ነገረ ኃይሌ…

“የማን ነህ ይሉኛል፣ የማን ልበላቸው?
ወዳጅ ዘመድ ሁሉ ልቤን አቆሰለው!”
 
አንጀት እየበላ በጆሮ በኩል የሚንኳለለው የበዛወርቅ አስፋው ሙዚቃ ነው። ትዝ ያለኝ ደግሞ፥ “የማን ፍቅረኛ ነህ?” ተብዬ ተጠይቄ አይደለም። . . . ግን እንዲያም ብጠየቅ፥ ‘….“አይቻልም ወይ መኖር የማንም ሳይሆኑ?” ብዬ ነበር፥… ዘፈኑን አስቀጥዬ የምመልሰው፤….’ ልበልና “Yohanes is single” የሚል ማስታወቂያ አስነግሬ ልለፋ! ሄሄሄ . . . .
 
ነገሩ ወዲህ ነው፥… ‘በጀግናው (ለእኔ፥ ጀግነነቱ በሩጫ ላይ ብቻ ተወስኖ) አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ “የፕሬዝዳንትነት ምኞት” እና በወጣቱ የፖለቲካ ተንታኝ፥ ጃዋር መሀመድ ዘርና ሀይማኖት ተኮር ደረቅ (“የማይነፋ” እንዲሉ) ዲስኩር ላይ፥ ሰዉ ሁሉ ‘አፋጀሽኝ’ ሲል፥ ምን ቆርጦህ ዝም አልክ?’ ብለው፥ አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች፥ በinbox በኩል ሜንጫ እያውለበለቡ፥. . . . ሲመጡብኝ ጊዜ፥ ምናምን. . . ብዬ ልቀውጠው እንዴ?! ሄሄሄ…
 
በርግጥ ዝምታዬ ርዕሰ ጉዳዮቹን በማናናቅ ሳይሆን፥ ትኩረት ላለመስጠት በመፈለግ ነበር። አሁን ግን ሊሰጣቸው ይገባል ብዬ ከማስበው በላይ ትኩረት አግኝተው በወሬው ሰንጠረዥ ላይ ነግሰው መቅረታቸውን መመልከቴ እየቆሰቆሰኝ (በተለይ የጃዋር)፥ እኔም የተሰማኝን ለመናገር ተወሰወስኩኝ። ያው በቦታዬ፣ እኔ እንደተሰማኝ ነው! (በአጭሩ፥ it happened to be in my mind; and wanted to update a status with the real feelings of mine).
 
ሲጀመር ግን ማንኛውም ሰው ላደረገው የትኛውም ዓይነት ያልተገባ ድርጊት ወሰኑን ያለፈ ማጣጣልና መወገዝ ሲደርስበት ነገሩ ላይ ሲበረታና ሲገፋበት እንጂ፥ መለስ ሲልና ሲፀፀት ማየት አልተለመደም። ይሄም በego (የአማርኛ አቻ ቃሉን እንጃ) ዓይነት የሚወሰን ይመስለኛል። ማንም ሰው ከegoው ጋር ጦርነት መግጠም አይፈልግም። ድንገት ሲገጥም ግን በegoው ተገዶ ነው። …ድንገት ሲገጥም ደግሞ ማሸነፉ ከባድ ይሆንበታል። (ይላል የራሴው ፍልስምና። ሃሃሃ….) ምንም እንኳን በሁለቱም ግለሰቦች ምክንያት የተፈጠሩት ወከባዎች ምንጮች egoዎቻቸው እንደሆኑ ባምንም፣ ያልተገባ እውቅና መስጠት እንደሆነ ይሰማኛል። ቢሆንም…
 
ውሸት ምን ይሰራል? ሁለቱም – የኃይሌም የጃዋርም – ጉዳዮች እኔን አላስደነገጡኝም። ምናልባት ሁለቱንም በሆኑበት መልካቸው እጠብቃቸው ስለነበረ ይሆናል፥ እንደ ድንገተኛ ናዳ እጢዬን አላራገፈውም። ወይ ደግሞ የ ‘De’javu’ ስሜት? …..እንጃ፥ ግን ሁለቱም ነገሮች፥ በአወቃቀራቸው ተለይተው ለጆሮዬ እንጂ ለቀልቤ እንግዳ አልነበሩም። ወይ ደግሞ ከሁለቱም ግለሰቦች የሆነ ዓይነት ነገር ያስጠብቀኝ ዘንድ ደመ ነፍሴ ታድሎ ነበር።
 
….whatever!, ‘expectation kills’ and I’m alive!!
 
