ለጦቢኛ መልካት

ከጠይም ማህፀን: ከጠይሙ ምድር፣ ከጠይሙ ሰማይ፣
ከጠይም ደመና፣ ከጠይሙአድማስ፣ ከጠይሙ ቀላይ፣
የጠንቆጠቆጡ፣. . . ጠያይም ብርሀናት፣ ጠያይም ከዋክብት፣
አረንጓዴ፣ ቢጫ__ ቀይ መቀነት ታጥቀው — ጠያይም አካላት!
ጠይም ጃኖ ለብሰው፣ ጠይሙን ደርበው፣ ውብ ነጠላ – ጋቢ፣
– ተሰብስበው ቆመው፣ ቀልብ ሀሳብ ሰብሳቢ፣ 931521-15414150-640-360
— ጠያይም ቀለማት!
— አማርኛ መልካት!

. . . ከጠይም ጨረቃ፣ ከጠይሙ ፀሀይ፣
ከጠየመ ሜዳ፣ ከጠያይም ምንጮች፣ ከጠይም አፈር ላይ፣
ጠይም የጨለፋት፣ ጠይም ያበቀላት — ጠይሟ ዘመናይ!
ነይ ማታ፣ ነይ ማታ!
ጵጣ ጵጣ ቼኮላታ….

እዩ ልዩ ቆንጆ! – “ጠይም ዓሳ መሳይ፣
እኔ እናቷን ብሆን ለሰውም አላሳይ”
‘ምታባብል እንኮይ፣ ሰርክ የምታባብል፣
ዐይን የምታሸፍት፣ ልብ የምታሰልል፣
ሰውነት ምታርድ፣ ቀልብ ‘ምታነሆልል፤
አወይ ማርማላታ፣
ጵጣ ጵጣ ቼኮላታ….

የተሽቆጠቆጠች፣ የተሽሞነሞነች፣
የተሞናሞነች፣ ያማረች፣ ያጌጠች፣
— ጠይም ቀንበጥ ዛላ!
እግዚኦ የርሷ አሰራር፣ አቤት የርሷስ ገላ!
ወፍ ሲያልፍ እንኳ’ ቢያያት፣ እህልም አይበላ
– ጠይም ፍሬ ቃርሞ፣ የት ሊያሰኘው ሌላ?!

አያሳየኝ እሱን፣ – አንቺን ያየ ለታ፣
ስራውን ጣጥሎ፣ ሲቋጥር ሲፈታ፣
– ከላይ ከሰማዩ፣ ይደፋል ባ’ፍጢሙ፣
በራሪው፣ ቀዛፊው፣ እግረኛው በሙሉ፣555438_416208445123547_645465499_n
– ይነሳል በሽታው፣ የመጣል ህመሙ፣
ይታያል ፈንግሉ. . .
ከተደበቀበት፣ ይገለጣል ሱሱ፣ ይወጣል ዐመሉ፣
– መልክ የማወቅ አመል፣ የመደነቅ ጠባይ፣
ፊት ለፊቱ ሲቆም፣ ሲዟዟር ዐይኑ ላይ፣
– ውበት ከነጠባይ! — ከጠይም ገፅ ላይ!!
አወይ ማርማላታ፣
እግዚኦ ቼኮላታ፣. . .
ሲታሰብ ሲጣፍጥ፣ እንኳንስ ሲበላ!
ሀበሽኛ ውበት፣ ኢጦቢኛ ገላ!!

‘U la-la,…. U la-la’…
በማያውቀው ቋንቋ፣…
እንዲያው “ሰላ ሰላ”፣
“ሰላ በይ” ይልሻል. . . “በይልኛ ሰላ”፣
“ጀበናም የለኝም፣ ቡና እንዳላፈላ”፣
እግዚኦ ጠይም ውበት፣ አቤት ጠይም ገላ፣
በምን ይችሉታል? የተኮላን እንቁ፣ የተቆላ መና፣
በእውቅ የታነፀ፣ በታምር የቀና፣ የጠየመ ቡና፣
አቤት አቆላሉ፣ ውብ አወቃቀጡ፣
አቤት አፈላሉ፣ አቤት አጠጣጡ፣
ውይ አጨላለጡ….
ታምር ነው ውጤቱ – ልብ የሚያመረቃ፣
ትውልድ የሚሻገር፣ ዘመን የሚያነቃ፣
ሲታሰብ ሲጣፍጥ፣ እንኳንስ ሲበላ!
— ሀበሽኛ ውበት፣
— ኢጦቢኛ ገላ!!

አሰኚኝ ድረሺ፣ ‘በዪ ሰላ ሰላ…’250878hp2
ነይ ከቤቴ ግቢ፣
— አንቺን አንቺን ይበል፣ ደጄ ጠይም ያጥላ፣
ምናምን አርጊበት፣… ባርኪው እማ መላ፣
አቤት ማርማላታ፣
እግዚኦ ቼኮላታ፣
ጵጣ ጵጣ አረንቻታ….
– ሲታሰብ ሲጣፍጥ፣ እንኳንስ ሲበላ!
— ሀበሽኛ ውበት፣
— አማርኛ ገላ!!

ከጠይሙ ገፅሽ፣ ከጠይም መልክሽ ላይ፣
ጥርስሽን ፈልቅቂ፣ መልክሽን ሸልቅቂ፣
ዐይንሽን አንከባይ፣ ላ’ለም አብረቅርቂ፣
በቀለም ጨምሪ፣ በእውቀት ምጠቂ፣
የጥቁር ጥጧ ‘ቴ፣ በይ ምጪ እመቤቴ፣
ልልቀምሽ፣ ልፍተልሽ፣ ላዳውርሽ በሞቴ፣
— ፍጠኚልኝ ነፍሴ፣
— ገስግሽልኝ ልብሴ፣
— ሁኝ ግርማ ሞገሴ!!

የውበት እመቤት፣ ጠይም የደም ገንቦ፣
ተጠራርተው ወጥተው ይቃኙሽ በደቦ፣
“ታምር አየሁ!!” ይበል፣ ህዝባ’ዳም ይደመም!
“እኔስ የለሁ!!” ይበል፣ ህዝቤ-ዋን ይገረም!
“የሱ ናት…” ይበሉ፣ ጀማው እኛን ያውራ፣
“የእኔ እኮ ናት” ልበል፣ እኔም ባንቺ ልኩራ፣
ወጣ ብለሽ ታዪ፣ በአድባባይ አብሪ፣321395_415598975184494_472587591_n
በመልክሽ ታፈሪ፣ በፀባይሽ ኩሪ፣

የእኔ ቼኮላታ. . .
ከሁሉም ከሁሉም….
— ማሰሪያ ዶቃውን፣
— መጠፈሪያ ውሉን፣
— አቃፌ መልክሽን፣
— አቃቤ ገፅሽን፣
ራስሽን አስውቢ፤ ዘውድሽን አትርሺ፤
አንጎልሽን ይዩት፣ በውብ አሳምሪው፤
ጠይም ሀሳብሽን፣ በደንቡ ቅለሚው፤
አቤት ማርማላታ!
እግዚኦ ቸኮላታ!
“ወይ ጉድ…” አስብያቸው፤
“ጵጣ ጵጣ” አሰኛቸው፤
– “ጵጣ ጵጣ አንጎላታ!
ጵጣ ጵጣ ኢጦጲያታ!
ጵጣ ጵጣ ጠይም ናታ!”

/ዮሐንስ ሞላ/

(ለሀበሻ መልኮች!! (በተለይም ደቡብ አፍሪካ ላይ በድጋፍ ወቅት አፍዝ አደንግ ለነበሩት) ‘ጠይም ጠይም’ ቢልም…. ለቀያዮቹም በሙሉ ነው፡፡ ያው የእኛ ቅላት የጠይም ዘርነቱ ይለይ የለ?)

‘ወፌ ቆመች’ እንባባል

ባለፈው ከቡርኪናፋሶ ጋር ገጥመን የተሸነፍን እለት እናቴ ስታፅናናኝ “ዝም ብሎ ሲሳካማ ሰነፍና ጉረኛ ያደርጋል።” ብላኝ ነበር። ያኔ በ’ከየትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው’ ስሜት ውስጥ የነበርኩ ቢሆንም፣ ቆይቼ ዛሬ ሳስበው እውነቷን ነው። ከብዙ እድልና ጥረት በኋላ የነገሮች አለመሳካት ለትልቅ የቤት ስራ ትቶ ሲያልፍ ደግሞ ቀጣዩ ስኬት ይበልጥ የሚያኮራና የሚያስመካ ይሆን ዘንድ እድል የሚሰጥም ነው። – ልብ አብሮ እስካለ! አሸማቃቂውስ የቤት ስራውን ለመስራት ስንሰንፍና ስንለግም ነው።

ቻይኖች እኛ አገር መጥተው እንዲህ እንዳሸን ሳይፈሉ በፊት (ሃሃሃ…) ‘አንድ ሺህ ኪሎ ሜትር ርቀት በ1 እርምጃ ይጀመራል’ የሚል ምሳሌያዊ ንግግር ነበራቸው። መቼስ እኛ በቻይና ምርት መገልገል ብርቃችን አይደለምና ዛሬም እንዋሳቸው። — ‘አንድ ሺህ ኪሎ ሜትር ርቀት በ1 እርምጃ ይጀመራል።’ እነሆ እርምጃችን ተጀመረና ‘ወፌ ቆመች’ እንባባል ያዝን። ዋጥነውም አነቀንም፥ ላለፉት 31 ዓመታት በቅምጥ ነበርን።

ያለፉትን 31 ዓመታት ችላ በማለትና የሚመጡትን 31 ዓመታት በማሰብ፥ ከመወቃቀሱና ከመመካከሩ ጎን ለጎን ጥንካሬ ያልናቸውን ማውሳቱና ስለጥንካሬው ሁሉ ማመስገኑ… አንድም ብርታት ይሰጣል። ሌላም ደግሞ ተስፋ መቁረጥን በማስቀረት ጠንካራ እሴቶችን (ጎኖችን) አጥብቆ ለመያዝ ይረዳል። ማንም በሰራው ስራ ቢጣጣልና በሀሳቡ ቢናቅ ግን ራሱን ከመጥላት ይጀምርና ልግመኝነትን ያጎለብታል። በቀልና ጥላቻንም ገንዘቡ ያደርጋል። – ‘ሆድን በጎመን ቢደልሉት ጉልበት በዳገት ይለግማል’ ይባላልና… ጠንካራ ጎኖችን ማውሳቱም በማሻሻል/በመለወጥ/በመገንባት ላይ ያተኮረ ቢሆን መልካም ነው።

ኢንሻ አላህ! – ከኖርነው የምንኖረው ይበልጣል። በዚያም ላይ አሁን ያለንን ጥሩ ጥሩ ነገር አጠንክረንና ‘አልችልም። ደካማ ነኝ። ይሄ ነው የሚገባኝ። ይሄ ነው ምሴ።’ ምናምን ማለትንና በህብረት ተጋግዞ መስራት መጥላትን አሽቀንጥረን ጥለን፣ በቅንነት ከበረታን ለውጥና ትልቅነት (ቢያንስ እርካታና እፎይታ) ህልም ሆነው አይቀሩብንም። ለተተኪው ትውልድ (ለልጆቻችን)ም የተሻለ ነገር ማስረከብ እንችላለን። የተሻለን ነገር የመረካከቡ ወግ እስኪሞላልን ድረስም፥ ቢያንስ ወኔ መቀዳዳትና የእልኧኝነት (በቀናው) ስሜት ዱላን መቀባበል ትርፉ ብዙ ነው የሚሆነው።

ይሄ የእኔ ሀሳብ ነው። አሁን እኔን የመሰለኝ ነው። ምንም እንኳን መነሻዬ የዛሬው የኳስ ሁኔታ ቢሆንም፣ ያልኩት ሁሉ ለብሔራዊ ቡድናችን ብቻ እንዲሆን ሳይሆን፣ እንዲያው በጅምላው ሳስበው የመሰለኝን ነው የተየብኩት። ምናልባት የመሰለኝ ከመሰለዎት በዘርፍዎ እና በቤትዎ ይለማመዱት። ያደርጉትም ከነበረ አጠንክረው ይግፉበት። ‘አይ እኔን የሚመስለኝ እንዲህ ሳይሆን እንዲያ ነው’ ሲሉ ደግሞ ያካፍሉኝና የተሻለውን ያስቀዱኝ።

— ይላል ዮሐንስ ሞላ ሲያካብድ! ሃሃሃ

እንዲህ ባሉ ቀናት 2…

ተመስገን! መቼስ ዞረው አይገቡ የለ እኩለ ሌሊቱ አልፎ ቤት ገባሁ። እኛማ አብሮ መጫወት ልምዳችን አይደል? … ዛሬም አብረን ተጫወትን ነው የሚባለው መቼስ። ቁጭ ብድግ ስንል… እንደ ልማዳችን በየፊናና ቋንቋችን ስንቋጥር፣ ስንፀልይ….
“የአላህ ያረቢ፣
አትበለን እምቢ!”
እያልን በሆያ ሆዬ ስንኝ ቋጠሮ ስንማፀን…. ‘ማርያም… ማርያም…’ እያልን ስንቋጥር! ‘የማርያም ልጅ ሆይ እባክህን….’ እያልን ስንጣራ! ….ደግሞ ሁሉም ጭጭታቸው ፀንቶ…. ጎሉ እየሄደ ሲነከር – ስናዝን፣…. ሲደገም – ስንከፋ፣…. ሲሰለስ…. ጭው ብሎብን! ፍዝዝ ቅዝዝ ብለን ተስፋ መቁረጥ ላያችን ላይ ሲደፋ… ሰማዩ የተከለበሰብን ሲመስለን…

እንደልማዳችን አስርት ዓመታትን ወደኋላ ተጉዘን ስነቃል ይዘን መጥተን ነበረ…
“ቀና ብዬ ባየው ሰማዩ ቀለለኝ፣
አላህንም ሰፈራ ወሰዱት መሰለኝ።”

….ይሉትን ስነቃል። – ያልኖርንባቸውን፣ ያነበብናቸውን፣ የሰማናቸውን አስርት ዓመታት ተጉዘን…. – ምን ተስንኖን?! የጨነቀው እንዲሁ ነው። ግና ደግሞ በጩኧት ብቻ አይደለምና?!….

