“የደከመበትን አናውቅም።”

ከወዳጄ ጋር፥ 1815 ብር ዋጋ የተተመነለት የአርከበ መፅሐፍ ዋጋው ገርሞኝ ስናወራ የሰጠኝ መልስ ነው። መልሱ አብሽቆኝ እርር ያለ ንትርክ ውስጥ ገብተን ነበር። ስለ ዋጋ ትመና ሊያስረዳኝ ሞከረ። እኔም መልሼ የማውቀውን ጠቅሼ ተከራከርኩት። ካሰብነውም፣ ሊሆን ከሚችለውም በላይ ንትርካችን ቀጠለ። ወዳጄ ገራገር ሆኖ አይደለም። ሆኖም ይህን ሲል፥ በቅንነትና በነፃነት ነገሩን ማየት ፈልጎ እንደሆነ (100 %) እርግጠኛ ነኝ። ከራስ በላይ ማመን ቢኖር፥ እንዲህ ባለ ነገር ከራሴ በላይ አምነዋለሁና እሱ ማለቱን ትቼ፥ ነገሩ ላይ ላተኩር። በነፃነትና በተናጥል ለማየት መሞከሩንም አከብራለሁ። ቢሆን መልካም ነው ብዬ የምመኘውም ነገር ነው። ግን እንዴት ይሆናል?
 
በእርግጥ፥ ሰው በመፅሐፉ ዋጋ ተናዶ፣ በጅምላ “እነሱ እኮ አምባገነንነታቸው ልክ የለውም።” ቢል፣ ከመፅሐፍ ውድነት ጋር አምባገነንነት ምንም ባይገናኝም፣ ሰው እንዲያ ይል ዘንድ ግን ምክንያት አለው። መፅሐፉ ውድ ነው ሲባል፥ የአሰብን ወደብ ጠቅሶ ውድነቱ ላይ ቢከራከር፣ አልያም የታሰሩ ሰዎችን አጣቅሶ ግፍ ነው ቢል፥ ወደቡም እስር ቤቱም ከመፅሐፉ ውድነት ጋር ባይገናኝም፣ እንዲያ ይል ዘንድ ግን ምክንያት አለው። ቁስል ምክንያት አለው። አነሳሽ ምክንያት አለው። ካለበለዚያ ግን፥ “የደከሙበትን አናውቅም” ካልን፣ ለብዙ ነገር ጥሩ ማስተባበያ ይሆናልና አደጋ አያጣውም። (ስልጣኑን ከአረመኔው ደርግ እጅ ሲፈለቅቁ የደከሙትንስ እንዴት እናውቃለን?)
 
በትክክለኛና ቀጥተኛ ቅዋሜዎች መኖር ብስማማም፥ የሚቃወመው ነገር እውነት ባለበት ሁኔታ፥ አቀዋወሙ ጉዳይ ሆኖ ሊያነታርክ ይገባል አልልም። (ቀላል ምሳሌ፥ አንድ ሰው “የጨረባ ተዝካር” ላይ ጥሪ ተደርጎለት ቢሄድ፥ የአለባበሱ አጨራረብ ይብጠለጠል ዘንድ አግባብ አይሆንም። ከዚያ ቀደም ተዝካሩ መተቸት አለበት። ተዝካሩ መብጠልጠል አለበት።) ስለዚህ መፅሐፍ የማወራው መፅሐፍ ስለሆነ፣ “እንደ መፅሐፍ ነው”። ነገሩ እውቀት ነውና መታተሙ ላይም ቅሬታ የለኝም። መሸጫ ዋጋው ላይ ግን ቅሬታ አለኝ። የፈለገው ዓይነት pricing system ቢጠቀም ኢትዮጵያ ገበያ ላይ መፅሐፍ በዚህ ዋጋ ውድ ነው።
 
(በርግጥ ከዋጋ ውድነት ውስጣዊ ምክንያቶች አንዱ፥ ነገሩን ከሆነው በላይ ተምኖ ማሻሻጥን ማለም፣ ራስን ከፍ አድርጎ ማየት ሊጠቀሱ ይችላሉ። ተነበበ አልተነበበ፥ የዋጋው ውድነት በራሱ የተፃፈውን ነገር ከተፃፈው በላይ በማግነን ሚና ሊጫወት ይችላል። መፅሐፉን ወዶ የሚገዛ ሰውም፥ ለመፅሐፉ ያወጣው ዋጋ እንደባከነበት እንዲሰማው ስለማይፈልግ፥ እጅግ በጣም የተለየ መፅሐፍ እንደገዛ ሊያስብ ይችላል። መፅሐፍ ገዡ ከሻጩ ጋር ዝምድና ሲኖረው ደግሞ፥ የመፅሐፉ እጅግ ልዩነት ሌላ ፈርጅ ይኖረዋል።)
 
