲያስቁን ነበር።’ አሮጌ ተራም አይደል? ነገር ካላረጀ አገልግሎት ላይ አይውልም። ታዲያ ማን አሮጌ ሻማ አውጥቶ ይሸጥ ብለህ? – ማንም ካልሸጠስ፣ ማን ሊገዛ? የመብራቱ ብልጭ ድርግም መላ ካላገኘ ግን በቅርቡ ቆራሊያዎች — ‘ቆራሌዮ… አሮጌ ሻማ አሌዮ…’ ይሉ ይሆን?! ህህህ. . .

እውነት ግን. . . ይሄኔ ለሌላ ነገር (ለሌላ ዓላማ) ቢሆን እኮ የተቃጠለው ከርመው ነበር የሚመጡት። –ተዘንቦ! ተባርቆ! ነፋስ መጥቶ አመዱን ቡን ማድረግ ሲጀምር! ምቀኞች. . . ምናል ለእናት አዲስ አበባ ክብር እንኳን 125 ሺ ቤት ቢቃጠል? ደግሞ ለሚፈርሱ ቤቶች፤ ተቃጥለው እሳቱን መሞቅ ሳያተርፍ ይቀር ነበር ብለህ? ሄሄሄ. . . አንተዬ ‘ድንገተኛ አደጋ’ ስል ደግሞ እንትን ትዝ አይለኝ መሰለህ ‘አዲስ አበባ እኮ በዚህ እድሜዋ የግሏ መኪና ማንሻ – ክሬን – የላትም’ አሉ። አይገርምም?. . . (አይኔን ‘ባላየሁም’ ስብር አድርጌያለሁ፡፡)

ግን ምናለ ከገቢያችን ቢቀር፣ ጠግበን ሳንበላ… ከጎረስናት፣ ካየናት ሁሉ 15 መቶኛውን ‘ተጨማሪ ጃዝገለመሌ ግብር’ ብለው ሲሰበስቡ እንዲህ የሚያስፈልጋትን ነገር ቢገዙላት? ለአንድ ከተማ የድንገተኛ አደጋ መከላከያ መኪና የላትም ማለት እኮ አንዲት የደረሰች ልጃገረድ ግልገል ሱሪ የላትም እንደማለት ነው፡፡ ይሄ ቢቀር እንኳን. . . በአንድ ጊዜ ሁለት ሶስት ቦታ እሳት ቢነሳ በተራ በተራ ነው የሚያጠፉት። በጥቂት መኪናዎች የአደጋ መከላከል ድርጅት አቋቁመው የጉድ ቀን ሲመጣ. . . ‘ቆይ የያዝኩትን ጨርሼ መጣሁ ቢሉህ ምን ይሰማ ይሆን?’ በዚያ ላይ መንገዶቹ ሁሉ በልማት ሰበብ ተቆፋፍረው መኪናስ እንዴት ሊገባ? ብቅ ብለው ሲመሱም አይተናል። ብቻ ግን የሸገር ሰው ‘ተለያየ’ ሲሉት በእንዲህ ያለ ጊዜ ህብረቱ ያስቀናል። በምራቅና በእንባውም ያጠፋዋል። – እግዚአብሔር ይጠብቅ እንጂ!

የቆሻሻውን ነገርስ አለማንሳት ነው የሚሻለው። ሰዉ በማህበር – በጥቃቅንና አነስተኛ – ተደራጅቶ በየቅያሱ የሚሸና እና ቆሻሻ የሚጥል ነው እኮ የሚመስልህ። እንዲያውም ባለፈው ጎጃም በረንዳ ዋናው አስፓልት ላይ 10 ጎረምሶች በአንድ ቱቦ አፍ ላይ ሲሸኑ አይቼ ጉድ ነው ያልኩት። ኸረ እንዲያውም ሽንቴን አስመጡት፡፡ እንክት 10! ቆጥሬያቸው ነበር ስልህ። የሰዉን ሁኔታ ስታየው ሽንት ቤት ሆነው ሽንታቸው ቢመጣባቸው ራሱ ውጪ ወጥተው የሚሸኑ ነው የሚመስልህ። በየመንገዱ እንደዚያ ነው። ሰዉ ቆሻሻ የትም ይጥላል። መንገዱ ሁሉ ይሸታል።– 13 months of sunshine እንዲሉ 13 months of ጉንፋን! ያሰኝሀል፡፡ ቅቅቅ. . .

