ባንድ እነርሱ፥
— ብዙ —
እየተሸከሙ፣
ያደምቁኝ የነበር፣
ተስፋ ያለመልሙ፤
ዞር ባልኩኝ አፍታ፥
ባንጋጠጥኹኝ ቅፅበት፥
ካ’ይኔ ሲጋጠሙ፥
ያፍታቱኝ የነበር፥
ሀሴት ይቀምሙ፤
የብርሃን ቁሶች፣
የወጋገን ኳሶች…
ከሰማይ ተሰቅለው፥
ምሽቱን ያቀልሙ፣
ብትንትን ፈርጥ ሆነው፥
ውበት ይሸልሙ፤
ጨለማውን ሰማይ፥
ያሞግሱ፣ ያገርሙ፤
ምኞት ይቀምሩ፣
ተስፋን ይቀምሙ፣
የነበሩት ያኔ፥
የተስለመለሙ…
የብርሃን ነጠብጣብ፥
የተስፋ እንክብሎች
የት ሄዱ ከዋክብት?
ታነቃቃ የነበር፥
ታጃጅል የነበር፥
እያቁለጨለጨች…
የብርሃን ግንዲላ፥
በውብ ምሽት በቅላ፤
ያዙኝ ያዙኝ ‘ምትል፣
አውርዱኝ፣ አውርዱኝ፥
ብሉብኝ፣ ብሉብኝ፣
(ዋጡኝ ዋጡኝ፥ ወላ፥
ሰልቅጡኝ፣ ሰልቅጡኝ)
የምትል የነበር…
የወጋገን ግግር፣
የብርሃን ትሪ፥
ከሰማይ ተሰቅላ፥
ተስፋን ታለመልም፣
ባዶውን ትሞላ፤
የነበረች ያኔ፥
ስጋ ትቀባባ፥
ኩስምንምኑን ገላ፤
ሞጌ ጉንጩን ሁላ፥
ድንቡሽቡሽ ታስመስል፣
ፈገግታ ደልድላ፤
ታስውብ የነበረች፥
ዳፍንታሙን አየር፥
ብቅ ባለች ቅፅበት፥
ታፍመው የነበር፣
ታቀላ እንዳለላ፤
የት ሄደች ጨረቃ?
እ’ሷ ስታረፍድ፥
ከዋክብት ሲቀሩ፥
ብቅ ይሉ የነበር፣
ደስታ ይቆሰቁሱ፣
ሳቅ ይወተውቱ፣
ተስፋን ያነቃቁ፥
እምነትን ያደምቁ፥
ያጫውቱ የነበር፥
ካ’ሳብ ያናጥቡ፣
ኦናን ያዋክቡ፥
ድብርት ያጣጥቡ፣
ያጓጉ የነበር፥
የት ሄዱ አብሪ ትሎች?
ቅርንጫፎቻቸው፣
እርስ በ’ርስ ሲጋጩ፥
ሲያረግዱ፣ ሲንሿሹ፤
ንፋስ እያፏጨ፥
ሲገፋቸው ጊዜ፣
ደርሰው ሲወራጩ፣
እዚህ እዚያ ሲነኩ፥
ከብበው ሲፈነጩ፥
ያበሩ ይመስለኝ፥
የነበረው ያኔ፣
የት ሄዱ ዛፎቹ?
ቀን ሲመሽ ጠብቆ፥
ምሽቱ የጠመመ፣
ተደቅድቆ ጠቁሮ፥
ሰማይ የፀለመ፥
ሳቅ፣ ተስፋ የራቁ፥
እምነት የዘመመ፣
አልጋ እግሩ የዛለ፥
እንቅልፍ የታመመ፣
እረፍት የደከመ፣
ከቶ ለምን ይሆን?
ድፍንፍን ማለቱ፥
ከሌላ ተስማምተው፥
ከሌላ ተዋድድደው፣
ጨልሞ ሊቀር ነው?
የሚነግረኝ ማነው?
ከጊዜ በስተቀር፥
የሚያሳየኝ ማነው?
ብቻ ግን…
ይኽ ምሽት ካለፈ፥
ሌ’ቱ ከተገፋ፣
ፅልመት ከረገፈ፣
እንደምንም ብሎ፥
አንድ’ዜ ከነጋ፥
ዳግም አይጨልምም፣
ብርሃን ትቆማለች፥
(ብትፈልግ ከሰማይ—
እልም ስልም ትበል)
አትጠፋም ደጄ ጋ፥
አትጠልቅም ከእኔ አልጋ!
/ዮሐንስ ሞላ/