ኃይሌ በሮጠ ቁጥር አፌን ከፍቼ ተደምሜያለሁ። ተፎካካሪዎቹን ጉድ እየሰራቸው፥ እኔን ጉድ አስብሎኛል። (ወላ እርሱ 30 ደቂቃ የሮጠውን፥ እኔ ሰላሳ ጊዜ ነው የማወራው፣ ሰላሳ ጊዜ ነው የምሸልልበት።) ….ኃይሌ ብዙ ጊዜ አስለቅሶኛል። ባንዲራው ሲሰቀል፥ ትኩስ እንባው ከሲታ ጉንጩ ላይ ሲንዠቀዠቅ አንጀቴም አብሮ በስሜት እየተንሰቀሰቀ አንብቷል።
 
ከውዷ ጂጂ በመታሰቢያ በተበረከተለት “አቦ ሸማኔ” ሙዚቃ ስለርሱና በዚያ ሰሞን ጠብ እርግፍ እልላት ለነበረች ልጅ፥ ባንድ ላይ የሸለልኩበት ጊዜ፥ የትናንት ይመስል ሁሉ ዛሬም ትዝታው ትኩስ ነው። — “የእኔ ነው… የእኔ ናት…” እያልኩ በአደባባይ! … “በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ። “ — ታዲያ ወፍ ሲደራረብ ምን ይደረግ?!
 
ያኔ ያየኝ ቢኖር “አበደ” ሊልም ይችል ነበር። (‘ጆሮ ለባለቤቱ ባዳ ነው’ ይባል ሆኖ እንጂ፥ ይህኔ ብሎኝም ሊሆን ይችላል።) …ይበላ! ደግሞ የርሱን ማን አየና? …ለነገሩ ቀድሞ ሁሉም ባበደበት ሁኔታ ላይ ማን ማንን ይታዘብና? ….የሩጫ መሙ ላይ ሲሰየም ግን፥ ኃይሌ የምሩን ኃይለኛ ነው። ጥም መቁረጥ ያውቃል። ወላ ድህረ ድሉን ማሸብረቅ ይችልበታል። “ይቻላል!” ይልሃል!
 
እውነት ነው፥ አቅምን አውቀው በመቼቱ ሲሰማሩ፥ ሁሉም ነገር ይቻላል! …ሲያሸንፍ በደስታ ሰክረን አልወደቅንም እንጂ፥ በቁማችን ተንገዳግደናል። በፈንጠዝያ ብዛት ጨርቅ አልጣልንም እንጂ፥ አብደናል። አቅላችንን ስተን ወጥተን ጎዳና ላይ አላደርንም እንጂ፥ ጎዳና ላይ ወጥተን አምሽተናል። በኩራት ብድግ ብሎ መብረር አልሆነልንም እንጂ፥ ደረታችንን ገልብጠን አኮብኩበናል። ….እንዲህ እንዲህ፣ እንዲያ እንዲያ ብዙ ሆኗል።
 
እያለቀሰ ያስለቀሰኝ ኃይሌ ግን፥ በማላገጥ እየሳቀም አስለቅሶኝ ያውቃል። ….ከዚያ ”ኃይሌ ማስለቀስ እንጂ ማሳቅ አይችልም“ የሚል ድምዳሜ ላይ ባልደርስም፥ ከዚያ በኋላ ብዙ ዓይነት የአፍ ወለምታዎች ሊገጥሙት እንደሚችሉ እጠብቅ ነበረ። ….ያኔ ከሰይፉ ፋንታሁን ጋር ሆኖ ነበር ያላገጠብን። ….በወቅቱ ለአስተማሪዎች መቶ የማታልፍ ብር ደመወዛቸው ላይ ተጨምሮ ዜናው ሲደራና የገበያ ዋጋ ለማናር ግብአት ሲያስተርፍ፣ መምህራን ‘የተጨመረልን ደመወዝ በጣም ትንሽ ነው፤ ዜናው ይስተባበል’ ዓይነት ቅሬታ ሲያሰሙ፥….
 