‘የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው!” ብለን ብንጮህም ዱቄቱን አየሁ የሚል ጠፋ። አልቀናንም ወይም አልቻልንም… እናም ቡርኪና ፋሶ አፍሳ ወስዳዋለች። ምናልባት እርሷ ከእኛ የተሻለ አስፈልጓት ሊሆን ይችላል። ወይ ደግሞ ከእኛ በበለጠ ተገብቷት ሽልማቷ ሆኖላት ይሆናል። ብቻ ግን አልቀናንም!! በዚያም የብዙው ሰው የገፅ የአየር ንብረት ተለዋወጠ። ፀባያችን ከመቅፅበት ከፍ ዝቅ አለ።

ቀላል በትምክህት ደንፍተን ነበር አያ?! ደግ አደረግን!…. መደንፋት እንደው ከመልካም ምኞት ነውና ምንም ጉዳት የለውም። ቅሉ ወሰኑን አልፎ እርግጠኝነትን ሲያጎናፅፍ፥ ላልሆነ ብስጭትና ሀዘን ይዳርጋል እንጂ። እኛ ብንቋጥርም። እኛ ብንደነፋም። በረኛቸው በቀይ ቢወጣም። ቢጫ ቢፃፍ። ምን ቢባል… አላህ ዛሬ የፈረመው ለእኛ አልነበረም። ለቡርኪናፋሶ ነው።
“ወረዳ ፈረመ፣
ቀበሌ ፈረመ፣
አላህ ካልፈረመ፣
ነገሩ ከረመ።” ብለንም አልነበር?!….

….እነሆ ነገራችን ከረመና ለሌላ የቤት ስራ አቀብሎን ሄደ። ከቤት ስራው መሀል ግን የእኛን ሚና የዘነጋነው ይመስላል። ‘ባርሴሎና’ ምናምን ብለው ቡድናችንን ሲያንቆላጵሱት ጊዜ ላለፉት 31 ዓመታት ሰው ሲራመድ ቁጭ ማለታችንን ረስተነዋል። በመዳህ መስመር ውስጥ እንኳን ሳንውል ከአፍሪካም አፍሪካ የቆዳ ቀለምና ምናምን እያማረጥንና እየተከፋፈልን ስንደግፍ መኖራችንን ዘንግተነዋል።

ወደድንም ጠላንም ‘ወፌ ቆመች’ በመባል ላይ ያለ ቡድን መሆኑን ግን ሁላችንም ማወቅ ያለብን ጉዳይ ይመስለኛል። ቆሞ መሄድ እንዲህ የአንድ ሌሊት ክስተት አይደለም። ልጅ መቆም (መዳህ) ጀምሮ ‘ወፌ ቆመች’ ሲባል እንኳን ብዙ ጊዜ ወድቆ ይነሳል። አንዴ ደፋ አንዴ ቀና ሲል እናቱ (ቤተሰቦቹ) በብስጭት ተስፋ ቆርጠው ወይም ደግሞ በመሰልቸት ችላ ብለው ቢተውት ልጁ አረንጓዴያም እግረ ስንኩል ነው የሚሆነው። ዘለዓለሙን የሰው ልጅ ቆሞ እየሄደ ሲጫወት በጉልበቶቹ እጥፍጥፍ ብሎ በራፍ ላይ ተቀምጦ ተመልካች ነው የሚሆነው።

ቡድናችንንም ከዚያ በተለየ ማሰብ ያለብን አይመስለኝም። ገና ወፌ ቆመች እየተባሉ ነውና አብረን እንበላቸው። ድክመታቸውን አብረን እንድከምና እናግዛቸው። ‘Rome wasn’t built in a day’ ይለናል Sam cook…… ስለዚህ የቡድን ግንባታው ላይ እንረባረብ። መሰረቱ ላይ ነንና መሰረቱ ያምር ዘንድ አብረን ብንበረታ በእውነት ነገ ትልቅና ጠንካራ ቤት ይሰራ ይሆናል። በቤቱም እኛ እንደልብ ተንሰራፍተን ብዙ እንኖርበት ዘንድ ቢዘገይ እንኳን ለመጪው ትውልድ ኩራት ነው። (ትናንት ተገንብቶልን ቢሆን ኖሮ ዛሬ መሰረት ማውጣት ላይ አንደክም እንደነበር ልብ ይሏል።)

ውድድሩን በጥሩና ደረጃውን በጠበቀ ብቃት የጀመሩትን ልጆቻችንን….
“ወፌ ቆመች
አልደከመች”
…እያልን ከጎንና ከጎን፣ ከትከሻና ትከሻ እንደግፋቸው። ድጋፋችንን ሲያዩ በሂደት ይበረታሉና!!

* እንዲህ ባሉ ቀናት…
ፖሊሶች አያሳዝኑኝም። እንኳን አላግባብ በስሱም እንኳን የሚቦርቅ ደጋፊ የለምና ምንም የሚጠብቁት የላቸውም። በመሆኑም ከየትም ወደየትም አይርመሰመሱም። ዝም ብለው ጥግ ጥጉን ይዘው ይቆዝማሉ። ስራ መፍታታቸው ደስ የሚላቸው አይመስለኝም። ያው እነሱ መሮጥ፣ ማሯሯጥ አይደልም ስራቸው? የራሳቸው ጉዳይ…. ግን አያሳዝኑኝም።

** እንዲህ ባሉ ቀናት…
እንዲህ ባሉ ቀናት የኤርታ ጋዜጠኞች አያሳዝኑኝም። የቲቢውም ሆነ የሬድዮው ያው ናቸው። ድንገት ሲነቁ – ‘እንዲህ መሆን ነበረበት አልነበረበትም ብለው ሂስ ቢሰነዝሩ ነው።’ እንደልማዳቸው ሲፈዙ ደግሞ – ‘ሽንፈቱ ልማቱን እንደማያደናቅፍ አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለፁ።’ ‘ቡርኪናፋሶ 4 ጎል ማስቆጠሯ የፀረ ልማት ሀይሎች እጅ እንዳለበት ኢዜአ ዘግቧል’… ምናምን ቢሉ ነው። ወይ ደግሞ ምንም እንዳልተፈጠረ ሁሉ ወደ ሰርክ ጥዝጠዛቸው (propaganda) ያመራሉ። ያም ሆነ ይህ ግን አያሳዝኑኝም።

*** እንዲህ ባሉ ቀናት…
እንዲህ ባሉ ቀናት ህዝቡ አንዠት አይበላም። ይልቅስ ቆሽት ያቃጥላል። ያበሳጫል። የስሜታዊነቱ ልክ ጉልጉል ብሎ ባንዴ ይዘረገፋል። ለምቦጩም አብሮ ይዘረገፋል። ለምቦጭ ባይኖረው እንኳን ሞጌው ከበፊቱ በላይ ይሞግጋል። አጎብዳጅ መስሎ ይታያል። (ወይም ቀድሞም አጎብዳጅና ወረተኛ ነበረ።)…. ከብርቱው ጋር መሰለፍ ነው ህልሙ።

እናም ብርቱ ያለው ሲሰንፍበት ያዝናል። አንገቱን ይደፋል። አልፎም ተርፎም ይሳደባል፣ ትናንት ያከበረውን ያንኳስሳል። ድካሙን ሊደክምለት ቀርቶ ‘አይዞህ ወንድሜን’ ሊለው አይችልም። ሊለያዩት ለሚያስቡት ፊት ይሰጣቸዋል። ሁሉም በየስራ መስኩ ሰርክ ስኬታማና አንደኛ የሆነ ይመስል ብሔራዊ ተወካዮች ላይ ለመዘባበትና ብቃታቸውን ለማብጠልጠል ህዝቡ አንደኛ ነው።

[ክፍል ውስጥ 1ኛ ከሚወጣ ሰቃይ ተማሪ፣ መጨረሻ እስከሚወጣ ተስፋቢስ ተማሪ ድረስ፤ መስሪያ ቤት ውስጥ ከሚመሰገንና ከሚሸለም ጎበዝ ሰራተኛ፣ አልማጭና ስራው ላይ ቸልተኛ እስከሆነ ሰራተኛ ድረስ…. ሁሉም ብሔራዊ ተወካዮችን ማብጠልጠል ላይ ይበረታል። ነገሩን ለመረዳትና በእነሱ ቦታ ሆኖ ለማሰብ ጊዜ የለውም።] ለምን ይህ ሆነ? አልልም… ግን ይገርመኛል።

**** እንዲህ ባሉ ቀናት….
እንዲህ ባሉ ቀናት ግራ ገብቶኝ እንከላወሳለሁ። የምይዝ የምጨብጠው ነው የሚጠፋኝ። ….ግራ ሲሉኝ – ቀኝ! ቀኝ ሲሉኝ – ግራ!… በቅጡ አልሰማም። በቅጡም አላወራም። በብዙ ምክንያቶች ሆዴ ይንቦጫቦጫል። ሰው ማየት ያስጠላኛል። እንባዬ ቅርር ይላል። በሆነው በአንዱ (በሽንፈታችን) አጮልቄ ብዙ ነገር ነው የማየው። ዛሬም በህዝቡ ውስጥ ብዙ ነገር ነው ያየሁት። በተጫዋቾቹም ውስጥ ብዙ ነገር። በተጫዋቾቹ ውስጥ ደግሞ ራሴን አያለሁ።

***** እንዲህ ባሉ ቀናት….
እንዲህ ባሉ ቀናት ተጫዋቾቹ (ብሔራዊ ተወካዮቹ) ያሳዝኑኛል። በጣም አንዠቴን ይበሉታል። ውጤቱን ማጣታቸው ከማንም በላይ አንደኛ የሽንፈቱም የወቀሳውም ገፈት ቀማሾች ናቸውና ከማንም በላይ እንደሚያዝኑ ሳስብ ሀዘኔ ይብስብኛል። ሰማንያ ሚልዮን ጉጉት፣ ተስፋ፣ ምኞት፣ ጥም፣… ተሸክመው ነው የሚንቀሳቀሱት። …የምንበላውን ነው የሚበሉት።

በሚጫንባቸው ሀላፊነት ልክ ምግብ እንኳን በቋሚነት እንደሚለወጥላቸው እንጃ። መዘጋጃውና መለማመጃውም ቢሆን እንዳቂሚቲም ቢሆን ምቹ አይደለም። በአንፃሩ ፖለቲካዊም ማህበረሰባዊውም ጫና እነርሱ ላይ ይበረታል። ዛሬ እንኳን ‘አንድ ጎል ሲገባ ማሊያውን ገልጠው ቲሸርት እንዲያሳዩ ታዘዋል’ መባሉን ሰምቼ ጉድ ብዬ ነበር።

ያም ሆኖ ሳለ ሀላፊነት መቀበላቸው በርግጥ ኩራት ቢሆን እንጂ ጉዳት የለውም። ግን እንዲህ ሽንፈት ሲመጣ ባይተዋርነታቸው ድቅን ይልብኝና ግብግብ ያረገኛል። ከሚመጣው ነገር ይልቅም ያለፈው ነገር ላይ እያጠነጠኑ “እንዲህ ቢሆን ኖሮ” እያሉ ሲበሳጩና ራሳቸውን በፀፀት ሲጎዱ ከሚመጣው ነገር ላይ ብዙ እንደሚያጎድሉ ሳስብ ደግሞ ይበልጥ አዝናለሁ።

እንደዚያ የሚያደርጉት ደግሞ አገራቸውን (ያው ከነኗሪው ነው) በጣም ስለሚወዱና ስለሚያከብሩ መሆኑ ይሰማኝና ይበልጥ ያሳዝነኛል። እኛ አገር አኗኗራችን ቅርብ ነው። በመሆኑም ስንወቃቀስ እንኳን የመጎሻሸም ያህል ህመሙና ስሜቱ ይሰማናል። እነሱም ያንን ይመስለኛል ይበልጥ ፈርተውት አቅማቸውን የሚጨቁንባቸው።… ብቻ ግን ያሳዝናሉ!!