ሽታው ሲያማርረኝ ምነው የአፍሪካ ህብረት ስብሰባ በጠራና መንግስታቱ አዲስ አበባ መጥተው ባንቀላፉ ነው የሚያሰኘኝ። ፓ ያኔ እኮ አስባፓልት ሳይቀር ይታጠባል። ኧረ ምን እሱ ብቻ? የጎዳና ተዳዳሪም ይደበቃል። — ሰው እንደ ቆሻሻ። ኧረ እነሱስ በትንሽ በትልቁ ነው የሚደበቁት። ‘የምን ጎዳና ተዳዳሪ? አሉ ወይ?’ ኧረ. . . አንተ ደግሞ! ዛሬም ድረስ አሉ ስልህ። መኖሩንስ ይኑሩ። – ዋናው ቤት ቦታ ከታጣላቸው ጎዳናውም እኮ አንዱ ክፍሏ ነው።

ግን ቆሻሻ ለበሱ ብላ አፍራባቸው እንግዳ በመጣ ቁጥር መጋረጃ አበጅታ ከጀርባ ማስቀመጧ ሰርክ ያስተፋፍረናል እንጂ! – ግን ምናለ እንግዳ ሲመጣ አንድ አንድ ካናቴራ ብትገዛላቸው? ብትፈልግ እንግዶቹ ሲሄዱ መልሳ ተቀብላ ስቶር ታስቀምጠው፡፡ ደግሞ ምን… በኮንትሮባንድ ሰበብ በየጊዜው ከነቦንዳው ለሚቃጠል ካናቴራ. . .

አሁን አውንማ እናቶችም ወደ ጎዳናዎች ብቅ እያሉልህ ነው። – ነጠላ ለብሰው ሊለምኑ። ‘የሰው ፊት አያሳይህ’ ይሉት ምርቃት ትልቅነት የሚገባህ እነሱን ስታይ ነው። እንዲያው ሲያሳዝኑ። አይናይንህን ነው የሚያዩህ. . . አይናይንህን እያዩ አንጀት አንጀትህን ይበሉታል፡፡ ሲፈሩ ሲቸሩ በደንብ በማይከፈት አፍ ‘እርዳኝ ልጄ’ እያሉህ፡፡ እንደዚያ ዓይነት ሰው ይለምናል ብለህ ስለማታስብ ያስደነግጥሀል . . ግን ምን ታደርገዋለህ? – ከገባህ ሳንቲም መስጠት ነው።

ደግሞ ብዙዎቹ ስማቸው እንዳይጠፋ ፈርተው ከሰፈር ርቀው ነው የሚለምኑት። እና በታክሲ ስትመላለስም ያጋጥሙሀል። እንዲያው ጎንህ ቁጭ ያሉ ገራገር እናት ከወያላው ጋር ቀንስ አትቀንስ እንደሚከራከሩ እቅዳቸውን ቀድመው ያማክሩሃል። “ኧረ ወዲያ፣ ዝም ስንል አበዙት እኮ. . . ብር ከአርባ? ኧረ እኔስ ከ1 ብር በላይ አልሰጠውም። ታያለህ፡፡ መንግስት የሌለበት አገር አደረጉት እኮ፡፡” ምናምን ምናምን ይሉሀል. . .

