የ“ምንም አልሆንኩም” (I’m alright…and everything is so) ስሜት ፈጠራ በሽታ (pseudologia fantastica?) ተጠቂዎችን ሳይ ያስቀኛል። እየተናደድኹም ቢሆን እስቃለሁ። ….ብዙውን ጊዜ ስለሆኑት ነገር ሳይሆን ለሌላው ስለሚመስሉት ነገር ነው የሚጨነቁት። (“ደህና ነኝ” የሚለውን ስሜት ለመትከል መጣሩም የሚመጣው ደህና ካለመሆን ይመስለኛል።) ስለሆነም፥ ያልሆኑትን ለመምሰል በብዙ ይጨነቃሉ። በብዙም ይቀባባሉ። በመደዳም ይዋሻሉ።
መጣላታቸውን ሀገር ምድር ያወቀባቸው ጥንዶች ጥቂት ሲስማሙ፣ (ወይም ሳይስማሙ በፊት) ሀሜቱን ሲፈሩት “ወረኛም ያውራ ሀሜት ይደርድር፥ እኛስ ሆነናል ፍቅር በፍቅር“ ዓይነት ይዘት ያላቸው ዜማዎችን ለማቀንቀን ማንም አይቀድማቸውም። …ከጠብ መልስ ያለውን የመፋቀር ጊዜ እንኳን ሳያጣጥሙ፥ ‘ታርቀናሉን’ ለመንዛት ነው የሚቸኩሉት። …ባይታረቁ እንኳን፥ የምንም አልሆንኩም ስሜቱን ለማቀንቀን ላይ ታች ይላሉ።
ያልተገባ ነገር እንዳደረጉ የሚያውቁና፥ በዚያም ድርጊታቸው ሰው ያወገዛቸው ሰዎች “ሆነ ብዬ ነው የሰራሁት፥ እንጂ ሁሉም ሰላም ነው” (I did it intentionally; otherwise, everything is okay) የሚል ስሜት መፍጠር ይፈልጋሉ። ይህንንም፥ በ“ካፈርኹ አይመልሰኝ” ዘዬ፥…. ወይ ያልተገባውን ነገር በመደጋገም፣ ወይ ደግሞ ስለርሱ ነገር ፈታ ብለው በመተንተንና ማብራሪያ በመስጠት፥ የስነ ልቡና ጨዋታ ለመጫወት ይጥራሉ።
….በበሽታ ማቅቆ ከዛሬ ነገ ይሞታል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረ ሰው፥ ምናልባት ወዳጅ መሳይ ባላጋራዎቹን ማበሳጨት ቢፈልግ (ምናልባት በህመሜ ምክንያት ታምቻለሁ፣ ተደስተዋል ወይም ተገልያለሁ ብሎ ሲያስብ) እንዲሁ የሞት ሞቱን ተነስቶ ባልባስ ያሸበርቅና ድምፁ እንዲሰማ ከፍ አድርጎ ይጫወታል፣ ይጣራል፣ ይበሳጫል። – ጮክ ብሎ! …በአሽሙር ‘ተሽሎኛል (I’m alright) ይብላኝ ለእናንተ’ መልዕክቱን ለማስተላለፍ ይጥራል።
ምርምር ባላካሄድም፣ ወይም የጥናት ወረቀቶችን ባላነብም፥… እንዲያው በደመነፍስ እና ከልምድ ተነስቼ ስገምተው፥ የዚህ በሽታ ተጠቂዎች በብዛት የታችኛው ክፍል ሰዎች ይመስሉኛል። የታችኛው ማለቴ፥… አለ አይደል? – የታዕታይ ስሜት (inferiority complex) የሚያነጫንጫቸው…. በሰላሙ (normal condition) ወይም በላዕላይነት ስሜት (superiority complex) መንጫጫት ወቅት፥ በግልፅ ማሳየት እያለ፥ ፈጠራው ይቀንሳል። – መሰለኝ!
ይህን ሁሉ የሚያስቀባጥረኝ ኢቲቪ ነው። ከስንት ጊዜ በኋላ፣ ለያውም በክፉ አጋጣሚ፥ ዛሬ ኢቲቪ ባይ የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩን ዶ/ር ቴዎድሮስንና የአረብ እንግዶቹን በብዛት ተመለከትኹኝ። የዶ/ር ቴዎድሮስ ስምና ምስል በየዜናው (4 ወይም 5 የሚሆኑ ዜናዎች ላይ) ስመለከት የ“ጓዶች፥ ተረጋግተናል… ወረኞች ወደየቦታችሁ“ ዓይነት መልዕክት እንዳለው ገመትኹኝ። (not taking it personally!, but feeling it as a failed mockery &mocking back on it. Hehehe….)