እንዳልኩት፥ ስለመፅሐፉ ማወራው እንደመፅሐፍ ነው። (በርግጥ፥ ከፀሐፊው – ከዶ/ር አርከበ – ጋር የግብር ከፋይና የግብር ተከፋይ ዝምድና አለን። ያ ዝምድና ደግሞ የፈጠረብን ቅያሜዎች ብዙ ናቸው። ሆኖም፥ ያንን ከግምት ከትቼ አይደለም ይህን የምለው። ቢሆንም ግን፥ ስለ “ድካም/ጥረት” ነውና የምናወራው፥ ለንፅፅርና ለነገር ማማር፥ ፀሐፊው ያሉበትን ነባራዊ ሁኔታ ማጣቀስ ተገቢ ሳይሆን አይቀርም።)
 
1) ፀሐፊው ከባለስልጣናቱ ጎራ ስለሆኑ ሲማሩና ሲፅፉ የሚደረግላቸው (ሊደረግላቸው የሚገባ) የተለየ እንክብካቤ ይኖራል። (ለምሳሌ፥ የት/ት ወጪ አያስጨንቃቸውም። የአየር ቲኬት አያሳስባቸውም። ሲፅፉ የቡናና መሰል ማነቃቂያዎች ወጪ አያሳቅቃቸውም። ማጣቀሻ መፅሐፍትና መጣጥፎችም ምንጮች አይደርቁባቸውም። መቼስ ጉዳዩ ለ“እድገትና ልማቱ” የሚያበረክተው ነገር ስለማይጠፋ፥ ወጪው ተሸፍኖላቸው ሊታተምም ይችላል።) ስለዚህ፥ እርሳቸውን በዚህ ለክተን “የደከሙበትን አናውቅም” ብለን 1815 ብር ዋጋ አግባብ ሊሆን የሚችልበት ክፍተት አይኖርም።
 
(አንድ የሙሉ ሰዓት ፀሐፊ ወይም የአደባባይ ምሁርን ወስዳችሁ አስቡት። ሲፅፍ የቡና እንኳን ከየት እንደሚያመጣና ምን ዓይነት ድካሞች ውስጥ እንደሚያልፍ ገምቱ።)
 
2) ዋጋ ትመና ሲካሄድ የሚሸጥበት ቦታም ከግምት ይገባል። በኢትዮጵያ ገበያ የፈለገው ዓይነት ነገር ቢታተም 1815 ብር “ውድ” ለመባልም ሩቅ ነው። (ገበያ ወጥተን ዋጋ የምንደራደረው፣ ቀንስ የምንለው፣ መጨረሻው ብለን የምንሟገተው፥ የሻጩ ዋጋ ከገዡ አቅም ጋራ ሲቀራረብ ነው።) ስለሆነም፥ እንዴትም ቢደከምበት 1815 ብር ለውድነትም ሩቅ ነው።
 
(አንድ በዓለም አንደኛ የሆነ ሙዚቀኛ፣ ሲዲ ሲያሳትም፣ የፈለገውን ያህል ቢደክምበት፣ ለስራው ማማር የከፈለውን ያህል ቢከፍልበት፣ ጨረቃ ላይ ወጥቶ ቢያስቀርፀው፥ የሚሸጠው ከገበያው የሲዲ ሽያጭ ዋጋ ብዙ ሳይርቅ ነው። የሆነ ሰው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለ ሙዚቃ ቤት ሄዶ የሆነ ዓይነት ሲዲ ሊገዛ ፈልጎ ዋጋ ሲጠይቅ “1000 ብር” ቢባል ሳይሳደብና በአፀፋው ሳይሰደብ/ወይ ሳይደበደብ ይመለሳል? እዚያ አምባጓሮ ለመፍጠር አቅምና ድፍረት ቢያንሱትስ፥ ተገርሞ ከወዳጆቹ ጋር ሲያወራና ሲብሰለሰል መዋሉ ይቀራል? ስንት ጊዜስ፥ “ህግ የሌለበት አገር አረጉት እኮ” ይላል በሆዱ? ዛሬ እንኳን ፌስቡክ ውሎ ይግባ፣ እዚህ መጥቶም ቢሆን ይተነፍሰዋል።)
 