አዲስ ሆኖባቸው አይደለም። ዋጋው ዛሬ ተወዶም አይደለም። ካንተ በላይ ያውቁታል፡፡ ለምደውታል። ስራ እንዳለበት ሰው ማልደው ወጥተው አምሽተው ይመለሳሉ። (ነገሩን ሳስበው፣ ለልጆቻቸው (ካሏቸው) እና ለጎረቤት “ስራ” ብለው ይሆን የሚወጡት? የሚል ጥያቄ ሁሌ ይጭርብኛል።) ለሆድ በሰው ፊት እሳቱ ተገርፈው የቃረሟትን ጨርሰው እንዳይከፍሏት አሳዝናቸው ነው። ከገባህ ትሞላላቸዋለህ። ከዚያም ትለምደዋለህ፡፡ ህምምም. . .

ግን ምናለ ‘ግብር’ ተብሎ ከገቢያችን የሚቆረጠውን ትተውት ቢያንስ ከአፋችን የቆጠብናትን 15 ፐርሰንት ግማሽ ያህሏን ምግብ ፍለጋ ጎዳና የወጡት ሰዎችን መቀለቢያ ቢያደርጉት? አዛውንቶቹን ቢጦሩበት? ተ.እ.ታ. ስንከፍል… ልክ መቶ ጉርሻ ስንጎርስ 15ቱን ለእነሱ እንዲያጎርሱልን ቀኝ እጃችንን እንደሰጠናቸው ቢያስቡት? እንዲያ ቢሆን ማን ፆሙን ያድር ነበር ጃል?!

ኧረ የሸዋስ ጉድ መች ተወርቶ ያልቅ ብለህ? ደግሞ ከዚህ ሁሉ ኮተቷ ጋር ‘ከዐለም መታየት ካለባችው ከተሞች አንዷ ሆና ተመረጠች’ ይሉሀል ካስመረጧት ትሩፋቶቿ መሀል ዋናው የካፌዎቿ ብዛት መሆኑን ሲነግርህ ደግሞ ሳቅ ያፍንሀል…. (ስለሱ ሌላ ጊዜ አጫውት ህ ይሆናል) የስዋ ነገር ግን እንዲያው ጉንጭ አልፋ ነው። እኔም በወሬ ሰቅዤ በልደትህ ማግስት አደረቅሁህ አይደል?

ውይ ሳልነግርህ ደግሞ፥ ትናንትና እናቴን “ዛሬ እኮ የዮሐንስ ልደት ነው።” ስላት ምን እንዳለች ታውቃለህ? “ዮሐንስ፣ ዮሐንስ… ዮሐንስ የዐይን አባትህ?” ሃሃሃ… ዐይኔ እስኪጠፋ ነው የሳቅኩት። እኔ የታወቅሁልህ ታዲያ? ግን አዲስ አበባ የዓይን አባት አላት እንዴ? ማለቴ መጎሳቆሏን የሚያይላት የዐይን አባት። መውጣት መግባቷን በስስት የሚመለከት የዐይን አባት? አዪዪ. . . የዐይን አባት ትርጉሙ እንደዚያም አይደል ለካ? ሃሃሃ. . .

በል አንተዬ ንግስቲቱ መጥተው online ሳይፈነክቱኝ፣ እንተንም “አንበሳ ሲያረጅ”ን ለንጉስ ሳላስተርትህ በፊት ከትናንት በስቲያ ወዳጄ ያደረሰችኝን የበዕውቀቱ ስዩም “ወይ አዲስ አበባ” ግጥም ልልቀቅብህና ልሰናበትህ፡፡ ኧ ማነው ዝንብ አንተ?. . . ዝንብማ ከቆሻሻዋ አዲስ አበባ ማደሪያ ቦታ አታጣም። ሃሃሃ… ይብላኝ ለእኔ – ለ40/60 ተስፈኛ. . . ሆሆሆ. . .

ወይ አዲስ አበባ. . .
ወይ እመ ፊንፊኔ. . .
ንቅሳትሽን ስታሳይኝ፣ ጠባሳሽን አያለሁ እኔ፡፡
የሴቶችሽ ውበት – የገባኦን ጸሀይ
ሲወጣ ነው እንጂ፤ ሲጠልቅ የማይታይ፡፡

በረንዳ ላይ ሆኜ
ቁስል ለበስ ለማኝ. . .
ማየቱ ቢቀፈኝ፣ አይኖቼን ጨፍኜ
ስንት አንገት፣ ስንት ጡት. . .
ስንት ዳሌ አለፈኝ?!

