ከገጠር ወደ ከተማ የሚሰደዱ ስሞች…

ስም መጠሪያ ነው። – አንዱን ከአንዱ መለያ! አፍ ላይ ቀለለ፥ ከበደ፤… ጣፈጠ አልጣፈጠ፥ ያው መጠሪያ ነውና በስም አንቀልድም። ይህንንም የምጭረው የማንም ስም ላይ ለማሽሟጠጥ (ወይም እንዲያሽሟጥጡ በር ለመክፈት)፣ አንዱን ከአንዱ ለማለካካትና ለማበላለጥ… ወይም በሌላ የተለየ ምክንያት ሳይሆን፥ አሁን ስላለው ነባራዊ ሁኔታ በቀለለኝ መልኩ ለመጫወት በማሰብ ነው። ይህን ከገለፅሁ ዘንዳ ጨዋታዬን ልቀጥል…
*
*
*
ብዙ ጊዜና ብዙ ቦታ ለሰው ልጆች ስም ሲወጣ እንዲሁ ዝም ብሎ አይደለም። በሆነ ዓይነት ምክንያትና ፍላጎት እንጂ! በማውቀው ልክ (በብዛት ካስተዋልዃቸው መካከል) የስም አወጣጥ/አመጣጥ ምክንያቶችን ልከፋፍላቸው ብል፤… በጣም ውድ (ብርቅ) በሆነ ነገር መሰየም፤ ለምሳሌ: – አልማዝ፣ እንቁ፣ ወርቅነሽ፣ ብርቄ፣ ብርነሽ፣….፥ ለአፍና ለአጠራር በሚጣፍጥ ቃል መሰየም — ትርጉሙን አወቁትም አላወቁትም! (ይሄ በማደግ ላይ ያሉ ከተማዎች ውስጥ ይዘወተራል።)፤…

ልጅ የተወለደ ሰሞን በሚፈጠር ህብረተሰባዊ ክስተት መሰረት መሰየም፤ ለምሳሌ: – ደርጉ፣ ነፃነት፣ አብዮት፣ ህዳሴ፣ ግድቡ፣ አባይ፣ ድሌ፣ ፋሲካ፣ ገና፣….፥ በአንድ ገናና ወቅታዊ ጉዳይ ወይም ግለሰብ ስም መሰየም፥ ለምሳሌ: አብዮት፣ ሉሲ፣ ሚሊኒየም፣ ዚዳን፣ ኦባማ፣….፥ ምኞትን፣ ተስፋን ወይም ፍላጎትን ለማንፀባረቅ በማሰብ መሰየም፤ ለምሳሌ: – ተስፋዬ፣ ይልቃል፣ ስንሻው፣ አንሙት፣ ፍላጎት፣ ደምመላሽ፣ ማለፊያ፣ ሰላም፣ ይበልጣል፣….

ፅድቅና መንግስትን በማሰብ፤ ለምሳሌ: – ቸርነት፣ ምህረት፣ ፃድቁ….፥ ለማመስገን፤ ለምሳሌ: – ምስጋና፣ ስጦታ፣ ፀጋ፣ እድላዊት፣….፥ ልጁ እስከተወለደበት ጊዜ ድረስ የነበረን ተድላም ሆነ ውጣ ውረድ ጠቅለል አድርጎ ለማስቀመጥ በማሰብ፤ ለምሳሌ: – ሙሉቀን፣ ስንታየሁ፣ ብዙአየሁ፣ ምንታምር፣ ነጋ….፥ ከኑሮ ጋር የሚደረግን ግብግብና ሁኔታውን ለመግለፅ በመፈለግ፤ ለምሳሌ: – በርታ፣ ጠንክር፣ አንሙት፣….፥ ቅዱስ መፅሐፍትን በማጣቀስ፤….