ከሰው መርጦ ከሰይፉ ጋር፥ “አስተማሪዎች እኮ ስራ ፈትተው ነው የሚውሉት። ይሄ ደመወዝ መች አነሳቸው? ለምን ሌላ ሥራ አይሰሩም?” ምናምን ብሎ ስለማያውቀው ነገር ዘበዘበ። …“ወጥ ረገጠ” ብዬ ታዘብኩት። እናቴ ራሷ “አወቅሽ አወቅሽ ቢሏት” ይሉትን ተረት አስቀድማ፥ “በዚህ ምን አገባው? …ዝም ብሎ ሮጦ አያሸንፍም?! ኧረ ለአስተማሪስ ደመወዝ ያንሰዋል….! ከልጅ ጋር መድረቅ ያለውን ስቃይ የት አወቀ? ሌላ ሥራ ሲሰሩ ልጆቹን እርሱ ያግዳል?…” ምናምን ብዙ ብላ ታዘበችው።
 
ብዙ ሰው ታዘበው። ኃይሌ በመምህርነት ሞያ የሚሰራውና የሚቀረፀው ቁስ ሳይሆን የሰው ልጅ አእምሮ መሆኑን ዘንግቶት ነበር፤…. ወይ ደግሞ እንዲሁ ጨዋታ አጣፍጥ ብሎ፥ ቀባጠረ! ከዚያም ባለፈ ኃይሌን አውቀነዋል። ንግድ፣ ሽምግልና፣ ምናምን፤…. የራሱ ምርጫ ቢሆንም ባንዳንዱ አሸማቆናል። አሳቆናል። አስቆናልም። …ከንግድ ጋር በተያያዘ ታስሮ ተፈታ ሲባል ሰምተንም እናውቃለን።
 
“የኖርሽ የኖርሽና፣ ሰርግሽ በደመና” እንዲሉ፥ ማስለቀስ ላይ ጎበዙ ኃይሌ ቀጣይ ፕሬዝዳንት የመሆን ፍላጎቱን አረዳን። (ብስራት ለሆነላቸው አበሰራቸው።) ….አሁን ግን አላስለቀሰኝም። አላሳቀቀኝምም። ከዚህ የከፋ ነገርም እጠብቅ ነበር! ….ደግሞም ከዚህ በፊትም እንደጨዋታ ይህን ምኞቱን መናገሩን አስታውሳለሁ። ….ያም ሆነ ይህ ግን መመኘት መብቱ ነው።
 
በዚያም ላይ፥ ሰው egoውን እየተከተለ ባለበት ወይም ማህበረሰብን በናቀበት ወቅት “ጎበዝ” ቢባል፥ እንደ ልጅ “ለአሁን ለሁልጊዜ” ብሎ የመጠየቅ አቅም እንኳን ሳይኖረው፥ እንደሞኝ “ለሁልጊዜ” ብሎ ነው የሚሰማው። የፍቅር ጠላ ምንጩ ሲዘነጋ ስካሩ ከአናት ይደርስና ተቀባይነትን እንደተቀዳጁና ጭራሽ የጠላው ጠማቂ እንደሆኑ ያሰማል። ሲንጠራራም ጣሪያው ሳይሆን ሰማዩ ነው የሚታየው። — ‘the sky is z limit’ ይልሃል! ይበላ! …. ‘ልብ እንኳን እንቅርት ይመኛል’ ይባል የለ?! ወዲያ፥… የፍቅርአዲስ ዘፈንም አለ፤ — “ልዑል አስወደደኝ”!
 
