ከጠይም ማህፀን: ከጠይሙ ምድር፣ ከጠይሙ ሰማይ፣
ከጠይም ደመና፣ ከጠይሙአድማስ፣ ከጠይሙ ቀላይ፣
የጠንቆጠቆጡ፣. . . ጠያይም ብርሀናት፣ ጠያይም ከዋክብት፣
አረንጓዴ፣ ቢጫ__ ቀይ መቀነት ታጥቀው — ጠያይም አካላት!
ጠይም ጃኖ ለብሰው፣ ጠይሙን ደርበው፣ ውብ ነጠላ – ጋቢ፣
– ተሰብስበው ቆመው፣ ቀልብ ሀሳብ ሰብሳቢ፣
— ጠያይም ቀለማት!
— አማርኛ መልካት!
. . . ከጠይም ጨረቃ፣ ከጠይሙ ፀሀይ፣
ከጠየመ ሜዳ፣ ከጠያይም ምንጮች፣ ከጠይም አፈር ላይ፣
ጠይም የጨለፋት፣ ጠይም ያበቀላት — ጠይሟ ዘመናይ!
ነይ ማታ፣ ነይ ማታ!
ጵጣ ጵጣ ቼኮላታ….
እዩ ልዩ ቆንጆ! – “ጠይም ዓሳ መሳይ፣
እኔ እናቷን ብሆን ለሰውም አላሳይ”
‘ምታባብል እንኮይ፣ ሰርክ የምታባብል፣
ዐይን የምታሸፍት፣ ልብ የምታሰልል፣
ሰውነት ምታርድ፣ ቀልብ ‘ምታነሆልል፤
አወይ ማርማላታ፣
ጵጣ ጵጣ ቼኮላታ….
የተሽቆጠቆጠች፣ የተሽሞነሞነች፣
የተሞናሞነች፣ ያማረች፣ ያጌጠች፣
— ጠይም ቀንበጥ ዛላ!
እግዚኦ የርሷ አሰራር፣ አቤት የርሷስ ገላ!
ወፍ ሲያልፍ እንኳ’ ቢያያት፣ እህልም አይበላ
– ጠይም ፍሬ ቃርሞ፣ የት ሊያሰኘው ሌላ?!
አያሳየኝ እሱን፣ – አንቺን ያየ ለታ፣
ስራውን ጣጥሎ፣ ሲቋጥር ሲፈታ፣
– ከላይ ከሰማዩ፣ ይደፋል ባ’ፍጢሙ፣
በራሪው፣ ቀዛፊው፣ እግረኛው በሙሉ፣
– ይነሳል በሽታው፣ የመጣል ህመሙ፣
ይታያል ፈንግሉ. . .
ከተደበቀበት፣ ይገለጣል ሱሱ፣ ይወጣል ዐመሉ፣
– መልክ የማወቅ አመል፣ የመደነቅ ጠባይ፣
ፊት ለፊቱ ሲቆም፣ ሲዟዟር ዐይኑ ላይ፣
– ውበት ከነጠባይ! — ከጠይም ገፅ ላይ!!
አወይ ማርማላታ፣
እግዚኦ ቼኮላታ፣. . .
ሲታሰብ ሲጣፍጥ፣ እንኳንስ ሲበላ!
ሀበሽኛ ውበት፣ ኢጦቢኛ ገላ!!
‘U la-la,…. U la-la’…
በማያውቀው ቋንቋ፣…
እንዲያው “ሰላ ሰላ”፣
“ሰላ በይ” ይልሻል. . . “በይልኛ ሰላ”፣
“ጀበናም የለኝም፣ ቡና እንዳላፈላ”፣
እግዚኦ ጠይም ውበት፣ አቤት ጠይም ገላ፣
በምን ይችሉታል? የተኮላን እንቁ፣ የተቆላ መና፣
በእውቅ የታነፀ፣ በታምር የቀና፣ የጠየመ ቡና፣
አቤት አቆላሉ፣ ውብ አወቃቀጡ፣
አቤት አፈላሉ፣ አቤት አጠጣጡ፣
ውይ አጨላለጡ….