በእዚያ አካባቢ በሚመጡ እንግዶች ስም መሰየም (ለምሳሌ: – እኔ በምሰራበት አካባቢ ዶክተር የሚባል ልጅ ነበረ። ገርሞኝ ምክንያቱን ስጠይቅ እርሱ በተወለደበት ጊዜ ዶ/ር ገዛኸኝ የሚባሉ ሰው እዚያ አካባቢ ስለነበሩ ነው። እዚህ ጋር ፈገግታ የሚያጭረው “ዶክተር” እንደማዕረግ ስም ሳይሆን እንደ መጀመሪያ (መጠሪያ) ስም መወሰዱ ነው።)፤…. ወይም ሌሎች ብዙ ምክንያቶችን ተንተርሶ ስም ይወጣል።
*
*
*
ዛሬ መጫወት ያማረኝ ግን በጣም ውድ (ብርቅ) በሆኑ ነገሮች ላይ ተመርኩዘው (በሌላ ምክንያት ሳይሆን፥ ብርቅነታቸው ተወድዶ ብቻ) ስለሚሰጡ ስያሜዎች ነው። እንደሚታወቀው ውድነትና ብርቅነት፥ ብዙ ጊዜ፥… በተዘዋዋሪ ከገቢና አቅርቦት ጋር ይያያዛል። ወርቅ ውድ የሚሆነው ወርቅ እንደልብ በሌለበት ነው። ብር ውድ የሚሆነው ብር እንደልብ በሌለበት ነው።… ወይም ደግሞ የቁሶቹ ተፈላጊነት ከፍተኛ በሆነበት ቦታና ሁኔታ ነው።

የልብን ፍላጎት ለማሟላት ወይም የሚወዱትንና የሚሳሱለትን ልጅ — “እንደዚያ ውድ ነገር የከበርክ/ሽ” ለማለት ስያሜው ሊወረስ ይችላል። በዚህ አካሄድ አስበነውም፥ የሆኑ ዓይነት ስሞች ከገጠር ወደ ከተማ ሊሰደዱ እንደሚችሉ መገመትና መጫወት እንችላለን። …. ከገጠር ተሰድደው መምጣት ብቻ ሳይሆን እንደ አዲስ የሚወለዱትንም መጠርጠር ይቻላል።
ለምሳሌ: – ድሮ መብራት ብርቅ በነበረበት ዘመን፥ የከተማው የመብራት መስፋፋት ወሬ ወደ ገጠሩ ሲዛመት፥… ልጅን በውዱ መብራት ስም “መብራቱ፣ መብራቴ፣ መብራት ነሽ፣ አበራሽ፣ ፋኖሴ፣ ማሾ….” እየተባለ ይሰየም ነበር።

አበው ወእመው፥ “መልከ ጥፉ በስም ይደግፉ” እንዲሉ በሁኔታዎች የጎደሉ ነገሮችን በስያሜ ይሞላሉ። በዚህ ረገድ ብዙ ነገሮችን ማንሳት ይቻላል።ራሱ “ከተማ” ብሎ ስም፥ ሰያሚዎቹ ለከተማ የሰጡትን ነገር ሊያሳየን ይችላል። ዛሬ ግን ከተማው ውስጥ በየጊዜው በሚታየው የመብራት መጥፋት ችግር ምክንያት እነ ”አበራሽ፣ መብራቴ፣ መብራት ነሽ፣ ፋኖሴ፣ ማሾ….” ከተማ ውስጥ ለሚወለዱ ልጆች …የነገሩን ብርቅ ድንቅነት በማድነቅ ብቻ ተወስኖ… መሰጠት ይጀምሩ ይሆናል። ከውኀ ጋር በተያያዘም እነ “ውሃ ወርቅ” ወደ ከተማ መጥተው ለሚወለዱ ልጆች ስያሜ ይሆናሉ።

የድሮ ባላባት መውዜርና ምንሽሩን ይወለውል እንደነበር፥ የዛሬ የከተማ እመቤትና ጌቶች ለውሃ መቅጃ እቃዎቻቸው የሚያሳዩት እንክብካቤ ሲታይ፥…. ምናልባት ወደፊት “ቧንቧዬ፣ ባልዲዬ፣ መቅጃዬ፣ ሃይላንዷ፣ ጀሪካን፣ ለገዳዲ፣….” እየተባለ እንዳስፈላጊነቱ ሌሎች ውድ ስሞች ከውድ ልጆች መወለድ ጋር ሊወለዱ እንደሚችሉ ያስጠረጥራል።