****** እንዲህ ባሉ ቀናት. . .
እንዲህ ባሉ ቀናት ወደ

ወደ ማህበራዊ ድህረ ገፆች መምጣት ያስጠላኛል። ስሜታዊው ብዙ ነው። አግባብ ያልሆኑ ፀያፍ ስድቦችን አያለሁ። ለምሳሌ አሁን ወዲህ ብቅ እንዳልኩ ‘ብታምኑም ባታምኑም በቁም ሞተናል።’ አለ መንግስቱ ኃ/ማርያም… የሚል update ተመልክቼ ደበረኝ። እርግጠኛ ነኝ የለጠፈው ሰው የመንግስቱን ታሪክ አያውቅም። ቢያውቅ ኖሮ መንግስቱ ንፁሀንን ዝም ብሎ ሲገድል ይበልጥ መዋረዱን በቁም መሞቱን ያውቅ ነበርና ለጥቅስ እርሱን አይጠራም ነበር።

ዝቅ ስል፥ “ዘሪሁን ዘርህ ቡን አይበል፥ እጅ አለኝ ብለህ አገር ታቈርጣለህ…ጀማልም ያው ነህ ለአድዋ ሰማእታት የተዘፈነ ዘፈን እየሰማህ ነው እንዴ ደቡብ አፍሪቃ የገባሀው? ምንታረገው እርግጫ እየተጫወትክ አድገህ…” የሚል ሌላ update ተመልክቼ ሌላ አዘንኩ። (በመሰረቱ ማንም በዘሪሁን ቦታ ላይ ስላልነበረ የሚሰጠው ነገር ከአስተያየት ስለማይዘል ስድብ ሊቀላቀልበት አይገባም።) ነውር ያይልብናል። የሀዘን ድባብ ያጠላበታል። ቅሬታ። ዝምታ። የሆነ ውሀ የተርከፈከፈበት ነው የሚመስለው። ለያውም የጎርፍ ውሀ…

******* እንዲህ ባሉቀናት. . .
እንዲህ ባሉ ቀናት እናቴን ማየት ደስ ይለኛልም አይለኝምም። ከሀዘን ብዛት ትደነግጣለች። በጣም ታዝናለች። አሁንም ሀዘኗ የሁለት እዮሽ ነው። — አንድም ኢትዮጵያ በመሸነፏ (እንደማናችንም)። ሁለትም እኛ ልጆቿ እንደሚደብረን ስለምትገነዘብ። ዛሬም በውድቅቱ ቤት ስገባ ድምፅ ሰምታ ከእንቅልፏ ነቅታ ጠርታኝ….

“እንዴት ሆኑ?… እኔ አንድ ሲገባባቸው ከዚያ በላይ እንዳልደነግጥ ብዬ እረፍት ላይ ተኛሁ” አለችኝ። የሆነውን ነገርኳት። ነቃ አለች። አዘነችም። ማዘኗን ያወቅሁት ከ “አዪዪዪ…” አባባሏ ድምፅ ነው። ወዲያው በተኛችበት ማፅናናቷን ቀጠለች። ….

“አይዞህ አባ! ምን ይደረጋል። ሁልጊዜ ፋሲካ የለም። እነዚያም እኮ እንዲህ ጓጉቶ የሚጠብቃቸው ሰው አያጡም።” ….ወዲያው መለስ ብላ “ግን አበቃላቸው?” አለችኝ። እንዳላበቃላቸው ነገርኳት “ተመስገን!… ታዲያ አንዳንዴ መሸነፍ እኮ ጥሩ ነው። ካለዚያ ጉረኛና ሰነፍ ያረጋል።” አለችኝ።…. (ይገርመናኛል! ሩጫ ስንሸነፍም እንዲህ ነች።)

*** ኳሱ ፍቅርሽ…
ታይቶኝ ከባህር ስትጠልቂ፣ ከምድር ከሰማይ ስትርቂ፣
ታይቶኝ ከነፋስ ስትረቅቂ፣ ከፀሀይ ጨረቃ ስትደምቂ፣
ሲጠጣ እንዳደረ ሰው ሲጨልጥ ውስኪ አረቂ. . .
ጢንቢራዬን የሚዞረው፣ ሰውነቴ የሚርደው፣
ኧረ በምን ነው ዓለሜ? በምን ያል የቀን ለከፋ፣
ስምሽ ሲነሳ ‘ሚያልበኝ፣ ነገር ዓለሜ ሚጠፋ?
በዐይኔ ዞሮ ያስቀኛል. . .

ንቅሳትሽ፣ ድምድማትሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ኩል፣ ቀለምሽ፣ ውቅራትሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ብር አምባርሽ፣ ድሪና አልቦሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ጥበብ ቀሚስ፣ ውስጥ ልብስሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
የአንገት ልብስሽ፣ መቀነትሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ነጠላ ጋቢ፣ ኩታ ጃኖሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
በዐይኔ ዞሮ ያስቀኛል. . .
/ዮሐንስ ሞላ/

ብለን ነበር ባለፈው። አሁንም ሌላ አንጨምርም። ይህንን እያቀነቀንን የቀን ትሻልን እንናፍቃለን።
መች ተነካና?
ይቀራል ገና!!
እያልን በቀሪውም አምላክ ይረዳን ዘንድ ጥበቡንም በተጫዋቾቻችን ላይ ያደርግ ዘንድ እንማፀናለን።
አሜን!!

ነበር….ነበር…

ነበር….ነበር…ነበር…. ብዙ ነገር ነበር…. በጣም ብዙ ነገር!!….ወድቆ ባይሰበር!!….

እንስራ የሴት ወገብ ጌታ ነበር፣…ጀርባዋ ላይ ጉብ ብሎ የሚያደምቃት፣ የሚያደቃት፣ የሚያሞቃት፣ የሚጨቁናት፣ የሚያደክማት፣ የሚያዝላት፣ ነፃነቷን የሚቀማት፣ ተመልካች ጉብል የሚጠራላት፣….. – ጌታ!!… ያው ወድቆ ባይሰበር ነበር!!….

የሌሎቹም ሸክላዎች ታሪክ እንደዚያው ነው። የሸክላ ድስት፣ የጀበና፣ የአበባ ጌጥ፣ የስኒ፣ የምናምን የምናምን…. ሸክሎቹ እስኪሰበሩ ድረስ የሆነ ነገር ነበሩ። ሲሰበሩ ግን ያው ሰባላ ሸክላ ናቸው። — ገል! ገላቸው ሲደቅ ደግሞ ሸክላ አፈር ይሆናሉ። እንደ አዲስ ሊቦኩና ለሌላ ተሰባሪ ነገር ተሹመው እስኪጠፈጠፉ ድረስ!

ሰውነትም እንዲያ ነው፡፡ እስኪሰበር ድረስ ብዙ ነገር ነበር!! ….ነው!! …ይሆናል!! የሰውነት ባህርዩም ከዚያ አያልፍም። …ከባህርያቱ መካከል ደግሞ ሀዘንና ደስታ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ተፈራራቂዎች ናቸው። አንዱ ሲመጣ፣ አንዱ… አንዱ ሲሄድ፣ ሌላው… እያሉ ተካ ተካ ይጫወታሉ። ሱዚ ይጫወታሉ። በሕይወት ገመድ ዙረት ላይ ገመድ ይዘላሉ።

ገመዱን እኛው ነን የምንዘውርላቸው። – ጠበልተኞቻቸው! የገመዷ ኗሪዎች!! እስከጊዜው ድረስ…. — አንዱ የአንዱን ቦታ ወስዶ “ነበር” እስኪያሰኘው ድረስ፡፡ አንዱ ቦታውን ተቀምቶ “ነበር” እስኪባል በተራው፡፡ እንዲህ ናቸው እነሱ! እንዲህ ነን እኛ! እንዲህ ናት ህይወት!! — ላንዱ ጩቤ፣ ላንዱ ቂቤ!!

ትናንት አሸንፈን ነበር?!… አዎ ነበር! ነበር… ባይሰበር!! ሄሄሄ…. ኧረ ጨዋታ ነው፣ እንጂ መች ወደቅን? ለእኔ ከማሸነፍም በላይ ሆኖልኝ ነበር። በዚያ ላይ ብቃታቸው! ኧረ ውሸት ምን ይሰራል?… ማለፋችንን ያወቅን እለት ከተሰማኝም ብዙ የሚልቅ ስሜት ነበር። ነበር ነበር ነበር….

የምር ግን ደስታን ማሳጠር ቀላል ነው። እንዲህ ነበር፣ እንዲያ ነበር…. ቢሆን ኖሮ፣ ባይሆን ኖሮ… ኖሮ ኖሮ ኖሮ…. የሚለውን ካሰብነው ምንም የሚያስደስተን ነገር ስለማይኖር በብስጭት ተጠቅልለን እንተኛ ነበር፡፡ የእናንተን አላውቅም….እኔ ግን በሆነ ከምለው ነገር ይልቅ የሆነው በልጦብኛል።

ሌላም ጊዜ እንዲሁ ነኝ። ብስጭትን መንከባከብ አልወድም። ድብታና ድብርትን እሹሩሩ ማለት ያሰለቸኛል። በቃ ዝም ብሎ ያልሆነውን ትቶ የሆነውን መቁጠር ነው። ከሆነው ነገር ላይ የሚሆን ነገር ፈላልጎ መልቀም ነው። በርግጥ የትናንቱ ከዚያም በላይ ነበር! ደስ የሚል!!

ደስታውና ስሜታችንን ሳንሰስት መግለፃችን ለቡድናችን ብርታት እንደሚሆነው እንዲሁም ሀላፊነት እንደሚጥልበት ሳስብ ደግሞ ይበልጥ ደስስስስ… ይለኛል። ሀላፊነት የሚያስፈራ ቢመስልም ደርሶ ሲጨበት ብቃትም ነው። ውበትም ነው። ህብረትንም ያጠነክራል።… ብዙ ነዎችንም ያመጣልናል!!

ፓ… 80 ምናምን ሚሊዮን ጉጉት፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ጭንቀት፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ጣእር፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ጥሪ፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ዋይታ፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ጩኸት፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ስጋት፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ተስፋ፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ጥቀርሻ፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ቁጭታ፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ብድግታ፣ 80 ምናምን ሚሊዮን ድብታ፣ 80 ሚሊዮን ፍቅር፣ 80 ሚልዮን ብርታት፣….

ለ11 ሰው አደራ (ቆይቶም በ10) ተሰጥቶ… 11 ሰው ትከሻ ላይ ተጥሎ… 11 ሰው ወገብ ላይ ተዱሎ… 11 ሰው እግር ላይ ተጥሎ… ፤ በፋራም ባራዳም ሲሰምር! በጥረትም በጥበብም ሲሳካ! በአንድ መቀነት ሲቋጠር! በአንድ መስፈሪያ ሲሰፈር!….

— በአረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ!!!!!

ፓ!…. ቀላል ያምራል?!

አቦ… የማርያም ልጅ ይሁነና!!

ግን እንዴት ያል ፍቅር ነው? እንዴትስ ሊተነትኑትና ሊዘከዝኩት ይችሏል?!… ዝም ብለው ይኖሩታል እንጂ!!

የሬድዮና የቴሌቪዥን ጋዜጠኞች የሰሞንኛ ቃላቶች ትርምስ ህመም

የጀመራቸው ሰሞን “እግዚአብሔር ይማር!” እያልን ባልሰማ፣ ባላየ ነበር የምናልፈው። አሁን አሁን ግን በሽታው ከሬድዮና ከቲቢ አልፎ ህትመት ሚዲያዎች ላይ መንሰራፋቱ ሲታየን ጊዜ ወደ እኛም እንዳይመጣ በመስጋት ኧረ ኡኡኡኡ…. አልን። ለነገሩ እዚህ አካባቢም መታየት ከጀመሩ ሰነባበቱ። የኢቲቢና የኢ-ሬ ጋዜጠኞች “ህዳሴ…. ህዳሴ…. ህዳሴ…. “ እያሉ ቢያደነቁሩን ጊዜ፣ በልጅ ኮልታፋ አንደበታችን….

“ለሞኝ ለቅሶ ቅዳሴ፣
ለስንፍናቸው ውዳሴ፣
የተፈጠረ አዲስ ቃል…
— ህዳሴ!”

