ስብሀት ለአብ አንድ ዓመት?! :( ነፍስ ይማር!!

481115_155642161260189_1320307630_n

የሽንት ቤት ፅሁፎች (graffiti)

እንደ መግቢያ

ጨዋታን ጨዋታም አይደል የሚያነሳና የሚጥለው…. እናም ትናንትና መክሸፍ እንደ ታገል ሰይፉ ብለን ወሬያችንን ካቀናበርንና ካጋጋልን በኋላ፣ ብዙ ወዳጆች ሽንትንትኑ ታገል “እንዴት ፌስቡክን የሽንት ቤት ግድግዳ ይለዋል?” ብለው ክፉኛ መንገብገባቸውን ተረዳሁ፡፡ (በነገራችን ላይ እድሜ ለታገል ይሁንና በትናንትናው እለት “ሽንትንትን” የምትል ቃል ለምንወዳት አማርኛችን ያበረከትንበት ሁኔታ ነው ያለው። ሃሃሃ…)

ከዚያ በኋላ፣ የወዳጆቼ መንገብገብ ከነበረብኝ መንገብገብ ጋር ተዳምሮና ስሜቴን አልቆት በእህህ ስቆዝም፤ እንዲሁም ወዳጅ Abe Tokichaw በጉዳዩ ላይ ያጫወተንን አነበብኩና ስለ ሽንት ቤት ፅሁፎች ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ስለ ግድግዳ ላይ ፅሁፎች ማሰብ ጀመርኩኝ። አስቤም አልቀረሁ፣ ጎለጎልኩኝ፡፡ ጎልጉዬም አልቀረሁ የመሰጡኝን ነገሮች አጠር መጠን አድርጌ ለእናነት ተንገብጋቢ ወዳጆቼ ላካፍላችሁ ወደድኩ፡፡ (ለገብጋባ አላልኩም፡፡ ሃሃሃ…)

ትርጉም (በስለሺ! ሃሃሃ….)

የግድግዳ ላይ ፅሁፍ ጥበብ በእንግሊዘኛው  graffiti ይባላል፡፡ ቃሉ ሲወርድ ሲዋረድ መጥቶ በዋናነት የግድግዳ ላይ ፅሁፎች ስያሜ ሆኖ የቀረ ይምሰል እንጂ አፈጣጠሩና አገባቡ ግድግዳን በመቦርቦር የሚፃፉ ፅሁፎችን (ስዕሎችና ቅርፆችን ጭምሮ) ለመግለፅ የሚውል  ነው፡፡  የግራፊቲ ስርወ-መሰረትም “graffiato” የሚል የጣሊያንኛ ቃል ሲሆን፤ ትርጉሙም scratched ማለት ነው። — የተፋቀ፣ የተፋፋቀ እንደማለት፡፡

እነሆ የተፋቀ ከሚለው የጣሊያንኛ ቃል ግራፊቲ የሚል ቃል መጣና ግድግዳ ላይ በፍቀት ለሚሰሩ የጥበብ ስራዎች ስያሜነት ሲያገለግል ኖሮ ኖሮ፣ ….በሂደት ቃሉ የአግልግሎት አድማሱን በማስፋት (ሄሄሄ….)፣ አሁን ግድግዳ ላይ በፍቀት፣ በፅሁፍ ወይም በስፕሬይ የሚፃፉ ፅሁፎችን በሙሉ ለመግለፅ ይጠቅማል፡፡ – ግራፊቲ!  ይህን አገባቡን ሲያሰረግጥልንም የ oxford መዝገበ ቃላት…..

‹‹Graffiti is writing or drawings that have been scribbled, scratched, or sprayed illicitly on a wall or other surface in a public place. Stickers and other adhesives are not considered graffiti. ›› ብሎ ይተረጉመዋል፡፡ ለግራፊቲ ወጥ የአማርኛ ቃል ማግኘት ስላልቻልኩ ግራፊቲ እያልኩ በእንግዘሊዘኛ ስያሜው በመጠቀም እቀጥላለሁ፡፡

ከግራፊቲ ታሪክ ላይ በማንኪያ…

ግራፊቲ ከክርስቶስ ልደት በፊት ጀምሮ በተለያዩ ቦታዎች የነበረ መሆኑ ይነገራል። በምሳሌነት ግብፅ ውስጥ የሚገኙ ጥንታዊ የግራፊቲ ስራዎች የሚጠቀሱ ሲሆን፤ ያኔ የእንስሳት አጥንቶችን በመጠቀም ሰዎች በፍቀት የተለያዩ ፅሁፎችንና ቅርፆችን በዋሻዎችና ገዳማት ግድግዳዎች ውስጥ ያኖሩ እንደነበረ ይነገራል፡፡ በነዚያ ወቅቶች ሰዎች በፍቀት የፍቅር ጥቅሶችን፣ ፖለተካዊ ይዘት ያላቸውን ፅሁፎች፣ እና የተለያዩ ሀሳቦችንና ፍልስፍናዎች ያሰፍሩ የነበረ ሲሆን፣… በአንፃሩ አሁን አሁን በብዛት በግራፊቲ የሚገለፁት ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሀሳቦች ብቻ መሆናቸውን በዘርፉ የተመራመሩ ሰዎች ይናገራሉ፡፡

ግራፊቲ ቋንቋን በማስተላለፍና በማሳደግ ረገድ ያለው ሚናም ትልቅ ነበር፡፡ እንደ ምሳሌ፡ ከክርስቶስ ልደት በፊት 1ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ እስከ ከክርስቶስ ልደት በኋላ 4ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ እድሜ እንዳለው የሚነገርለት የሳፋይቲክ ቋንቋ ብቸኛ መገኛ ምንጩ በደቡብ ሴርያ፣  ምስራቅ ዮርዳኖስ እና ሰሜን ሳውዲ አራቢያ በረሀዎች በረሀ ውስጥ በሚገኙ የግራፊቲ ፅሁፎች ላይ መሆኑ ይነገራል፡፡

ግራፊቲ ዘመናዊ መልክ ይዞ ብቅ እንዳለ የሚነገረው ደግሞ በጥንታዊት ግሪክ ኤፈሰስ ከተማ ውስጥ ልብ ቅርጽ ላይ ያረፈ ዱካን ከቁጥሮች ጋር በቅንብር ማስቀመጥ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ነው፡፡ እነዚያ ግራፊቲዎች ሴተኛ አዳሪነት ህይወት (prostitution) ማስታወቂያዎች እንደነበሩ የአካባቢው አስጎብኚዎች እንደሚገልፁ የወሬ ማህደሮች ያትታሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያለ ግራፊቲ የተለያዩ አገር ሰዎች፣ በተለያዩ ጊዜያት አሻራቸውን ያኖሩ ዘንድ በመጥቀም የራሱን አሻራ ያኖረ የጥበብ ዘርፍ ነው፡፡

ወፍ አይሞትም! (ጀግና አይሞትም እንዲሉ)

እንደ ምሳሌ፡ በአሜሪካ ኦሪገን ግዛት በአንድ ብሔራዊ መስህብ ቦታ፣ የመፈረሚያ ድንጋይ ነበረ፡፡ በ1970ዎቹ ደግሞ የፈረንሳይ ወታደሮች በግብፅ ዘመቻቸው ወቅት፣ ስማቸውን በዋሻዎች ውስጥ ያኖሩ ነበር፡፡ ከዚህ ባሻገር ግራፊቲ ከሂፕ ሆፕ ባህል ጋር የተቆራኝ እንደሆነም ይነገራል፡፡ ቢሆንም ግን ከሂፕ ሆፕ ባህል ውጭም በተለያዩ ቦታዎችና ጊዜያት ላይ በጉልህ የሚታዩና ብዙ ኗሪ የሚጠቀማቸው የግራፊቲ ስራዎች አሉ፡፡

በ2ኛው የአለም ጦርነት ወቅት እና ከዚያ በኋላ በነበሩ አስርት አመታት ውስጥ፣ “Kilroy was here” የተባለና ከዚያ ቀደም ብብዙ አሜሪካውያን ይባል የነበረ ግራፊቲ በዓለም ላይ በብዛት የተስፋፋና በጥቅም ላይ የዋለ እንደነበር ይነገራል፡፡ በቅፅል ስሙ ‹ወፍ› ይባል የነበረው አሜሪካዊው ሳክስፎኒስትና የጃዝ አቀናባሪ ከሞተ በኋላ በኒው ዮርክ አካባቢ ይፃፍ የነበረው ግራፊቲ ‹‹ወፍ አይሞትም/ይኖራል›› ትርጉም የነበረው ነው፡፡ (‹‹ሀበሾቹም ጀግና አይሞትም›› እንድንል፡፡ ሃሃሃ…..)

ግራፊቲና ሊሾ (የሲሚንቶ ልስን)

በዓለም ላይ ግራፊቲ እንደ ተራ መታሰቢያ ማህተምነትም ያገለግላል፡፡ በጣም የተለመደው አይነትም ሰዎች አሻራቸውን በርጥብ ሲሚንቶ ላይ የሚያሳርፉበትና መታሰቢያቸውን የሚያኖሩበት መንገድ ነው፡፡ በልማድ እንዲህ ያለው ግራፊቲ የሚደረገው የህብረት ስራን (ትብብርን) ለማስታወስ፣ ወይም ደግሞ የሰውየውን በዚያ ቦታ ላይ ለመዘከር እንደሆን በዘርፉ ላይ ትኩረት ያደረጉ ሰዎች ያትታሉ፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘ በአራችንም ከትንሽ የበረንዳ ሲሚንቶ (ሊሾ) ስራ አንስቶ እስከ ትልልቅ የግንባታ ስራዎቸ ሲደረጉ በቦታው ያሉ ሰዎች ስማቸውንና አመተ ምህረቶችን ሲፅፉ ማየት የተለመደ ነው፡፡ ከዚያም ባለፈ ሰዎች በጣም አጭር የህይወት ታሪካቸውንና፣ የሚወዱትን ሰው ስም በሲሚንቶ ላይ ሲያርፍ ማየት አዲስ አይደለም፡፡ (ስድብና ዘለፋውን ችላ ብለን)

ግራፊቲና ተሳዳቢነት

ከዚህ ባሻገር ግራፊቲ የሰዎችን ስብህና ለማንቋሸሽና ለማጣጣልም ሲያገለግል ይስተዋላል፡፡ በዋናነትም ዘረኝነትን ለማስፋፋትና የተወሰነ ግሩፕን ለማንቋሸሽ/ለማጣጣል የሚውሉ ግራፊቲዎች ይጠቀሳሉ፡፡ ሆኖም እንዲህ ያሉ ግራፊቲዎች በሚመለከታቸው አስተዳደሮች ስለሚነሱ (ወይም ደግሞ በተጠቂዎቹ መልሰው ስለሚፈቀፈቁ – ምናልባትም ሌላ ስድብ ሰፍሮባቸው!) በታሪክ ማጣቀሻነት ይውሉ ዘንድ ፀንተው አይቆዩም፡፡ ብዙ ጊዜና ብዙ ቦታ የዘረኝነት ግራፊቲዎች በኮድ እነድሚፃፉና፣ ለተራ ተመልካች ስድብ እንደማይመስሉ የሚነግረን ‹ሆንኩዊስት‹ የተባለ ተመራማሪ ነው፡፡ ወደ እኛ አገር ስንመጣ ደግሞ በተለይ የሽንት ቤት ፅሁፎች በዘረኝነት ዙሪያ ሲያጠነጥኑ መመልከት የተለመደ ነው፡፡

WTC 9/11 ሰማይ ጠቀስ ህንፃ ግራፊቲዎች 

ግራፊቲን በተመለከተ በቅርብ ከምናስታውሳቸው ውስጥ አስገራሚ ዜና የነበረው  በመንትዮቹdad3c7a4e6ef7e02270f6a706700ac3a ህንፃዎች ምትክ የሚገነባው WTC 9/11 ግንባታ ላይ ግራፊቲ መፈቀድ ነው፡፡ በብዙ ግንባታዎች ላይ ሰራተኞች ግራፊቲ እንዳያስቀምጡና እንዳይፈርሙ ይከለከሉ የነበረ ቢሆንም፣ በዚህኛው ሰማይ – ጠቀስ ህንፃ ግንባታ ላይ ግን ግራፊቲ ያሰፍሩ ዘንድ መፈቀዱ ብዙዎችን አስገርሞ አልፏል፡፡ ግንባታ ቦታው ላይ ከሰፈሩት ግራፊቲዎች መሀልም ….