“ንፁህ” ም ከጠፋበት ይገኝና እንዳዲስ ያገለግል ይሆናል። እነ “ጥም ቆራጭ” የሚሉ ስሞችም ይወለዱ ይሆናል። ….ከስልክ አገልግሎት መስፋፋት ጋር የተሰጡ ስሞች መኖራቸውን ከዚህ ቀደም ሰምቼ ባላውቅም፣ ነገሩ አሁን ባለው ሁኔታ ከቀጠለ ግን “ኔትወርኬ” የሚል ስም በቅርቡ በሽ እንደሚሆን እንጠረጥራለን። 🙂

ያው ጨዋታ ነው! – ግን ብሶት ወለድ ጨዋታ!

በገጠርና በከተማ መካከል ግን ከመልክአ ምድራዊ አቀማመጥ ውጭ ምንም ልዩነት እንዳይኖር አገልግሎቶች በጥራትና በብዛት ይሟሉ ዘንድ እንማፀናለን!

እስኪ እናንተም ጨዋታውን ቀጥሉበት… አርብም አይደል?! 😉

መልካም የእረፍት ቀናት!

 

 

 

 

 

 

 

“የብርሃን ልክፍት”ን ለመግዛት (ለማዘዝ) ከታች ያለውን ይጫኑ።

Buy Now Button with Credit Cards

ሰርግና ሙዚቃው

“ሙዚቃ እያሰሙ ገደል ይከቱታል።” የምባል ዓይነት ነኝ። ከየትኛውም ዓይነት ሙዚቃ ጋር መንፈሴን ልክክ አድርጌ ሌላውን ነገርና አካባቢዬን መርሳት እችላለሁ። ልክ የብርሃን ልክፍት መፅሐፍ ላይ ገፅ 60 ላይ በ“ፍቅሬ ሙዚቃዬ” እንዳልነው ዓይነት መሆኑ ነው….

“ሀገር ቢደባለቅ፣ ቢዘነብ ቢባረቅ፣
ቢተኮስ ቢደለቅ፣ ቢነጠፍ ቢወደቅ፣
ቢበተን ቢሰፋ፣ ቢወረቅ ቢጨረቅ፣
ቢከፈት ቢገለጥ፣ ቢቀበር ቢደበቅ፣
ቢታረስ ቢዘራ፣ ቢታጨድ ቢወቃ፣
ቢታዘል ቢታቀፍ፣ ቢጎሸም ቢደቃ፣
ውድሽ መች ልሰማ?!”

/ዮሐንስ ሞላ – የብርሃን ልክፍት ከገፅ 60 ላይ የተቀነጨበ/

በዚያም የተነሳ ይመስላል፥…. በስምና በመደብ ዓይነት መተንተኑን ባልካንም፥ ራሴን ደስ በሚያሰኘኝና ደረቴን በራሴ ፊት በሚያስገለብጠኝ (በሚያስናፋኝ) ልክ ሙዚቃ እንደምረዳም አምናለሁ። ሄሄሄ…. “ሁን” ተብዬ ተማክሬ ባውቅ ኖሮ “ሙዚቀኛ” ነበር የምለውና የምሆነው። በርግጠኝነት “ይህን በሆንኩ ኖሮ” ብዬ በማስብበት የትኛውም ቅፅበትም “ሙዚቀኛ በሆንኩ ኖሮ” ማለቴ ቀዳሚውን ስፍራ ይይዝብኛል።…

ቢቀዳ ቢደፋ፣ ቢታረድ ቢበላ፣
ቢበጠር ቢነጠር፣ ቢሰጣ ቢቆላ፣
ቢሰባበር ባላ፣ ቢፈራርስ ገላ፣
ሕዝባ’ዳም ቢሸበር፣ ቢታመስ ከተማ፣
ሺህ ቢወድቅ ቢገደል፤ ቢቆስል ቢደማ፤
ሀገር ቢበረበር፣ ቢወረር ባድማ፤
ውድሽ መች ልሰማ?!”

