ወፍ በረራዊ ትውስታ: ነጻነት ወፍትህ!

ነጻነት የልጅነት ጓደኛዬ ነበረች። ነጻነት ዓለማየሁ። ክፉና ደግ አልነበረንም እንጂ እንዋደድ ነበር። ማለቴ በተለየ መልኩ እንዋደድ ነበር። አለ አይደል፥ የልጅነት መዋደድ? …ለምሳሌ፥ ሰው ሳይሞት ለመጀመሪያ ጊዜ ያሳዘነችኝ ነጺ ነች። ያኔ፥ “አይዞኝ” በትምህርትና በልምድ የሚባል ሳይሆን፥ ሰው አንጀት ሲበላ ተፈጥሮ ራሷ፥ ለሀበሾች ብቻ ደብቃ የሰጠችው፥ የሁለት እዮሽ አንጀት አርስ፥ የማፅናኛ ቃል እንደሆነ ነበር ያመንኩት። (ራሴን “አይዞሽ” ስል ማግኘቴን እንጂ፥ ከዚያ በፊት ቃሉን መስማቴን አላስታውስም።) የሆነ ገጸ ባህርይ ነገር ነበረች። ታሪካም የሆነች ህፃን። እሰማ እሰማና፥ አያት አያትና “አይዞሽ” እላታለሁ።

እህህ… ለምሳሌ፥ ስኳር ግዢ ተብላ ተልካ እንደሆነ፥ ስኳሩን ለእኔ ሳታስቀምስ ቤቷ አትሄድም ነበር። ስኳርነቱን የሚረጋገጠው በምላሴ ማህተም ነበር። “ምን ነካሽ?” ቢሏት፥ “እሱ ሳይቀምሰውና ምላሱን ወጣ ገባ እያረገ፣ ከንፈሮቹን እያጋጨ በምራቁ ሲያወራርደው ካልተየ፥ ስኳር ምኑን ስኳር ሆነ?” ሳትል ትቀር ነበር ብላችሁ? ብቻ እንዴትም ያህል ቸኩላ ቢሆን፥ ደጄን ሳትሳለም፣ እኔም እንዴትም ባለ ውክቢያ ውስጥ ደጇን ሳንሳለም አንተላለፍም። አለክልካ ትመጣና፥ “ቸኩያለሁ” ብላኝ ትሄዳለች።

ያኔ፥ እግር እንደምንም ከቤት ይውጣ እንጂ፥ ሳንተያይ ቤት ቤታችን እንደማንገባ፥ ጨረቃና ፀሐይ ቋሚ ምስክሮች ናቸው። እንዳይረሱት አድርገን ተልጠንባቸዋል። …ሰበብ ፈልገን የተገናኘንባቸው ጊዜያትም አይቆጠሩም። በቃ ተገናኝቶ ዝም፣ ፍጥጥ ነው። ድንገት የምታወራልኝ ነገር ካለ፥ ሰምቶ ሰምቶ “አይዞኝ” ማለት ነው። …በልጅነት ሰው ባይጠላላም፥ የእኛ መዋደድ ብርቱ እንደነበር ከርሞ ነው ያወቅኹት። ነፍስ ስዘራ ነው የገባኝ። ሰው ሳይ እርሷን ሳስታውስ ነው ክው የምለው። …እንደ ልጅ እንኳን “እወድሻለሁ” እንዳልላት፥ ልጅነታችንም ፀሐይ እየበላው፣ እየገፈፈ፣ ቀለሙን በመያዝ እና በመልቀቅ መካከል፥ ሁለቱም እያፈጠጡ፥ የምንምታታበት ወቅት ነበር።

ክፍለ ሀገር ሄደች….

(ሆኖም ግን፥ ያኔ የነበረኝን ጣፋጭ የልጅነት ስሜት፣ በሌላ ተርጉሜ አላራክሰውም። ፍሩድን ስላልሆንኩ እንደዛ ያለ ትንታኔ ለመስጠት አስቤም አላውቅ።) ታዲያ ምን አልኩ? ሳድግና ግጥም መጻፍ ስችል ሁለት ረጃጅም ግጥሞች አልፃፍኩላትም? 🙂

የጂጂን፥

ሸጋው ያንተ ፍቅር፥ የህልም እንጀራ ነው
ሆዴ ጠግቦ አልበላም፥ ዘንድሮም ረኀብ ነው።

ስሰማ ነጻነት እንጂ ሌላ ማን ትዝ አለኝ?
.
.

