“ምነው ተለየሽኝ መስከረም ሳይጠባ?
እንቁጣጣሽ እያልን፥ ሳናጌጥ በአበባ”
ያሉትን ቀልቤ፥
እውነት መስሎኝ ያልኩሽ፥…
ዝም ብዬ ሳስበው፥
ለካስ ውሸቴን ነው፥ አይደለም ከልቤ!
መሄድሽ ለማይቀር፥ መስከረም ከራርሞ፣
¬ ጥቅምቱ ሲገባ፥ ብርዱ ሲበረታ፥
ከማቃስት ብቻ፣ ልቤ ባ’ንቺ ታምሞ፥
¬ ሙሾ ከማውረዱ፥ ነፍሴ በኀዘን ቃትታ፥
¬ ባዶ ቤት በበጋ፥ ፈዝዛ ተኮራምታ፥
ተሸሽጋ ከርማ፥ ከክረምት ተጋፍታ፣
ደስታ ከመጥለቋ ባ’ዲስ ፀሐይ ታይታ፥…
ሙዚቃ አድሼያለሁ…
“እንኳን ተለየሽኝ መስከረም ሳይጠባ?
እንቁጣጣሽ እያልን፥ ሳናጌጥ በአበባ”
ልብ አንዴ ተነስቶ መቆየት መክረሙ፥
ከተራ ሀሜት ጋርዶ፥ ይበዛል ህመሙ፤
እንጂ ምን ይረባል?
ደግሞስ ዓለሜዋ፥… ከአዲሱ ሰማይ ላይ፥
አዱኛ እንደሌለ፣ እንዳልሞላ ሲሳይ፥
ማን አየ? …ማን ያውቃል?
‘አትሂጅ’ ብሎ ዋትቶ፥
¬ ከሂያጅ ጋር ተጓትቶ?
የት ይቀር መስሎሻል፥ ዐይን ተንከራትቶ?
ይሻል ቀን ይመጣል!…
ወይ ከውጭ ያስገባል፥
…..የሄደበት አይቶ!
ወይ ውስጥ ውስጡን ያያል፤
…..የሚያርፍበት አጥቶ!
እናም እልሻለሁ፥…
እንኳን ሄድሽ ከፊቴ፤
አበባ ሸክፎ…
በወፍ ምሪ መጥቶ የሚቆም ከቤቴ፥
ከአደይ ተከታትሎ፥ የተስፋ ፏፏቴ፥
እንዳምነሸነሸኝ፥…
ባ ወ ቅ ሽ!…
ዞረሽ በተመለስሽ!
¬ ደጄን በቃኘሽው፥
ማማሩን ባደነቅሽ፥
¬ ጀርባዬን ባየሽው።
/ዮሐንስ ሞላ/
P.S. “ምነው ተለየሽኝ?” የዕውቁ ግርማ ነጋሽ ዘፈን መሆኑ ይታወቃል። ሙዚቃውን ለማዳመጥ ይህንን ይጫኑ: “ምነው ተለየሽኝ”