…. ብለን ነገሩን ወረፍ ለማድረግ ሞክረን ነበር። ያኔ ባይሰሙንም “ትራንስፎርሜሽን” እንዲሁም “አባይ ይገደባል…” “ቦንድ ይሸጣል” ምናምን ይሏቸው ሀረጋት መጥተው ለአፍታ ፋታ ሰጡን። ቅሉ ጠሚው ሲሞቱ ለቅሶ ለመድረስ ይሁን ለምን እንጃ ከያሉበት ተኮለኮሉ። ተጎለጎሉ። ‘የህዳሴው እትትትት….. የህዳሴው ናናናና….. የህዳሴው መሀንዲስ… የህዳሴው ዶ/ር… የህዳሴው ገበሬ…. ህዳሴውን ለማስቀጠል… ፒርርርር….’ ምናምን ይባልልን ያዘ። ልክፍቱ ዛሬም ቀጥሏል….

መቼስ ማልጎደኒ ብለን “ያለበት ሁኔታ ነው ያለው” የሚለውን ሀረግ ከደማችን የደባለቅንበት ሁኔታ ነው ያለው። ሃሃሃ…. ሌላው ደግሞ ተግዳሮት የሚለው ቃል ነው። ተግዳሮት… ተግዳሮት…. ተግዳሮት… — በተለይ የመንግስት ጋዜጦች፣ ጦማሮች፣ ሬድዮኖችና ቲቢው (አንድ ለእናቱ ሞኖፖላይዝድ….) የሚያቀነቅኑት ሰሞንኛ የቃል ዜማ ነው። መጀመሪያ ሰሞን በልማድ በፈረንጅ አፍ የምንጠቀማቸውን ቃላት ተመጣጣኝ የአማርኛ ቃላት በመተካት ጥረቱ ‘ተግዳሮት’ የምትለውን ቃል ጎልጉሎ አምጥቶ በወጉና በቦታው እየተጠቀመ ያላመደን የነበረው አዲስ ነገር ጋዜጣ ነበር። ከነጣዕሙና ከነውበቱ…. (በእኔ ማስታወስ)

ከዚያ አዲስ ነገርነት ተግዳሮት በማለት መስሏቸው ይሁን ባልታሰበ ወረርሽኝ ሁሉም ያቀነቅኑት ያዙ። መጀመሪያ የቀድሞው ጠሚ እንደተጠቀሟት ነው የማስታውሰው… ከዚያ ሌሎች ሚንስትሮች…. ከዚያ የክልል ሀላፊዎች… ከዚያ የአውራጃ የበላዮች…. ከዚያ የክ/ከተማ ሹሞች… ከዚያ የወረዳ ባለስልጣኖች… ከዚያ የቀበሌ… ከዚያ የመንግስትን የስብሰባ አበል የበሉ ግለሰቦች…. ከዚያ ሞዴል ገበሬዎች…ከዚያ… ማቆሚያ የለውም። በተዋረድ ለሁሉም ይደረሳል። በተለይ ቲቢና ሬድዮው አደነቆሩን በሚባል መጠን ይጠቀሙታል…

“ልማቱ ዲዲዲዲ….ተግዳሮት እንዳለው ተገለፀ።”
“አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ነነነነ….ተግዳሮት እንዳልገጠማቸው ገለፁ”
“ፓፓፓፓ……ተግዳሮት….”
“ቂሊው ቂሊው ቂሊው…. ተግዳሮቶቹን ዘርዝሮ አቀረበ…”
“ተግዳሮቶቹን ለማሻሻል….እንዲህ እንዲህ እንዲህ…. ”
“…መንገዱን በታሰበው ጊዜ ላለማጠናቀቅ የነበሩ ተግዳሮቶች….”
“የፊልሙ ኢንዱስትሪ ተግዳሮቶች…. ቋቋቋ….”
“ነዋሪዋ አይጦቹ የፈጠሩትን ተግዳሮት በማሻሻል ልማቱን ማስቀጠል እንደሚቻል ጠቆሙ።”
“ኮብል ስቶን ስራው በቶሎ ተሰርቶ አለማለቅ፣ ውሾች አካባቢያቸውን ከሌባና ከፀረ ሰላም ሀይሎች ለመጠበቅ እንዳይችሉ ከፍተኛ ተግዳሮት እንደሆነባቸው ተገለፀ” ጳራራራ…. ጴሬሬሬ…. – የምር ድንቁር አረጉን።

“አግባብ” “ሌጋሲ” “በወፍ በረር” እና “የአንበሳውን ድርሻ” ደግሞ ሌላ አዝግ ድግምግሞሾች ናቸው። ለመሀላ የተባሉ ይመስል በያንዳንዱ ዜናና ዝግጅት ላይ ይጠቀሳሉ። አግባብ የጠሚው ውርስ ነበረች። ጠሚው፣ ለሚንስትሮች፣ ለክልሎች፣ ላውራጃዎች…. እያስተላለፉ ዛሬ ያደረሷት። ከዚያ ደግሞ ማረፊያቸውን የሬድዮና የቲቢ ፓሮቶች ላይ ያደረጓት….። የምር ግን በነሱ አጠቃቀም “አግባብ” ማለት ምን ማለት እንደሆነ ዛሬም አይገባኝም።

“….ከዚህ አግባብ… ተተተተ…”
“….የልማት አግባብ…ነነነነ….”
“እእእእ….በዚህኛው አግባብ ልናየው እንችላለን።”
“ዲሪሪሪ…. በወፍ በረር እንቃኛለን….”
“…ባልደረባችን ኧከሌ በወፍ በረር እንደተመለከተው….ጡጡጡ…”
“ርርርር… ለስፖርቱ ዜና በወፍ በረር….”
“ቷቷቷቷ…በወፍ በረር ደርሰን ስንመለስ…”
“ብላ ብላ ብላ….የአንበሳውን ድርሻ ይይዛል….”
“አንበሳ ግቢው አዲስ አበባ ካሉት የቱሪስት መስህቦች ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ ይይዛል። ”
“ለወጣቱ የስራ እድል በመፍጠር የአንበሳው ድርሻ የኮብል ስቶን ነው።”
“የቦንዱ ሽያጭ ለግድቡ ስኬት የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለፁ።”

ሌሎችም ብዙ ቃላት እየተደጋገሙ እያዛጉን ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። ሄሄሄ…. ይህንንም ሁኔታ እኔና እህቴ በወፍ በረር ያደረግነው ጨዋታ፣ ጉዳዩን በርዕስነት እናነሳው ዘንድ የአንበሻውን ድርሻ ይይዛል። ነገሩን ከዚህ አግባብ ስንመለከተው ራዕይውን ለማስቀጠልና የኢትዮጵያን ህዳሴ ለማረጋገጥ በሚደረገው እንቅስቃሴ ሁሉ ተግዳሮቶቹን ለማጥፋት እንደሚረባረብ ህብረተሰቡ የገለፀበት ሁኔታ ነው ያለው። ሄሄሄ….

…ኧረ ባካችሁ!! ….ኧረ ባካችሁ!! …ኧረ ባካችሁ!!

እንዲህ ባሉ ቀናት 1…

ዛሬ አብረን ተጫወትን ነው የሚባለው፤ ቁጭ ብድግ ስንል… – ከኋላችን ያሉት ሲጮሁብን! — እኛም ከፊት ለፊትያሉት ላይ ጮኧን አፀፋችንን ስንመልስ፤ በሙከራዎች ሁሉ ስንተቃቀፍ፤ ስንጮህ፣ ስንጨርፍ… – መቼስ ከሞላ ጎደል ሁሉም ጋር እንዲሁ ነበር?!… ደግሞ ስታዲየሙ ውስጥ ያለው ሀበሻ ሲታይ አንዠት ሲበላ?! ለነገሩ እኛንስ በጭለማው ማን ለይቶ አይቶን እንጂ፥ ቀላል እናባባ ነበር?!

ብቻ ሁላችንም በየፊናችንና በየቋንቋችን….
“ያ አላህ ያ ረቢ፣
አትበለን እምቢ!”

(ሀሳቡን) እያልን በሆያ ሆዬ ስንኝ ቋጠሮ ስንማፀን…. ‘ማርያም… ማርያም…’ እያልን ስንቋጥር! ‘የማርያም ልጅ ሆይ እባክህን….’ እያልን ስንጣራ! ….ደግሞ ሁሉም ዝም ጭጭ ያሉን መስሎን ስንተክዝ!….. ብቻ ከየትም መጣ ከየት፣ ማንም ፈጨው ማንም በዚያች ቀውጢ ሰዓት ዱቄቱ ነበር የሚፈለገው። – ‘የትም ፍጪው ዱቄቱን አምቺው!”ም አይደል ተረታችን?!

ክብሩ ይስፋ! ቆይቶ ዱቄቱም ከተፍ አለልን። ደስም አለን። አያልቅ የለ 90 ደቂቃው አልቆም ይበልጥ ደስ አለን። ተመስገንም አልን!! እንደ እምቦሳ ቦረቅን። ፈነጠዝን። ዘለልን። እልልልልል…. ተመስገን!!

መሀል ላይማ ብንጣራ፣ ብንጮህ…. ጠብ የሚል ብናጣ ጊዜ…. ለጆሮ ጠብ የሚል ነገር ፍለጋ በሀሳባችን አስርት ዓመታትን ወደኋላ ተጉዘን ስነቃል ይዘን መጥተን ነበረ…

“ቀና ብዬ ባየው ሰማዩ ቀለለኝ፣
አላህንም ሰፈራ ወሰዱት መሰለኝ።”

….ይሉትን ስነቃል። የጨነቀው ያለውን። – ያልኖርንባቸውን፣ ያነበብናቸውን፣ የሰማናቸውን አስርት ዓመታት ተጉዘን…. – ምን ተስንኖን?!…. የጨነቀው እንዲሁ ነው። ከእግዜር ጋር ጠብ ደንቡ ነው። እርጉዝ ያገባል።

ግና ከምኔው ተገላብጦ፣ ከእረፍት መልስ ነገሩ ሁሉ ፉርሽ ሲሆንብን፣ ቡርቅርቅ ብለን…. ሌላ ስነቃል ፈልገን መዘዝን (ይህችን ስነቃል እንኳን መጀመሪያ ከወዳጃችን ነበር የሰማናት)

“ወረዳ ፈረመ፣
ቀበሌ ፈረመ፣
አላህ ካልፈረመ፣
ነገሩ ከረመ።”

በቀይ ወጣ፣ በአረንጓዴ ገባ፣ በቢጫ ተጠነቀቀ…. ትርጉም አጥተው ነገሩ ሁሉ በድል ሆነልን። አረንጓዴ ቢጫ ቀይም አሸበረቀች!! በግሌ ከማሸነፍም በላይ ብዬዋለሁ። አይደለም እንዴ? የምር እንዲህ ያለ የጨዋታ አቅም አለ ብዬ የት ጠርጥሬ? የት ጠብቄ? ቀላል አይደሉምሳ አያ?! እሰይ…. እንኳን ያልሆኑ። እንኳን የከበዱ። እንኳን ያከበዱን። እንኳን ያሰከሩን። እንኳን የሆነልን። አሃ! ፐርቸስቸስ ብለን አመሸናታ….- ‘እንኳንስ ዘንቦብሽ፣ እንዲሁም ጤዛ ነሽ’ ይሉም የል?!

* እንዲህ ባሉ ቀናት…
እንዲህ ባሉ ቀናት ፖሊሶች ያሳዝኑኛል።…. ፌደራል ፖሊሶች። የሚገኝ ሳይኖር ልባቸውን መሬት ከህዝቡ ጋር ጥለው፥ በመኪና አርፋ ይዘው (ተንጠላጥለው) ከተማዋን እንዳበደ ዶሮ ይዞሯታል። በእግራቸው ዱላቸውን በወግ እያርመሰመሱ ይኳትናሉ። …መቼስ መጨፈር አይፈልጉም አይባልም። ቀላል ይፈልጋሉ? አየናቸው እኮ…. ባለፈው ማለፋችንን ያወቅን ጊዜ ዱላቸውን ትተው በስታዲዮም ዙሪያ ከእኛው ጋር ሲያረግዱም አልነበር?!
ብቻ እንኳን ደስ አላቸው!!

* * እንዲህ ባሉ ቀናት…
እንዲህ ባሉ ቀናት የኤርታ ጋዘጤኞች ያሳዝኑኛል። በተለይ የቲቪው። ውይ… ዝም ብለው እኮ ነው የሚቀባጥሩት። እኩዮቻቸው ሲቦርቁ እነሱ የእነሱን ቡረቃ ፖሊቲሣይዝ ያደርጉታል። ያድርጉታ! – ቀረባቸው። ግን እንዲያው እንዲያ ሲባክኑና ሲካለቡ ሳይ አንዠቴን ይበሉታል። የሆድን ስፋትም ቁልጭ አድርገው ያሳዩኛል። ቀላል ሰፊ ነው አያ?!

ግን ምናለ እንዲህ ባሉ ቀናት ጣቢያውም ስራ ቢያቆም? ለእርሱም ክብር ነው። …መቼም ‘በለፈለፉ በአፍ ይጠፉ!’ ነውና ነገሩ ብዙ ባወሩ ቁጥር ብዙ ይገመታሉ። እነሱ ደግሞ እንዲህ ባሉ ቀናት ብዙ ያወሩ ዘንድ ግድ ነው። ሆድ ነዋ… እንጀራ…. – ድንቄም እቴ!
ብቻ እንኳን ደስ አላቸው!!