ባልተያያዘ ጨዋታ….

ፍትህ የምትባል ልጅ ነበረች። ት/ቤት ነው የማውቃት። አይኑካ ነበረች። ያይኑካ ነገር… ስሟን እንኳን ልወቅ ብዬ ሳጣራ ይገርማል። ማለቴ፥ ሰው ፍትህ ሲባል ስሰማ እሷ ላይ ነበር የመጀመሪያው። የሆነች ቀንበጥዬ ልጅ ነበረች። ደግሞ ጠይም ናት። (ፍቅር መልኩ ምንድን ነው ብባል፥ “ጠይም” እል ይመስለኝ ድረስ፥ i’m crazy about it 🙂 …no offence ቀያይ ወዳጆች፥ ደማችሁ ጠይም ነውና 😉 ) መቼስ መግባባት አይቀር ተግባባን። እንዲሁ ዝም ብሎ መግባባት። ወዲህ ወዲያ የሌለው መግባባት። ሁለት ሶስት ሳምንት ሲቆይ፥ ክራሹም እልም አለ። (እናቱ ነች!)

“ክራሽ ነበረኝ እኮ” ሳልላት መራራቃችን ግን ሳስበው ይነደኛል።

እና የአስቱካ…

የሰው ሰው ወድጄ፥ ያውም የተውሶ
የልቤን ሳልነግረው ሄደ ተመልሶ።

ስሰማ፥ ካለሷ ዐይኑካ ያልነበረ ይመስል፥ ፍትህ ስንቴ ትዝ አለችኝ?
.
.
.
እስኪ ባካችሁ፥ ነፃነትንና ፍትህን ካገኛችኋቸው፥ “አንቺ የልጅነት ንፁህ ወዳጁ… አንቺ ዐይኑካው… ዮሐንስ ሞላ ሰላም ብሏችኋል።” በሉልኝ በየተራው።

ሰላም!

ደስታዬን ሳንሱር አታርጉት!

አንዳንድ ህልም የሚመስሉ ቀኖች አሉ። ቅዠት የሚመስሉ ስሜቶች አሉ። የዛሬው ደስታ እንደዚያ ነው። ከስንት ውጣ ውረድ፣ ለቅሶ፣ ምልልስና ተስፋ መቁረጥ በኋላ፥ የዞን 9 ጦማርያን በሙሉ (ከዚህ ቀደም የ2 ጦማርያንና የ3 ጋዜጠኞች ክስ መቋረጡ ይታወቃል) የተከሰሱበት የሽብር ክስ ተነስቶላቸው፣ በነጻ እንዲሰናበቱ የተበየነ ሲሆን፤ በፍቃዱ ኃይሉ ብቻ፥ በወንጀለኛ መቅጫ ህግ አንቀጽ 257 እንዲከላከል ተበይኗል።
የእሱም ቢሆን፥ የተከሰሰበት አንቀጽ ቀላል እስር የሚያስቀጣ በመሆኑ፣ እስካሁን የታሰረው ተቆጥሮ በነጻ እንደሚሰናበት እናምናለን። ጠበቃው ባቀረቡት የዋስ መብት ውሳኔ ለማግኘት ለፊታችን ረቡዕ ጥቅምት 10 ተቀጥሯል።
zone-9nersበዚህ ጉዳይ ላይ ግራ የሚገባኝ ነገር…

“ወዳጆቼ ስለተፈቱ ደስ ብሎኛል” ስል… “ተው እንጂ ጆ! ምን የሚያስፈነጥዝ ነገር አለው? ‘በነጻ ተሰናብተዋል’ ከመባሉ ደስታ ይልቅ ጥፋት ሳይገኝባቸው በግፍ የታሰሩበት ዓመት ከምናምን ይበልጥ ያንገበግባል።” የሚሉኝ ወዳጆች ነገር ነው።