“Freedom Forever. WTC 9/11”. “Change is from within” “God Bless the workers & inhabitants of this bldg.” ይጠቀሳሉ፡፡ በተጨማሪም “We remember. We rebuild. We come back stronger!” የሚለው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ የግንባታ ቦታውን በጎበኙበት ወቅት ያሰፈሩት ግራፊቲ ነው፡፡ የጥቃቱ ሰለባ ቤተሰቦችም ስማቸውንና አስተያየታቸውን እንዲያሰፍሩ ተፈቅዶላቸዋል፡፡

ፀረ – ግራፊቲ (ፀረ – ሽብር እንዲሉ! ሃሃሃ….) 

ፀረ ግራፊቲ ቅብ ደግሞ ሰዎች በማጥፋት አባዜ የህዝብና የግለሰቦችን ንብረቶች እንዳያበላሹ ለማድረግ የሚጠቅም ዘዴ ሆኖ ብበዙ ቦታዎች ላይ የሚተገበር ነው፡፡ በዓለም ላይ በፀረ ግራፊቲ ዘመቻ ወቅትም ብዙ ቢሊዮን ዶላሮች ወጪ እንደሚሆኑ የ‹አንድሬው ቱርሌይ› ዘገባ ያትታል፡፡

ግራፊቲ በኢትዮጵያ (በተለይ የሽንት ቤት ፅሁፎች)

በኢትዮጵያ የግራፊቲ ጥበብ ከመች ጀምሮ እንደመጣ ባይታወቅም ጥንታዊነቱ ግን አይጠረጠርም፡፡ ለዚህም የአክሱም አካባቢን የድንጋይ ላይ ፅሁፎች መጥቀስና፣ ቢያንስ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የመጣ እንደነበር መገመት ይቻላል፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን ግራፊቲ በተለያየ ጊዜ ለተለያየ አላማ ያገለግላል፡፡ የትኛውንም የመፃፊያ ሰሌዳ ግድግዳ ብንለው፣ በርሱ ላይ የተፃፈ ነገር ሁሉ ግራፊቲ ነው ማለት ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የሰው ልጆችን ግድግዳ (የቆመ ነገርን ለመግለፅ ብቻ) አድርገን ብናስባቸው፣ ንቅሳት እንደ ጥሩ የግራፊቲ ምሳሌ ሊጠቀስ ይችላል፡፡ (ሃሃሃ…)

ንቅሳት (ታቱ) እንዲህ በዘመናዊ መልክ ከመስፋፋቱ በፊት በአገራችን ሰዎች የሚወዷቸውን ሰዎች ስም፣ ምስሎች እጃቸው ላይ ያሳርፉ ነበር፡፡ ከዚህ በተጨማሪ፣ ከላይ እንደ ተገለፀው፣ በአገራችን ብበዛት የሚስተዋለው የሲሚንቶ ላይ ግራፊቲ ነው፡፡ ሊሾ ሲሰራ፣ በቦታው ያለ ሰው፣ በትኩሱ የሆነ ነገር ያትማል፡፡ ቢከለከል እንኳን ብዙ ጊዜ ተደብቆ (በጨለማ መጥቶ) ሲያደርገው ይስተዋላል፡፡ አሁን አሁን እየተለመደ የመጣው ደግሞ የሰርግ ስርዓት ላይ የፊርማ ግራፊቲ ነው፡፡

በተጨማሪም በጥሩም በመጥፎም ጎኑ የሚነሳው የሽንት ቤት ግራፊቲ ሌላውና ዋነኛው ነው፡፡ (የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳል እንዲሉ፡፡ ሃሃሃ….) ሌላው ደግሞ የትምህርት ቤት ግድገዳዎችን ለግራፊቲ መጠቀም ነው፡፡ ዴክሶችን መፈቅፈቅም የተለመደ ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ሂደት ግን ከሰል፣ ቾክና፣ ሹል ብረቶችና ቀለም የሚተፉ በዕሮች ዋነኛ መገልገያ መሳሪያዎች መሆናቸው ይታወቃል፡፡

ለምን ሽንት ቤት?

 ከሞላ ጎደል እንደምንረዳው የግራፊቲ ጥበብ ሀሳብን የመግለፅና መልእክትን የማስተላለፍ ፍላጎት ውጤት ነው፡፡ ሰዎች ሀሳባቸውን እንዳይሰጡ በሚጨቆኑባቸው ቦታዎች ደግሞ የግራፊቲ አጠቃቀም በድብቅ፣ ንብረቶችን በማበላሸትና ህሊናቸውን በመጨፍለቅ ዋጋም ቢሆን ሲተገበር ይስተዋላል፡፡ በርግጥ ከላይ እንደጠቀስነው ግራፊቲ በተለያዩ ቦታዎች  የራሱ የሆን የአጠቃቀም ታሪክ ያለው ቢሆንም ወደ እኛ አገር መጥተን ስንመጣ ግን አብላጫው ታሪኩ ህዝባዊ ግድግዳዎችን በማበላሸት መተግበሩ ነው፡፡

ሰዎች በየሽንት ቤቱ፣  መጥፎ ሽታውን ተቋመውና ግድግዳውን እያበላሹት መሆኑን እያወቁም ጭምር የሚፅፉት ለምን እንደሆነ ጠይቀን መልሱን ብንፈልግ፤ ብዙ መድከም ሳያስፈልገን፣ በሰዎች ሀሳብን የመግለፅ ፍላጎት ላይ መታፈንና ይሉኝታ ተጨምረውበት መሆኑን በቀላሉ እንረዳለን፡፡ (ለመሳደብ የሚጠቀሙትን ሳንቆጥር፤ ሆኖም ግን ተሳዳቢዎቹ ቢሆኑም ጀርባቸው ቢጠና ስነልቦናዊም ሆነ ማህበረሰባዊ ትንታኔ ሊሰጠው የሚችል አመጣጥ ሊኖራቸው እንደሚችል እገምታለሁ፡፡) እዚህ ጋር መሳት የሌለብን አንድ ነጥብ ደግሞ ሀሳብን በመግለፅ ፍላጎት ውስጥ የመደመጥ ፍላጎትም መኖሩን ነው፤ እንዲያ ባይሆንና ይነበብልኝ ባይልማ ቤቱም ሊፅፈው ይችል ነበር፡፡

መጠየቅ ነውርና ለጥላቻ ዋዜማ በሆነበት ቦታና ጊዜ ወቅት ሰዎች ጥያቄያቸውን ተደብቀው ይጠይቃሉ፡፡ (በዚህ ረገድ ሀይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ ለማውራት መተፋፈር፤ እንዲሁም ገዢ መንግስትን ለማውገዝ መፍራት በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡) የሰዎች አስተሳስብና እምነት በማይከበርበት ቦታ ላይ ሰዎች ተደብቀው ሀሳባቸውን የመግለፅ ፍላጎት ያዳብራሉ፡፡ የሚያምኑበትና ጠቃሚ የሚሉት ነገር ሲኖራቸው፣ እንደ አቅማቸው መጠን ተደብቀው ይሰብካሉ፡፡ ለዚህም መጠናቸው እንደልብ ባያንከላውስም፣ ለአገራችን ህዝባዊ ሽንት ቤቶች ዋነኛ የግራፊቲ መድረኮች ናቸው፡፡

ፌስቡክ የእኛ ግራፊቲ ማስፈሪያ ግድግዳ!!

ምንም እንኳን ፌስቡክ በአካሉ ግድግዳ ስላልሆን የግራፊቲን ትርጉም አገባብ ቢፃረርም፣ (እኛ ግን ታገል በቀደደው ገብተን) ፌስቡክ ዘርፈ ብዙ የሆነ የግራፊቲ ማስፈሪያ ግድግዳችን መሆኑ ግልፅ ነው፤ እንላለን፡፡ ከላይ እነደዘረዘርነው የተለያየ የግራፊቲ አጠቃቀም አይነት ፌስቡክ ላይም በአይነትና በጥራት ተሰባጥረው ይገኛሉ፡፡ (አንዳንዴ በድብቅ፣ ብዙ ጊዜ ደግሞ በትክክለኛ ስም፡፡) በተለይ በዚህ – ጋዜጦችና መፅሄቶች እንዲዘጉ በሚገደዱበት – ወቅት ሰዎችን በማስተንፈስና መረጃ በማቀባበል ዘንደ፤ እንዲሁም ህብረተሰባዊ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶችን ለማድረግ የፌስቡክ ሚና ትልቅ ነው፡፡ እናም እንላለን!! —

ፌስቡክ ሆይ ለዘላለም ኑሪ!!!

በክፉ ያየሽ – ዐይኑ ይጥፋ!!!!

/ዮሐንስ ሞላ/

መክሸፍ እንደ ታገል ሰይፉ

እንደ መግቢያ

በመጀመሪያ ይህንን ጨዋታ “መክሸፍ….” ብዬ ላለመሰየም ከራሴ ጋር ጥቂት ውይይት አደረግሁና በሁለት ምክንያቶች ‘ተውኩት እንደገና።’ (ሃሃሃ….) አንደኛው ታገል የደረሰበትን ሁኔታ “መክሸፍ” ከሚለው ቃል በተሻለ የሚገልፀው ሌላ ቃል መፈለግ ዝቅ ማለትን ሊጠይቅ ይችላልና፥ ‘በውረጅ እንውረድ’ ፈሊጥ ከወረደ ጋር አብሮ መውረዱን አልወደድኩትም።

ሌላው ደግሞ ትናንትና ወዳጅ Tamrat “መክሸፍ እንደሰው ልጅ” ብሎ በውብ ቀምሞ ያቀረባትን ፅሁፍ አንብቤ፥ (Btw, የታሜን ፅሁፍ ታነብቡት ዘንድ ጋብዤያችኋለሁ።) ….ምናልባት መክሸፍ የሚለው ቃል አንባቢን ስለሚገፋ (ሰሞኑን በመደጋገሙ ምክንያት)፣ ሌላ አዲስ ቃል ተጠቅሞ ቢሰይመው ሊሻል ይችል እንደነበር አስተያየቴን ስሰጠው… “ያው መክሸፍ መክሸፍ ሲል ሰው ሁሉ፣ እስኪ እንሞክረው ብለን ነው።” በማለት በጨዋታ መልክ መመለሱን አስታውሼ፥….

…ሰው ሁሉ ‘መክሸፍ መክሸፍ’ ካለ ዘንዳ፥ በእኔ እይታ፥ ክፉኛ ለከሸፈው ታገል ሰይፉ ብጠቀመው፣ ሁኔታውን ለመግለፅ ይበዛበት እንደው እንጂ አያንስበትም ብዬ ነው። በዚያም ላይ ለበጣም ክሽፍ ሰው/ነገር መክሸፍ የሚለውን ቃል አለመጠቀም መሸፈጥ ሆኖ ከህሊና ጋር ሊያስተዛዝብም ይችላል። ነገራችንን “መክሸፍ” ብዬ በፕሮፌሰር መስፍን አዲስ መፅሀፍ ርዕስ ከሰየምኩ አይቀር ደግሞ፥ ኋላ ደጋፊ/አስራጭ (አሰረፀ እንድንል) ሲያሻኝ ማጣቀሱ ይቀለኝ ዘንድ አስቀድሜ ከ’ርሳቸው መፅሀፍ ላይ የሚከተለውን መዝዤ አስቀምጣለሁ።

“አንድ ሰው በአደባባይ ሲናገርም ሆነ ፅሁፍ አሳትሞ ሲያሰራጭ ራሱን አጋልጧል፤ የተናገረው ወይም የፃፈው መቶ በመቶ  ያህል በራሱ ጉዳይ ላይ ብቻ ከሆነ፣ የመተቸት ወይም ሀሳብ የመስጠት ግዴታ የለብንም፤ ነገር ግን የተናገረው ወይም የፃፈው በአገርና በህዝብ ጉዳይ ላይ ከሆነ፣ የዚያ አገር ዜጋ ሁሉ በጉዳዩ ውስጥ የመሳተፍና ሀሳቡን በሙሉ ነፃነት የመሰጠት መብት አለው፤ አለዚያ በየጓዳችን በሀሜት ብቻ እየተዘላዘልን እውነትን አንጥሮ በአደባባይ የማውጣቱን ዘዴ ሳንማር ሌላ ሶስት ሺህ ዓመታት እንቀጥላለን።” ~ መስፍን ወልደማርያም (2005) ‘መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ’ ገፅ. 78 – 79.