ታምር ነው ውጤቱ – ልብ የሚያመረቃ፣
ትውልድ የሚሻገር፣ ዘመን የሚያነቃ፣
ሲታሰብ ሲጣፍጥ፣ እንኳንስ ሲበላ!
— ሀበሽኛ ውበት፣
— ኢጦቢኛ ገላ!!
አሰኚኝ ድረሺ፣ ‘በዪ ሰላ ሰላ…’
ነይ ከቤቴ ግቢ፣
— አንቺን አንቺን ይበል፣ ደጄ ጠይም ያጥላ፣
ምናምን አርጊበት፣… ባርኪው እማ መላ፣
አቤት ማርማላታ፣
እግዚኦ ቼኮላታ፣
ጵጣ ጵጣ አረንቻታ….
– ሲታሰብ ሲጣፍጥ፣ እንኳንስ ሲበላ!
— ሀበሽኛ ውበት፣
— አማርኛ ገላ!!
ከጠይሙ ገፅሽ፣ ከጠይም መልክሽ ላይ፣
ጥርስሽን ፈልቅቂ፣ መልክሽን ሸልቅቂ፣
ዐይንሽን አንከባይ፣ ላ’ለም አብረቅርቂ፣
በቀለም ጨምሪ፣ በእውቀት ምጠቂ፣
የጥቁር ጥጧ ‘ቴ፣ በይ ምጪ እመቤቴ፣
ልልቀምሽ፣ ልፍተልሽ፣ ላዳውርሽ በሞቴ፣
— ፍጠኚልኝ ነፍሴ፣
— ገስግሽልኝ ልብሴ፣
— ሁኝ ግርማ ሞገሴ!!
የውበት እመቤት፣ ጠይም የደም ገንቦ፣
ተጠራርተው ወጥተው ይቃኙሽ በደቦ፣
“ታምር አየሁ!!” ይበል፣ ህዝባ’ዳም ይደመም!
“እኔስ የለሁ!!” ይበል፣ ህዝቤ-ዋን ይገረም!
“የሱ ናት…” ይበሉ፣ ጀማው እኛን ያውራ፣
“የእኔ እኮ ናት” ልበል፣ እኔም ባንቺ ልኩራ፣
ወጣ ብለሽ ታዪ፣ በአድባባይ አብሪ፣
በመልክሽ ታፈሪ፣ በፀባይሽ ኩሪ፣
የእኔ ቼኮላታ. . .
ከሁሉም ከሁሉም….
— ማሰሪያ ዶቃውን፣
— መጠፈሪያ ውሉን፣
— አቃፌ መልክሽን፣
— አቃቤ ገፅሽን፣
ራስሽን አስውቢ፤ ዘውድሽን አትርሺ፤
አንጎልሽን ይዩት፣ በውብ አሳምሪው፤
ጠይም ሀሳብሽን፣ በደንቡ ቅለሚው፤
አቤት ማርማላታ!
እግዚኦ ቸኮላታ!
“ወይ ጉድ…” አስብያቸው፤
“ጵጣ ጵጣ” አሰኛቸው፤
– “ጵጣ ጵጣ አንጎላታ!
ጵጣ ጵጣ ኢጦጲያታ!
ጵጣ ጵጣ ጠይም ናታ!”
/ዮሐንስ ሞላ/
(ለሀበሻ መልኮች!! (በተለይም ደቡብ አፍሪካ ላይ በድጋፍ ወቅት አፍዝ አደንግ ለነበሩት) ‘ጠይም ጠይም’ ቢልም…. ለቀያዮቹም በሙሉ ነው፡፡ ያው የእኛ ቅላት የጠይም ዘርነቱ ይለይ የለ?)