ወይ አዲስ አበባ . . .
ወይ እመ ፊንፊኔ. . .
ሴቶችሽ እርጉሞች ሀሳባቸው ክፉ፣
ቀስተ ደመና ላይ ቡትቶ እየጣፉ፣
ውበት አስጠየፉ፡፡

ወይ አዲስ አበባ. . .
ወይ እመ ፊንፊኔ፤
የብረት አበባ – የማይረግፍ ፔታሉ፣
የሚዝግ ነው እንጂ የማይደርቅ ቅጠሉ፤
የአዱኛ ሽራፊ፣  የመከራ ግንጥል፣
አልኖርብሽ ባ’ማን፤ አልለይሽ በጥል፤
በዕንባ በሳቅ መሀል እንደተቸነከርኩ
. . . አብሬሽ ልቀጥል፡፡

/በዕውቀቱ ስዩም/

ሀይማኖት፣ አገርና ትምህርት…

የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ እያለን…ትምህርት፣… ጥናት፣… የቤት ስራ፣… ትምህርት ቀረህ፣… አረፈድክ… ምናምን ጭቅጭቁ ሲመረን… ባልተገራ የልጅ ዜማ እንዲህ እንል ነበር፡፡

“ሀይማኖት የግል፣
ሀገር የጋራ፣
ትምህርት የፋራ”

መቼም በዚያ እድሜያችን እንዲያ የምንለው የሀይማኖት – የግልነትና… የአገር – የጋራነት ዘይቤ በወጉ ገብቶን አልነበረም፡፡ ያው እንደ ልጅ ጉጉቱ ሁሉ… ማደግ፣ ታላላቆች ላይ መድረስ ነበርና…ብዙው ከሚለውና፣ ‘ይስማማበታል’ ብለን ካሰብነው ነገር ጋር የእኛን ነጥብ አጣብቀን ለማስተላለፍ የተጠቀምንበት ነገር ይመስለኛል። — የእኛ ነጥብ ‘ትምህርት የፋራ!’ የምትለዋ ነበረች፡፡

ሀይማኖት የግል?!

ሀይማኖት የግል መሆኑ እየተነገረ፣ ህገ መንግስቱም ላይ ሳይቀር መንግስትም ሆነ ማንኛውም ግለሰብ በሀይማኖት ላይ ጣልቃ እንዳይገባ፣ የግለሰቦችን የእመነት ነፃነት እንዲያከብር በግልፅ የተቀመጠ ቢሆንም እውነታው ግን መንግስትም ሆነ ግለሰቦች በሀይማኖት የግልነት በሀሳብ (በመርህ ደረጃ) እንጂ በተግባር የሚስማሙ አይመስልም። ‘ሀይማኖት የግል ነው’ ይልና፣… ሁሉም የራሱን እምነት ሌላው ላይ ለማጋባት የመኳተን ዝንባሌውን ይቀጥላል፡፡

እንኳንስ በስም ተለይተው ታውቀው በህብረት የሚያመልኩት ይቅሩና ‘የእምነት ተከታዮቹ በህብረት ማምለክ ነዋሪውን ጎድቶታል፣ …በድህነት እንድንመላለስ ሰበብ ሆኗል፣… የስራ ባህላችንና ተጠያቂነታችንን ጨቁኖታል፣….’ ሌላም ሌላም  ብለው የእግዚአብሔርን መኖር የማያምኑ (ኢ-አማንያን – athiests) ሳይቀሩ ህብረታቸውን ማጠንከርና ብዙ ሰዎችን መሳብ ይፈልጋሉ። ሁሉም ባይሆኑም… አማኞቹን ካለአግባብ መንቆርና ‘ቅዱስ’ ብለው የሚያክብሯቸውን ማንቋሸሽ ላይ ይበረታሉ፡፡ (የሌላ እምነት አማኞችንም ይጨምራል፡፡)