አንዳንዴ፥ አንድ ጊዜ የከሸፈ ነገር ደግሞ ሲከሽፍ ይታያል። ደጋግሞ መክሸፍ – በአካሉ – ብርቅ ባይሆንም ደርሶ ሲመጣ ማስገረሙ ግን አይቀርም። (ልክ ከሙታን ተለይቶ ተነስቶ እንደገና ሞተ እንደማለት ሆኖ ይሰማና እንደ ጉድ ይገርማል…) ለእኔ የታገል ነገር እንደዚያ ነው የሆነው። — በርግጥ ታገል ከከሸፈ ቆይቷል (ምናልባትም ደጋግሞ)፤ እነሆ በየካቲት ወር 2005 “ቁም ነገር መፅሄት” ቅፅ 12 ቁ. 145 እትም በኩል ደግሞ እንደ አዲስ መክሸፉን ተመለክቼ ስለርሱ ሽምቅቅ አልኩኝ።

ታገል – ታገል! 

ዛሬ በወዳጆች የinbox ጥቆማ ታገል ከቁም ነገር መፅሄት ጋር በነበረው ቆይታው፥ በአላዋቂነት ሊያሽሟጥጥብን ሞከረ መባሉን ሰማሁና አመሻሹ ላይ መፅሄቱን ፈላልጌ አነበብኩት። ሆኖም ግን ነገሮችን የሚመለከትበት መንገዱ ቀላልነት እንጂ ማሽሟጠጡ አልታየኝም። ማንም ገላውን ለመሸፈን በማይበቃ ቁራጭ ድርቶ ሊሸፋፈን ሲሞክር ራሱን ያጋልጣል። ‘ራሴን ሸፈንኩ’ ሲል – እግሩ፤ ‘እግሬን’ ሲል ደግሞ – ራሱ እየተገላለጠበት አበሳውን ያያል። ስህተት ለማረም ሌላ ስህተት ይሰራል።

እኔ ታገልን የተመለከትኩት እንደዚያ ነው። አንዱን ሲሸፍን አንዱ ሲራቆትበት ተመለከትኩትምና አንጀቴን በላው። እግዚአብሄር ምስክሬ ነው ከሚያሳዝነኝ በላይ አሳዘነኝ። ከምሳሳለት በላይ ሳሳሁለት። ግን ምን ያደርጋል? …እግረ መንገዱን ዘጭ አለብኝ። በፊት በየዋህነት (innocence) አድርጎትም ሊሆን ይችላል ያልኳቸውን ስህተቶቹን ሁሉ በቀይ አሰማመረባቸውና ተፈጠፈጠባቸው። የአፈጣፈጡ ሁኔታም “ጠላቴን ስመርቅ” የሚለው የቀድሞ ግጥሙን አስታወሰኝ፤…

“በሀብት ከፍ ከፍ፣
በስልጣን ከፍ ከፍ፣
ከዚያ የወደቅህ ‘ለት፥
አጥንትህ እንዳይተርፍ።”

[ግጥሙን ቃል በቃል በሙሉ ባለማስታወሴ ይቅርታ እጠይቃለሁ።]

ምስኪን!… የቱ ጠላቱ መርቆት ይሆን እንዲህ የባሰበት? መቼስ ሰው እንዲህ ሲሆን “ራሱን አጠፋ” ይባላል። ሆኖም ግን ራስ የማጥፋት ድርጊት ቸል ከተባለ፥ የልብ ልብ ሰጥቶ ‘በአጥፍቶ ጠፊነት መርህ’ ሌሎች  የዋሃን (ወይ ደግሞ ደቀ መዛሙርት) ይዞ ሊያጠፋ ይችላልና ስለርሱ ሳይሆን ስለነርሱ በስሱ በማሰብ ስል ይህንን መፃፉ አግባብ እንደሆነ ተሰምቶኛል። እናም “እግዜር ይሁነው” እያልኩ ወደ ገደለው እገባለሁ።

ቃለ መጠይቁ “በሲዲ የሚቀርብልን ነገር ግጥም አይደለም።” የሚል የፌስቡክ አስተያየት መኖሩን ጠቅሶ፥ የታገልን ሀሳብ በመጠየቅ ነው የሚጀምረው። እርሱም ለዚህ መልስ ሲሰጥ፣ በሲዲው ሽፋን ላይ – ግጥም ሳይሆኑ ለማዝናናት የቀረቡ መሆናቸውን መግለፁን በማስታወስ “…የተመለካታችሁኝ በኦርጂናል ሲዲ አይደለም። እባካችሁ ቅጂ ይብቃችሁ።…ነው የምላቸው።” በማለት በእርግጠኛነትና በግልፍተኝነት ነው።

በመሰረቱ ሰው እንደተረዳው (ወይም ግራ እንደገባው) መጠን አስተያየቱን ሲሰጥ ‘ከኦርጂናል ሰማህ ከቅጂ’ ብሎ ከመሞገት በፊት… አስተያየት ሰጪው ግር የተሰኘበትን ነገር አቅም በፈቀደ ካጠሩ በኋላ፣ ቀጥሎ የኦርጂናል ግዙ ምክሩን መለገስ የተሻለ ነው። ምናልባትም እንደተናጋሪው ትህትናና አዋቂነት፣ መልሱ “ኦርጅናል ግዙ” የሚለውን መልዕክትም አብሮ ያስተላልፍና ‘በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ’ ሊሆንም ይችል ነበር።

ሌዋታን?!

(ሌዋታን ታገል ከዚህ በፊት መንግስትን ያብጠለጠለበት (እንዲያ የነበብኩበት) የልብወለድ ስራው ርዕስ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡)

ከዚህ ቀጥለው የቀረቡለት 3 ተከታታይ ጥያቄዎች የሚያጠነጥኑት ደግሞ በ”በሚመጣው ሰንበት” መፅሀፉ ውስጥ ባካተተው ምስጋናና በሰጣቸው መታሰቢያዎች ዙሪያ ነው። ይህንንም ሲመልስ “….መቼም አባትየው ለአገሩ ጊዘውን መስጠቱን ደጋፊውም ተቃዋሚውም የማይክደው ነገር ነው። አከራካሪው ጉዳይ ለአገሩ በሰጠው ጊዜ ምን ያህል ጠቀማት፣ ጎዳት የሚለው ይመስለኛል። እኔ እዚህ ውስጥ አልገባሁም።….” ይልና…. እንደተድበሰበሰ ትቶት ከ’ሁለት ያጣ ጎመን’ ላለመሆን ይዳክራል። ምክንያቱም ይፈራል። –  ወይ ህዝቡን ወይ መንግስትን ይፈራል። …ነገሩን መመለስ ቀጥሎም “የኔ ጉዳይ ልጆቹ ናቸው፣ ልጆቹ ደግሞ የፖለቲካ ምልክት የለባቸውም።” ይለናል በእርግጠኝነትና በልዩ ቅርበት። (በእርግጠኝነትና በልዩ  ቅርበት ስል: እርግጠኛ ለመሆን ቅርበት ያስፈልጋል ብዬ ነው። የቅርበቱ ልዩ መሆን የሚስተዋለው ደግሞ ልጆቹን “ጉዳዬ” ማለት ሲጀምር ነው።)

ስፈልግ ደግሞ…“ታገል ማሽቃበጥ ካልሆነ በቀር አባት ሲሞት የመጀመሪያው ነው እንዴ? ስንቱ አገሩን ለመጠበቅ (በየትኛውም የፖለቲካ አጀንዳ ስር ሆኖ) ጊዜውን የሰጠ አባት “የኢትዮጵያ” የመባል ወግ እንኳን ቀርቶበት “የደርግ ወታደር” እየተባለ ልጆቹን በትኖ ሞቶ የለ? ስንቱ አገሩ ያበቀለችው እህል ናፍቆት ከረሀብ ብዛት አጣጥሮ ይሞት የለ? ስንቷ እናት ከምግብ ናፍቆት የተነሳ ህይወቷ አልፎ ልጆቿ ደረቅ ጡቷን ሲምጉ ተከትለው የለ? ስንቱስ ስንኩል አካሉን (እድሉን) ይዞ በስተርጅና ለልመና ተሰማርቶ የለ? ስንቱስ (ትክክል ባለው ፖለቲካዊ አጀንዳ) ጊዜውን ለአገሩ ሲሰጥ ልጆቹን በትኖ እስር ቤት ተጥሎ የለ? በግፍ ተሰቃይቶስ አልፎ የለ? ስንቱስ ልጆቹን አገር ቤት በትኖ፣ በሞያው ተሰድዶ በየሰው አገሩ ባክኖ ቀርቶ የለ …” እያልኩ መሞገት እችላለሁ። ግን አውቆ የተኛ’ እንዲሉ ቢፈልግ እንደማይጠፋው ስለማውቅ ድካም ብቻ ሊሆን ይችላል።

በርግጥ መፅሀፉን ለማን መታሰቢያ ማድረግ እንዳለበትና እንደሌለበት የሚያውቀው እርሱ ነው። ማንምም ጣልቃ ገብቶ ልንገርህ አላለውም። መፅሀፉን ገዝቶ ካነበበው በኋላ ግን ቅሬታውን ገለፀ፤… ታዲያ በውኑ ይሄ እርሱ እንዳለው “ጅልነት” ሊባል ይችላልን? ምኑስ ከድፍረት ይቆጠርና ነው እንዲህ ያለውን “ልኩን የማያውቅ ደፋር ብቻ መሆኑን ነው መልሼ የምነግረው” ማለቱ? እርሱ “ግጥም አይደሉም” ያላቸውን ግጥሞች ለማዝናናት በሚል ፈሊጥ አትሞ ሲሸጥ ማን ደፋር አለው? መፅሀፉ ላይ እንደፈለገ ምስጋናና መታሰቢያ አድርጎ በ27 ብር ግዙ ሲል ማን ደፋር አለው?

በስሜት ተነሳስቶ የፃፋቸውን ግጥሞች፣ በስሜቱ ተመርቶ አመስግኖና መታሰቢያ አድርጎ ሲያበቃ… ስለምን የአንባቢው ስሜት ማዳመጥ ጋር ሲደረስ ይቆጣል? …ወይስ የማፈን (የሰዎችን የመናገር ነፃነት የመገደብ) ውርስ ነው? ቢያውቅስ — ልክ እርሱ ለማንም ምንም ማድረግ እንደሚችል እንደሚያውቅ ሁሉ፣ ሌላውም እርሱ ያለውን ነገር ካለምንም ማብራሪያና ድጋፍ፣ ቁጣና ማበሻቀጥ መረዳትና መተንተን ይችላል። እዚህ ጋር ከላይ ያስቀመጥናትን የፕሮፌሰርን ሀሳብ መመልከት ነገሩን ያጠነክረዋል። ደግመን ስናነባት እንዲህ ትላለች….

“አንድ ሰው በአደባባይ ሲናገርም ሆነ ፅሁፍ አሳትሞ ሲያሰራጭ ራሱን አጋልጧል፤ የተናገረው ወይም የፃፈው መቶ በመቶ  ያህል በራሱ ጉዳይ ላይ ብቻ ከሆነ፣ የመተቸት ወይም ሀሳብ የመስጠት ግዴታ የለብንም፤ ነገር ግን የተናገረው ወይም የፃፈው በአገርና በህዝብ ጉዳይ ላይ ከሆነ፣ የዚያ አገር ዜጋ ሁሉ በጉዳዩ ውስጥ የመሳተፍና ሀሳቡን በሙሉ ነፃነት የመሰጠት መብት አለው፤ አለዚያ በየጓዳችን በሀሜት ብቻ እየተዘላዘልን እውነትን አንጥሮ በአደባባይ የማውጣቱን ዘዴ ሳንማር ሌላ ሶስት ሺህ ዓመታት እንቀጥላለን።” ~ መስፍን ወልደማርያም (2005) ‘መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ’ ገፅ. 78 – 79.

