ከሳሁኝ፣ ጠቆርኩኝ፣ ጉልበት ደሜ ነጣ፣
አካሌ ‘ረገበ፣. . . ደም ስሬ ተቆጣ፣
ክብደቴ ቀነሰ፣. . . ቆዳዬ ገረጣ. . .
በአስራ አምስት በመቶ!
ኩም ኩርምት አለ፣ አጠረ ቁመቴ፣
ደም-ግባቴ ጠፋ፣ ከዳኝ ሰውነቴ፣
ወዜ ጠንጣፈፈ – ነጠፈ ከፊቴ፣
በአስራ አምስት በመቶ!
ለዛ ቢስ ሰው ሆንኩኝ፣ ከውካዋ ዘረጦ፣
አቅም ከድቶኝ ዛሬ፣ አጥም፣ አጥንቴ ገ’ጦ፣
ፀጉሬ ሸሽቶ፣ ሳስቶ. . . ቁመናዬ ጎብጦ፣
በአስራ አምስት በመቶ!
ችጋሩ ተጠጋኝ፣ ‘ራቀኝ ብልፅግና፣
ችሮታን ዘነጋሁ፣ ጠፋኝ ልግስና፣
ደጃፌ ተዘጋ፣. . . ቤቴ ሆነ ኦና፣
በአስራ አምስት በመቶ!
ንፉግ ሆንኩ፣ ስስታም፣ አጓጉል ቋጣሪ፣
እንኳንስ ከሌላው፣ ከአፍ ነጥቆ ቀባሪ፣
አጎብዳጅ፣ ተልከስካሽ፣ ተባራሪ ኗሪ፣
በአስራ አምስት በመቶ!
ያንንም. . . ያንንም፣. . . ብዙ ክፉ ክፉ፣
በአስራ አምስት መቶኛ፣ ምን ያልሆንኩት አለ?
ካየሁ፣ ከበላሁት፣ ካሸተትኩት ሁሉ
ካፌ እየነጠቀ – አንድ እሴት ሳይጨር – ‘ቀፈቱ እየዶለ።
/ዮሐንስ ሞላ/