3) ዋጋ መተመን ሌላ፣ አሻሻጥ ደግሞ ሌላ ናቸው። በመደበኛው የስነ ምጣኔ ሳይንስ፥ ዋጋ ትመና ውስጥ ከግምት ከሚገቡ ጉዳዮች መካከል፥ የፍላጎትና የአቅርቦት ሁኔታ ይጠቀሳሉ። ይህም በሆነበት፥ ሻጭ ዋጋውን ሲተምን የገበያውን ባህርይ ማወቅና ያንን ከግምት መክተት ይኖርበታል። እንዲያ ሲያደርግ ነው ሀቀኛ ነጋዴ (rational seller) የሚባለው። እና ይህ ባለበት ሁኔታ፥ መፅሐፉ የሚሸጥበት ገበያ ከግምት አልገባም። በዚህም አልነው በዚያ፥ ንቀት ታክሎበታል። – ‘የማን ምን ያመጣል’፣ ወይም የ’ማን ሊያነብ’ (አንባቢን የመገመት) ንቀቶች። እንዲህም ከሆነ፥ መድከም የሚፅፉለትን ማኅበረሰብ ሁኔታ መረዳትና ከግምት መክተትም ይጠይቃልና አሁንም ደከሙ ማለት አንችልም።
 
(በእርግጥ ስለአሻሻጡ መላ ላይጠፋ ይችላል። ለመንግስት ቢሮዎች፣ በመንግስት ወጪ በትኖ ለሰራተኞችና አባላት በስጦታ ማደልም ይቻላል። – as simple as this. ይህን የምለው ከመሬት ተነስቼ አይደለም። ከዚህ ቀደም ቀበሌ ውስጥ የሰለጠኑ ሰዎች፣ ካለፈቃዳቸው፥ በጅምላ፥ ከአበላቸው መቶ መቶ ብር ተቆርጦ የአዲስ ልሳን መፅሔት ተረካቢ (subscribers) ተደርገው እንደነበር አጣቅሼ ነው። ስለዚህ፥ 100% “መራጭ”ና ይህ ሁሉ አባል ባለበት ሁኔታ፥ ሽያጩ እዳው ገብስ ነው።)
 
4) የሆነ ጊዜ ተወርዶ የእነ ስጋና ቢራ ዋጋ ሳይቀር ተተምኖልን ያውቃል። (ያው ፖሊሲ ፖሊሲ ነው ብዬ ነው።) “ስግብግብ ነጋዴ” የምትለው ታርጋም የእኛው እድሜ ያላት ናት። እና እንዴት ነው ይሄ የሚታየው? 1815 ብር ለመፅሐፍ፣ በኢትዮጵያ ገበያ? (ነገ አንዱ ብድግ ብሎ ጤፍ 10000 ብር ቢል፥ ነፃ ገበያ ተብሎ ጣልቃ አይገባበትም?)
 
5) ይሁን። ደክመው ሊሆን ይችላል። የደከሙትንም ልክ አላውቅም። …ግን እርግጠኛ ነኝ፣ አንድ የመንግስት ተቃዋሚ አንድ መጣጥፍ ላይ የፈለገውን ሀሳብ ለመፃፍ ከሚደክመው በላይ አይደክሙም። እኔ ካቅሜ፥ ይህችን ቁራጭ ሀሳብ ‘ልፃፋት/ልተዋት’ ብዬ ከደከምኩት በላይ ሊደክሙ አይችሉም። በጭራሽ!
 
ሌላም ሌላም።
 
በነገራችን ላይ፥ መፅሐፉን የምትገዙ ሰዎች ታስነኩኛላችሁ። ወይ ደግሞ እንደራጃ። 😉
 
P.S. ይሄ የተፃፈው አሳታሚው ኦክስፎርድ መሆኑን ሳላውቅ በፊት ነው። አሁንም ቢሆን ግን፥ ኦክስፎርድ ሲያሳትም ካለርሳቸው እውቀት ነው? Just curious.

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s