ለሰው ልጆች ሁሉ!

477907-hand-1355208385-980-640x480.jpgእኛ አገር “መቻል” ቀላል ስብከት ነው። ብዙ ጊዜ እንዲችሉ የሚጠበቅባቸው አቅመ ቢሶች እና ተጠቂዎች ናቸው እንጂ፥ አጥቂዎችና ባለጊዜ ጉልበተኞች አይደሉም። (የማጥቃትና ጉልበታቸውን የማሳየት ፍላጎታቸውን እንዲችሉትና፣ ስሜታቸውን እንዲገዙት።)

ከተረትም ሳይቀር፥ “አህያን ውጭ አስረው ጅብን ነገረኛ ያደርጋሉ።” እንላለን። ለአህያ በጅብ መበላት ማስተባበያዊ ትንታኔያችን ‘ውጭ መታሰሯ’ ነው እንጂ የጅቡ አውሬነት አይደለም። የጅብ ጉልበተኛነት ተለይቶ ታውቋልና እውቅና ተሰጥቶታል። አህያ ግን ከጌቶች አንስቶ ሲረገጥ ችሎ ስለሚኖር፥ መቻል ግብሩ እንደሆነ ተቆጥሮም፣ ውጭ ስለመታሰሩ ጌታዋ ይወቀሳል።

ሰፈር ውስጥ የታወቀ ጉልቤ፥ ልጅ ፈንክቶ ወደ ወላጆቹ አቤቱታ ሲቀርብ፥ “አህያን ውጭ አስረው ጅብን ነገረኛ ያደርጋሉ።… እሱ እንደው ለእኛም እንዳስቸገረ ታውቃላችሁ። እሱስ ይሄን እያወቀ ለምን ከሱ ጋር ይጣላል?” ይባላል።

“ሴት ተደፈረች፣ ተደበደበች” ሲባል፥ “አህያን ውጭ አስረው ጅብን ነገረኛ ያደርጋሉ።… ማን አጭር ቀሚስ ልበሽ አላት? ማን አምሽተሽ ግቢ አላት? ዝም ብሎማ እንዲህ አያደርጋትም።” ይባላል።

“ኧከሌ የተባለ ጋዜጠኛ/ፖለቲከኛ ታሰረ” ሲባል፥ “አህያን ውጭ አስረው ጅብን ነገረኛ ያደርጋሉ።… አርፎ አይቀመጥም ነበር? …ጀብደኛ መሆኑ ነው? …የሆነ ነገርማ ሳያደርግ እንዲሁ አይሆንም።” ይባላል።

“ተማሪዎች በፖሊስ ሀይል ተገደሉ” ሲባል፥ “አህያን ውጭ አስረው ጅብን ነገረኛ ያደርጋሉ።… ማን ውጡ አላቸው? አርፈው አይማሩም ነበር? እስካፍንጫው የታጠቀ ወታደር ፊት ምን ያንጎማልላቸው ኖሮ?”

“ቻሉት… መቼስ እስኪያልፍ” ብለን ከንፈር የምንመጠውም ለተጠቂው ነው እንጂ ላጥቂዎቹ አይደለም። እነሱንማ እውቅና ሰጥተናቸው ማን ጣልቃ ሊገባ?

የሰው ልጆች ጥቃት መቆም ያለበት፥ ባጋጣሚ በሚገኝ እድልና በተጠቂው ሰው ሽሽት ሳይሆን በተስተካከለ ለውጥና ቀጥ ባለ ስልጡን ስርዓት አማካኝነት ነው። ስለዚህ ሁሉም ራሱን ይፈትሽ። ለመብቶቻችንና ለነጻነቶቻችን በጋራ እንቁም። ጥቃቶችን እናውግዝ!

ዛሬ ዓለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ቀን (የ16ኛው የጾታዊ ጥቃትን የማውገዝ ወንድ-መር ዘመቻ ማብቂያ) ተከብሮ ሲውል ከብዙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶቻችን ጋር ሆነን እንደሆነ የታወቀ ነው። ብዙ ብዙ ችግሮች አሉብን።

ብዙዎች በጣም ቅርብ በሆነ የቤተሰብ አባላት ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል። ብዙዎች ‘ህግን ያስከብርልኛል፣ ሰላም ወጥቼ እንድገባ ዘቤ ነው’ ብለው ለደመወዙም እንዲሆን ግብር በሚከፍሉለት የፖሊስ አካል ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙዎች ከቤት ተገፍተው በየሰው ሀገር ተበትነው ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙዎች ከፍለው በሚያሰሯቸው አሰሪዎቻቸው ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙዎች በአደራ በተረከቧቸው የቤተሰብ አባሎቻቸው ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙዎች በመርማሪዎች ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙዎች በቆዳ ቀለማቸው የተነሳ ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙዎች በዘራቸው የተነሳ ጥቃት ደርሶባቸዋል። ብዙ ህጻናት ማስረዳት በማይችሉበት ሁኔታ ጥቃት ደርሶባቸዋል። ቢዘረዘር አያልቅም። ጥቃት በየፈርጁ፣ የትየለሌ ነው።

ምናልባት መጠኑና ዓይነቱ በጆሮና በዐይን የሚሰጠው ግምት ከፍ ዝቅ ይል ይሆናል እንጂ፣ የሰብአዊ መብት ጥሰት ትልቅና ትንሽ የለውም። “በእንቁላሉ ጊዜ በቀጣሽኝ” ማለት ለሰብአዊ መብቶችም ይሰራል። መንገድ ላይ ሲለክፍና እጅ ጠምዝዞ ሲለቅ ዝም የተባለ ሰው ራሱን ወደ ላቀ አጥቂነት ሊያሸጋግር ይችላል። በዱላ ቸብ አድርጎ የተኛም ነፍሰ ገዳይ ሆኖ ከእንቅልፉ ሊነቃ ይችላል።

ስለዚህ “ሳይቃጠል በቅጠል” እንዲሆን፥ ሁሉም እንደ ችሎታው መጠን፣ እንደመረዳቱ ልክ፣ እና እንደ አቅሙ ሁኔታ ሊያወግዝና የኅሊናውን ሰላም ሊጠብቅ ይገባዋል። የሰብአዊ መብት ጥሰት ትንሽና ትልቅ እንደሌለው ሁሉ፥ እርሱን የማውገዝ፣ የማጋለጥ እና የመከላከል ሂደቱም ትንሽና ትልቅ የለውምና ሁላችንም በዙሪያችን ዐይናችንን እንግለጥ።

ለሰው ልጆች ሰላም!!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s