ታገል ቀጥሎም

“የአንድን ደራሲ መፅሀፍ ሲገመግም ጣልቃ ከማይገባባባቸው ጉዳዮች አንዱ የመታሰቢያ  ገፅ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የምስጋና ገፅ ነው። አንድ ደራሲ ለህሊናው ታማኝ ከሆነ የሚያመሰግነውን ሰው የሚመርጠው ሰውየው በሌሎች ኧይን የሚታይበትን ገፅታ ከግምት አስገብቶ መሆን የለበትም ይልቁንስ ሰውየው በእርሱና በስራው ላይ ካሳደረው በጎ ተፅእኖ አንፃር ነው።…”

ሲል ይሰብካል።

ሆኖም ግን የሳተው ነገር ማንም የምታመሰግነውን ሰው እኔ ልምረጥልህ አለማለቱን ነው። እድሉ ወይም ፍላጎቱ ሆኖ ግን ያመሰገናቸው ሰዎች በይፋ የሚታወቁ ስለሆኑ አስተያየት ተሰጠበት። በቃ! እርሱ ሲያመሰግንና መታሰቢያ ሲሰጥ እንዲህ ዓይነት አስተያየቶች  ሊሰጡት እንደሚችሉ ቀድሞ ካልጠረጠረ ጅሉ እርሱ እንዳለው አስተያየት ሰጪው ሳይሆን፣ ራሱ ነው። በዚያም ላይ ታገል ያመሰገነውና መታሰቢያ የሰጠው በህዝብ ጉዳይ ላይ ነው። (የተለየ ቅርበት አለኝ ቢልም እንኳን) በመሆኑም ፕ/ር ቁልጭ አድርገው እንዳስቀመጡት ‘የዚያ አገር ዜጋ ሁሉ በጉዳዩ  ውስጥ የመሳተፍና ሀሳቡን በሙሉ ነፃነት የመስጠት መብት አለው።’

እንደዚያ ካልሆነ ግን ፕ/ር ቀጥለው እንደገለፁት ‘በየጓዳችን በሀሜት ብቻ እየተዘላዘልን እውነትን አንጥሮ በአደባባይ የማውጣቱን ዘዴ ሳንማር…’ ሌላ ብዙ ጊዜያት ያልፋሉ። በመሆኑም ከጓዳ ወጥተው ስሜታቸውን በፌስቡክ የገለፁትን (የገለፅነውን) ሰዎች “ችግር ፈጣሪ” እና “ለፌስ ቡክ ክብር የሌላቸው” ብሎ እርሱ ሀሳቡን ለሚገልፅ ሰው ክብር እንደሌለው መግለፅ አልነበረበትም። ይልቅስ ፌስቡክ ላይ አስተያየት መሰጠቱ፥ ይህንን የመናገርና ሀሳቡን ቦርቀቅ አድርጎ የማስረዳትና ራሱን በተሻለ የመግለፅ እድሉን አመቻችቶለታልና በጥሩ ጎኑ ተመልክቶት ማመስገንና፣ ፌስቡክ የተጫወተለትን ሚና ማድነቅ ይቀለው ነበር። ቅሉ ‘ከምን የዋለች ጊደር…’ ነው።

በክሽፈቱ ሲቀጥል…

“ደሀን የማመሰግንበት ምንም  ምክንያት አልነበረም። ከሀብታሙም ቢሆን እኔን ሳይሆን ኪነጥበቡን ለማገዝ የጣሩት ተመርጠው  ተመስግነዋል። በነገርሽ ላይ አሁን አሁን ግብፅ ስለአባይ አስር ሺህ ዘፈኖች አሏት። የእኛ ግን ሀምሳ አይሞሉም  እያሉ የሚተክዙሰዎች መነሳት ጀምረዋል። የግብፅ መንግስት የኪነጥበብ ሰዎችን ህይወት በተለያየ ሁናቴ ይንከባከባል። ለምሳሌ አንድ ደራሲ ቤቱን ዘግቶ መፃፍ ቢፈልግ የዓመት ደመወዙን ሰጥተው ይሸኙታል። ስራ ከሌለውም ድርሰቱን ቁጭ ብሎ የሚጨርስበትን በቂ ገንዘብ ይሰጠዋል ብቻ በቂ ችሎታ ይኖው።”….

በማለት አንድም ለደሀው ያለውን ንቀት በግርድፉ ያሳያል፤ (ሰውን በገንዘቡና ድጋፍ በማድረግ አቅሙ በመለካት) እንዲሁም ኢትዮጵያን ከግብፅ ጋር በማነፃፀር ለእድሜውም ለፆታውም የማይመጥን* ነገር ያወራል። በውስጥ ታዋቂነትም “እንዲህ ተንከባከቡኝ” ብሎ ይማፀናል። ወይ ደግሞ “እንዲህ ነው የተንከባከቡኝ” ሲል ያስረግጣል። እኛንም እኮ ይህ ፍላጎቱን መረዳታችን ነው “ጥበብ ሸረሞጠች” ያስባለን። ስለአባይ መፃፍ ካለበት ግብፅ 1000 ስላላት አይደለም። መፃፍ ካለበት ካለምንም ሁኔታ ይፃፋል እንጂ ማነፃፀሩ የትንሽ ነው።

[*ሴቶች ሆይ: “ለፆታው የማይመጥን” ስል ብዙ ወንዶች (በምናውቀውና በምንስማማበት መልኩ) ከሌላ ጋር መነፃፀር እንደሚደብረን ለመግለፅ ነው እንጂ ለሌላ አይደለም።… ምናልባት አታውቁ እንደሆነ ከጉዳዬ ወጣ ብዬ አንድ ምስጢር ሹክ ስላችሁ ‘ብዙ ወንዶች ከሴቶች ጋር ያላቸውን ግንኙነት ከሚያቋርጡባቸው አንኳር ምክንያቶች አንዱ በሴት ጓደኛቸው ከሌላ ወንድ ጋር መነፃፀር (compare መደረግ) መሆኑን የእኔ ጥናት ያሳያል። ሃሃሃ… የምር ግን ብዙ ወንድ “ኧከሌ ስላደረገ አድርግልኝ” ሲባል ደስ አይለውም።]

ታገልን በአካል ሳውቀው…

ታገልን ለመጀመሪያ ያወቅሁት እንዴት እንደነበረ ማስታወሱ “ደሀን የማመሰግንበት ምክንያት አልነበረም።” ማለቱን ኢ-ልክነት (የ “ኢ”ን አፍራሽነት ልብ ይሏል።) ለማሳየት ይረዳናልና ላጫውታችሁ። (ኢ-ልክነቱ በእኔ እይታ እንጂ አሁንም ቢሆን የምርጫው የርሱነት እንደተከበረ ነው።) ከእለታት በአንዱ እሁድ ነበረ። ቄራ መብራት ሀይል የሚገኝ ኢስት-ዌስት የተባለ አዳራሽ፣ የቤተሰብ ሰርግ ስለነበረብን ሁላችንም ተበታተንን፤ በብተናው መሰረትም እኔና የእህቴ ጓደኛ አብረን ለመሄድ ከሜክሲኮ ታክሲ ተጋፍተን ያዝንና ጉዞው ተጀመረ።

ትንሽ ተጉዘን መሀል መንገድ ላይ ታክሲው የጎደለበትን ሰው ለመሙላት ሲቆም ከሚጋፉት ሰዎች መሀል አንዱ ታገል ነበር። ተሳፋሪው እርሱ መሆኑ እንደተስተዋለ፥ ከውስጥም ከውጭም ትኩረት ሳበ። ‘ታገል ታገል…’ እያለ ሰዉ ሁሉ ስሙን ማንሾካሾክ ጀመረ። ከውጭ ያሉትም ግፊያቸውን ረገብ አደረጉት። ከውስጥ ያሉትም በማክበር ቦታ ለማስፋት ብድግ፣ ብድግ… ጠጋ፣ ጠጋ አሉለት። ‘ና እኔ ጋ፣ ና እኔ ጋ’ በሚል ማባበያ ዓይነት። — ታገል ነዋ!

እርሱም የትኩረት ማዕከል መሆኑ እንዳልተመቸው እያስታወቀበት እጅ ነስቶ ለመግባት ሲል ቀድመው የገቡት ታክሲውን ሞልተውታል። ረዳቱም “ሞልቷል” ለማለት አፍሮ ፀጉሩን ሲደባብስ፣ ፊት ያሉ ተሳፋሪዎችም በአንድ ጎን ከርሱም ጋር ተሳፍሮ  ለመቆየት፣ በሌላው እርሱን አክብሮ (እንዲሁም እርስ በርሱ ተከባብሮ) ቦታውን ለመልቀቅም በማሰብ “እኔ ልውረድ እኔ…” በማለት ሲገባበዙ…. ነገሩ ያልገባው ሾፌር ተበሳጭቶ “እናትህ እንዲህ ትሁን!  ዝጋውና እንሂድ አቦ…” (ዓይነት) ብሎ ዞር ሲል፣ ፊት ለፊት ታገል ነው። እርሱም በተራው ጋባዥ ሆኖ “እንዴ ለርሱማ ቢፈልግ ልቀጣ ጫነው” ብሎ ታገል ተጭኖ፣ በትህትና አመስግኖና በክብር እጅ ነስቶ ጉዞው ቀጠለ።

[ስፅፈው ረዥም ይምሰል እንጂ ሁሉም ነገር የአፍታ ክስተት ሆኖ አሰልቺ አልነበረም። ይህ ሁሉ ሲሆንም ታገል ፍፁም ሌሎቹን በማክበር….. አለመፈለጉን በትህትና በመግለፅ ሲታገል ነበር። ታገል – ሲታገል…. ሃሃሃ…] ታዲያ ይሄ ደሀ፣ በችርቻሮ ባይሆን እንኳን በጅምላው መመስገን ያንስበታል? (በችርቻሮውማ… ‘ሰማይን የሚያህል ብራና ተፍቆ፣ አባይን የሚያህል ቀለም ተበጥብጦ’ም አይዘለቀም።) እንግዲህ ይህ እኔ ከአንዳ’ንድ የገጠመኝ ነገር ነው። ይህ ቢቀር እንኳን ከያኒው ለስንት ፅሁፎቹ መነሻ ሀሳብ ከድሀ ህይወት አላገኘም? ፅፎ ሲያሳትምስ አብላጫው ገዝቶ አንባቢው ደሀው መሆኑን አላወቀም? (ሀብታም እንደው ብር ቢኖረው፣ ወይ ልብ ወይ ጊዜ የለውም ብለን ኮምፓችንን እናንጫጫው እንዴ? ሄሄሄ….)

‘ፍየል ወዲህ…’

አቶ ታገል ከሌላ አገራት ጋር የጀመረውን ንፅፅር በመቀጠል….

“አብደላ እዝራ እንዳጫወተኝ ደግሞ የመን ውስጥ አንድ ገጣሚ ከተነሳ የአገሩ ሀብታሞች በሙሉ ተጠራርተው ለኑሮው የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ ያጎርፉለታል። ይንከባከቡታል። እኛ አገር ደግሞ ይኧውልሽ በስንት ዘመን አንዴ ኪነጥበብን የሚንከባከቡ ጥቂት ግለሰቦች ብቅ ሲሉ ለምን ተመሰገኑ ብለን እንተቻለን። ደስ አንልም?”

ብሎ  ለማሽሟጠጥ ይሞክራል። ተንጋሎ በማሽሟጠጥ ለአናቱ እያስተረፈ። ….አሁን ይሄን እንተንትነው ቢባል ጉንጭ ከማልፋት ያለፈ ፋይዳ ይኖረዋል?…. ሌላ ሌላውን ትተን ግን ከሰሞኑ የተዘጉብንን መፅሄቶችና ጋዜጦች ማንሳት የኪነጥበብ እንክብካቤውን አቅጣጫ ፍንትው አድርጎ ያሳያል።

የፌስቡክ ማህበረሰብን ሲተች ደግሞ …..