/ዮሐንስ ሞላ – ላይ ከተቀነጨበው የቀጠለ/

አሁንም ቢሆን እንደ ኃይለኛ ህልም ውስጥ ገብቼ ምናምን ሳስብ …ራሴን የሆነ ጊዜ ላይ፣ የሆነ ቦታ ላይ፣ የሆነ ዓይነት ሙዚቃ ራሴን ችዬ ስጫወት አየውና ሳቅ ያፍነኛል፤ ደግሞ ጊታር ነው የምጫወተው… የምጫወተው ለህዝብ ይሁን ለራሴ እንደሆነ ሳልለይ ግን ህልሙ እልቅ ይልና ብንን እላለሁ። ስለሙዚቃ ሌላ ጊዜ እንጫወታለን፥ ዛሬ ግን ወደ አሰብኩት “የሰርግ ሙዚቃ” ወሬ ላሽ ልበል።

የሰርግ ሙዚቃ

ሰርግ አልወድም። የሰርግ ሙዚቃ ስሰማ ግን በሆነ ርቀት ልክ ከፍ እላለሁ።13792785-wedding-picture-bride-and-groom-in-love የሆነ ነገር መጥቶ ውርር ያደርገኝና ልቤን ያሳክከኛል። ወደ ሆነ የማላውቀው ቦታ ይወስደኝና ይመልሰኛል። ከዚያ ስመለስ ደግሞ ወደ ሆነ በትንሹ የምፈራው ቦታ ያደርሰኛል። የምፈራው ስለማላውቀው ነው። አብሮኝ የሚጓዘውን ሰው ምንነትና ከየትነት መንገር ስለማልችል ነው። ግን ያው ሲለመድ ይረሳል። ሙዚቃውም እየበረታ ሲሄድ ነገር ዓለሙን ያዘነጋልና ፍርሃቱም እንግድነቱም ቅፅበታዊ ነው።

ልጅ እያለሁ ከሰፈር ርቄ ወደ ማላውቀው ቦታ ከጠፋሁባቸው ምክንያቶች ከሌላ ሰፈር የሚመጣን የሰርግ ሙዚቃ ተከትሎ መሄድ— ይገኝበታል። ከአንዴም ሁለት ሶስት ጊዜ የሰርግ ሙዚቃ ተከትዬ ጠፍቼ አውቃለሁ። (ሙሾ ተከትዬም ጠፍቼ አውቃለሁ። እርሱን ሌላ ጊዜ እንጫወት ይሆናል።) ሰፈር ውስጥ ሰርግ ካለ ከጓደኞቼ ጋር ደጃፉ ላይ ነበር የማመሸውና ቤት ደስ አይላቸውም። ባይላቸውም ግን እየተቆጣሁም ቢሆን ሄጄ አመሻለሁ። ….ልቀላውጥ! ምግብ አይደለም… የሰርግ ሙዚቃ ልቀላውጥ!

ልቤ “ውድሽ መች ልሰማ?” ማለቱን ይቀጥላል!– በኩራት ከፍ ብሎ!

ሙዚቃውም ቀጥሏል…..

“ዲን ዲን ዲሪሪን
ዲን ዲን ዲሪሪን….
የወይን አበባዬ፣ የወይን፣
የወይን አበባዬ፣ የወይን፣
እኛም ወደናል ትሁን።”

አፅዳቂና ፈቃጅም አለ ማለት ነው። ግን ባይወዱ ኖሮስ….?! ውዷ መች ሊሰማ?!

“ሙሽሪት ባንድ አልጋ፣
ሙሽራው ባንድ አልጋ፣
መልአክ ይመስላሉ፥
ክንፉን የዘረጋ።….”

ከሙዚቃው ጋር ልቤ ቅልጥ ይልና፣ ሊቀየር ጋብ ሲል ልቤ ይጠይቃል። “ለምን በአንድ አልጋ በአንድ አልጋ ይሆናሉ? ሰርግ አይደል እንዴ? ክንፋቸውን የዘረጉ የሚመስለው አብረው ለመሆን ስላኮበኮቡ ነው? ለምን ጊዜ ይገድላሉ?….አብረው አይተኙምና ክንፉን የሰበሰበ መልአክ አይመስሉም?” ምናምን ምናምን…..

“አናስገባም ሰርገኛ፣
እደጅ ይተኛ….”