እንግዲህ ይህ የሚሆነው ‘የለምና አላመንነውም’ ብለው የተውት ቦታ ጋር በሀሳብ ተመልሰው ነው፡፡ እንቆቅልሹም እዚህ ጋር ነው። – ‘በህብረት ማምለኩ ጎድቶናልና በህብረት ሆነን የተመላኪን አለመኖር እናሳይ’ አይነት ነገር፡፡…ምናልባት በሂደት የራሱ መተዳደሪያ ደንቦች ተቀርፀውለት፤ዲስኩሮችና ስብከቶች ይዘጋጁለትም ይሆናል። (እስካሁንም ይኖር እንደሆን እንጃ!) — በሀይማኖቶች ሀልዮት ተበሳጭቶ ራሱን የወለደ ተመላኪ-አልባ ሀይማኖት እለዋለሁ፡፡ (ምናልባት ይሄን ሀሳቤን ፈታ አድርጌ መፃፍ ካማረኝ ራሱን አስችዬ ሌላ ቀን እመለስበት ይሆናል፡፡ — ያው በመሰለኝ ነውና ‘ሲመስለኝ’ ብዬ! )

ሰው ስለራሱ ሀይማኖት ጥንካሬና ውበት፣ መልካምነትና ሰማያዊነት፣ ዘላለማዊነትና ፍፁምነት… ቢናገር ስለሌላው ሀይማኖት ድክመትና አስቀያሚነት፣ መጥፎነትና ምድራዊነት፣ ወቅታዊነትና ከንቱነት መናገሩ ነው ማለት አይደለም። ብዙ ሰው ግን እንደዚህ አይረዳውም፡፡ ወዳጁ እውነት ያለውን ነገር መስማት ያሳምመዋል፡፡ ‘ከእኔ ሌላ እውነት ላሳር’….በሚመስል ሽለላ፡፡

እንደ እኔ ግን ማንም እውነት አለኝ ሲል…ሌላውን ሳያስታክክ ይመስክር። ሌላውንም ሰው በሀሳቡ አይናቀው። ‘አይ…ይሄማ ሀሰት ነው፡፡’ የሚለው ተቃዋሚ ቢኖር… ተቃውሞውን ከዘለፋና ከንቀት የፀዳ ያድርገው፡፡ ያ ካልሆነ ግን የሚከራከርለትን እውነት አቅም ውሱንነት ቀድሞ ማመን ሊመስል ይችላልና አያተርፍም፡፡ አያስታፍርም፡፡ ምናልባት ቢያስተፋፍር ነው፡፡

መቼም ከቁስ ጣዖት አምላኪዎች በቀር በሌሎች እምነት ውስጥ የሚገኙ ሰዎች አምላክን በመለኮዊ ረድኤቱ እንጂ በገፁ ያየው የለም፡፡ ያም ነው እምነት ማለት፤ – ያላዩትን ነገር መኖሩን አውቆ መረዳት፡፡ በዚያም ውስጥ ለግብሩ ይመጥናል ተብሎ የሚታሰበው ነገር ሁሉ እየተደረገ ለህግጋቱ መገዛት ይመጣል፡፡ ያመለክነው እንዲረዳንም በተስፋ እንማፀናለን፡፡ …ከዚህ የዘለለ ነገር የለውም።

ሆኖም  ግን በተለያየ ጊዜ የምናየው ነገር ከዚህ በጣም የተለየ ነው። ሰዎች ስለሚያመልኩት (ስለሚያምኑት) ነገር እርግጠኛነቱን ማግኘት የሚፈልጉት ከልባቸው ሳይሆን በአካባቢው ከሚመለከቷቸው ሰዎች ነው። በተለይ ሰዎቹ ታዋቂ ሲሆኑ ፍለጋው ይበረታል፡፡ ብዙ ሰው አዋቂነትን እና ታዋቂነትን ለመለየት ይቸገራልና ልቡ ሲጠገንም… ሲሰበርም ወዲያው ነው፡፡ (እዚህ ጋር ብዙ ነገር ማለት ይቻላል፡፡ ሆኖም ግን ነገሩ እንዳይንዛዛም ሀይማኖታዊ ዲስኩር እንዳይመስልም ተውኩት…)