“ከዚህ የተነሳ ሰው ሲሞገስ ለምን እንላለን ነገር ግን ዳገቱ የቁልቁለቱን ያክል ነው የሚባል ተረት አለ። ምናልባት በየፌስቡኩና በየሚዲያው ታላላቅ የአገር ባለውለታዎች የሚናገሩትን በማያውቁና የማያውቁትን በሚናገሩ ምላሶች ዝቅ ዝቅ መደረጋቸው ከፍ ከፍ እንዳረጋቸው ያነሳሳኝ ይመስለኛል።… ስለዚህ ጀግኖችን ለማንሸራተት ያበጁት ቁልቁለት ካልሰቀጠጣቸው የቁልቁለቱን  ያክል ብድግ ያለውም ዳገት ሊረብሻቸው አይገባም።  ምክንያቱም የኔን ዳገት የፈጠረው የእነሱ ቁልቁለት ነው።”…

….በማለት ስለማያውቀው (ወይም አይቶት ስላልገባው) ነገር ይዘባርቃል። — ለዚያውም በ“ይመስለኛል”። ዳገቱን ያወራልናል። ዳገቴ ካለው ቦታ ሆኖም ፌስቡክ ተጠቃሚዎችን ወደማያውቀው ቁልቁለት እያቆለቆለ ለመዘርጠጥ ይባዝናል። …እግረ መንገዱን (ከላይ ራሱ በጀመረበት መልኩ) ‘ልኩን የማያውቅ ደፋርነቱንና… ከማሞ ቂሎ የዘቀጠ ጅልነቱን’ ይነግረናል። ….“የጊዮርጊስን መገበሪያ የበላ ሳይጠይቁት ይቀባጥራል” እንዲሉ፥ ሳይጠየቅ። (ጥያቄው ‘….አንዳንድ ሀብታሞችን በጣም ታሞግሳቸዋለህ ብለው የሚተቹም አሉ።’ ይላል እንጂ የፌስቡክን ስም አለማንሳቱን ልብ ይሏል።)

በእውነት ለዚህ ከንቱ ንግግሩ ማብራሪያ  መስጠት ማሰቡ ትንሽ ወደ ታች መውረድ ሊፈልግ ይችላልና ለአፍላፊው ሀይማኖቴና አስተዳደጌ ስለማይፈቅዱልኝ አላደርገውም። ሆኖም ግን ቢያንስ ለማሞገስ ያነሳሳውን ነገር በ“ይመስለኛል” ማለፉ አሳፋሪ መሆኑን መጠቆም አግባብ ይመስለኛል። (እኔም ይመስለኛል። ሃሃሃ….) ደግሞ እንደ ሀይለኛ ነገሩን ሲቀጥል “በእርግጥ እኔም የጥበብ ሰው ከሆንኩ ሌሎች ምን ይሉኛል ሳልል የስሜቴን ጅረት ተከትዬ መፍሰስ አለብኝ።”…. ይላል። ታዲያ ስለምን አንባቢው “ታገል ምን ይለኛል” በሚል የስሜቱን ጅረት ተከትሎ እንዲፈስ በመጠየቅ፥ የተሰጡትን አስተያየቶች በማብራራት ፈንታ በተራ ፍልስፍና ያወግዛል?

ከተፎው ታገል! (ክትፎው አላልኩም) 

ከ“ምናውቃለሁ እንጃ” ግጥም ስር ያሰፈረውን ማብራሪያ በተመለከተም….

“መገምገም ካለብኝ ባቀረብኩት ስራ እንጂ ባቀረብኩት ስፍራ መሆን የለበትም። ለምሳሌ በእዛን እለት በሚሊኒየም አዳራሽ ያቀረብኩት ግጥም ተጀምሮ እስኪያልቅ የሚተርከው በአፄ ፋሲልና በአፄ ላሊበላ ዘመን ስለነበረችው ታላቋ ኢትዮጵያ ነው።”

በማለት ጀምሮ፥ በ ‘ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ’ ነገር፣ መልሶ ወደ ማነፃፀሩ ይሄዳል፤ እንዲህ በማለት. . . .

“ከማውቀው ድረስ በሰለጠኑት አገሮች ሳይቀር ታላላቅ የመንግስት ክብረ በዓሎች ላይ ገጣሚያንን መጋበዝ የተለመደ ነው።…. መሪዎቻችን አገራቸውን አይወዱም ከማለት አንፃር ከሆነ አገሩን  ከማይወድ መሪ ፊት ቆሞ የአገር ፍቅርን ማዜም እራሱ ጀግንነት ነው። መሪዎቻችን አገራቸውን ይወዳሉ ከተባለም እዚያ ስፍራ በቀረበው ግጥም ኢተገቢ ነገር አልተፈፀመም ማለት ነው ብዬ ነገሩን ችላ አልኩት።”……

በማለት አሁንም ቢሆን ጥግ ለመምረጥ መፍራቱንና፣ መሀል ሰፋሪነቱን በማደናገር ይነግረናል።

“ተወደደ የሚሉም አሉ።” ተብሎ ሲጠየቅ… “27 ብር?” በማለት ይጠይቅና፣ ዝብዘባውን በከንቱ ምሳሌ አጅቦ ይቀጥላል…

“ከሆነ እንግዲህ ሻይ ቤት ገብተሽ አንድ ሳህን ሙሉ ፓስታ በስምንት ብር ትመገቢያለሽ እንበል። ሆቴል ገብተሽ ደግሞ ሲኒ ማስቀመጫ በምታክል ጣባ እፍኝ ክትፎ በሰማኒያ ብር ትመገቢያለሽ የክትፎውን ዋጋ ውድ ነው ካልሽ ርካሽ ነገር ታውቂያለሽ ማለት ነው። ይህ እውቀት ግን አንድ ጣባ ክትፎን ለመገምገም በቂ አይደለም። ምክንያቱም የሆቴሉ ባለቤት ሰማኒያ ብር ሲያስከፍልሽ የስጋውን፣ የቅቤውን፣ የቅመሙን፣ የመስተንግዶውን ወጪ እግምት አስገብቶ ነው። ስለዚህ ከሻይ ቤቱ ፓስታ ጋር አነፃፅሮ ተወደደ ማለት ትንሽ ይከብዳል። የቀረበልኝ ነገር ዋጋውን ይመጥነዋል ወይ ብሎ መጠየቅ ግን ይቻላል። የዚህን ጥያቄ ትክክለኛ ምላሽ የሚያገኙት ታዲያ ዳርዳሩን በሽፋኑ በመታሰቢያው በግርጌ ማስታወሻው በምስጋናውና በዋጋው ዙሪያ የሚባክኑት ሳይሆኑ ግጥሞቹን ገልጠው ማንበብና ማጣጣም የሚችሉ ብቻ ናቸው።”

በማለት የአንባቢው ርካሽ የማወቅ ችግር እንጂ የርሱ ውድ መሆን ያለመሆኑን በትምክህት ይነግረናል። የርሱን ክትፎነትና የሌሎቹን ፓስታነት በኩፈሳ ያወራል። — እንግዲህ የመጥፋትና የመክሸፍ (መልሶ መላልሶ) ጥግ ማለት ይሄ ነው። (ካልሆነ ግን በአክብሮት ስለማተሚያ ቤት ዋጋ ውድነት ማውራት ይበቃው ነበር።)

‘ሽንትንትኑ’ ታገል (ሽንት እንትን አላልኩም!)

(እንትንትን የሚል ቃል ከዚህ በፊት ሰምቼ አላውቅም፡፡ የታገል ነገርም ታይቶ እንዳልታወቀ ነገር መላ ቅጡ ቢጠፋብኝ፣ በፈቃዴ ተሰምቶ የማይታወቅ ቃል ፈጠርሁለት፡፡)

ጥያቄው ቀጥሎ…. “እስካሁን ድረስ በፌስቡክ ላይ ለወረዱብህ ውግዘቶች ይሄን  ሁሉ ምላሽ ይዘህ ድምፅህን ያጠፋኧው ለምንድን ነው?” ተብሎ ሲጠየቅ

“ከመፅሀፍ ቅዱስ የምወደውና የሚመራኝ አባባል አለ። “የባልቴቶችን ከሚመስል ወሬ ራቅ” ይላል። እኔ ድሮ የማውቀው የባልቴቶች ወሬ በረከቦት ዙሪያ እንደነበር ነው። አሁን ወጣት ባልቴቶችን የሚሰበሰቡት ረከቦት ፌስቡክ ሆነ። ስለዚህ ከዚያ አካባቢ  ወሬ /መልስ ባለመስጠት/ መራቅ ነበረብኝ።”

…በማለት አጉል አዋቂነቱን ይቀባጥራል።

‘ባልቴት’ ካላቸው መሀል በሌሎች አገራት ፌስቡክ ረከቦት ዙሪያ ተገናኝተው መንግስት መገልበጣቸውን አያውቀውም። ምክንያቱም ወይ ፌስቡክ አካውንት የለውም፤ ወይ ደግሞ እርሱ ዙሪያ ያሉት ባልቴቶች ብቻ ናቸው። አገራችን ውስጥም በፌስቡክ አማካኝነት ብዙ ዓይነት የማህበረሰብ ስራዎች መሰራታቸውን አያውቅም። ምክንያቱም ወይ ፌስቡክ የለውም። ወይ ደግሞ ፌስቡክ መጠቀም አይችልም። ደግሞም እርሱ እንዳለው ባልቴቶች ተሰብስበው እያወሩ ነው ቢባል እንኳን የመፅሀፉን ጥቅስ በግርድፉ ወስዶ እንደጋሻ በመጠቀም፣ ከመራቅ ይልቅ እንደተቆርቋሪ ዜጋ መርዳትና ማስረዳት ይችል ነበር። ግን ወይ ፌስቡክ አካውንት የለውም። ወይ ደግሞ ፌስቡክ መጠቀም አይችልም።

ከድንዛዜው ቢነቃ ግን ኢንተርኔት በውሀ አለመስራቱን (በተለይ እኛ አገር) በመገንዘብ፣ ፌስቡክ ላይ ያሉ ወጣቶች (በእርሱ መፅሀፍ ዙሪያ ለመወያየት ፍላጎት የሚኖራቸው) ቢያንስ ኢንተርኔት የመጠቀም ጥቂት እውቀትና፣ ለኢንተርኔት የመክፈል አቅም ያላቸው መሆኑን ገነዘብ ነበር። መፅሀፉንም ቢሆን ገዝተን አንብበን ማውገዛችን ይገባው ነበር። ቅሉ ቅልብልብ ነውና…. “….ከጠፋ ራስ ጋር አተካራ መግጠም  አልሻም።….” ምናምን ብሎ ቃለመጠይቅ አድራጊዋ ሳታሰናብተው ለመቋጨት ያመሰጋግናል።

ከዚያም እህት አልጋነሽ “እኔ መች ጨረስኩ?” ትለዋለች። እርሱም (የምንተእፍረቱን መሰለኝ) “ቀጥይ” ይላታል። ጠየቀችው…. “ከዚህ ሁሉ ውዥንብር አንፃር ፌስቡክ ጠቃሚነው ትላለህ?” (መቼስ ተጠይቆ “አላውቅም/ይለፈኝ” ማለት ነውር ነው) መለሰላት….

“ጠቃሚነቱ ምንም አያጠያይቅም ግን ይህን የሚወስነው አጠቃቀማችን ነው። እዚህ ላይ የማስታውሰውን ገጠመኝ ልንገርሽ…”

ይልና ስለፌስቡክ ጊዜ መግደያነት ራሱ የፈጠረውን እንጨት እንጨት የሚል ቀልድ በአንድ አዛውንት ስም ይነግረናል። (የአዛውንትን ቋንቋ ጠንቅቄ ስለማውቅ።… አዛውንቱ የተማሩና የነቁ ስለሆኑ ነው ብንል እንኳን፥ እርሳቸው ፌስቡክ ስለመክፈት ቢያስቡ እንጂ ጊዜ መግደያነቱ አይታያቸውም ነበር።) ይቀጥልናም…

“እንደኔ እንደኔ ፌስቡክ ላይ ችግር የሚፈጥሩት ለፌስቡክ ክብር የሌላቸውና ፋይዳውን በቅጡ ያልተገነዘቡ ወገኖች ናቸው። እነዚህ ወገኖች ድሮ ድሮ ስማቸውን ደብቀው በየሽንትቤቱ ግድግዳ ላይ ብዙ ዓይነት ሀሜቶችንና ነውሮችን ሲፅፉ የኖሩ ይመስለኛል። አሁን ደግሞ ፌስቡክን እንደ ሽታ አልባ የሽንት ቤት ግድግዳ ላይ እንደሚያደርጉት ዛሬም ስማቸውን ደብቀው ያሻቸውን ነውር ይፅፋሉ። ያም ሆኖ ፌስቡክ የሽንት ቤት ግድግዳ ሆኖ የቀረው በነዚህ ወገኖች ደካማ ግንዛቤ ብቻ እንጂ በአግባቡ በሚጠቀሙት ወገኖች አይደለም።”

በማለት በከንቱ ነውር በጅምላ ያወራል። (ደግሞም የርሱ መፅሀፍ ላይ አስተያየት መስጠት ትልቅ ችግር የሆነ ያህል።)

አሁን ለዚህ መልስ ይሰጣል? ቢሰጥስ “ሽንት”ን ገላጭ (adjective) አድርጎ ካልሆነ የሚመጥን ነገር ይገኝለት ይሆን?? ከሁሉም በላይ ግን የገደለኝ “ሽንት ቤት” ካለው ቦታ ድድ ማስጣቱ። ወይ ደግሞ ሽንት ቤት ካለው ቦታ የተለቀሙለትን ወሬዎች አምኖ ተቀብሎ ራሱን መጉዳቱ። ሃሃሃ….

ከዚህ በላይ ክሽፈት ግን ከወዴት ይገኛል?!

