ዝናቡ ጣሪያውን ሲቆረቁረው ሰማሁና እንደ ልጅነቴ፣ መለመላዬን ወጥቼ “ሩፋኤል አሳድገኝ” እያልኩ መቦረቅ አማረኝ። ሩፋኤል ላይ ዝናብ ሳይዘንብ የማይቀረው ነገር ደግሞ ሁሌም የሚገርመኝ ነገር ነው። ያው የሰፈሬን ሰማይ ነው የማየው።
ምድር ገላዋን ስትታጠብና ቆሻሻዋን ስታፀዳ ይመስለኛል። ሰዉም ንጽህናን መናፈቁ ግልፅ ሳይሆን አይቀርም። ግን ወዲያው እንቆሽሻለን። ከመቆሸሽ ጋር እንዋዋላለን። በሩፋኤል ፀበል የናፈቅነውን መንፃት፣ “ግባ” ያልነውን የጎመን ምንቸት፣ በእንጉጣጣሽ ቢላዋ ስንዝር፥ ሳይርቅ ጎትተን እናመጣዋለን። የገንፎ ምንቸትማ ወጣ ገባ ሲል በመሀል ቤት ሳይሰበርም አይቀር።
ይህን እያሰብኩ ልቤ ሩቅ ሩቅ ወደ ገጠሮቹ ሄደብኝ። ከተማውን ሳይ የማላውቀው፣ ወይም ድንገት በጉብኝት የማውቀውን ገጠር ነው የማስበው። ለበዓላት ድምቀት ቱባውን ባህል ኀሰሳ ገጠሩ ነው ባይኔ የሚዞረው። አሁንም እንደዚህ ሆነ። በምናብ ኀሰሳዬ መካከል በረሀብ የተጠቁ አካባቢዎች ያሉ ህፃናት ዐይኔ ላይ ተኮለኮሉ። የህፃን መልክ ሳይታይ ይታወቃል። መልካቸውን ማምጣት ቀላል ነው። የሆነ ፊት ላይ የልጅ ፈገግታና ንፅህና ማሰብ ነው። የማንንም ልብ መግዛትና ለርኅራኄ የሚያስገድድ ገጽ መገመት ነው።
እነሱ ዛሬ ዝናብ አያውቁም። እነሱ እንኳን “ሩፋኤል አሳድገኝ” ብለው ሊቦርቁ፣ ዛሬ ላይ ቢኮረኮሩም መሳቃቸውን እንጃ። ወላጆቻቸው ቀናቱንም ላይለዩ ይችላሉ። ሆድ ጠላቱ፥ ይበላል። ክፉኛ ያሳክካል። ይታከክበት፣ ገል ይሆን ቁራሽ አጥቶ ዝም ብሎ ያሳክካል። እንዲህ ላለ ሰው በዓል ቅንጦት ነው። ዝናብ ከሞት ወደ ሕይወት የሚመልስ ፈውስ ነው። ግን ይሄም ያልፍና ይረሳል። ተጎሳቁለን እንደማናውቅ እንንቀባረራለን። ተንቀባርረን እንደማናውቅ እንጎሳቆላለን። – ሌላ ጅምላ መከራ እስኪሰማ!
ያም ሆነ ይህ ግን አሁን ካልጋዬ ተነስቶ መለመላዬን ዝናብ ላይ መጣድ ነው ያማረኝ። ሁለት ቴፕ የተከፈተ ይመስል ሁለት ሙዚቃዎች ጆሮዬን እኩል ይደበድባሉ። የሁለቱ ንብርብር፣ ዝብርቅርቅ ያለ ድምፅ ፈጥሮ ያስጨንቃል።
“ዋይ ዋይ ሲሉ፣
የረሀብን ጉንፋን ሲስሉ”
እና
“ልጅነቴ ናፈቀኝ
ተመልሶ ላይመጣ”
ለሩፋኤል ፀበሉም ባይሆን የነገሮችን ህመም ልክ ላለማወቅ ልጅነት በጣም ይናፍቃል። የሰውን ዋይ ዋይታ ላለማስተዋል ልጅነት ወሳኝ ነው። ደግሞ መከራና ስቃዩ ሲቆጠር፣ ራስን ከመካራ ለማስጣል የመፍጨርጨርና መላ የመምታት ውሱንነቱ ሲታሰብ፣ “እዚህ ጋር አመመኝ” ብለው የማይናገሩት ነገር ሲታይ፥ ልጅነት ይሸክካል።
ዝናቡን የበረከት ያድርግልን!
አዲሱ ዓመትም ህፃናት የሚቦርቁበት፣ አረጋውያን የሚመርቁበት ይሁንልን! በዓሉንም የተቸገሩትን እያሰብን እንድናሳልፈው ይሁን!