ሲጀመር፥ “በነጻ ተሰናብተዋል” የሚለውን ዜና ሙሉ ስሜት ለማወቅ ነገሩን በቤተሰብነት ስሜት ለማየት መጣርን ይጠይቃል። መፍረድ ቀላል ነው። ማናችንም ከቤተሰባችን አንዱ ታስሮ ቢፈታ፥ ስለመፈታቱ እንደሰታለን እንጂ፣ መታሰር ሳይገባው ስለታሰረበት ጊዜ አንብሰከሰክም። ያ ቆም ብለን ሂሳብ ስንሰራ፣ እያደር የምንበግንበት ጉዳይ ነው።

ደግሞ ምንም ነገር ሊሆን እንደሚችል (ከሆይሆይታና status update ያለፈ ምንም ዓይነት ነገር እንደማናደርግ) በሚታወቅበት አገርና ሁኔታ “እዬዬም ሲደላ ነው” ይባላልና በመፈታታቸው ደስታን መቆጠብ፣ በመታሰራቸው ያለማዘን ውጤት ካልሆነ፥ አጉል መመጻደቅ ነው።

ደግሞ፥ ሰዎች በግፍ የታሰሩበት ዓመት የሚያንገበግበን፣ “መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ ተሰናብተዋል” የሚል ብይን ስንሰማ ነው እንጂ፣ “ይከላከሉ” ተብሎ ሲፈረድ ያን ያህል ምላሽ አናሳይም። “በይቅርታ ተፈቱ” ሲባል እንኳን ያ ስሜት አይሰማንም። ታዲያ በግፍ የታሰሩበት ዓመት ከምናምን እንዳያንገበግበን ሲባል በሀሰት ወንጀል ክስ እንዲከራከሩ መበየን ነበረበት? ከዚያ ጥፋተኝነታቸው ባልታየበት ክርክር ሊፈረድባቸው ይገባ ነበር?

ማነው ከእስክንድር ነጋ ላይ ጥፋት ሳይገኝበት በግፍ የታሰረበትን ዓመት የሚቆጥረው?

ማነው ርዕዮት ዓለሙና በቀለ ገርባ በግፍ የታሰሩበትን ዓመት የቆጠረው? (መፈታት ከነበረበት ጊዜ ባሻገር የቆዩትን ትተነው)

ማነው ተመስገን ደሳለኝ በግፍ የታሰረበትን ዓመት የሚያሰላው?

ማነው እስር ላይ ያሉና ታስረው የተፈቱ ሌሎች የፖለቲካና የህሊና እስረኞች በግፍ የታሰሩበትን ዓመት የሚቆጥረው?

ማነው ከቤተሰብና ወዳጅ እስር ቤት መመላለስ የባከነውን ወጪና ጊዜ የሚያሰላው?

ማነው እስር ቤት ውስጥ የመቆየትንና እስር ቤት የመመላለስን ስነልቡናዊ ጫና የሚያሰላው?

ስሜት ሳንሱር አይደረግምና ደስታዬንም ኀዘኔንም ሳንሱር አላስደርግም። ሳዝን አዝናለሁ። ስደሰትም እደሰታለሁ። ውሸት ምን ይሰራል? – ሲታሰሩ ካዘንኩት በላቀ ሲፈቱ ደስ ብሎኛል።

ከናካቴው ጠፍንጎ “እምጷ ቀሊጥ” ቢልም ምንም እንደማላመጣ አውቀዋለሁና መፈታታቸው ያስደስተኛል። እስር ቤት ውስጥ ካለ ሰው ይልቅ ከእኛ ጋር ያለ ሰው ለምኑም ለምንም ጠቀሜታው ላቅ ያለ ነውና፥ መፈታታቸው ያስደስተኛል። የቤተሰቦቻቸውንና ጓደኞቻቸውን ስቃይና ሰቀቀን አውቃለሁና፥ መፈታታቸው ያስደስተኛል። ወጣትነታቸው በከንቱ ሲማገድ ማየት ያመኛልና፥ መፈታታቸው ያስደስተኛል። ለምናፍቀው እንደሚገባን የመኖርና ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት መከበር ማስያዣ ይሆን ዘንድ፥ የማንም ሰው ስጋና ኅሊና እስር ላይ እንዲቆይ አልመኝም።

