ከነገረ ኢትዮጵያ / Negere Ethiopia ላይ ያገኘነው መረጃ እንዲህ ይላል…..
የሰማያዊ ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ በአራት አባላቱ ላይ የብሄራዊ ሥነ-ስርዓት ኮሚቴ ያስተላለፈውን ከፓርቲው የማሰናበት ውሳኔ እንደማይቀበለው አስታወቀ፡፡
የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ዛሬ ጥር 9/2008 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ ባካሄደው ስብሰባ አቶ ዮናታን ተስፋየ፣ አቶ እያስጴድ ተስፋየ፣ አቶ ዮናስ ከድር እና አቶ ጋሻነህ ላቀ ላይ የተላለፈውን ውሳኔውንም ሆነ ሂደቱን እንዳልተቀበለውና ውሳኔውም በሰማያዊ ደንብ መሰረት ተግባራዊ እንደማይሆን፣ ተባረሩ የተባሉት አባላትም በሙሉ ኃላፊነታቸው እንደሚቀጥሉ በሙሉ ድምጽ መወሰኑን የሰማያዊ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
‹‹የተላለፈው ውሳኔ የሰማያዊን መሰረታዊ ሀሳቦችና እምነቶች፣ ማለትም ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትና የግለሰብን ነጻነት የተጋፋ ስለሆነ ተቀባይነት የለውም›› ብለዋል ሊቀመንበሩ፡፡
የክስ አቀረራረቡም ሆነ የውሳኔ አሰጣጡ በሰማያዊ ደንብ መሰረት ምላዕተ-ጉባኤ ሳይሟላና ቃለ ጉባኤ ሳይፈረም የተሰጠ ውሳኔ በመሆኑ ውሳኔው ተቀባይነት የለውም ሲል ስራ አስፈጻሚው በሙሉ ድምጽ መወሰኑን ኢ/ር ይልቃል አስረድተዋል፡፡
———-
1. ይህ በእንዲህ እንዳለ፥ መግለጫው አሁንም የተሟላ ለመባል የሚያስችል አይመስለኝም።
2. “የብሄራዊ ሥነ-ስርዓት ኮሚቴ”ው በሰማያዊ ፓርቲ ደንብ መሰረት፣ ጉባኤው ሳይሟላ እና ቃለ ጉባኤ ሳይፈረም ውሳኔ ስለመስጠቱ ምንም ዓይነት ተግሳጽ አይደርስበትም ማለት ነው?
3. 2ኛው ላይ ያለውን ጥያቄ መሰንዘሬ፥ ቀድሞ የተላለፈው ውሳኔ፥ “ጥፋት” የተባሉ ነገሮችን ዘርዝሮ የአቃቤ ህግ ምስክርነት ሰነድ ያዘጋጀ ስለሚመስል ነው።
4. ይህ በእንዲህ እንዳለ፥ ቅዳሜ ለወጣ ጋዜጣ እስከዛሬ ከሰዓት መጠበቅ ነበረባቸው?
ስህተት የትም አይጠፋም። የስህተቶቹን ደረጃ ስለመቀነስ መምከር ግን ያስፈልጋል። አሁንም ያልጠሩ ነገሮች አሉ። “አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ” ይባላልና፥ አባላቱ በቅንነት እና በማስተዋል ቢመካከሩ መልካም ይሆናል።