ማስታወሻ: ከዚህ በፊት በመፅሀፉ ላይ በግሌ የሰጠሁትን አስተያየት ማንበብ የሚፈልግ ቢኖር ይሄን በመጫን ማንበብ ይችላል፡፡

/ዮሐንስ ሞላ/

ይግባኝ! – ለ ኢትዮ ቴሌ…

ለ ኢትዮ ቴሌ

ጉዳዩ: – ይግባኝ!

የቅድመ ክፍያ ሂሳብ ሽያጭ ካርድ ዓይነት ከፕላስቲክነት ወደ ካርቶንነት መለወጡ ይታወቃል። ለውጡን ያስተዋልነው ሰሞን፥ ምክንያቱ ምን እንደሆነ ባለሱቆቹን ስንጠይቅ ግምታቸውን “ከቻይና ነበር የሚመጣው፣ አሁን እዚህ መስራት ስለጀመሩ ነው።” ብለው ነገሩን። እኛም ከውጭ መምጣቱ አዲስ እውቀት፣ በአገር ልጅ መሰራቱ ደግሞ ብርቅ ሆኖብን ነበር ያሳለፍነው።

ከዚህ ጋር በተያያዘ ግን አልፎ አልፎ ያስተዋልነው ችግር ቁጥሩን ለማየት ቅቡ ሲፋቅ ያታግልና ቁጥሩም አብሮ ይፋቃል። ከዚህ በፊት ቁጥሮቹን እየገመትንና እያገጣጠምን ይሰራልን ነበር። ዛሬ ግን የ50 ብር ካርድ ገዝቼ ስፍቀው ቁጥሩ አብሮ ተፍቆ ሂሳቤን ሳልሞላ የቀለጥኩበት ሁኔታ ነው ያለው። ቁጥሩን እያገጣጠምኩ ልሞክረው አስቤ የነበረ ቢሆንም፣ የልጅነት እድሜዬ በሙከራ እንዳያልቅ በመስጋት ትቼዋለሁ።

[በነገራችን ላይ ከ10 ብር ባንዴ ወደ 50 ብር የተመነደግሁት 10 ደቂቃ ቦነስ አገኝ ብዬ መሆኑና፤… በፊት ደግሞ ከ100 ብር ወደ 10 ብር ያቆለቆልሁት፥ ብከስርም የ10 ብር ካርድ ልክሰር ብዬ እንደነበር ይታወቅልኝ።…ብዬ ላካብድ እንዴ? ሄሄሄ…]

ይህንን ጉዳይ ላማክረው ባለሱቁ ጋር ስሄድ “ቴሌ የምታውቀው ሰው ካለ በቀለላሉ በሴርያል ቁጥሩ ያወጡታል። የምታውቀው ከሌለ ግን እሺ አይሉህም። በፊት ይነግሩ ነበር፣ አሁን ግን ጠያቂው ሲበዛ ተማረው አቆሙት።” አለኝ። እኔም በሆዴ “ለዚህም ዘመድ?” ብዬ… ነገሩን አጥብቄ ብጠይቀውና እርሱ ካርድ ሊገዛ ሲሄድ እንዲጠይቅልኝ ባግባባው፣ እርሱ ራሱ ለራሴና ለደንበኞቼ ስሞላ ከሰርኩ ያላቸውን ካርዶች አውጥቶ አሳየኝ።

ለምስኪኑ፣ ወር ጠብቆ ኗሪና የብድር ተዳዳሪው እኔ ዛሬ በኤኮን “chop my money” የማላልፈው ጠንከር ያለ ዱላችሁ ስላረፈብኝ በአደባባይ “ይግባኝ” ስል እጮሃለሁ።

ምርጫ አልባው የዘወትር ተቃጣይ ደንበኛችሁ ዮሐንስ ሞላ

(የማይነበብ ፊርማ)

እኛና ኢትዮ ቴሌኮም

መቼም እኛና ኢትዮ ቴሌኮም ‘ምንና ምንድን ነን?’ ብሎ መጠየቅ አላዋቂ ያስብለናልና እሱን አናነሳም። ግን የግድ ‘ምንና ምን ናቹ?’ ብሎ በቀን 40 ጊዜ ከድርጅቱ እንደሚደርሱን የፅሁፍ መልእክቶች ችክ ብሎ የሚጠይቀን ቢመጣ ግን….
‘እኛና ETC ምንና ምንድን ነን፣
ጣውንጥ፣ ባላጋራ፣ የእንጀራ ዘመድ ነን’…..ምናምን ብለን እንመልሳለን። (ሆሆሆ….የገጣሚ ፈቃድን (poetic license) መጠቀም ይሏል እንዲህ ነው። ግን የእንጀራ ዘመድ የሚባል ነገር አለ እንዴ? ሆሆሆ…. ደግሞ ታች ድረስ ወርዶ በመከፋፈል ወንጀል መዝገብ እንዳንከሰስ ይቅርብን። — ስራ መፍታት ከሳሽና ተከሳሹን ያበዛዋል ብዬ እኮ ነው። ሃሃሃ….)

መቼም እንዲሁ ቤት ይምታልን ብለን እንጂ፣ በሁለተኛው ስንኝ ውስጥ በክፋትና ተንኮላቸው የሚታወቁ/የተለመዱ/በልማድ የተለዩ ወይም ደግሞ ክፋትና ተንኮልን አጉልተው የሚገልፁ ቃላትን ሁሉ ማጨቅም ነገሩን አይገልፀውም። ‘ምነው የለመድነውንና የረሳን የመሰልነውን ነገር ትቆሰቁሰው ዘንድ ምን አነሳሳህ? ያውም በምሽቱ?’ ምናምን ብሎ የሚጠይቅ ወዳጅም አይጠፋም። መቼም የእኛ ሰው ለመልስ ሳይጨነቅ መጠየቁን ተክኖታል…. ብዙ መልስ የሌላቸውን ጥያቄዎች ይጠይቃል…

ለጥያቄዎች መልስ ይሁን ብሎ ቃላት ቢሰትር፥ እዳው ኮብል ስቶን ነው የሚሆንበትና አያስበውም። (‘እዳው ገብስ የሚሉት አማርኛ ከገብስ መወደድና ከጌቶች ቆጣ ቆጣ ማለት ጋር ተያይዞ ተወዷል’ የሚል ወሬ ሰምተን እኮ ነው። ግን ምናለ ወጣቶቹ በጥቃቅንና በአነስተኛ ተደራጅተው ጆሮአችንን አሸዋ ቢገርፉልንና ከድካም ቢታደጉን? የምሬን እኮ ነው….) የእኛ ነገር!…አሁን ማን ጠርቶን እንዘባርቃለን?…. እርሱን ትተን የተነሳንበትን እንጫወት እስኪ። ነገሩ እንዲህ ነው…..

ዛሬ ካርድ የ15 ብር የሞባይል ካርድ ገዝቼ፥ አንድ ወዳጅ ጋ ስልክ ደውዬ (2 ደቂቃ ከ 24 seconds) እና e-mail አይቼ (ከ2 ደቂቃ ያነሰ) ወጣሁኝ። ከዚያም አገር ሰላም ብዬ፥ አንድ ወዳጄ የላከልኝን የፅሁፍ መልእክት ለመመለስ፥ አቀናብሬ ‘sent’ ብለው….. “Your account balance is insufficient for SMS Service. Please recharge first, dial 909 to recharge your account.” የሚል መልእክት ባናት ባናቱ 3 ጊዜ መጣልኝ። (ባለፈው 27text ልከውልኝ ስለነበር ’27 ጊዜ መጣልን’ ልንል አልንና ‘ተውነው እንደገና’ ሃሃሃ…)

ሶስትም ግን ብዙ ነው። አንዱ ይበቃ ነበር። ምናልባት ግን አንገብግበው ካርድ ማስገዛት አስበውም ሊሆን ይችላል። (የእኛና የነሱ የልጅ የጅል ጨዋታ አንዱ አካል…..ተነቃቅተናል….;) [ቀደምት አበወ ወ እመው፥ ‘በደንባራ በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ’ እንዲሉ ብስጭቱ ተደማምሮ ደሜን ከፍ አያረገውም?! (ሃሃሃ… ‘ሲሉ ሰምቼ፣ ከኮልፌ መጣሁ በሩን ዘግቼ!’ ሄሄሄ…..)] ከዚያም ቀሪ ሂሳቤን ለማወቅ 804 ደውዬ ሳነብ 0.11 ሳንቲም ብቻ ነው ያለኝ። ነገሩ ግራ አጋባኝ። አስደነገጠኝ። (ኦ…ማንበብ የማይችሉ ዓይኖች ምንኛ የታደሉ ናቸው? ምናምን ብዬም ጠይቄያለሁ….ሃሃሃ…ጋዜጣ ማንበብ ስለቻልን አይደል ከጌቶች ጋር ሌባና ፖሊስ የምንጫወተው?… እነሆ አዲስ ታይምስንም አቀለጧት!)

ሂሳቡ እንዴት እንዲህ ይወርዳል? ብዬ መልስ የሌለው ጥያቄዬን ጠየቅኩኝ። ወዲያው ግን እንደ መረጋጋት አድርጎኝ፤ የእነርሱንና የእኔን ሌላኛውን የልጅ፣ የጅል ያላዋቂ ጨዋታ አስታውሼ….ከዚህ በፊት ኢንተርኔት ስጠቀም አላግባብ የተቆረጠብኝ ሳንቲም መልሶ መጥቶልኝ ያውቃልና ካርድ ሳልሞላ ጠበቅኩት። (መቼም ነገሩ ቢያሳፍርም እንዲህ ተማምኖ መመላለሱም ተመስገን ነው። ….ግን ምናለ በማይነጥፈው የፅሁፍ ጭቅጭቃቸው እንዲህ ሲያጠፉ ‘ይቅርታ’ ምናምን የምትል ነገር አክለው ቢልኩልን ኖሮ? ወይ ደግሞ መቀጫ 1ነፃ SMS….ሃሃሃ…

ትናንትናማ ሲላብን አመሸ አይደል? Recharge &Get Free local Airtime/SMS!
– 100Br get 15Min,
– 50Br get 10Min,
– 25Br get 3Min,
– 15Br get 5SMS
From Feb.5 – Mar.5, 2013/Tir 28 – Yek.26, 2005. ቂቂቂ….
ወይ ኢትዮ ቴሌ፣… :-/

ቆይቼ ድጋሚ 804 ደውዬ የቀረኝን ሂሳብ አየሁት። ተረጋጋሁ…..ከፍ ብሏል….(አስራ ምናምን….ቦታው ይመስላል።) ግን ብዙ ጥያቄዎች መረጋጋቴን ተከትለው መጡ። እንግዲህ በመጨረሻው ዘመን መረጋጋትም በሽታ ነው….ብዙ መልስ የሌላቸውን ጥያቄዎች ያስከትላልና…..። በቀን ስንት ጊዜ አንዱን መልእክት እየደጋገሙ በመላክ የሚያሰለቹን ለምንድን ነው? አሃ….እርሱን ስናነብ ደክመን መፅሀፍ ምናምን እንዳናነብ ነው? …ሃሃሃሃ…..

[መጀመሪያ ሰሞን ‘ደንቆሮው ህዝቤ በ5 ዙር ምናምን ካልነገሩት አይገባውም ብለው ለእኛ አስበው ነው።’ ምናምን ብለን ለመፅናናት እንሞክር ነበረ።…..አሁን ሳስበው ግን የፅሁፍ መልእክቶቹን operate የሚያደርግ ህፃን ልጅ ሳይኖር አይቀርም። ያው ያንዱ ልጅ እየተጫወተ እንዲያገለግል….በሁለት ድንጋይ…ሄሄሄ… ምናምን ብለን ልንቀውጠው አልንና ‘ተውነው እንደገና።’ ለካስ በዚህ ረገድ ትልቅ መሻሻል አሳይተዋል።]

ደግሞ ቀሪ ሂሳብ ከ2ብር ሲያንስ “ያሎት ቀሪ ሂሳብ አነስተኛ ነው። እባክዎትን ተጨማሪ ካርድ ገዝተው ይጠቀሙ።” የሚለውን ደግ ማስፈራሪያ ለምን ይሆን የተዉት? (መቼም እዚህ አገር ደግ አይበረክትም….እንግዲህ እርሱም ድሮ ከቀሩት እሴቶች ተርታ መመደቡ ነው…. ልንል አልንና፣ ይሄንንም ‘ተውነው እንደገና’ አሁንማ አሻሽለውት ለፍተላ አልተመቸንም። ሃሃሃ… )

በፈለጉት ሰዓት ሳንቲም እየቆረጡ ቆይተው የሚልኩልን ለምንድን ነው? (ካርድ ማሻሻጫም ሊሆን ይችላል….ሃሃሃ….) ደግሞ ሳይልኩልን ቢቀሩስ? ያወጡትን ታሪፍ በአግባቡ ተጠቅመው እንደሚቆርጡብን በምን እናውቃለን? (መቼም አንድ በደወሉ ቁጥር ቀሪ ሂሳብን ማየት በመኪና ዘመን በአህያ እንደመሄድ ነው….ደግሞስ አግባብ ባይሆንስ ማን ይጠየቃል? ማን ይከሰሳል? ለማን ይከሰሳል?)