ይህ ሁሉ ሲሆን ግን፥ በከንቱ የባከኑ ጊዜያት ሳይሰሙኝና ሳያንገበግቡኝ ቀርተው አይደለም። የመንግስትንም ፀባይ አጥቼው አይደለም። ነገም ሌላው ታስሮ ተጨምሮ ‘free’ እያልን ብዙ ጊዜ እንደምናባክን ይሰማኛል። (እንደውም ቅድም ለተስፋለም “ፍቅረኛ ሆኑብኝ እኮ” ብዬው ስንስቅ ነበር። እንደ ፍቅረኛ ባንድ ቃል ሰማይን ከነጉዝጓዙ ይደፋብኛል። ደግሞ ሲፈልጉ ባንድ ቃል ከሰማይ ከፍ አድርገው ያስፈነጥዘኛል። ሳቄንም እንባዬንም መቆጣጠር እንደተሳካላቸው መግለጽ እችላለሁ። የአቅመ ቢስነት ውጤትና ኗሪነቴ ያስገኘልኝ ‘ትሩፋት’ ነውና ቢያበግነኝም ምንም አላመጣምና ለምጄዋለሁ።

በተረፈው ግን፥ ደስታዬን መሸሸግ አልችልም። ከዚህ ሁሉ ውጣ ውረድና ሰቀቀን በኋላ ጓደኞቼ ስለተፈቱልኝ በጣም ደስ ብሎኛል። የበፍቄንም ጉዳይ ቸር ወሬ እንደምንሰማ አምናለሁና በጉጉት እጠብቃለሁ። ደስታችን ሙሉ የሚሆነው ግን፥ በግፍ የታሰሩ ሁሉ ሲፈቱ ነው። ስለነሱ ዘወትር እንማልዳለን!

ለቤተሰብ፣ ወዳጅ ዘመድና ጓደኛ ሁሉ እንኳን ደስ አላችሁ!

ጊዜው ግን እንዴት ይሮጣል?

time-fliesየጊዜ መሮጥ ሁኔታ ከሰው ሰው፣ ከቦታ ቦታ የሚለያይ ቢሆንም፥ ስሜቱ ግን በተለያዩ ምክንያቶች የሚፈጠር ነው። የጊዜ መሮጥ ስሜት፣ በተለይ ከዕድሜ መጨመር ጋር ተያይዞ ይሰማል። ዕድሜያችን ሲገፋ በአጭር ጊዜ ርቀት ውስጥ ብዙ ጉዳዮች ስለሚከናወኑ፣ ያቀድናቸውን ሁሉም ማሳካት ስለማንችል፣ ‘ጊዜው ሮጠ’ ያሰኘናል። ፍጥነቱም ከዓመት ዓመት የሚበረታና የሚጨምር ይመስላል። የምንከፍላቸው ክፍያዎችና ወጪዎቻችንም የጊዜውን መሮጥ ሊያባብሱት ይችላሉ።

በልጅነትና በጉርምስና፥ እንቅስቃሴዎችን ሁሉ ከዚያ በፊት ያልተከሰቱ፣ አዳዲስ ነበሩ። መገናኘት/መዋደድ እንጂ መለያየት ብዙም አይከሰትም። ቀናነትና ንፁህ የልጅነት የጨዋታ ስሜቶች እንጂ፥ የበረታ ክፋትና ተንኮል አይታሰብም ነበር። ለብዙ ነገር ጉጉትና መሻት ይታይብናል። በቆይታችን ውስጥ የሚከሰቱ ጉዳዮችም ብዙ አይሆኑም። ማኅበራዊ ተሳትፎዎቻችንና ኃላፊነቶቻችንም ያን ያህል አይሆኑም። በልጅነትና በጉርምስና፥ በቤተሰብ ስር ስለምንሆን፣ ለብዙ ውድቀቶቻችን እኛን የሚጨንቀን አይመስልም። ማስተባበያውና መሸሸጊያው ብዙ ነው። እዚህ ላይ ነጻነትን የመፈለግና ቁጥጥርን የመጥላት ነገር ሲደመርበት ጊዜው የተጎተተ ሊመስለን ይችል ይሆናል።