* * * እንዲህ ባሉ ቀናት…
እንዲህ ባሉ ቀናት ህዝቡ አንዠት ይበላል። በቋፍ እንዳለ ሁሉ ትንሽ ነው የሚበቃው። ከ__ እስከ__ ሳይል ወጥቶ፣ ከ__ እስከ__ ሳይል ቅርጥፍጥፍ አርጎ ነው የሚበላው። የምር… እምባ አማጭነቱ ያይልበታል። በቃ ሊለያዩት ያሰቡትን ሁሉ አንድ ሆኖ ያበሳጫቸዋል። አቅሉን ስቶ ይቦርቃል። ማንም ማንንም አቅፎ ይስማል። ጎዳናው ላይ ተጥለቅልቆ ጎርፍ ይሰራል።

— የሰው ጎርፍ! የነፃነት ጎርፍ! የፍቅር ጎርፍ! የጉጉት ጎርፍ! የናፍቆት ጎርፍ! የምኞት ጎርፍ! የትልቅነት ተስፋ ጎርፍ! የአገር ስስት ጎርፍ! አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ጎርፍ… ልጅ አዋቂ፣ ሴት ወንድ፣ ሙስሊም ክርስቲያን፣…ምንም ሳይመራረጥ ሰውነትና ኢትዮጵያዊነት በቅተውት እርስበርሱ ይንቆላለጫል።
ኧረ እሰይ ሆነለት። እንኳን ደስ አለው!!

* * * * እንዲህ ባሉ ቀናት….
እንዲህ ባሉ ቀናት ግራ ገብቶኝ እንከላወሳለሁ። የምይዝ የምጨብጠው ነው የሚጠፋኝ። ውይ….ግራ ሲሉኝ – ቀኝ! ቀኝ ሲሉኝ – ግራ!… በቅጡ አልሰማም። በቅጡም አላወራም። እንዲህ ደስ ሲለኝ ከጣሪያ በላይ እጮሃለሁ። ወይ ደግሞ ከመሬት በታች ዝም እላለሁ። ኧም ጭጭ!… ኧረ ምኔም አይታወቅ። ሆኖም ግን አገላለፄ ይለያይ እንጂ ደስታ የእኔው ነች። የሰዉን ሁኔታ ሳይ ደግሞ እንባዬ ቅርርር ይላል። ችሎ ባይወርድም ቅርር ይላል… እንደ ስስ… እንደ ሆደ ቡቡ…. – ነኝ እንዴ? የራሴ ጉዳይ! ዛሬ ግን ችሎ ፈሰሰ… – ግን መነፅራም መሆኔ በጀኝ አያ!
ኧረ እንኳን የሆነልኝ። እንኳን ደስ ያለኝ!!

* * * * * እንዲህ ባሉ ቀናት. . .
እንዲህ ባሉ ቀናት የፌስቡክ ወዳጆችን ማየት ደስ ይላል። (ያው በወል ከህዝቡ ቢደመሩም)… በፅሁፍ ሲታዩ ደስ ይላል። ሲነበቡ ያምራል። ዜማው ሁሉ አንድ ነው። ወሬው ሁሉ ተቀራራቢ ነው። ጉዳዩ ሁሉ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ላይ ያጠነጥናል። ከዚህ ቀደም በሀሳብ ከእኛ አይገጥሙም የምንላቸው እንኳን እንዲህ ባሉ ቀናት ልክክ ነው የሚሉት። የእኛኑ ሙዚቃ ይሞዝቃሉ። እኛም የእነርሱን ሙዚቃ እንሞዝቃለን። – ሲገርም! ለምን? ምናምን… ብለን በማጣራት አንደክምም። አንድም አይደለን?!
ኧረ እንኳን ሆነልን። እንኳን ደስ አለን!!

* * * * * * እንዲህ ባሉቀናት. . .
እንዲህ ባሉ ቀናት እናቴን ማየት ደስ ይለኛል። እርሷን ዝም ብሎ ማዳመጥ። የሆነ የሆነ ነገር እያወሩ ብዙ ማስወራት። ውይ! ስታውቅበት!…. እናቴ አልተማረችም። ‘ዐይኔ አይሰጠኝም’ ብላ ሞክራ ትተወዋለች እንጂ በስሱ ማንበብ ትችላለች። (ለምሳሌ “አዲስ ነገር” ጋዜጣ ታነሳና “አዲስ ነገር” የሚለውን ካነበበች በቃ!! …ስትፅፍ ከስሟ አትዘልም። ‘ዐይኔ የት ያያል?’ ትላለች። …ግን እርሱንም ‘እድሜ ለመንግስቱ ኃ/ማርያም እያለች ነው።’ በመንግስቱ ጊዜ መሰረተ ትምህርት ተምራ ነበር። ደግሞ ጎበዝ ሆና ትሸለም ነበር።

ያም ሆነ ይህ ግን ‘ተማርን’ የሚሉ ጎረቤቶቻችንን አለቅልቃ ትበልጣቸዋለች። (ወይም ለእኔ እንዲያ ይታየኛል።) እናቴ ስለሆነች አይደለም። በሀቅ ነው የምናገረው። የእኔ ሁለት ዲግሪዎችንም ችላ አፈር የምታበላቸው እናቴ ብቻ ነች። በፊቷ ያሸነፍኳት ልምሰል እንጂ ከእርሷ ጋር ማውራት ስጀምር ልቤ በቂጡ ቂብ ይላል። አይችልበትም።

እንደ እኔ መፅሀፍ አታጥቅስም። (ምናልባት ምዕራፍ ቁጥሩን ትታ መፅሀፍ ቅዱስን?!…እርሱንም ቢሆን የእምነት አባቶቿ ካስተማሯት አስታውሳ።) መጣጥፍ አታውቅም። ጋዜጣ የለ! መፅሄት የለ!…. ግን ‘መቼስ ካንተ አላውቅም… አልተማርኩም’ እያለች ልክ ልኬን ትነግረኛለች። ደስ ይለኛል። ከዚያ በላይ ደግሞ ስለምታሳምነኝና በአመክንዮ ስለምታምን በጣም ደስ ይለኛል። ስታምንም አታስቸግርም። ራሷን ከጊዜውና ከዘመኑ ጋር ማስተካከል ማንም አይችላትም። የማታውቀው ነገር ዛሬ ቢነገራት፣ ከዛሬ በኋላ ትተገብረዋለች… – ብቻ ትመንበት!

ገፍታ አለመማሯ ቢቆጫትም አትጠላውም። እንዲያውም ታመሰግንበታለች።…. በዚህ ረገድ ከ10 ዓመት በፊት ያለችኝን አልረሳውም። ሳጥኗን ከፍታ መሰረተ ት/ት ስትማር የተሸለመችውን የምስክር ወረቀት አውጥታ አየችውና በቁጭት “አዪ… ባላቋርጠው ይሄኔኮ እጨርስ ነበር።” አለችኝ።…. ወዲያው ደግሞ “ለነገሩ እንኳን አልተማርኩ። ደግሞ ልጅ አታብዙ የሚል ትምህርት ተምሬ አልወልዳችሁም ነበር ይሆናል።” ብላ አጣጥፋው ወደቦታው ወረወረችው።

እኛ ነን ማመስገኛዎቿ። እኛ ኮምፑተር ወይም መፅሀፍ ገልጠን ጓደኞቿ ቡና ሊጠጡ ሲመጡ ድምፃቸውን ዝግ እንዲያረጉ ቀስ ብላ ተጠቁማቸዋለች።… ‘የእኔን ስራ ነው የሚሰሩት…መጦሪያዬን…’ ትላቸዋለ። [ሲጀመር እኛ ቤት ካለን ጠይቃን ነው ቡናም የምታፈላው] … (ከመስመር ወጥቼ ቀባጠርኩ አይደል?)

ብቻ እንዲህ ባሉ ቀናት እርሷን ማየት ደስታን ይጨምራል። ዛሬ ግን ቤት አይደለሁምና አላየኋትም። ሆኖም ግን መገመት አይቸግረኝም። እንዲህ ያሉ ጨዋታዎችን ስናይ አብራን ትቀመጣለች። ሲጀመር ጀምሮ ተማፅኖዋ ብዙ ነው። “እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን።” ብላ ጀምራ ብዙ እያለች ትቆያለች። ማን ከማን እየተጫወተ እንደሆነ ብትጠየቅ ግድ የላትም። “ኢትዮጵያ አለች አይደል?” ትላለች። መልሱ “አዎ” ከሆነላት ሌላው ትርፍ ነው። “ቢሆንም ባይሆንም አገር ነው መቼስ” ትላለች…

አንድ አስር ደቂቃ እንደታየ ደግሞ ጭንቀቱ አላስችል ቢላት ብድግ ብላ ወደ መኝታዋ ለመሄድ ትነሳለች። “እግዚአብሔር ይሁናቸው። ጭንቀቱ ገደለኝ….ልተኛ። ካገቡ ግን ቀስቅሱኝ…” ብላ…። ግን ችላ አተታኛም። – እርሷም እኛም እናውቃለን። ከመግባቷ ሙከራዎችን ምናምን አይተን ድምፅ ካሰማን አያስችላትም… ድምፅ ባናሰማም አያስችላትም። መጀመሪያ መኝታዋ ሆና የአንዳችንን ስም ትጣራለች። ማንም አልሰማ ሲላት ደግሞ ከነፒጃማዋ ከመኝታዋ ብቅ ትላለች። የመጀመሪያ ጥያቄዋ “አገቡ?” የሚል ነው…

ከዚያ ደግሞ ዐይን ዐይናችንን ታይና መምከር ማፅናናት ትጀምራለች። “አይዟችሁ አባኤ…. ለነርሱ ካለው አይቀርም። አትበሳጩ።” ምናምን ብላ በተራ በተራ እያየችን ትደጋግመዋለች። – ሰማናትም አልሰማናትም! ለርሷ ጭንቀቱ የሁለት እዮሽ ነው። — አንድም ስለ ኢትዮጵያ፣ ሌላም ስለልጆቿ።…. ‘የወለደ አልፀደቀ’ እንድትል ራሷ።
ብቻ እንዲህ ወጣ ገባ ስትል እንቅልፏንም በቅጡ ሳታንቀላፋ ከእኛ ጋር ታመሻለች። ጨዋታው ሲያልቅ ደግሞ የእኛን ጨዋታ እንቀጥላለን። ዛሬ ግን ናፍቃኛለች። ክፉኛ!! ልደውልላትም ብሞክር ኔትዎርክ እምቢ አለኝ። ደስታዋ ግን አይጠረጠርም….
ኧረ እንኳን ሆነላት! እንኳን ደስ አላት የእኔ እናት!!

* * ኳሱ ፍቅሯ….
ታይቶኝ ከባህር ስትጠልቂ፣ ከምድር ከሰማይ ስትርቂ፣
ታይቶኝ ከነፋስ ስትረቅቂ፣ ከፀሀይ ጨረቃ ስትደምቂ፣
ሲጠጣ እንዳደረ ሰው ሲጨልጥ ውስኪ አረቂ. . .
ጢንቢራዬን የሚዞረው፣ ሰውነቴ የሚርደው፣
ኧረ በምን ነው ዓለሜ? በምን ያል የቀን ለከፋ፣
ስምሽ ሲነሳ ‘ሚያልበኝ፣ ነገር ዓለሜ ሚጠፋ?
በዐይኔ ዞሮ የሚያስቀኝ. . .

ንቅሳትሽ፣ ድምድማትሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ኩል፣ ቀለምሽ፣ ውቅራትሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ብር አምባርሽ፣ ድሪና አልቦሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ጥበብ ቀሚስ፣ ውስጥ ልብስሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
የአንገት ልብስሽ፣ መቀነትሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
ነጠላ ጋቢ፣ ኩታ ጃኖሽ – አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ፣
በዐይኔ ዞሮ የሚያስቀኝ. . .

ነበር ያልነው ጠዋት? አሁን ሌላ አንጨምርም። ይህንኑ እየደገምንና “አለ ገና” እያልን እንስቃለን…
እንኳን ሆነልን!! እንኳን ደስ አለን!!!

ኮብል ስቶን ስትለክፈኝ….