እኛና ኢትዮ ቴሌ እንዴት ነው የምንተማመነው? አንድ እነሱ ብቻ የቴሌኮም አገልግሎት በሚሰጡበት አገር ውስጥ ‘ሲም ካርድ በርካሽ ግዙ’ ምናምን ሲሉ አይደብራቸውም?…ልንል አልናና ይሄንንም ‘ተውነው እንደገና።’ ይሄ የፅሁፍ መቅረቱንም ልብ ይሏል። ደግሞስ ነጋዴውን ላንድ ዓይነት እቃ አንድ ዓይነት ንግድ ፈቃድ ምናምን ብለው ህግ ከጣፉለት በኋላ በጎን ቀፎ መሸጣቸውን ምን አመጣው? ….ብዙ ጥያቄዎች…..

ይህ በእንዲህ እንዳለም ልንል አልንና ‘ተውነው እንደገና’ ያልናቸውን ነጥቦች ስናስብ ከዚህ በፊት በየstatus updateኡ “ኡኡ…” የማለታችን ውጤት ሊሆን እንደሚችልም ተሰማንና የልብ ልብ ተሰማን። 🙂 አያይዘንም፥ ሲደብራቸው ሊሰሙን ይችላሉና መጮሃችንንም አናቋርጥም ስንል ለራሳችን ቃል ገባን። ህህህህ….

እኔ የምለው የአርማ ለውጡን ግን ምነው አዘገዩት? ወይስ እንዳያዳግም አድርገው ለመቀየር ነው? እንዲያ ከሆነ፥ በጄ!!

ጋሽ ተስፋዬ ለማ – ነፍስ ይማር!!

እኛም አለን ሙዚቃ፣
__ስሜት የሚያነቃ!
በገናችን — ♫ ♬♩ ♪ ♫ ♬
መሰንቆአችን — ♩ ♪ ♫ ♬ ♬
ክራራችን — ♩ ♪ ♫ ♬ ♫
ዋሽንታችን — ♩ ♫ ♬♩ ♫ ♬
እምቢልታችን — ♩ ♪ ♬♩ ♪ ♬…

የኢትዮጵያ ሬድዮ እንዲህ ሳይበላሽ በፊት፣ የባህል ሙዚቃዎች ምሽት መግቢያ የነበረው530849_322089074578799_1430219762_n ሙዚቃ የተስፋዬ ለማ ስራ ነበር። እንዲህ ብሎ ስለሙዚቃዎቻችን በሙዚቃ ያወራው ተስፋዬ፥ በተለይ የኢትዮጵያን ባህላዊ ሙዚቃ በማስተዋወቅ ረገድ ከተለያዩ የአገሪቱ ቦታዎችና ብሔሮች የተውጣጡ ከ30 በላይ አባላት በነበሩት “ኦርኬስትራ ኢትዮጵያ” ዳይሬክተርነት (3ኛው ዳይሬክተር በመሆን) የተጫወተው ሚና ጉልህ ነበር።

በጎ ፈቃደኛ በመሆን በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ (በቀድሞ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ዩኒቨርስቲ) እንግሊዘኛ ትምህርት ያስተምር የነበርውን ጀማሪ ሙዚቀኛ፥ አሜሪካዊው ቻርለስ ሳተንን ወደ ኦርኬስትራው በመደባለቅ ከኢትዮጵያ ሙዚቀኞች ጋር አስተዋውቆት፤…. በኋላም ከቻርለስ ጋር በመተባበር የኦርኬስትራ ኢትዮጵያ በአሜሪካ የኢትዮጵያን ባህላዊ ሙዚቃዎችን ይዞ “ብሉ ናይል ግሩፕ” በሚል ስም፥ ከ20 በላይ የአሜሪካ ከተሞች ዞሮ ያቀርብ ዘንድ ተስፋዬ የመሪነትና የአስተባባሪነት ስራ ሰርቷል።

በኋላም ኦርኬስትራ ኢትዮጵያ 2ሙሉ ስራዎችን አስቀርፆ አበርክቷል። (የአንደኛውን ባላውቅም አንደኛው በኢትዮፒክስ ቁጥር 23 ላይ ያለው መሆኑን ቀን ፋና ኤፍ ኤም የጣዕም ልኬት ላይ አድምጫለሁ።) ከዚህ በተጨማሪም ጋሽ ተስፋዬ ብዙ ሙዚቃዎችን ለብዙ ሙዚቀኞች ሰርቶ ሰጥቷል። ከብዙ በጥቂቱ፣ ጥላሁን ገሰሰ፣ ነዋይ ደበበ፣ ፀሀዬ ዮሐንስ፣ ኤልያስ ተባባል፣ ኤፍሬም ታምሩ፣ ይጠቀሳሉ። (እንዲያውም ፀሀዬና ነዋይን ችሎታቸውን ተገንዝቦ በራስ ቴአትር የሙዚቃ ባንድ እንዲታቀፉና ዘርፉን በይፋ እንዲቀላቀሉ ብዙው ጥረት የርሱ እንደነበር የጣዕም ልኬት ፕሮግራም ላይ ተዘግቧል። በዚህ ባለሞያን ፈልጎ ከሙዚቃው ጋር በማገናኘት ግብሩም በሚያውቁት ዘንድ ዘወትር ይመሰገናል።)

ጋሽ ተስፋዬ፥ በተለይ በድራማዊ ሙዚቃ ስራዎቹ የሚታወቅ ሲሆን፤ ብዙም ትኩረት የማይሰጣቸው ማህበራዊ ጉዳዮችንም በሙዚቃ በመስራት ረገድ ሚናው ትልቅ ነበር። እንደምሳሌ ለፀሀይ እንዳለ የሰራላትን “የህፃኑ ልጅ ለቅሶ” እና ለጥላሁን የሰራለትን “አንዳንድ ነገሮች”ና “አጉል ነው” ማንሳት ይቻላል፤ ከሙዚቃዊ ድራማዎቹ ደግሞ “ማሚቴና ከበደ” እና “ለቅዳሜ አጥቢያ” መጠቀስ ይችላሉ። ከዚህ ባሻገር ዛሬም ድረስ በተማሪዎች የምረቃ ባህል ላይ የምንጠቀምበትን የ“እንኳን ደስ አላችሁ” ህብረ-ዝማሬ ሰርቶ አበርክቷል።

እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር በ1980ዎቹ ተስፋዬ ወደ አሜሪካ በስደት ሄዶ፣ ቆይቶ73770_322089047912135_1438254975_n የኢትዮጵያን ሙዚቃ፣ ባህል፣ እና ጥበብ ከአሜሪካዎቹ ጋር ለማቆራኘት በማሰብ፥ የኢትዮ-አሜሪካን የባህል ማዕከል፣ የናይል ኢትዮጵያ ጥምረትና ተስፋ ሙዚየምን መስርቷል። በመካከል በገጠመው የጤና እክል ምክንያት እንቅስቃሴዎቹን እስኪገታ ድረስም ቀድሞ ኦርኬስትራ ኢትዮጵያ ሳለ ከሚተዋወቁ ሰዎች መሀል አራቱ – ተስፋዬ፣ ቻርልስ ሳተን፣ ጌታመሳይ እና መላኩ ገላው – ድጋሚ አሜሪካ ላይ ተገናኝተው በጋሽ ተስፋዬ ዳይሬክተርነት “ዞሮ ገጠም” (reunion) የሚል መጠሪያ ያለው የኢትዮጵያ የባህላዊ ሙዚቃዎች ስብስብ አልበም አስቀረፁ። አልበሙን “ዞሮ ገጠም” (reunion) በማለት የሰየሙትም፥ ዞረው መገናኘታቸውን ለመዘከር የነበረ ሲሆን፣ ከአልበሙ የተገኘው ገቢ በሙሉም ለ Institute of Ethiopian Studies (ለኢትዮጵያ ጥናቶች ተቋም) እንቅስቃሴዎች መርጃ አበርክተዋል።

ጋሽ ተስፋዬ ለማ በ2000 ዓ/ም Ethiopian Yellow Pages የተባለ ድርጅት ያዘጋጀውን ኢትዮጵያ ሚሊንየም የክብር ሽልማት ተሸላሚ እንደነበረም ይታወቃል። ከዚህ አስተዋፅኦው ባሻገር ጋሽ ተስፋዬ በኤትኖሙሲኮሎጂስትነት ደረጃ፥ የሙዚቃንና የዳንስን ህብረተሰባዊና ባህላዊ ባህርዮቻቸውን ሲያጠና ነበር። ኋላም ላይ ከቅርብ ወዳጁ ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ ሙዚቃ ላይ የሚያጠነጥን መፅሀፍ ፅፎ አበርክቷል። በነበረበት የጤና ቀውስ ምክንያት ለረዥም ጊዜ በህክምና ሲረዳ ቆይቶ በትናንትናው እለት (ጥር 24/2005 ዓ/ም) ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

የሚችልና ስለ ጋሽ ተስፋዬ ለማ አስተዋፅኦዎች በሰፊው ለማወቅ ያደረበት ቢኖር ከዚህ በፊት ከመዓዛ ብሩ ጋር በስልክ ያደረጉትን ቃለ መጠይቅ ነገ ምሽት ጨዋታ ፕሮግራም ላይ (ሲደገም) አልያም ከሸገር ኤፍ.ኤም. ማህደር ውስጥ አውርዶ ያዳምጥ ዘንድ እጋብዛለሁ።

ከተስፋዬ ግጥምና ዜማ ስራዎች ውስጥ የኤልያስ ተባባል “ማማዬ” እነሆ ተቀንጭቦ…

ኦሆሆሆሆ….
ከረጅም ማማ ላይ ጥንቅሽ የበላ ሰው፣
ከጎድጓዳ ስፍራ፣ ጠይም የሳመ ሰው፣
እንኳን ሽማግሌ፣ ዳኛም አይመልሰው፣ (2x)
ደጅ ጠናሁ፣ ደጅ ጠናሁ ከእንግዲህ ታከተኝ፣
የሆዷን ጠይቆ ማን ባሰናበተኝ?!

ማማዬ ማማዬ፣ ኧረ ነይ ማማዬ፣
ማማዬ ማማዬ፣ ሸጋ ልጅ ማማዬ፣
ማማዬ ማማዬ፣ ቆንጆ ልጅ ማማዬ፣

ዐይነ ኩሎ (?)፣ ሽንጠ ሎጋ የወለዱ እንደሆን፣
መልካም ፀባይ ያላት የወለዱ እንደሆን፣
እውቀት የምትሻ፣ የወለዱ እንደሆን፣
ታመጣለች አማች ብረት መዝጊያ ‘ሚሆን።

ማማዬ ማማዬ፣ ኧረ ነይ ማማዬ፣
ማማዬ ማማዬ፣ ሸጋ ልጅ ማማዬ፣
ማማዬ ማማዬ፣ ቆንጆ ልጅ ማማዬ

ነፍስ ይማር!!

መላ ብሎ ዝም!