ሆኖም ግን የኃይሌን የፕሬዝዳንትነት ምኞት የማጣጥለው ቦታው ይመጥነዋል አይመጥነውም ብዬ አይደለም። ቦታውና ሰዉ ተመጣጥኖ የሚያውቅ አይመስለኝም። ….ኃይሌ ከነበረው ተቀባይነትና ተፅህኖ ፈጣሪነት አንፃር፥ ስለህዝቡ ቢቀር ስለልጆቹ ነገ ቢያስብ፥ ከፕሬዝዳንትነት የተሻለ ነገር ስለመሆን መመኘት ይችል ነበር። (ደግሞም ከምኞቱ በፊት/ውጪ ከዚያ የተሻለ እንደሆነም አምናለሁ።) ….፤ የሆነ ሰፋ ያለ — የሰፊውን ሕዝብ ህልም እንደመፍታት ያለ — ሰፊ ህልም ኖሮት፣ የተሻለ አልጋ ባሰበ ኖሮ፤…. እላለሁ። አለ አይደል? – ከምኞት ባህር ውስጥ ጠልቆ ከዝም ብሎ ጀብደኝነት (adventure) የተሻለ ምኞት ይዞ መምጣት ቢችል!
 
“እንደ ሰሙት አይሆን በፎቶ እንዳዩት” ይላል ቴዲ አፍሮ። ….ዝም ብዬ ሳስበው ኃይሌ ጋሽ ግርማን ለአመት በዓል ለዓመት በዓል፥ ብቻ በቲቪ አይቷቸውም ሊሆን ይችላል፥ የፕሬዝዳንትነት ምኞቱን ያረገዘው። ወይ ደግሞ ከድል መልስ ድል ያለ ድግስ ተደግሶ ሲጠራ። ….ጉራጌዎች፥ “ፋሲካ የገባች ሁልጊዜ ፋሲካ ይመስላታል” ብለው እንደሚተርቱት። ያም ሆነ ይህ ግን ኃይሌ ለፓርላማው ይበዛል ያንሳል ሳይሆን ላለው ስምና ዝና – በሩጫና በንግድ ላይ ተወስኖ – አይመጥንም ባይ ነኝ። እንጂማ ፓርላማው የት የሚያኮራውን?! 
 
ያም ሆኖ ግን ፕሬዝዳንትነት የሚጠይቀው የራሱ ክህሎት አለው። የመናገርና የመግባባት ጥበብ ይጠይቃል። ንግድ ላይ ካለው በተቃራኒው፥ ተማምኖ የመታለል ዘዴ ይፈልጋል።… (የማታለል አላልኩም) ኃይሌን ጎበዝ ተናጋሪ የምንለው ራሱን ማስተማሩን ስለምናደንቅም ይመስለኛል።… እንጂ ከንግግር መሀል ሲጠቀስለት እንኳን ያችው የፈረደባት ባለ አንድ ቃል አረፍተ ነገር ነች ብቅ የምትልልን፤ — ይቻላል!
 
Hence, I don’t think, being a president is not only about giving warm hugs to guests, &cheering up with drinks!, never making opening speeches and attending inagurational ceremonies!, … it is also about acting – as if!, disgracing self and lieing the people; wisdom glazed mockery on the people at times; cooperating on something he has no idea about; signing on whatever paper found on the desk; being locked at the compound and giving up on wandering on the roads…ምናምን ምናምን!
 
‘ፍላጎት ወሰን የለውም፤ ወሰን ለሌለው ፍላጎት ግን የተወሰነ ሀብት ነው ያለው።’ ይለናል የምጣኔ ሀብት ሳይንስ ትምህርት ዘርፍ። ማግኘት ክብር ከሆነ፣ ማግኘት ፍቅር ከሆነ፣ ማግኘት ገንዘብ ከሆነ፣…. ኃይሌ ብዙ አግኝቷል። ብዙ ነገር አለው። ….“አመድ በዱቄት የሚለውጥ” እያለ እንደ ስንዝሮ ወንድሞች በየመንደሩ የመዞር ጀብደኝነት ካሰኘው ቅንጦት ሆኖ፥ መብቱ ነው። …በመቀናጣቱ ልቀጥል ካለም፥ ይመቸው። ፍላጎቱ ከፈቃዳቸው ስምም ከሆነ ደግሞ እንደምኞቱ ይሆንለታል።