የውድ እህቴ፥ ውድ ባለቤት ቀስቅሶኝ ነገሬን በ‘ነበር’ ባያስቀርብኝ ኖሮ… ዛሬ ጠዋት አርፍዶ መነሳት ነበር እቅዴ። ከእንቅልፌ ሲቀሰቅሰኝ፥ ከሞት የመንቃት ያህል ከብዶኝ ነበረ። ሆኖምለዛሬ…ቀጠሮ የያዝንለት ጉዳይ እንዳለን ሳስታውስ፥ ሳላንገራግር ከመነሳት ውጭ ሌላ አማራጭ አልነበረኝምና ተነሳሁ።… ተነስቼም ከቤት ወጣሁ።…. እስካሁንም ከተማውን ሳስስ አለሁ።

ዛሬ ጠዋት…

ፊቴን ታጥቤ ከቁርስ በፊት ከቤት ወጥተን ወደ ጉዳያችን ቢሮ አመራን። ሆኖም ግን ጉዳያችን ያለበት ቢሮ ቦታው አልነበረም፡፡…. ማለቴ ባለቢሮዋ ቢሮዋ ውስጥ አልነበረችም። ከብስጭት በፊት ድንገት አርፍዳ እንደሆነ ብለን  ጎረቤት ቢሮ ጠየቅን።  “ዛሬ አልመጣችም…. ሰኞ ትመለሱ ተባልን፡፡” (በትህትና እና በቀጭኑ) ከትናንት ወዲያም ለዚሁ ጉዳይ ወደ ቢሮዋ ሄጄ አልነበረችምና ሰኞ መመለሷም አጠራጠረን። በመሆኑም ለጎረቤቱ ባለቢሮ ነገሩን አስረድተን ስለሁኔታው ለማጣራትምንም… ምንም አያውቅም፡፡ እሱ እቴ!  ጭራሽ…”ከትናንት በስቲያ እኮ ቢሮው ክፍት ነበር። አልመጣችሁም።” ብሎ ሸመጠ፡፡

ያን በካደበት ሁኔታ ላይም እሱን ማመኑ ከባድ ነበርና እኔ ቆይቼ ልመለስ ተስማምተን ከእህቴ ባል ጋር ተለያየን —
የእህቴ ባል ወደ ስራ….
እኔ ወደ ቤት…
“ወደ ቤት…
ወደ ማድቤት…
አንድ እንጀራ ለጎረቤት…”

ወደ ቤት የተመለስኩት ቁርስ ለመብላት ነበር፡፡ ከዚያ በልቶ ለመመለስ፡፡ ከዚያ በኋላ፥ ሲሄዱ…. ሲሄዱ… ሲሄዱ… እንዲሉ፥ እኔም ስሄድ… ስሄድ… ስሄድ… ለኮብልስቶን ስራ በየቅያሱ ወደተቆፋፈሬው ሰፈሬ ተቃረብኩኝ። ስሄድ ያልታወቀኝን ያህል ስመለስ ቀፈፈኝ። በየቅያሱ ያልተቆፈረ መንገድ ለማግኘት እንደነዳጅ (ወይ ማዕድን) ፈላጌ መቆፈር ያሰኝ ነበርና ከተቆፈሩት በአንዱ ገባሁ። መቼስ ማልጎደኔ?!…
“አልበር እንዳሞራ፣ ሰው አርጎ ፈጥሮኛል፣
አንተን ባጣሁ ጊዜ ግራ ይገባኛል፡፡” ሃሃሃ….

ይሄንን ዜማ በጠዋቱ የመዘዝነው ከቁርስ በኋላ ለምናገኛት ቡና ማንቆላጰሻ ነበር። ውይቡንዬ…ቡኒ…ቡና…ቡን…፤ ድብርታችንን ሁሉ ቡን ለማድረግ፣ ሳንጨርሰው የወጣነውን እንቅልፍ ቦታው ላይ ለመበየድ፣ እንዲሁም ቀናችንን ለማንቃትና ለማቃናት…. ቡና ጥሩ መላ! ብለን ነው። ቡና የመጠጣቱ ሀሳብ ነበር መንገዴን ያስቀየረኝ: ከወደ ቤት –> ሰፈር ወዳለ ሆቴል —> ከዚያ ፊትለፊቱ ወዳለ ቡናቤት —-> ከዚያ….

ሀሳቤን እንዲያ ብቀይርም መንገዱ ግን ያው በየመውጫ መግቢያው እንደተቆፋፈረ ነው። አማራጭ ባጣ፥ ከተቆፈሩት ካንዱ ወጥቼ ወደተቆፈሩት ወዳንዱ ዘለቅሁኝ፡፡ ከወዲያኛው የመንገዱ ጫፍ ሰዎች ቆመው ያየሉ፡ ወጣቶች… እናቶች… አባቶች… የትምህርት ቀን ስለሆነ ለአቅመ ት/ት መማር የደረሱ ህፃናትና ወጣቶች ሲቀሩ ከሁሉም አይነት ሰው ተኮልኩላል።

መጀመሪያ ጠብ ተፈጥሮ መስሎኝ…. የተፈነቃቀሉትን ድንጋዮች እያሰብኩም ‘ሜዳውም ያው ፈረሱም ያው!’… በለው! ብዬ በልቤ ሳጋግል ነበር፡፡ ከዚያ ግን ከግርግሩ ጎን የቆመ የጭነት መኪና ላይ ድንጋዮች እየተጫኑ እንደሆነ ሲገባኝ፥ ከመሀላቸው አንድ ቻይናዊ የመንገድ ሰራተኛ እንዳለ ጠረጠርኩኝ፡፡ መቼስ የእኛ ሰው ቻይኖች ሲሰሩ ማየት ይወዳል፡፡ እንዲያውም ትክ ያለው አስተያየታቸው፣ የቻይኖቹ አይኖች ጠባቦች ስለሆኑ ስለነሱ ሊያዩላቸው ነው የሚመስለው፡፡

እዚህና እዚያ እየረገጥኩኝ፥ መንገዱን አጋምሼ ስቃረብ… ድንጋይ ሰራተኞቹ ቻይኖች እንዳልሆኑ አየሁ። በዚህ ሁኔታው… ቁፋሮው እኛ በር ጋ ሲደርስ ታታሪዋ እናቴ ስራ ፈትታ ቆማ እንደማታያቸው እርግጠኛ መሆን እንደማይቻል አስቤ ፈገግ አልኩኝ፡፡  ፈገግግግ! — እናቴ ወሬ ስትከልም ታይቶኝ… ኧረ ጨዋታ እንጂ እሷስ ወሬ ጠላቷ ነው።…ብቻ ግን ድንጋዩ ሸክሙን ለመመልከት ከብበው ከቆሙት ምስኪን እናቶች ሁኔታ ውስጥ እናቴን ተመለከትኳት። ቤት ስሄድ ደግሞ ምናልባት የእናቴ ሁኔታ ውስጥ እነሱን እመለከታቸው ይሆናል።

ከመንገዶቹ ግራና ቀኝ ያሉት ቤቶች አብዛኞቹ እድሳት ላይ ነው የሚመስሉት፡፡ በተለይ ፊትለፊታቸው ከሚሰራላቸው የኮብልስቶን ሀሳብ ጋር ሲነፃፀር መድከማቸው ይጎላል። …ልዩነቱ ሱፍ በላስቲክ ጫማ እንደማድረግ ነው የሚሆነው፡፡ አዳሽ ያስፈልገዋል፡፡ ነዋሪው ቤቱን እንዳያድስ የሚፈርስ ሰፈር ስለሆነ በሚል ሰበብ ቀበሌው የእድሳት ፈቃድ የማይሰጥበት ጊዜ እነደነበር ትዝይለኛል፡፡….ለዚህም ይሆናል ያዘመሙ አጥሮች ይበዛሉ፡፡

‘አጥሮቹ እንደጠ/ሚው ጥርስ ፍንጭት ይበዛቸዋል’ ልል አልኩና ‘ተውኩት እንደገና’…- ለካስ እኔም ጥርሰ ፍንጭት ነኝ፡፡ ሃሃሃ…. – “ለጥርሰ ፍንጭት ሰው ምስጢር አትንገረው” ይልሃል አማርኛው ደግሞ! — ሳያውቅ! ሂሂሂ…. የምር ግን አጥሮቹ የሳዝናሉ፡፡ የሚንሾካሾኩ ይመስል እንደሾካካ አንዱ ወዳንዱ ሹክክ ብለው ነው የቆሙት፡፡ በዚያ ላይ የስር ጠባቂ ድንጋዮቻቸው ተፈልቅቀው ተወስዶባቸው… — በለው! ‘በደንባራ በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ’…– ልቤ አሁንም ያጋግላል፡፡

እንዲህ እንዲያ እያልኩ….
“ድናጋይ ለድንጋይ ዘለለች ጦጣ
እኔ አልለቅም ነፍሴ ብትወጣ…”

የሚለኝን የቡና አምሮቴን ላስታግስ ድንጋይ ለድንጋይ እየዘለልኩ ስተላለፍ….. ከፊትለፊቱ 60 ዓመት የሚገመቱ አዛውንት የቆሙበት በስርዓት ያልተቀመጠ ድንጋይ አይቼ እግሬን ጢብ አረግሁበት፡፡…. አዛውንቱን ለትንሽ ገፍቶ ሳታቸው፡፡ ጮሁ። ደነገጥኩኝ። ወዲያው ግን ምንም ስላልተጎዱ ደስ አለኝና ዝቅ ብዬ እግራቸውን እየዳበስኩ “ይቅር በሉኝ አባቴ!” አልኳቸው… አልሰሙኝም።… እሳቸው ይራገማሉ… ሰፈሩም ይራገማል… እንዳልሰማ ሆኜ ይቅርታዬን እያደጋገምክ ጎዘጎዝኩት። አልሰሙኝም ወይም አይፈልጉም ነበር። ብቻ በጣም አመረሩ…

እኔም ነገሩ ግራ ገብቶኝ “አባ እኔ እኮ አይደለሁም፣ ድንጋዩ አጉል ቆሞ ስለነበር ነው፡፡ ከተጎዱ ደግሞ ሀኪም ቤት እንሂድ፤ ግን ምንም አልሆኑምና ይቅርታዬን ተቀበሉ፡፡” …አልኳቸው፡፡ (በልባዊ ትህትና) አልሰሙኝ መሰል በቁጣው ቀጠሉ፡፡ እኔም በልቤ ተናደድኩ፡፡ ዝም ብዬ እንዳላልፍ ሰዉ ወሬ ቅርሚያ ከፊት ለፊቴ ተከምሯል፡፡ ግራ ገባኝ…

በቆምኩበት… ከጎረምሶቹ አንዱ፥ “ደግሞ ይናገራል እንዴ? መሰባበር ነበር…” ሲልና እርሱን ተከትለው እርግማኑን እንዳዲስ ሲቀባበሉት….ንዴቴን ከልቤ ወደ ምላሴ አመጣኋትና….

“እንደውም ምንም ይቅርታ አያስፈልገውም፡፡ እስካሁንም ይቅርታ ብዬ የለመንኩዎት በትህትና ነው፡፡….እንግዲህ እርሱን ካልወደዱ ደግ አደረግኩኝ!…. ድንጋይም በተፈጥሮው ሰባሪ ነው፣ እግርም ተሰባሪ ነው፡፡… እርስዎስ መጀመሪያ አይተው አይቆሙም፡፡ ተጎዳሁ ሲሉ አሳክሞታለሁ፡፡ ወንጀል ሰራ ሲሉ ይክሰሱኝ፡፡…ፓራራራ…. ታታታ…. ” ምናምን ምናምን አዘነብኩባቸው። እርግማኑ ቀጠለ… መንገዱም ተከፈተ….

ነገሩ በማበሳጨትና በማዝናናት መሀል ሰንጎኝ ስሄድ፣ የ9ኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ የገጠመኝ ነገር ትዝ አለኝ….

እንድ ግድንግድዬ ወጠምሻ ከሁለት (ወይም ከሶስት) መሰል ጎረምሶች ጋር እየተንከባለለ ይመጣል፡፡ እኔም ወሬ እየቃረምኩ ክጓደኞቼ ጋር ግራ ቀኝ እያየሁ ነበርና የምሄደውና…ከየት መጣ ሳይባል (ከየት ሄድኩ ሳይባል) ሆዱ ላይ ተቀረቀርኩኝ፡፡ እሱም እሳት ለብስ እሳት ጎርሶ፣ (ሁኔታው ከነመልኩ ዛሬም ትዝ ይለኛል)… እኔንም እንደሚጎርሰኝ ሁሉ ጠቅልሎ ይዞኝ…

“እያየህ አትሄድም?” አለኝ፡፡

….ሰደበኝ። ሲሳደብ ስላላስቻለኝ (ከመሰደብ መመታት ይቀለኛል)

“እኔ ባላይ አንተ አታይም?” አልኩት እኩል ተቆጥቼ….