የሚለውን ሲሰማማ ልቤ በሳቅ ይፈርሳል። ማጨብጨቡን ትቶ ይበሳጫል። “ምን ያካብዳሉ?….ለምን ያስመስላሉ?“ ምናምን እያለ ብቻውን ይቆዝማል። ኧረ እንዲያውም ልጅ እያሁ “አናስገባም” የሚል ግጥም ፅፌ ነበር። (በኋላ ማስታወሻ ደብተሬን ፈልጌ እከልማትና፥ ብቻዬን እስቃለሁ።)

ሙዚቃው ቀጥሏል….

የሰርግ ሙዚቃ እውነተኛ ዳኛ ነገርም ይመስለኛል። “ማነሽ ባለተራ?” እያለ ሁሏንም እኩል ያንቆላጵሳል። ባለተራ የሆነችውን ሁሉ በውዳሴ ያቀላልጣል። ሚዜ አይቀረው፣ ቤተሰብ አይቀረው… ጎረቤትና ጓደኛ አይቀረው… አማረች አላማረች ጉዳዩ አይደለም። ወፍራም ብትሆንም ”ችብ አይሞላም ወገቧ“ ይባልላታል። እናቷ ፈትለው ባያውቁም ”እናቷ ፈታይ እንዝርት ሰባቂ“ ይባልላታል።…. ዓለሟ ነዋ!

“ዓለምሽ ዛሬ ነው ዛሬ፣
እቴ ሸንኮሬ….”

እያለ ማቀላለጥ ነው። እህ…. የራስ ዓለም ከሆነ ማን ምን ሊያገባው? ኧረ ማንም! የሰርግ ዘፈኖቹ ይውረዱ፣ እኛም ከአልጋችን እንውረድ። ዛሬ የሁለት ከባባድ ወዳጆች ሰርግ አለብኝ!
.
.
.

“ኦሆ… የቤተ ዘመዱ፥
ይታያል ጉዱ!
ኦሆ… ዘመድ ነን ያላችሁ፣
እስኪ እንያችሁ!
ኦሆ… ጓደኛን ያላችሁ፣
እስኪ እንያችሁ!

እስክስ… እስክስ…
እንዲህ… እንዲያ…
.
.
አይፈራም ጋሜ አይፈራም፣
ወገብሽ ልክ አይሰራም፤”

ሠናይ ቀዳሚት!

የብርሃን ልክፍትን ለመግዛት ከታች ይጫኑ።

Buy Now Button with Credit Cards

የብርሃን ልክፍት መግቢያ

xhfanበወዳጆች ጥያቄ መሰረት…

.

.

በእኔ ልምድና መረዳት፥… የራስን ስሜት በመንከባከብ ሰበብ፥ የጻፏቸውን ግጥሞች፥ የሆነ ዓይነት ደረጃ እንዲኖራቸው ተጨንቆና፣ ከሰዎች ጋር ተማክሮ፥ በመጽሐፍ መሰብሰቡ… በተለይ፥ ከመጻፉ ጋር ሲነፃፀር እጅግ አድካሚ ነው።

ምንም ሆኑ ምን፥ የገጣሚው እፎይታ ግጥሞቹን ሲጽፋቸውና ውስጡ የሚመላለሰውን ሐሳብ ችሎ ወረቀት ላይ አስፍሮ ሲገላገለው ነው። — መሰለኝ። ከዚያ በኋላ ደግሞ፥ የጻፋቸውን ግጥሞች ከማኅበረሰቡ ጋር ለመደባለቅ በማሰብ ሌላ መንገድ ይጀምርና፥ በጊዜ ሲዘልቀው ዳግም ‘እፎይ’ ይላል። አሁን ለእኔ እንደዚያ ሆኖልኛል።

እውነት ነው… ደረጃቸው ምንም ሆነ ምን፥ ግጥሞቹን ስጽፍ ከነበረኝ ድካም ይልቅ… በመጽሐፍ መልክ እንዲሰበሰቡ ለመወሰን ሳንገራግር፣‘ይሁኑ’ ያልኋቸውን ስመርጥ፣ መመጠን አለመመጠናቸውን ለመረዳት ስመረምር፣ ከወዳጆች ጋር ስማከርና፣ በመጽሐፍ እንዲሆኑ ሳዘጋጅ የበለጠውን ደክሜያለሁ።