አሁን ጠይም በረንዳ: ዘ ዮሐንስ ሞላ/ Chocolate Porch: Yohanes Molla’s ላይ መለስ ቀለስ በማለት ውሀ ልኩን፣ ስፋት ጥበቱን ቃኝተን ስናበቃ፣ ጨረቃን እያደነቅን ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። የምር ግን ጨረቃዋን ጠቅልሎ ይዞ ቤት መግባት ቢቻል እንዴት አሪፍ ነበር?! ኡኡቴ… ሲሉ ሰምተን! ሄሄሄ….
ዛሬ በወፍ በረር ኢቲቢ3 ላይ “መላ” የተሰኘ ፕሮግራም ተመልክተን ነበር። ‘በወፍ በረር’ ማለታችን ለወሬያችን ጥራት እርግጠኛ መሆን ስለማንችል ነው። እኔ ወሬው ጆሮዬ ሲገባ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች እየተወያዩ ነበር። የውይይቱ ርዕስ – “ፍቅር ያስፈልጋል አያስፈልግም?” የሚል ነበር።
እንግዲህ በሰላም ለመኖር፣ ትውልድ ለማስቀጠል መሰረታዊ ስለሆነው ፍቅር መላ ሊመታ ነው ውይይቱ የታለመው።…የተፈጠርንበትን ዓላማ (በተለይ ማንም ከወሰን በላይ ምድር ላይ ሊኖር ካለመቻሉ ጋር አነፃፅረነው) ስተው በማያፋጨው ሀሳብ አፋጩ። ከዚያም የአንድ ጉብል አስተያየት ባለፈው ስለቃላት ውርርስ ከፈተልነው ጋር ገጥሞ ጆሮዬን ያዘው፤ እንዲህ አለ…”በሰው ልጆች ህይወት ውስጥ ፍቅር የአንበሳውን ድርሻ ይይዛል!”…እኔም በሆዴ “አንበሳ ይብላህ!”!! ሃሃሃ…

ቸር ቸሩን ያሰማን አቦ!!

** የሰፈሩ አሉባልታ…. (የዛሬ ዓመት ገደማ የሰማሁት)

ካሚላትና ደምሰው አገር ምድር፣ ወዳጅ ቤተሰብ የሚያውቃቸው የፍቅር ጓደኛሞች በነበሩበት ወቅት እሷ “ኧከሌ” ከሚባል ‘አፈቀርኩሽ’ ብሎ ይጨቀጭቃት ከነበረ ነጋዴ ሰው ጋር የሆነ ዓይነት ግንኙነት ጀመረች። …አሉ። ግንኙነቱ በገንዘብ (በሌላ ጥቅም) የተሳሰረ ነበረ።…አሉ። እርሷ ከሰውዬው ጋር ያንን ነገር ስታስብና ስትጀምር በወቅቱ ከሰውየው የምታገኘውን የገንዘብ ጥቅም በማሰብ ነበረ።…አሉ። ኧከሌውም ስለፍቅረኛዋ ደምሰው መኖርና በይፋ መዋደዳቸውን ያውቅ ነበርና በ“ባንዘልቅ እንኳን አብረን እንደር” ወግ ነበር የገባበት።…አሉ።

ከዚያ ግን አንዴ የሚፈልገውን ካደረገና የምትፈልገውን ካደረገላት በኋላ አመረረ። ፍቅር ያልቅ ይመስል “አስጨርሺኝ”… “አብረን ካልኖርን ሞቼ እገኛለሁ። ያዙኝ ልቀቁኝ።” አለ፤. . . አሉ። ካሚላት ደግሞ ከወዳጇ ከደምሰው ጋር ያላት ግንኙነት በወዳጅ ዘመድ ዘንድ የሚታወቅ ነበርና እርሱን የመካዱ ነገር ፍፁም ስላልተዋጠላትና ማህበራዊ ገፅታዋን እንዳያበላሽባት ስለፈራች ‘ኡኡ አሻፈረኝ’ አለች።…አሉ። ከዚያ ብሩን እንድትመልስለት ጠየቃትና እንደሌላት ነገረችው።…አሉ። እንዳሉት ከሆነ፥ በዚህ ብስጭት ነበር አፍቃሪው ሰዎች ቀጥሮ አሲድ ፊቷ ላይ እንዲደፋባት ያደረገው። [አሉባልታውን ጥቂት ገታ እናድርገውና የሆነውን ደግሞ እናውራ…]

** አሲዱ የተደፋባት ሰሞን ከሚዲያዎች የሰማሁት….

ከተደፋባት በኋላም ወሬው ጉድ ተብሎ ሲቀባበል ቆይቶ በሚዲያዎች ቀርባ ስትጠየቅ አሲዱን የደፋባት ፍቅረኛዋ ደምሰው መሆኑን መሰከረች። ቤተሰቦቿም መሰከሩ። ሁኔታዎችን እያቀናበሩና እየዘረዘሩ ተነተኑት።….በሌላው ወገን ደግሞ ደምሰውና ዘመዶቹ (በተለይ ምስኪን እናቱ) እላይ ታች እያሉ ተከራከሩ። “እግዚአብሔር ይፍረድ” ብለው ተሟገቱ። አለቀሱ። ኗሪውም ግራ ገብቶት ሀሳቡና ፍርዱ ለሁለት ተከፈለ። ምንም ጠብ ሳይልላቸው ደምሰው ላይ የሞት ፍርድ ተፈረደበት ተባለ።

አንዳንድ ትልልቆች “እሰይ! የታባቱ! እንዲህ ልኩን አስገብቶ መቀጣጫ ማድረግ ነው እንጂ።” ሲል ነገሩን አከባበዱት። ሌሎች ትልልቆች ደግሞ የነገሩን ጭምጭምታ አውቃለሁ በሚል (ወይም ሰምተው ኖሮ) “ምስኪን የእኔ ጌታ… ባላደረገበት ከሆነ ግን ያሳዝናል። ቸኩለው ባይፈፅሙ ምናለ? ኧረ የድሀ አምላክ…” ምናምን እያሉ ክፉኛ አዘኑ። ህፃናትም ከሁለተኞቹ ወገኖች አሉባልታውን ቃርመው ኖሮ በR-Kelly “burn it up” ዜማ ከጣሪያ በላይ እየጮሁ ተጫወቱ… — “ካሚላት… ባሏን ስትከዳው አሲድ ደፋባት” እያሉ። ትልልቆቹም ነገሩን እነሱ እንዳላመጡት ሁሉ መልሰው ተቆጧቸው። አፋፋቸውን አሏቸው። “ጡር ነው” በእንዲህ ያለ ነገር አይቀለድም ብለው ቆነጠጧቸው።

ሁሉም እርሱን እየተቀባበለ የፍርዱን ፍፃሜ ለመስማት ቸኮለ። መቼስ እኛ ነገር ጉዳይ የሚፈፀመው ተዘንቦ ተባርቆ ስለሆነ (እንዲህ ባለ ጊዜ ጥሩም ነው) ፍርዱ ወዲያው አልተፈፀመበትም። እርሱም ይግባኝ ጠይቆ በክርክር ፍርድቤቱ ፍርዱን አቀለለት። አቃቤ ህግ በተራው ይግባኝ ጠይቆ ፍርዱን አከበደበት። ….20 ዓመት።…. ከዚያ ደግሞ መልሶ እድሜ ልክ። – ለእናቱ ሁለቱም እኩል ነበር።

** አሉባልታውን እንቀጥል….

ሲኖሩ ሲኖሩ፣ ከለዕታት ባ’ንዱ ቀን ተደራቢው አፍቃሪ በገንዘብ ምክንያት ምስጢሩን ከሚያውቁ ወዳጆቹ ጋር ከፍተኛ ጠብ ውስጥ ገቡ።…አሉ። ከዚያ በኋላ ደካማ ጎኑን ጠብቀው ሲያጠቁት “እንደውም ይሄን የማታስተካክል ከሆነ ካሚላት ላይ አሲድ ያስደፋህባት አንተ መሆንህን ለፖሊስ እንናገራለን።” አሉት።… አሉ። እርሱም ደንብሮ ነገሩን በሰላም ፈቱት።….አሉ። ግና በአካባቢው ጆሮ ጠቢ ነበርና ነገሩን ሄዶ ለእናትየው ሹክ አላቸው።… አሉ። እናትየውም ለፖሊስ። የሰፈሩ ሰው ደግሞ በስማ በለው ላልሰማ። ወሬው ሰፈር ለሰፈር ሲቀባበል ደርሶን ጉድ አልን። ያኔ በሀዘኔታ በየፊናቸው ሲሟገቱለት የነበሩት የአሸናፊነት ስሜት ተሰማቸው። ጉድ አንድ ሰሞን ነውና ሳምንት ሳይሞላ ወሬው ተረሳ።
(እንግዲህ ከላይ ያለው ሁሉ “አሉ” ነው።)

** በትናንትናው እለት ደግሞ የአዲስ አድማስ ጋዜጣን ዋቢ አድርጎ www.amharictube.com የተባለ ድህረገፅ እንዲህ ዘገበ….

“በካሚላት አህመዲን ላይ አሲድ ደፍቷል በመባል የተከሰሰው እና የዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ደምሰው ድርጊቱን እንዳልፈፀመና “የፈፀምነው እኛ ነን” ያሉ ወጣቶች ሰሞኑን ለፖሊስ ቃል መስጠታቸውን ምንጮች ጠቆሙ። ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት የፍቅር ጓደኛው በሆነችው ካሚላት ላይ የአሲድ ጥቃት ማድረሱ በሰው ምስክርና በማስረጃ ተረጋግጧል ተብሎ የተከሰሰው ደምሰው፣ ጉዳዩን እንዳልፈፀመ በመናገር ቢከራከርም በሰውና በሰነድ ማስረጃዎች ተረጋግጧል በማለት ፍ/ቤት በሞት እንዲቀጣ ወስኖ ነበር።

ተከሳሽ ይግባኝ ጠይቆ ቅጣቱ ወደ 20 ዓመት ዝቅ ብሎለት የነበረ ቢሆንም ዐቃቤ ሕግ እና የሕግ ባለሞያ ሴቶች ማኅበር ይግባኝ በማለት ተከሳሹ የዕድሜ ልክ እስራት እንዲቀጣ መወሰኑ ይታወቃል። ከስድስት ዓመታት በኋላ ሰሞኑን “ድርጊቱን እኛ ነን የፈፀምነው” ያሉ ግለሰቦች መገኘታቸውን የተከሳሹ ወላጅ እናት ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን መጠቆማቸውን የሚናገሩት ምንጮች፤ የተባሉት ሦስት ወጣቶች ጫት ቤት ተቀምጠው የፈፀሙትን ድርጊት እያነሱ ሲያወሩ የሰሙ ሰዎች፣ ለተከሳሽ ቤተሰብ በመንገር ጉዳዩ ክትትል እንዲደረግበት ጥቆማ መስጠቱን ገልፀዋል።

የተባሉት ወጣቶችም ተይዘው በሰጡት ቃል፣ ድርጊቱን መፈፀማቸውን አምነው ቃላቸውን መስጠታቸውን እና ትላንት ደምሰው ከማረሚያ ቤት ወጥቶ በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ቃሉን ሰጥቶ መመለሱን ምንጮቻችን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጉዳዩን እያጣራ በመሆኑ መረጃ ለመስጠት እንደማይችል ገልፆልናል።”

** Moral of the story – in line with the አሉባልታ and z facts! – in my opinion!

1. አትስረቅ። (ከ10ቱ ትዕዛዛት አንዱ)
2. አታመንዝር። (ከ10ቱ ትዕዛዛት አንዱ)
3. በሀሰት አትማል እንዲሁም አትመስክር።(ከ10ቱ ትዕዛዛት አንዱ)
4. የባልንጀራህን ቤት አትመኝ የባልንጀራህን ሚስት ሎሌውንም ገረዱንም በሬውንም አህያውንም ከባልንጀራህ ገንዘብ ሁሉ ማናቸውንም አትመኝ። (ከ10ቱ ትዕዛዛት አንዱ)
5. በነገሮች ሁሉ ችኩል አትሁን።
6. አትበቀል። ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ። (ከ10ቱ ትዕዛዛት አንዱ)
7. ፍርድህ ሁሉ በጥንቃቄ ይሁን።
8. አትግደል። (ከ10ቱ ትዕዛዛት አንዱ)
(በበኩሌ ባልሰሩት ወንጀል እንዲህ መንገላታት ከሞትም የሚከብድ ከባድ ቅጣት ነው። 6 ዓመት አይደለም 6 ቀን እስርቤት ውስጥ መቆየትን ምንም እንደማያካክሰው አውቃለሁ።
9. ምናልባት ማረሚያ ቤት ውስጥ ያሉ ታራሚዎች በሙሉ በሰሩት ወንጀል ላይሆን ይችላልና ነገሩ ይጣራ። ፍርድ ሲሰጥም በጥንቃቄ ይሁን።
10. አሁንም ነገሩ ቶሎ እልባት ያግኝና ነፁህው ሰው ይለቀቅ። ጥፋተኛውም ባለው ሀይልና አቅም ሳይሆን በሰራው ስራ ተመዝኖ ይቀጣ።
11. ‘እውነትና ንጋት እያደር ይጠራል።’
12. እግዚአብሔር እውነተኛ ዳኛ ነው።
13. ሌላም ሌላም….

ቸር ቸሩን ያሰማን አቦ!!