ጓደኞቹ ሳቁበት…አዝኖ እንደለቀቀኝ ሁላ “አሳዛኝ” ብሎ የምንተፍረቱን ትቶኝ ሄደ።
(አማርኛ አተረፈችኝ። እነሆ ከዚያም በኋላ እንደ ነፍሴ መውደድ አረጋት ጀመርኩ ብዬ ላካብድ? ሃሃሃ…)

የቆሎ (የልጆች) ገና

ዛሬ ዋዜማ ነው። — የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓል ዋዜማ። አንድ ጊዜ ተኝተን ስንነሳ ደግሞ ገና ይሆናል።… ዋዜማው እኛ ቤት (እኛ ሰፈር) “የቆሎ ገና” ወይም “የልጆች ገና” ተብሎ ይታወቃል። ቆሎ በየቤቱ ስለሚበላ ‘የቆሎ ገና’ …. ልጆች ካለከልካይ ስለሚጫወቱና ስለሚቦርቁ ደግሞ በተለዋጭ ‘የልጆች ገና’ ይባላል። እነሆ ቆሎው ቀራርቦ እየተበላ ነው። ሲሆን ጠላም ይቀርባል። እኔም ይህን ፅሁፍ ስፅፍ እጆቼን በየመሀሉ የኮምፕዩተሩን ቁልፎች ከመጫን የማሳርፈው ጠረጴዛው ላይ ባለው የቆሎ ሳህን ነው። ….ገና ነዋ! የቆሎ ገና!

እንደልጅ የገና ጨዋታውን ተጫውቼ ዋዜማውን ‘የልጆች ገና’ በሚል ስያሜው ባላከብረው እንኳን ቤት የተዘጋጀውን (በእውቅ ተዘጋጅቶ የተገዛውን) ቆሎ እየቆረጠምኩኝ ‘የቆሎ ገና’ ብዬ አከብረዋለሁ። ሰፈር ያሉ (ባጋጣሚ በዋዜማው ገብቼ የማውቅባቸው) ቤቶችም ውስጥ በዋዜማው ሁሉም ተሰብስቦ ቆሎ ይበላል። በቆሎ ገናው ውጪ ስናመሽ ደግሞ የእኔ እናት ደስ አይላትም። ለምንም አይደለም…ቆሎውን እየቆረጠምን አብረናት እንድንጫወት ስለምትጓጓ እንጂ። እነሆ ቤት በጊዜ ሰፍረን ቆሎውን እንቆረጥመው ይዘናል…

እስከዛሬ ድረስ የቆሎ ገና ወይም የልጆች ገና በሁሉም ኢትዮጵያዊ ቤተሰብ ውስጥ የዋዜማው መጠሪያ ስያሜ ይመስለኝ ነበር። ቅድም ከወዳጆቼ ጋር ስለዋዜማው አከባበር ስንጫወት ግን እንዲያ እንዳልሆነ አወቅሁኝ። ውጪ እንድናመሽና ፐርቸስቸስ ብለን እንድናሳልፍ ሲጋብዙኝ ‘አይ… እናቴ በገና ዋዜማ ውጭ ብዙ ስናመሽ ይደብራታል። ቤት ሄደን ቆሎ እንበትን እንጂ…በቆሎ ገናው ቤት ተሰብስቦ ቆሎ መቆርጠም ነው…’ ምናምን ስላቸው በግርታ ‘የምን ቆሎ?’ ብለው ጠየቁኝ። ስለእኛ ቤት ዋዜማ አጫወትኳቸው። እንዲያ ያለውን ባህል ከዚህ ቀደም እንደማያውቁ ተረዳሁ።

ከዚያም ቤት ስገባ እናቴን ስለባህሉ አመጣት ጠየኳት…. “መቼም ሌላ ቦታም የራሱ አከባበር ይኖረው ይሆናል… የቆሎ ወይም የልጆች በዓል የሚባለው ግን በጉራጌዎች ነው….” በማለት ጀምራ እንዲህ …

(ለአቀራረብ ያመቸኝ ዘንድ ቃል በቃል ከማድረግ ይልቅ አንዳንዱን ወደራሴ አፃፃፍ አምጥቼዋለሁ።)

“…ልጆች ገና ሲደርስ የገና ጨዋታ (ሩር) ይጫወታሉ። ከተማ ውስጥ ቢቀርም ገጠር ግን አሁንም አለ። በዓሉ ከመድረሱ በፊት ህፃናት በቃጫ ኳስ ጠፍረው በቆልማማ እንጨት እየጠለዙ ይጫወታሉ። ኳሱ “ቁር” ይባላል። እንጨቱ ደግሞ – “ድቤ”። ሩር ብቻ አይደለም፤ ፈረስ ጉግስም አለ ሌላም ብዙ ዓይነት ጨዋታ…– “በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ” ይባላል። እውነትም ማንም አይቆጣቸውም። — በተለይ በዋዜማው።….

ያሆ ያሆ…ለበሞ542224_590713924288943_733926906_n
እንዞሪቴ ለበሞ ገና ለበሞ
ለበሞ ብንብና
ነባቼም በጉማ
ለበሞ ለበሞ
ድየ መሸም ይገቦ፣
ያሆ ያሆ…ለበሞ
እንዞሪቴ ለበሞ ገና ለበሞ
የገና ያበቾ፣
ያምና የርጅ ወርዶ፣
ያሆ ያሆ…ለበሞ
እንዞሪቴ ለበሞ ገና ለበሞ
በርጅ ኧርጆ
ሳምር ትፍጆ
ያሆ ያሆ…ለበሞ
እንዞሪቴ ለበሞ ገና ለበሞ
የገና ግየቶ
አዠሁ በዝ ቤቶ
ያሆ ያሆ…ለበሞ
እንዞሪቴ ለበሞ ገና ለበሞ
በገና ጨዋታ
አይቆጡም ጌታ
ያሆ ያሆ…ለበሞ
እንዞሪቴ ለበሞ ገና ለበሞ”

ይጫወታሉ። ይጨፍራሉ። … ጨዋታና ጭፈራው ለአንድ ቀን ብቻ ቢሆንም ደስታው ልዩ ነው። ጨዋታውን የሚያበቁት በዋናው በዋዜማው ምሽት ነው። ጨዋታውን ሲያበቁ ደግሞ በአካባቢው ካልወለዱ (መሀን) ሴቶች ካንዷ በራፍ  ላይ ጥለውት ለዓመቱ ልጅ ትወልድ ዘንድ ተመኝተው ነው። የጭፈራው ግጥምም በደፈናው ሲተረጎምም እንዲያ ነው የሚለው።

እንግዲህ በዚያ ቀን ያልወለደች ሴት እርሷ ደጅ ላይ ይጣልላት ዘንድ ጓጉታ ትጠብቃለች። “እኔ ደጅ ጣሉልኝ” ብላ አፍ አውጥታ የምትጠይቅም ትኖራለች። ያው የልጅ ጉጉቷ ነው የሚያስጠይቃት። እነርሱ ግን ቆመው ተመካክረው ነው ካንዷ ደጅ የሚጥሉት። የተጣለላትም ሴት እንደ አቅሟ ትሳላለች።…

…ከዚያ አምና ድቤውን ወደጣሉበት ቤት ይሄዳሉ። እዚያ ቆሎና ጠላ ተዘጋጅቶ ይጠብቃቸዋል። ስለት ከሰመረ ደግሞ በመነጋው የስለቱን ድግስ እዚያው ቤት ተገኝተው ይበላሉ።… እምነታቸው ይገርመኛል ብዙ ጊዜ ግን እንጨቱ የተጣለበት ቤት ሴት በዓመቱ ትወልዳለች። ከየቤታቸውም አምጥተውም ይጨምሩበትና ቆሎ ሲበሉ ሲበትኑ ያድራሉ። ገና ስለሆነ ቢበትኑም ግፍ የለውም። ማንም አይቆጣም።… ዛሬ ግን አይበተንም። ኑሮው አይሰጥም።

ከዚያ በዚያ ቤት ውስጥ ያድሩና ሌሊት 10 ሰዓት ገደማ ተነስተው ወጥተው እሳት ያነዳሉ። እንጨት ካልተዘጋጀላቸው አጥር ገንጥለውም ቢሆን ማንደዳቸው አቀርም። እሳት አንድደው ሲጨፍሩ ይነጋል። በገና ጨዋታ አይቆጡም ቤታ  ስለሚባል ምንም ቢያደርጉ ማንም አይቆጣቸውም። ሲነጋ ቤት ቤታቸው ሄደው ገላቸውን ታጥበው ገንፎ ይበላሉ። ተመልሰው ደግሞ አምና የጣሉበት ቤት ይሰበሰባሉ። ብዙ ጊዜ ስለምትወልድ ደስታ ነው….

ዛሬ ዛሬ በልምድ ተላልፎ በዓሉ ተረሳ እንጂ ሁሉም ትርጉም አለው። ቆሎው እረኞቹ የጌታን መወለድ ሲሰሙ ይዘው ይጓዙ የነበረውን ስንቅ በማሰብ ነው። እሳቱም የሚነደው ብስራቱን የሰሙት በሌሊት ስለነበር ነቅተው በመጠበቅ እሳት ይዘው ወደ በረቱ መሄዳቸውን በማሰብ ነው። ስለቱም ከአምላክ መወለድ ጋር ላልወለደ መልካም ለመመኘት ነው።…”

መልካም የገና በዓል!!

(ማስታወሻ: ፎቶ ከወንድም ዘሪሁን ተስፋዬ ግድግዳ የተገኘ)

ዐይኔ ዓለም አየ! (በትውስታ…)

ላሊበላ ሁለት ጊዜ ሄጃለሁ። መጀመሪያ የሄድኩት በ2001 ዓ/ም ነበር። ቀጥሎ ደግሞ በ20032011 Lalibela Felsen-Kreuzkirche ዓ/ም…. በ2004ም ላሊበላና ዙሪያው በዐይኔ ሲዞሩ ነበር፤ ሆኖም ግን ነገሮች ከአቅም በላይ ሆነውብኝ ሳንተያይ ተሸዋወድን። ይህ ዓመት ከማለቁ በፊት ብሄድም ደስ ይለኛል። በሚቀጥለው ዓመትም። ከዚያም… ከዚያም…. ኧረ ከዚያም…. ከኧኧኧኧ…ዚያም! ኧረ ከዚዚዚዚ….ያም!

እንደውም የላሊበላ ነገር ውል ሲለኝ እንደማልችልበት ልቤ የሚያውቀውን – “እዚያም በገደምኩ” ያሰኘኛል፤…ግን እርሱ ለተጠሩት ነው። ለእኔ ግን ደርሶ መመልከቱም እንደ መጠራት ሆኖልኝ አንዴ ያየሁት ዓለም ስሙ በተነሳ ቁጥር ያስፈነጥዘኛል። ከዚህ ቀደም ላሊበላን አይቶት የሚያውቅ ቢኖር ነገሬ ከጫፍ ጫፍ ይገባዋል። ከጫፍ ጫፍ

DSC01443ባይገባው እንኳን ጫፍ ጫፉን አያጣውም።

አይቶት የማያውቅ ደግሞ ‘አቦ ምን ያካብዳል?’ ዓይነት ስሜት ውስጥ ቢገባ አይፈረድበትም። – አላየማ! ….ደርሼ እጄን አፌ ላይ ጭኜ፣ ‘ኦ ማይ ጋድ!  ኦ ኦ ኦ… ኦ ማይ ጋድ!’ ብዬ እንደ ድንጋይ ክልትው ብዬ እስክቀር ድረስ፥ እኔም እንደዚያ ነበር የምለው። – ‘አቦ ምን ያካብዳሉ?!’… አሁን ግን አይቻለሁና፥ እላለሁ…. እመክራለሁ…. እዘክራለሁ….

ሀይማኖቱ — ኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክ፣ ጴንጤ፣ ሙስሊም፣ dsc01433ጣኦት አምላኪ፣ ጠንቋይ ቀላቢ፣ ኢ-አማኒ፣ ግራ-ገብ…. ሌላም የፈለገውን ሆኖ፣ መረዳቱ የፈቀደለትን እምነት የሚከተል ማንም (በተለይ ኢትዮጵያዊ) በህይወት እያለ፣… በላሊበላ ለመደነቅና ቦታው ደርሶ አይቶ ‘በዐይኔ ዓለም አየሁ’ ለማለት፥ ማህበረሰባዊ ጤና ያለው (socially healthy) ቢሆን በቂ ነው። ምናልባት ጤነኛነቱ ላይ የአገር ፍቅር ስሜት ቢጨምርበትና ባንድራው ትዝ ቢለው ደግሞ ደስታው እጥፍ ድርብ ይሆንለታል፡፡ — እንደ እኔ ነው!

የመጨረሻውን ትንፋሽ ከመተንፈሱ በፊት… ዓለምን DSC01372ከመሰናበቱና ወደ መጨረሻ ቦታው የመሄጃ ትኬቱን ከመቁረጡ በፊት…. ልቡ እንደምንም ቆርጦ፣…‘አልበላም አልጠጣም’ ብሎ ሳንቲም ቀርቅሮ፥ (ኧረ ሰርቆም ቢሆን) …ትኬት ቆርጦ በእድሜው ላሊበላን ቢያየው አይቆጭም። ስንት ነገር ለሚሆንላት፣ ከሰውነት ተራ ወጥቶ ስለርሷ ነፍሱን ለሚበድልላት ስጋውም ትልቅ ውለታ ነው። ከዚያ ወዲያ ምናልባት ላሊበላን በተመለከተ ሊቆጨው የሚችል ነገር ቢኖር ‘ወይኔ ላሊበላን ድጋሚ ሳላየው ሞትኩ’ ምናምን የሚል ቢሆን ነው። — ይሄም እንደ እኔ ነው!