ዓመታት በተቀያየሩና ዕድሜያችን በገፋ ቁጥር ግን መሰላቸትና መጣደፍ ይመጣል። ጉዳዮችና ክስተቶችም ይደራረባሉ። ሲዋደድ የኖረ፥ ስለመጠላላት ይማራል። የሕይወት ኩነቶችን (vital events) – ማግባት፣ መውለድ፣ መሞት፣ ማግባት፣ መሰደድ… – የሚያስተናግዱ ወዳጆች ቁጥር ይጨምራል። የኩነቶቹ አካል እንድንሆንም ይጠበቅብናልና ሁሉም ጋር ለመድረስ እንኳትናለን። በሕይወታችን ውስጥ የሚያልፉ ጉዳዮች ዓይነትና ቀለማትም በዓመታት መጨመር ሂደት ውስጥ አብሮ ይጨምራል። በጉልምስና፥ ኀዘንና ደስታ፣ ድብርትና ፈንጠዝያ ይፈራረቃሉ።

ከዕድሜ መጨመር ጋር፣ የምንሄድባቸው ቦታዎችና የምናገኛቸው ሰዎችም ብዙ ናቸውና፥ ማኅበራዊ ሕይወታችንም ይለጠጣል። (በስራ ሕይወት ውስጥ ብንመለከተው፥ አንድ መስሪያ ቤት ውስጥ ብቻ ያሳለፈና፣ መስሪያ ቤት የሚቀያይር ሰው እኩል የማኅበራዊ ኃላፊነት የለባቸውም። እኩል ጊዜው አይሮጥባቸውም።) ለብዙ ነገር እንጓጓለን። ደግሞ ይሰለቸናል። ከዚያ፥ ከዓመታት በፊት የተፈፀመ ጉዳይ የትናንት ያህል ይሰማናል። ነገር ሲደራረብብን መርሳት እንጀምራለን። ለዚህም፥ የምንፈልጋቸውን ነገሮች ቅደም ተከተል የማስያዝ ፍላጎት ያድርብናል። ስለዕቅድና ስለማስታወሻ ደብተር ማሰብ እንጀምራለን። ስንዘገጃጅ ጊዜው ይነጉዳል።

ከዚህ በተጨማሪም፥ ለነገሮች የምንሰጠው ዋጋና፣ ነገሩን ከቀረበው በላይ አቅርቦ የመመልከት ሁኔታ (telescopy)፣ የጊዜን መሮጥ ስሜት ሊፈጥርብን ይችላል። ለቀድሞ ክስተቶች የምንሰጠው ዋጋ እና እነሱን የምንተርክበት መንገድ የሚፈጥረው ስሜትም (reminiscence effect) የጊዜን ሩጫ በማባባስ ረገድ የራሱ ሚና አለው። ሌላው የጊዜ መሮጥ የሚብራራበት መንገድ ደግሞ የአልበርት አንስታይን የአንፃራዊነት ሀልዮት (relativity theory) ነው። የእንቅስቃሴዎቻችን ዘርፈ ብዙነትና የበጎ አድራጎት ስራዎች ተሳትፎዎቻችንም የጊዜ መሮጥ መገለጫዎች ይሆናሉ። በተለይ ደግሞ፥ በዘመነ ቴክኖሎጂ፣ የስልክና የማኅበረሰብ ትስስር ድህረ ገፆች (social networks) አጠቃቀሞቻችን በራሳቸው የጊዜን መሮጥ ያባብሳሉ።

የምንወደውን ሰው፣ ወይም የምንጓጓለትን ጊዜ ስንጠብቅ የተጎተተ የመሰለን ጊዜ (ኮሜዲያን ተስፋዬ ካሳ ፍቅረኛውን ቀጥሮ፥ “ዛሬ 8 ሰዓት የለም እንዴ?” ያለበትን ቀልድ ያስታውሷል) ከምንወደው ሰው ጋር ስንገናኝ፣ አልያም የጓጓንለት ጉዳይ ደርሶ ሲመጣ፣ የጊዜው መሮጥ ይሰማናል። ደመወዝና ሌሎች የገቢ ክፍያዎች በዘገዩበት አጋጣሚ፣ እኛ የምንከፍላቸው ክፍያዎች (ለምሳሌ የት/ቤት ወጪ) ቶሎ ቶሎ የሚደርሱ ይመስለናል። ደመወዝ እስኪወጣ “ዘገየ” ያልነውን ጊዜ፣ ወጪው ሲደራረብብን “ሮጠ” እንለዋለን። በስራ ተጠምደን የምናሳልፈው ቀን፣ በመባከን ከምናሳልፈው ቀን ጋር ሲነፃፀርም የቸኮለ ነው። የስራ አካባቢው የሚጨንቀው ሰው፥ በስራ አካባቢው ከሚደሰት ሰው ጋር ሲነፃፀር፣ ጊዜው ይጎተትበታል።