የሌላው እምነት (እውነት) ሲንቆላጰስ የእኛ እንደተብጠለጠለ አድርጎ ይሰማናል። በዚህም ሳናውቀው የተመላኪያችንን (የእውነታችንን) ባህርይ ሳንረዳ እንደ ደካማ እናሳየዋለን። እርሱ ግን ቤቱን ይጠብቃል። መንጋውንም ይንከባከባል። በአምሳሉ የፈጠረው ሁሉም መንጋው ነው ብለን እንናገራለን፡፡ – በሌላ ጎን። ሲመስለኝ ግን…. ማንም የፈለገውን ያድርግ። ማድረጉ ግን ለእግዚአብሄርና በእግዚአብሄር ይሆን ዘንድ መጠንቀቅ ነው ያለበት።

ሀገር የጋራ?!

የአገር የጋራነት ጋር ስንመጣም ከዚህ የተለየ ነገር አናይም፡፡ አንዳንዶች ከእኛ የተለየ የሚቆረቆሩልን፣… ለእድገታችን፣ ….  ለመውጣት መግባታችን፣…  ለመብላት መጠጣታችን፣ ….ለመጠለል መተኛታችን፣ ….ለማንበብ መስማታችን፣… ለመናገር መፃፋችን… ከእኛ በላይ የሚጨነቁ ይመስል፣ ጣልቃ ይገቡና፣ ‘እንወስንላችሁ’ ይሉናል።

በቀላሉ በሚነሱ የውይይት ሀሳቦችና በእንድ ወቅት ብልጭ ድርግም በሚሉ ጉዳዮች ዙሪያ እንኳን ብዙ እንደምንባባልና እርስ በርስ እንደምንተዛዘብ ዘወትር የምናየው ነገር ነው። ለገዛ አገራችን እየሰራን፣ ልክ ለኤርትራ (ወይም ለሌላ አገር) የሰራን ይመስል የሚያሳቅቁን የሚያሸማቅቁን ብዙ ናቸው። እንደ ምስኪን እናት ከአፋችን ቆጥበን የከፈልነውን (የተነጠቅነውን) የግብር ገንዘብ እንኳን ምን እንደተሰራበትና እንዴት እንደዋለ መጠየቅ እስከማንችል ድረስ አፋችን ይሸበባል፡፡ – አንዳንዴ በፍርሃት! አንዳንዴ ደግሞ በጉልበተኞች ጉልበት!

ምናልባት ጎበዞች፣ –  ራሳቸውን ሆነው፣ ጫናውን ለመቋቋም ድፍረቱንና አቅሙን ያገኙ ሰዎችን ስናይም እናሸማቅቃቸዋለን። ‘መግባት ፈለግሽ እንዴ?’ … ‘በል ቃሊቲ ስመላለስ አልገኝም።’ ምናምን ምናምን …. መንግስትም ቢሆን ይሄንን ስሜት የሚጠላው አይመስለኝም። በጋዜጣ አቅም እንኳን አንድ ጋዜጣ በስርዓቱ መነበብ ሲጀምር ተሯሩጠው ይዘጉታል። – እንዳናውቅ?… ሳስተውልን – እንዳናልቅ?… ብቻ ግን ማንም ከውዳሴ በቀር የሚያጣጥል ነገር እንዲናገር አይፈለግም። በዚህም በሀሳብ ደረጃ እንበለው እንጂ የአገር የጋራነት በተግባር አለመስረፁን እንረዳለን።

ትምህርት የፋራ?!