DSC02900

ከዚያ በፊት ስለላሊበላ በእውቅ እና በጥበብ የተቀናበረ የቪዲኦ ምስል ተመልክቶ፣ በአንደበተ ርቱዕና አፍ አስከፋች ተራኪ ተተርኮለት፣ ወይም ሌላ… ብቻ እንዴትም ተደርጎ ስለላሊበላ አስደናቂነት ተነግሮት ቢሆን፥ ልክ እዚያ ሲደርስ ነገሩ ሌላ ሆኖ ነው የሚጠብቀው። ቪዲኦውን – ይጠረጥረዋል! ፎቶውንም! መጀመሪያ የነገሩትን የተረኩለትንም ይታዘባቸዋል! – ብዙ አጉድለውበታላ። እየቆየ ሲሄድ ግን አይፈርድባቸውም። እርሱም የተመለከተውን ለማውራት እንዴት ጀምሮ እንዴት እንደሚጨርስ ግራ ሲገባው ይረዳቸዋል።

ፎቶ ሊያሳይ ያወጣና ፎቶው ከሚያስታውሰው ጋር ሲነፃፀር 2011 Lllibela Felsengangይደበዝዝበታል፡፡ ሰውየው ነገር መጠፈር የሚቀናው ከሆነ ደግሞ…. “የፎቶ፣ የቪዲኦ እና የትረካ፥ ከንቱነትና ስንፍና ሊታዩ  ከሚችልባቸው ቦታዎች አንዱ ላሊበላ ነው” ብሎ ቢደመድም አይፈረድበትም። “ይናገራል ፎቶ” ብለን ዞር ከማለታችን ለላሊበላ ሲሆን ፎቶ እንደማይናገር እንታዘባለን። ከዚያም እናሻሽለዋለን – “ፎቶ አንዳንዴ አይናገርም! ቪዲኦም!”

መጀመሪያ ስሄድ የ16 ቀን ጉዞ ነበር። መንገድ ላይ ያሉትን የጎብኚ መዳረሻ ቦታዎች አቅማችን እስከፈቀደ ድረስ እየበረበርን ነበር ያለፍነው። ጉብኝቱን ስናቅድ ላሊበላ መካተቱ ጉዞውን ሀይማኖታዊ ያደርገዋልና ይቅር ብለው አጥብቀው የተሟገቱ አንድ፣ሁለት፣ ሶስት… ወዳጆች ነበሩ። (ሁለቱ ፕሮቴስታንት ነበሩ። አንደኛው ደግሞ ሙስሊም።) ከዚያ ግን በሰው ብልጫ እና በብዙ DSC01328ሙግትና ማስረዳት ተረቱና ላሊበላም ተካተተ። ከዚያ በፊት በምንደርስባቸውና በምናርፍባቸው በፊት ቦታውን ከመበርበር በፊት ማረፍ ነበር የሚቀድመው።  ላሊበላ ስንደርስ ግን እንዲህ አልነበረም….

ማረፊያ ክፍል ይዘን እቃችንን ካስቀመጥን በኋላ መጀመሪያ ይቅር ብለው ሲከራከሩ የነበሩት ሶስቱ ሲቀሩ ሁላችንም ተያይዘን ወጣን። (ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ሶስቱም ያሳዝኑኛል) ሁላችንም በየፊናችን ስለ ላሊበላ ‘ቱቲ’ ሰምተን ነበርና ተጣድፈን ቦታውን በቅምሻ ለማየት ጓጓን። በቀጣዩ ቀን ለመጎብኘት የትኬትና የአስጎብኚ ከፍለን DSC01359ካመቻቸን በኋላ ወደ ቤ/ክኑ ተጣድፈን ገባን። የሌላውን በርግጠኝነት ባላውቅም እኔ ጭው አለብኝ። ፍዝዝ… ጭው…

ውሸት ምን ይሰራል? በወቅቱ የተመለከትኩትና የሄድኩት ሁሉ ህልም ህልም ይመስለኝ ነበር። ለሁለተኛ ጊዜ እስክሄድ ድረስም በዚያው የህልም ስሜት ውስጥ ነበርኩኝ። ህልም ይመስለኝና ደስታዬ ወሰኑን ሲያጣ “ህልም – እልም” ብዬ ለራሴ መሳቂያ አበጃለሁ፡፡ በፎቶና በቪዲኦ ከተመለከትኩት በላይ ትልቅ (ሰፊ) መሆኑ የመጀመሪያው የአግራሞት ምንጭ ሆኖልኝ ነበር። ከዚያ ሌላ ደግሞ ላሊበላ ሲባል፣ ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት በቅፅሩ ውስጥ እንዳሉ DSC02952በወሬ ብሰማም በቴሌቪዥን አዘውትሬ የማየው ቤተ ጊዮርጊስን ነበር። በሚገርም ሁኔታ ግን ሌሎች 10 አስደናቂ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት ግቢው ውስጥ መኖራቸውን አወቅሁኝ።

ስለ አሰራሩማ ምኑ ተወርቶ ምኑ ይተዋል? እንዲያው ታምር ነው። ካለምንም መሸራረፍ በቅርፅ መፈልፈላቸው፣ የመስኮቶችና የማዕዘናት እኩልነት፣ የውሀ ልኮች ልኬት፣ የግድግዳው መስተካከልና ልሙጥነት፣ የበሮች አሰራር፣ ስዕላቱ፣ በቅርፅና በደንብ የተሰሩት መተላለፊያዎች…. ምኑም ቢዘረዘርና ቢብራራ ነጋሪውንም ተነጋሪውንም አያረካም። ብቻ ጉድ እንዳልኩኝ አይቼው፣ ጉድ እያልኩኝ ተመለስኩኝ። ዛሬም ሳስበው ሌላ ነገር አልልም፡፡ — ጉድ ነው የምለው። “ሰው ነው የሰራው” “መንፈስ ቅዱስ” ብለው ለሚሟገቱ ሰዎች መልስ ለማቀናበር ሳልደክም ለራሴ ግልጋሎት የሚሆን መልስ ስላገኘሁ ደግሞ ይበልጥ ደስ ይለኛል። DSC01446እንዲህ ነው….

በእኔ እምነት ሰው ይህን ሰራ ቢባል እንኳን ያስበውና ደፍሮ ይጀምረው ዘንድ ወይ እብድ (የአእምሮ ህሙም) መሆን አለበት፣ ወይ ደግሞ የተለየ መንፈስ ሊኖረው፣ ሊያመላክተው ይገባል። ሌላ ሌላውን ብተወው እንኳን የድንጋዩና የፈልፋዩ በአንድ ቦታ መከሰት እንዲያው ግጥምጥሞሽ ነው ማለት ይከብደኛል። በተለይ መፈልፈሉና መፈፀሙ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ መውሰዱን ሳስተውል፤ ያም ሆነ ይህ ግን ከሚታየው ነገር ርቄ በማይታየው ነገር እየተብሰለሰልኩ የማንንም ዋጋ (credit) የማሳጣት ሀሳቡም፣ መብቱም፣ አቅሙምDSC01463 የለኝም። ማንም ሰራው ለምንም ሰራው… ላሊበላ ለዐይኖቼ ታምር ነው።

እንግዲህ ከ900 ዓመታት በፊት እኒያን የመሳሰሉ ህንፃዎች ተፈልፍለው ባለበት ሁኔታ በአካባቢው ላይ ተመሳሳይ የኗሪዎች ቤት አለመኖሩን  መመልከት ሌላ አግራሞት የሚያጭር ነገር ነው። (የሰው ሀሳብ ነው ብለን ለአፍታ ስናስብ) ሌላው ቀርቶ በአካባቢው ለመውቀጫና ለወፍጮ የሚፈለፍሉት ድንጋይ እንኳን ያን ያህል ሊስተካከልና ቀልብን ሊያማልል፣ ገና ሲታይ እንዲያስቅ ተደርጎ የተሰራ ነው የሚመስለው፡፡ በየመንገዱ የገበጣ ጉድጓዶችን ለመፈልፈል የተጀመሩ DSC02900ድንጋዮችም አሉ። ታዲያ ግን የጉድጓዶቹ ቁጥር ከመደበኛው የገበጣ ጉድጓድ ቁጥር ሳይደርስ ወይ መሽቶባቸው ወይ ደግሞ ደክሟቸው ሳይጨርሷቸው ሄደዋል። በመነጋው አልተመለሱበትም…. ወይ ረስተውታል… ወይ ደግሞ ከብዷቸዋል።

ለሁለተኛ ጊዜ ስሄድ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአየር መበላሸት ምክንያት ጉዞው እየተስተጓጎለበት ካሰብነው ጊዜ በላይ ነበር የቆየነው። በግማሽ ልብ እንደተጉላላሁ ቢሰማኝም፣ በግማሽ ልብ ደስ እያለኝ ነበር፡፡ ላሊበላ እንደ አዲስ ሲታይ እንደ አዲስ ሰለሚናፍቅ አምሮት ለማውጣት ጥሩ አጋጣሚDSC01361 ነበር የፈጠረልኝ፡፡ ምናልባት ለዚህም ይሆናል – የሁለተኛው ጉዞዬ ህልም አይመስለኝም። ሆኖም ግን ስሙን በሰማሁ ቁጥር ይናፍቀኛል፡፡ ያኔ አብሮኝ የተጓዘ እንግሊዛዊ ወዳጄ ስለተመለከተው ነገር ሲነግረኝ፣ – ‘ከዚህ በፊት ብዙ ቦታዎችን ተመልክቼ ተደንቄያለሁ ላሊበላን የሚያህል አስደናቂ ነገር ግን አላየሁም፡፡ ወደፊትም የማይ አይመስለኝም፡፡’

ከላሊበላ 42 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ የሚገኘው ደግሞ በዋሻ 20ውስጥ የተገነባው ይምርሀነ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ዋሻው ለቤተ ክርስቲያኑ እንደ ክዳን ሆኖለታል፡፡ ወይ ደግሞ ዋሻው እንዳይወድቅ ህንፃው ደግፎት ይመስላል፡፡ ይምርሀነ ክርስቶስ ከላሊበላ በ90 ዓመታት ገደማ  (ትክክለኛ ቁጥሩን አላስታውሰውም) የሚያረጅ ሲሆን በመፈልፈል ፈንታ የተገነባ ህንፃ መሆኑ ይበልጥ ያስገርማል፡፡ ግንባታ ከመሆኑ አንፃር በአካባቢው ተመሳሳይ ባይሆን እንኳን እንደ ነገሩ የተሞከሩ ግንባታዎች አይታዩም፡፡ እኔ ያየሁትን ተናገርኩኝ እንጂ፣ በላሊበላ ዙሪያ ይምርሀነ ክርስቶስdsc02870 ብቻ አይደለም ያለው፡፡ እንግዲህ የሞላለት ቦታው ደርሶ ልቡን በፈለገው ዜማና ስልት ማስዜም ነው፡፡ ምንም ሆነ ምን ግን የዜማው ይዘት

‘ዐይኔ ዓለም አይ እግሬ ደርሶ፣
የድንጋይ ወጋግራ የድንጋይ ምሰሶ፣’

ከሚል እንደማይዘል ይሰማኛል፡፡ ነገሬን ስቋጭም… ከላይ ካሰፈርኳቸው አንቀፆች አንዱን ደግሜ በማለት ነው…. ሀይማኖቱ — ኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክ፣ ጴንጤ፣ ሙስሊም፣ ጣኦት አምላኪ፣ ጠንቋይ ቀላቢ፣ ኢ-አማኒ፣ ግራ-ገብ…. ሌላም የፈለገውን ሆኖ፣ dsc03086መረዳቱ የፈቀደለትን እምነት የሚከተል ማንም፣ (በተለይ ኢትዮጵያዊ) በህይወት እያለ፣… በላሊበላ ለመደነቅና ቦታው ደርሶ አይቶ ‘በዐይኔ ዓለም አየሁ’ ለማለት፥ማህበረሰባዊ ጤና ያለው (socially healthy) ቢሆን በቂ ነው። ምናልባት ጤነኛነቱ ላይ የአገር ፍቅር ስሜት ቢጨምርበትና ባንድራው ትዝ ቢለው ደግሞ ደስታው እጥፍ ድርብ ይሆንለታል፡፡ — እንደ እኔ ነው!

 

DSC01372

DSC01441

DSC01442

DSC01447

DSC01458

19

21

bet emanuel lalibela

arcade-with-star-of-david-lalibela

aerial view,Lalibela comp

images

254881_533474059998532_520872321_n

ማስታወሻ፡ መጨረሻ ላይ በተከታታይ ያሉት አምስት ፎቶገራፎች ከኢንተርኔት የተገኙ ናቸው፡፡

መልካም የገና በዓል ለሚያከብሩት በሙሉ፡፡