ያም ሆነ ይህ ግን የጊዜ መሮጥ፥ ብስለት፣ ኃላፊነት፣ የሚወዱትና የሚጠብቁት ነገር መኖር፣ እና የኑሮን ጣዕም መረዳት የሚፈጥሩት ስሜት ነውና፥ ጤናማ ስሜት ነው። ዋናው ነገር የሚሮጠውን ጊዜ ማሯሯጥና ያሰብነውን ማሳካት ነው። ከዚያ በኋላ፥ ሮጠ፣ ዘገየ… ኬረዳሽ! እግራችንን ሰቅለን፥ በደበበ ሰይፉ ግጥም እናንጎራጉራለን። (ደበበ ሰይፉ (1992) “ለራስ የተጻፈ ደብዳቤ (የብርሃን ፍቅር ቅጽ ፪)”)TimeFlies

ጊዜ በረርክ በረርክ
ጊዜ በረርክ በረርክ
ጊዜ በረርክ በረርክ
ግና ምን አተረፍክ?
ግና ምን አጎደልክ?
ሞትን አላሸነፍክ
ሕይወትን አልገደልክ።

እናንተ ጋር ግን ስሜቱ እንዴት ነው ወዳጆች?

አያድርስ!

12107807_1230523080297504_52349465818428065_nሞልቶለት ለተገኘ… ከአመሻሽ ማራኪ ክስተቶች መካከል፥ የፀሐይን ወደ ምህራብ ማቆልቆል ተከትሎ፣ ወደ ቤተ አምልኮ (ቤተ ክርስቲያን፣ መስጊድ…) ሄዶ፣ ግቢ ውስጥ ሆኖ የእፎይታን አየር መሳብ፣ ጭንቀትን መዘርገፍ፣ መረጋጋትን መሰብሰብ፣ በዕምነት ሆኖ ተስፋን መሸከፍ፣ ከአምላክም ከራስም ጋር እኩል እያወሩ እርኩስ መንፈስን ማብሸቅ፣ ፈጣሪን መውቀስ፣ ራስን መፈተሽ፣ መፀፀትና ማመሰገን… ይጠቀሳሉ። (በተለይ የዕለቱ የአምልኮ መርሀ-ግብር ተጠናቅቆና የቀጣዩ ቀን መርሀ-ግብር ሳይጀመር፣ ግቢው ፀጥ ረጭ ሲል)

አመሻሽ ወደ ቤተ አምልኮ የሄደ ሰው ብዙ ዓይነት ትዕይንቶችን ሊመለከት ይችላል። እዚህም እዚያም ብቻቸውን የሚያወሩ አፎች ሞልተዋል። በየልቦቻቸው የሚራገሙና የሚዝቱ፣ በፀፀት የሚብሰከሰኩ፣ በምስጋና የሚፍነከነኩ፣ ስለነገ እየፀለዩ ነገን ከሩቅ እያዩ የሚደሰቱ፣ “የማታ እንጀራ” የሚለምኑ፣ የሚያማርሩ፣ የሆነ ዐይነት ከባድ ሸክም ከላያቸው ላይ እያስራገፉ ያሉ የሚመስሉ፣ ስለአገር ሰላም የሚማልዱ… ብዙ ዓይነት ሰዎች ይታያሉ። በየትኛውም ዓይነት ስሜት ውስጥ ሆነው ቢሞክሩት፥ እርጋታውና እርካታው አይጠረጠርም።

