“የዚህ ሰፈር ልጆች እቴ፥ ንቅሳት ይሰርቃሉ” ሲባል የሌብነታቸውን ዓይነት ስላችሁ ተገርማቹ ታውቃላችሁ?
“ኧረ እነሱስ፥ ሀሳብ ሳይቀር ይቀማሉ“ ሲባል ተደንቃችሁ “ሆ” ብላችኋል?
“ምራቅሽን ሰብስቢ፥ ኋላ ተመንትፈሽ እሪሪ ስትይ እንዳንሰማሽ” ተብሎ ሌብነት በግነት ሲወራ ሰምታችሁ ፈገግ ብላችሁ ታውቃላችሁ?
እርሱት!
ይኸው፥ ከወደ ኮልፌ ቀራንዮ፣ የምስኪን እናት ቀጤማ ይመነተፋል። እስር የወይራ እንጨቷ ሳይቀር ይነጠቃል። ጎመን፣ ሽንኩርት፣ ድንች፣ ቆስጣ፣ ሰላጣና ሎሚም አይቀሩ። ኧረ ምን እነሱ ብቻ፥ የዳቦ መጋገሪያ ኮባ ቅጠልና ኩበት ሳይቀሩ ይወረሳሉ። – “ህገ ወጥ ነጋዴ” የሚል ታርጋ እየተለጠፈ፥ በጠራራ ጸሐይ፣ ህገ ወጥ ህግ ማስፈፀም ይካሄድባታል።
እድሜዋ ከጠና ወደ ልመና፣ ጉልምስናው ላይ ከሆነች ደግሞ ወደ አረብ አገር ትገፋለች። ሄዳ ከፎቅ ተወርውራ ስትመጣ፥ ተሰብስበው የገፏትን ትትተው፣ ፍላጎቷን ተገንዝቦ የጎተታትን ደላላ ይረግሙላታል። ድንቁርናዋ ያመጣው ጣጣ መሆኑ ይወራላታል። (‘ማንበብና መጻፍ እንኳን ሳይችሉ ከአገር እየወጡ’ እየተባለ) ለልመና እንደው አዲስ አበባ ሆዷ ሰፊ ነው። እንደምንም ብለው አንዴ እሳቱን የሰው ፊት ደፍረው ማየት ይጀምሩ እንጂ፥ ማንንም ታስተናግዳለች።
ዝርዝሩ ላይ ያሉት ሁሉ የእናት እቃዎች ናቸው። የድሀ እናት እቃዎች ናቸው። የልጇን ሆድ ለመሙላት ላይ ታች የምትል፣ አሮጌ ነጠላ ለብሳ የምትዳክር፥ ኮስማና እናት እቃዎች ናቸው። ከዝርዝሩ ጋር አብሮ ምስሏ ይታያል። ሁኔታዋ ይታያል። ልጇ ፊቷ ላይ የተሳለባት እናት፥ ከነልጇ ምስል ትታያለች። (ሲቀሟት እንዴት አለች ይሆን? ባዶ ሆዱን የሚውለው ልጇን አስባ “ልጄን ልጄን” ብላ አለቀሰች? በ“ሽልንጌን ሽልንጌን…” ዓይነት አጯጯኽ… መረገደች? ቤቷን ጠላችው? እጇ ሙሉ የለመደ፥ እንዴት ባዶዋን ትግባ?) የቡና ቁርስ እንኳን ከሆዷ ቆጥባ ለልጇ የምትሸክፍ ምስኪን፥ የእለት ጉርሷ ሲቀማ እንዴት አደረጋት? “እኔ እናትህ እያለሁ” ያለችው ልጇን የተቀማች ለታ ምን ነገር ተካችለት?
ከሰንዳፋ ይሁን ከጫንጮ፥ ሳጠራ ቅርጫት ሸክፋ ሌሊት ተጉዛ አይብ የገዛች እናት፥ ልጆቿ ዳቦ ይዛ ትመጣለች ብለው ሲጠብቋት ባዶ እጇን ይቀበሏታል። መምጣቷን ደጅ ላይ ሲጠብቅ ውሎ፥ ከሩቅ ሲያያት “እማዬ መጣች” ብሎ፥ ከጉንጯ በፊት፥ እንደማገዝም፥ ቅርጫቷን የሚሳለመው ልጇ ቅርጫቷም ይናፍቀዋል። ። (ምናልባት ጸሐይ ጸሐይ ማለቷን እያማገቻቸው፣ ላቧን እያጠጣቻቸው።) ከፊት ለፊቷ ያለውም መስከረም ነው። የምዝገባው፣ የደብተሩ፣ የዩኒፎርሙ ጣጣ ያሳስባታል። አሁን እንደው እነሱ፥ “ቀጤማ በእንጀራ ለዋጮች”፣ “አይብ በዳቦ ለዋጮች” እንጂ “ነጋዴ” ሆነው ነው? ደግሞ እኮ ካዩት ከበሉት ጋር ቫት ከፋይም ናቸው።
ምድር ላይ፥ የሰው ልጅ ሊደርስበት ከሚችሉ ጉዳቶች ከፍተኛው ለወለዱት መሆን አለመቻልና የአብራክን ክፋይ ቁስቁልና ማየት ነው። በተለይ ለእናት። በተለይ ለደሀ እናት። – ሀብቷም፣ ተስፋዋም፣ እስትንፋሷም፣ ዓለሟም ያው ልጆቿ ናቸውና። ወላጅ ሆኜ ስሜቱን ባላረጋግጥም እንደዚህ ይሰማኛል። በዚህም ምክንያት የእናት ጉስቁልና ተለይቶ ያመኛል።
ደሀ ላይ ቆመው ከፍ ይሉና በሀብት ይታዩልኛል።
ይፈጥፈጡና!
ዛፍ ነቅለው የተከሉትን የመስታወት ህንጻ ቆጥረው አድገናል ይሉኛል።
ላያቸው ላይ አረም ይደግና!
ጥቃቅንነትና አነስተኛነት ላይ መደራጀቱ እንኳን ቅንጦት የሆነባትን “የደሀ ደሀ” እናት እየገበሩ “በጥቃቅንና አነስተኛ ያስመዘገብነው…” ብለው ይደሰኩሩልኛል።
ጥቃቅንና አነስተኛ ተባይ ይብላቸውና!
በነፍስ ወከፍ ገቢያችን ይህን ያህል ደርሷል ይላሉ።
አንዳች በሽታ ይወክፋቸውና!
(አውቃለሁ፥ እርግማን የአቅመ ቢስ ነው። ምነው ባለፈው ደላላ በቀጥታ ስርጭት ሲረገም አልነበር?)
“ህገ ወጥ” አንባል
እንባችንን ነጥቀው፥
ሳቃችንን ዘርፈው፣
መታረዛችንን ራባችንን ወስደው፥
አያውጡት ጨረታ፥
ጓሮ ጓሮ እናስስ፣
ቀን ቀን አንጎዳ፥
ውጭ ውጭ ይቅርብን
እናልቅሰው ጓዳ፣
እንሳቀው ማታ።
(እንጉርጉሮስ የማን ሆነና? ያው የአቅመ ቢስ ነው።)
11781814_1181906321825847_7677626806791924924_n

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s