ሌላው የትምህርት የፋራነት ነው። እዚህ ጋር ስለትምህርት ጥራት ጉዳይ አንስተን አንጥልም። ስለተማሪዎቹ ለትምህርት ተነሳሽነት አንተነትንም፡፡ ሆድ አደርነት ወይም ህሊና አክባሪነታቸውንም አንስተን አንነጋገርም። ሆኖም ግን ‘ተማርን’ የምንል (ቢያንስ ‘computer operate’ ማድረግ የምንችልበት እውቀት ያለን)፣ …ወይም በጣም አጥብበነው መፃፍና ማንበብ የምንችል ሰዎች ጋር ያለው የውይይት ባህል አሳፋሪ ነው። ‘መማር ምን ይሰራል?!’ እስኪያስብል ድረስ ያሸማቅቃል።

ሆድ ሆዳችንን እያየን ላይ ላዩን እንኖራለን፡፡ – ህሊናችንን እያፈንነው፡፡ ከእኛ ሀሳብ ልዩ የሆነ ነገር ሲነሳ ስድብ ይቀናናል። ሀሳብን በሀሳብ መቃወም በማንችልበት ቦታ ላይ መሰዳደብን እንመርጣለን። ሰውየውን እንዳንሰድበው… ትንሽ የቀድሞ ማክበራችን ሲቆነጥጠን፣ ወይም ደግሞ ‘ተሳዳቢነት ግብራችን አይደለም’ ብለን ስናስብ…. ከውይይቱ እናሸሸዋለን፡፡ (ውይይቱን እንዳይከታተል ለይተን እናግደዋለን፡፡) እስከ ዛሬ ብዙ ተዛዝበናል፡፡

እንኳን ስለራሳችንን… ስለምንወደው (ስለምናከብረው) ሰው ድክመት ሲነገር ብንሰማ ወዲያው ስሜታችን ይጎዳል፡፡ መቻቻል አርጧል፡፡ የውይይት ነገር ዜሮ ገብቷል። መደማመጥማ አይታሰብም፡፡ – ታዲያ መማሩ ምኑ ላይ ነው? ‘መማር የፋራ’…ብንለው በዚህ ደረጃ ቢበዛበት እንጂ ያንስበታል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የንባብ ባህላችን ሊነሳም ይችላል፡፡

ምናልባት ብዙዎቻችን የመጨረሻዋን መፅሀፍ ያነበብነው ት/ት ላይ እያለን…ለዚያውም ለት/ት አጋዥ የሆነን የመማሪያ መፅሀፍ። ከዚያ ከፍ ሲል ግን ብዙዎቻችን በ’ዴርቶጋዳ’ ተጠምቀናል። አንድ እርሱን ይዘን ምሁራዊነትን እናቀነቅናለን፡፡ አገራዊነትንና አዋቂነትን እንሰብካለን፡፡ የምሁራኑን ጎራ በአንድ መፅሀፍ ንባብ ለተቀላቀለ ምሁር መደማመጥና መከባበር የተራራ ያህል ከባድ ሲሆን እንመለከታለን፡፡ – ‘ትንሽ እውቀት ያጠፋል!’ እንዲሉ አበው ወእመው፡፡

ሁሉም መናገር ይፈልጋል። ሁሉም የርሱ እንደሚበልጥ ይሰማዋል፡፡ መልስ ባጣበት አጋጣሚም…ሲችል ይሳደባል! ሳይችል ደግሞ ጠያቂውን ይሳደባል፡፡ ያልገባው ነገር ላይ ማብራሪያ መጠየቅማ ታምር ነው፡፡ ሳት ብሎት ደግሞ ከቀድሞ – ‘አዲስ ነገር’ና ‘ፍትህ’… ከአሁን ደግሞ – ‘አዲስ ታይምስ’ እና ‘አዲስ ጉዳይ’ የቃረመማ… በቃ! በስማ በለው ከነጠቃቸው ጥራዞች እየመዘዘ፣ በብዥታ የሚያውቀውን በብዥታ ይተነትናል፡፡ – ባትንኩኝ ባይነት!  እርሱ ምሁር በመሆኑ ራሱን ከጥቂት እውቀት ከተላቆጡ የስድብና ንቀት ግንብ  አጥሮ… ቀድሞስ ማን ሊነካው ይቻለዋል? ማንስ ሊጋፋው ያይችላል?

— አሳፋሪ እውነት!