አማኝ ባይሆኑ እንኳን እግር ጥሎ አመሻሽ ዘው ቢሉ፥ ኢአማኒነት ተራግፎ ባይመለሱም በጥሩ መንፈስ ውስጥ ሆኖ መመለስ የሚቸግር ነገር አይደለም። በዓለም ላይ ስንኖርም፥ በዓለማዊነት አስተምህሮ ሳይቀር፣ ስለተስፋ ይሰበካል። ስለመረጋጋትና ጭንቀትን ስለማስወገድ መፍትሄ ጥቆማ ዓለም ይጨናነቃል። መበልጸግን ተከትሎ ስለሚጠፋ ሰላምና መረጋጋት ይሰበካል። ስለስበት ሀይል ይወራል። ከዛሬ ነገ ስለመሻሉ በተሰፋ ይነገራል። ሁሉም በየፊናው ደህንነቱን ለማረጋገጥ ስለጥበቃው ጥንካሬ ይዳክራል። ጥሪት መቋጠሪያ አጫጭር መንገዶችን ኀሰሣና ማስተዋወቅ ላይ ይደክማል። ብዙ ብዙ… መካሪውና ምክሩ ብዙ ነው። ምስጢሩና መንገዱ የትየለሌ ነው።

በየቤተ እምነቱም እነዚህ ጉዳዮች ይሰበካሉ። አማኞች ከአምላካቸው ጋር ሲነጋገሩ፥ በልባቸው “እደመጣለሁ” የሚል እርግጠኝነትና፣ “ይረዳኛል” የሚል ፅኑ ተስፋ አለ። “አድርጎልኛልና” ብለው ለምስጋና የሚመጡም አሉ። ሰማይ ተደፍቶ ትከሻቸው ላይ የወደቀ ሲመስላቸው ፈጣሪ ያቀናናል ብለው ያምናሉና ይሆንላቸዋል። ቢጎድል እና ቢሞላም የፈጣሪያቸውን መኖር ካሰቡ ቀጥሎ ስለሚኖራቸው እንቅስቃሴ መስመር መያዝ ጥሩ አጋዥ ይሆንላቸዋል። ከዚህም በላይ፥ ከሰው አእምሮ በላይ የሆኑ ችግሮቻቸውን ለፈጣሪ በመንገር ከእርሱ እርዳታ ማግኘት እንደሚችሉ ያምናሉ። ይህ የመረጡትና የተሰበኩት የሕይወት መመሪያቸው ውጤት ነውና ያተርፉበታል። (እዚህ ላይ መጥቀስ የፈለግኩት፥ ሄዶ በመቀመጥ ብቻ የሚገኙትን ጥቅሞች ነው።)

ታዲያ ይሄንን የሰው ልጆች እምነት፣ ሰላም፣ መረጋጋትና ተስፋ ለመንጠቅ ላይ ታች የሚሉ ሰዎች እንዴት የተረበሹና በክፋት ውስጥ ያሉ ናቸው? የሰዎችን የሕይወት መመሪያ ማፋለስን የራሳቸው የሕይወት መመሪያ አድርገው የሚንቀሳቀሱ ሰዎች በእንዴት ዓይነት ጭንቀት ውስጥ የሚገኙ ናቸው?

አለማመን ምርጫ ነው። የሰዎችን እምነት ለመንጠቅ መባከን ግን ከራስ ወዳድነትም አልፎ ሌላ ጠሊታነትን የሚጠይቅ መርገምት ነው። ስለሚያምን “ሞኝ” በተባለው ሰው አኗኗር ላይ ክፉኛ መቅናትንም ይጠይቃል። አያድርስ ነው!

የፈጣሪ ሰላምና ፍቅር ይብዛልን!

ዘሮች ይለምልሙ! ዘረኝነት ይውደም!

ማንነት የእምነትና የመቀበል ጉዳይ ነውና “ነህ” ተብለህ፤ ጉራጌ ነኝ ካልክ ትሆናለህ። አማራ ነኝ ካልክም ትሆናለህ። ኦሮሞ ነኝ ብትልም ትሆናለህ። ትግሬ፣ ወላይታ፣… ሌላም የመረጥከውን ዘር ጠቅሰህ “ነኝ” ብትልም ትሆናለህ። የሆነው ሆኖ በጉራጌነትህ፣ በአማራነትህ፣ በኦሮሞነትህ፣ በትግሬነትህ… ለምትኖርባት ምድር፣ ምን የሚጠቅም ነገር ሰርተሀል? ያው ዘር ቆጥሮ ቂም በቀል መቆለል ነው?