ግጥሞቹን ስጽፋቸው ከፈጀሁት ጊዜም በላይ፥ ስለ መጽሐፍ ሳስብና ይህንን መጽሐፍ ሳዘጋጅ ፈጅቼያለሁ። “ምነው ማሳተም ባልኖረና ባልጀመርሁት!” ያልሁበት ጊዜማ ብዛቱ!… ከአድካሚነቱ አንጻርም መጽሐፍ የማሳተም ሐሳቡን ሽሽት “ኧረ ምነው መጻፍ ባልወደድሁ ኖሮ!” አለማለቴም አንድ ነገር ነው።… ያም ሆነ ይህ ግን፥ ሁሉም ዘርፉንና አንባቢን ከማክበር የመጣ ነውና፥ ሲጀመር እንዳልነበረው ሲታለፍ ደስ ይላል።

የሆነው ሆኖ… በወዳጆች ግፊትና፣ የግጥም ሥራዎቹ ‘ለዘርፉ አስተዋፅኦ ቢያደርጉ’ በሚል የራስ ፍላጎት የተነሳ ይህን መጽሐፍ ለማዘጋጀት ከወሰንሁኝ (ከራሴ ጋር ከተስማማሁኝ) ከአንድ ዓመት በላይ ሆኖኝ ነበር።ከዚያም፥ አንዱን ሳነሳ ስጥል፣ ስሰርዝ ስደልዝ፣ ስጨምር ስቀንስ፣ ‘እንደዚህ ይሁን እንደዚያ’ ስል፥… ዛሬ ላይ ደርሼ፥ “ይመጥናሉ” ያልኋቸውን ሰብስቤ “ይሆናል” ባልሁት አቀራረብ “የብርሃን ልክፍት”ን አዘጋጅቼአለሁ።

እውነቱን ለመናገር፥ መጽሐፉን ለማሳተም ወስኜ ዝግጅቱን ስጀምረው… “ከእኔ ይውጣልኝና ልገላገል”… “ዘወትር መጽሐፍ እንዳሳትም የሚገፋፉኝን ወዳጆቼን ላስደስትና ጥያቄያቸውን በትህትና ልመልስ”… “መጻፌ ካልቀረ፥ መጽሐፍ ቢኖረኝስ?”… ምናምን ከሚል ተራ ስሜትና ሞቅታ ሳይሆን፤ ለሥነ – ጽሁፍ ዘርፍ ሊሰጠው የሚገባውን ክብር ለመረዳትና ለመጠበቅ በመጣር ነበር።

ያም ሆነ ይህ ግን፥ ይህ የግጥም ስብስብ መጽሐፍ የመጀመሪያ ሙከራዬ እንደመሆኑ መጠን፥ በአንባቢዎች ገንቢ አስተያየት፤ እንዲሁም በተሻለ የንባብና የኑሮ ልምድ ቢታገዝ፥ ቀጣይ ሥራዬ የተሻለ እንደሚሆንና እንደሚዳብር አምናለሁ። ስለሆነም ግጥሞቹን አንብባችሁ ‘እንዲህ ቢሆን… እንዲያ ባይሆን…’ የምትሉት ማንኛውም አስተያየት ቢኖርና ብታደርሱኝ ለእኔም ለዘርፉም መልካም ነውና… አደራ።

ዮሐንስ ሞላ

2005 ዓ/ም

ለመግዛት (ለማዘዝ) ከታች ይጫኑ።

Buy Now Button with Credit Cards

የብርሃን ልክፍት…

6742_10152813933260215_131275700_n

ሐሙስ ግንቦት 8/2005 ዓ/ም ከቀኑ 11:00 ሰዓት ጀምሮ፥ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ “የብርሃን ልክፍት” የተሰኘው የዮሐንስ ሞላ የግጥም መጽሐፍ፥ የኪነ ጥበብ ወዳጆችና ባለሞያዎች በሚገኙበት ይመረቃል። ለመግዛት (ለማዘዝ) ከታች ይጫኑ።

Buy Now Button with Credit Cards