ዶ/ሩ አንዴ አረብ ሲቀበሉ፣ አንዴ የቤተሰብ ምጣኔ ኮንፈረንስ ላይ ንግግር ሲያደርጉ ታዩ። ግን በጤነኛ አእምሮ የህዝቡ ጉዳይ ባያሳስባቸው እንኳን፥ የህዝቡ ስሜት ስለሚያስጨንቃቸው ተኝተው የሚያድሩ አይመስለኝም። በተለይ እርሳቸው፥ ከትዊተር ገፃቸውም የምረዳው ከህዝብ ጋር የመቀራረብ የከሸፈ ዝንባሌያቸውን ነው። (መክሸፉ የተሰማኝ ከሰሞኑ ነው) …(Hmm, but seriously, how easy is to pretend ‘its alright’, while it is not? ….if it is felt really, how easy is seeing-not a psychiatrist? – curious )
ሌላው የ’we’re alright…and won’t broke up’ ስሜት ያየሁት ደግሞ አረቦቹን ስመለከት ነው። ከቴዎድሮስ አድሀኖም ጋር የነበሩት ሲገርመኝ፣ የቢዝነስ ዘገባው የመጀመሪያ ዜናም ከአረብ ኤሚሬትስ ጋር ስለተደረገ ስምምነት/ ወይም ፍላጎት (or whatever) የሚያወራ ነበር። እዚያ ላይ ደግሞ አብረው የታዩት ፕሬዝዳንቱ ናቸው። (ከመገረሜ የተነሳ የወሬዎቹን ይዘት በጥልቀት ልብ አላልኹምና አትታዘቡኝ።)
…ምናልባትም ከፕሬዝዳንቱ ጋር የታዩት፥ ከሚንስትሩ ጋር የታዩት የቀደሙት አረቦች ይሆናሉ። እንዲያ ከሆነ ደግሞ… አንዴ የሆነውን ደግሞ በማሳየት የ“ደህና ነኝ”ኡን ስሜት፥ ወደ “በጣም ደህና ነኝ” ያሳድገውና፥ ሳቄን ከፍ ያደርገዋል።) …እኔማ ወላ፥ ለገፅታ ግንባታው የመጡ ተዋናዮች እንደሆኑ ተሰምቶኛል። (እነ ፀጉር ሰንጣቂዎች፥ ተሰምቶኛል እንጂ ነው አላልኹም። መቼስ የሚሰማኝ አማክሮኝ ስላልሆነ አትፍረዱብኝማ።)
በተቃራኒው ሲታይ ደግሞ፥ ነገሩ ሁሉ፥ “እናንተ እኮ ዝም ብላችሁ ነው እንጂ፥ እኛ ታምመናል።” ዓይነት የውሸት ስሜት ፈጠራ በሽታ (factitious disorder) ተጠቂነት ውጤት ይመስላል። እንጂ ሰው በሰላሙ እንዴት የሚያስገብረውንና ሰጥለጥ አድርጎ የሚገዛውን ሕዝብ ያቆስላል? …መቋሰሉ ደግሞ ሉአላዊነትን አሳልፎ በመስጠትና ለሌሎች በማሸርገድ ዋጋ መሆኑን ማሰብ ደግሞ ከቁስሉ በላይ ያማል።
አቶ ሽመልስ ከማልማ ‹‹የሳውዲ መንግስት በአገሩ የአሰሪና ሰራተኛ ህግ መሰረት እርምጃ የመውሰድ ሉአላዊ መብት እንዳለው እንገነዘባለን›› ብለው የዓመቱን አስገቡልን። ኧረ እኔስ፥ ወረድ ብለው ‹‹የኢትዮጵያ መንግስት በአገሩ የፀረ ሽብር ህግ መሰረት ሰልፍ የመከልከልና የጉልበት እርምጃ የመውሰድ ሉአላዊ መብት እንዳለው እናስገነዝባለን።›› ይላሉ ብዬም ፈርቼ ነበር።
ጨዋታው ይቀጥላል! ….ግድ የለሽነታቸውም! ….መቃጠላችንም! መቼስ ማልጎደኒ!
…ሰው ግን ወዶ አይደለም ለካ የባለጌ ነገር የሚሳደበው?!