ደግሞ ልቁጠር ልሰንጥቅ ካልክ፥ አማራንም ጎንደር፣ ወሎ፣ ጎጃም፣ መንዝ ብለህ ልትከፋፍለው ትችላለህ። ጉራጌም ሶዶ፣ ሰባት ቤት፣ ሊባል ይችላል። ሰባት ቤቱም፥ ኧዣ፣ እነሞር…ሶዶውም ዶቢ፣ መስቃን፣ ክስታኔ… እየተባለ መውረድ ይችላል። ኦሮሞም ብትል፥ የወለጋ፣ የሸዋ እያልክ ልትዘረዝር ትችላለህ። ሌላውም ዘር እንዲሁ መተንተንና ለሽኩቻ መዋል ይችላል። መቅጠን ቀላል ነው። መጥበብ የመፈለግ ውጤት ነው። ግን ምን ስናስብ ነው ያንን የምናደርገው? ለምን እንፈልጋለን?

እቧደነዋለው፣ እዛመደዋለሁ የሚለውን ዘር ቆጥሮ ሌላውን ዘር ሲያንኳስስና ደረጃ ሲደለድል የሚውል ሰው ሌላ ትልቅ ቁም ነገር ቢቀር፥ እዛመወደዋለሁ፣ እቧደነዋለሁ ካለው መሬት ክልል ላይ አንዲት ችግኝ ተክሎ ያውቃል? እዚያ ሲደርስ፥ እጁ የያዘውን ቆሻሻ (የአፉን መርዝ ችላ ብንለው እንኳን) ሳይጥል ተመልሷል? ለአካባቢው ኅብረተሰባዊ መስተጋብር ተጨንቆ ሰዎች በሰላም እንዲኖሩና እርስ በርስ ከመነዛነዝ ይልቅ የተሻሉ ሀሳቦች ላይ እንዲያተኩሩ አግዟል?

በእርግጥ ዝምድና ያለና የሚኖር ነው። በአግባቡ ተቆጥሮ ሲውልም ቅመም ነው እንጂ መጥፎ ነገር የለውም። ሰው ቤተሰቡ እንደሚያኮራውና ስለቤተሰቡ እንደሚያወራው፣ ዘሩን ጠቅሶ፥ እኔ እንዲህ ነኝ ቢል ክፋት ላይኖረው ይችላል። የራስን ማውራት ግን የሌላውን ማንኳሰስን አይጠይቅም። በሌላው ዘር መንኳሰስ የሚጎላና ከፍ ከፍ የሚል ማንነት አለኝ ብሎ የሚያስብ ሰው ግን ራሱን ቢፈትሽ የተሻለ ከፍ ከፍ ማለት የሚችል ይመስለኛል። በዚያ ላይ፥ የትና የት ጅምላ የጋራ ችግሮች ባሉን ሁኔታ ላይ በዘር መቸራቸር ጉዳት እንጂ ጥቅም የለውም።

ዘሮች ይለምልሙ!

ዘረኝነት ይድረቅ!

On teachers’ day…

59_n“Empowering teachers, building sustainable societies” is 2015’s World Teachers’ Day slogan

It is not the whereabouts that you passed (or are passing) through that makes you a good student; it is rather your keenness to imbibe an existing knowledge, and your ability to pay attention to z lessons that are offered (or being offered) by your professors.

Learning something out of a penury and hardships is a whole time achievement that only very few brave (lucky too) students can!…and sharing knowledge out of a scarcity and even through inconvenient medias is a life time wisdom and generosity that only few patriots (lucky too) can do. 

Most importantly, in teaching, it is not any kind of good/material; it is rather a human mind that teachers try to shape and re-shape. And upon successful accomplishment of offering their lessons, they will cherish it all, having beautifully shaped mind as an end product. 

And in learning, it is not to any good that students’re being shaped/made, nor to any kind of good/material; it is rather to a better mind that they’re being shaped and re-shaped!! And upon successful accomplishment of taking their lessons, they definitely will cherish your achievements (with all the limitations) – being a different, self standing mind!

Whatsoever, I’m grateful for the hard times that I’ve been a student, and the wonderful times that I’ve been teaching out of my penury 😉

Happy Teachers’ Day!

Mean the slogan!, empower teachers right!, and let them build sustainable societies!