‘ከስሜት ባሻገር’

ቅዱስ ላሊበላ፥ ከአንድ ወጥ ድንጋይ፣ መሰረቱ ከጣራው የተጣለ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን በሚያስደንቅና የሰው ልጅ ሊያስበው በማይችለው ጥበብ አንጾ አበረከተልን። ዓለም ዛሬም ድረስ በኪነ ህንጻው ይደመማል። ያየው ሰው ሁሉ ይደነቃል። “ላሊበላና ሞት ሁልጊዜ አዲስ ነው” እስኪባል ድረስ በታየ ቁጥር አዲስ ነው።

ምን ያህል የተጻፈ ቢነበብ፣ የተቀረጸ ቪዲዮ ቢታይ፣ ነገር አዋቂ ሰው ሲተርክ ቢሰማ፥ ደርሰው ሲያዩት ስሜቱ ከቃላት በላይ ነው። ልክ ልጅ መውለድን በሉት። (በዚሁ አጋጣሚ ያላያችሁት እዩት።) የራስን ልጅ ወልደው እስኪያቅፉ ድረስ፥ ምን ለልጅ ቢንሰፈሰፉ፣ የስሜቱን ከፍታ ያውቁት ዘንድ ከባድ ይመስለኛል። እንዲህ ያለውን ድንቅ ነገር ላሊበላ አበረከተልን።

እኛ ደግሞ፥ ለላሊበላ አድናቆት ይሁን ተብሎ፣ እጅግ በረቀቀ ቋንቋና ምስክርነት ከተጻፈ ወስዋሽና ቀስቃሽ ውዳሴ ጽሁፍ ውስጥ “አዳራሽ” የሚል ቃል መዘን፥ የነገርንና የክርክርን ድንጋይ ስንፈለፍልና፣ ጥላቻንና ፍረጃን ስናንጽ እንውላለን። ውዳሴ አጻጻፉ ላይ ስህተት ቢኖር እንኳን፥ ስለብዙው ጥሩ ነገር አድንቀን መጀመር እንችል ነበር። (በጣም የደነቀኝ ደግሞ፥ ላሊበላን አይቶት የማያውቅ ሰው ሁሉ በጉዳዩ ላይ አስተያየት ሲሰጥ ነበር።)

ላሊበላ አካባቢ የነበሩት ድንጋያት ወደ ድንቅ አብያተ ክርስቲያናት ሲፈለፈሉ፥ በሌላ ቦታ ድንጋይ አልነበረም ማለት አይደለም። ቅዱስ ላሊበላ ድንጋያቱን ለህንጻ ቤተክርስቲያን አልሞ፣ ጥበብን ከፈጣሪ ጠይቆ ሲያገኝና ሀሳቡን ሲያሳካ፣ ሌሎች ድንጋያት ግን ለሌሎች ተግባራት ውለው ነው። ልክ እንደዚሁ፥ ነገርን ሁሉ በበጎም በጠማማም መልኩ መመልከት ሊፈጠር ይችላል።

ፋሲካን ለመብላት ቦታ እንዲያሰናዱ ጴጥሮስንና ዮሐንስን ሲልካቸው “ወዴት እናዘጋጅ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲሉት፥ “እነሆ፥ ወደ ከተማ ስትገቡ ማድጋ ውኃ የተሸከመ ሰው ይገናኛችኋል፤ ወደ ሚገባበት ቤት ተከተሉት፤ ለባለቤቱም። መምህሩ። ከደቀ መዛሙርቴ ጋር ፋሲካን የምበላበት የእንግዳ ቤት ክፍል ወዴት ነው? ይልሃል በሉት፤ ያም በደርብ ላይ ያለውን የተነጠፈ ታላቅ አዳራሽ ያሳያችኋል፤ በዚያም አሰናዱልን። ሄደውም እንዳላቸው አገኙና ፋሲካን አሰናዱ።” እንዳላቸው በመጽሐፍ ተነግሮናል። (የሉቃስ ወንጌል 22: 1-12; የማርቆስ ወንጌል 14:1-15) በመዝሙረ ዳዊት 47: 12 -13ም “ጽዮንን ክበቡአት፥ በዙሪያዋም ተመላለሱ፥ ግንቦችዋንም ቍጠሩ፣ በብርታትዋ ልባችሁን አኑሩ አዳራሽዋን አስቡ ለሚመጣው ትውልድ ትነግሩ ዘንድ።” ተብሎ ተጽፏል።

ከዚህ የምንረዳው፥ “አዳራሽ” የሚለው ቃል፣ ሆን ተብሎ የተጣመመ አገባብ እንደሌለው ነው። መዝገበ ቃላት ብናገላብጥም፥ “አዳራሽ ማለት ታላቅ ቤት፣ ብዙ ሰው የሚያገባ፣ ይኸውም ክብ፣ ሰቀልኛ ነው።” ወይም “ወደ ታሰበበት ነገርና፣ ጉዳይ የሚያደርስና የሚያገናኝ አድራሽ፣ አቃራቢ።” ተብሎ ይተረጎማል። ለእኛ ግን፥ ለላሊበላ አድናቆት “ኢአማኒ ነኝ” ባለ ሰው በተጻፈ ጽሁፍ የተነሳ ቃል መዘን ለክርክር እናውለዋለን።

ቁጣ፣ ክርክር፣ ተሳዳቢነት፣ ዛቻና ፌዘኝነት በመጽሐፍ ቅዱስ አንዱም ጋር በአዎንታዊ መልኩ አልተጻፈም። እንዲህም አልተማርንም። ሆኖም ግን፥ የምናምነው አምላክ የማይወደውን ነገር ተጠቅመን፥ በሀይልና በማንኳሰስ፣ በትምክህትና በመመጻደቅ የእርሱን ቤት እንዳስከበርን እናስባለን። ነገር ግን “ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም አላቸው።” (የሉቃስ ወንጌል 5፥32) ተብሎ ተነግሮናልና እግዚአብሔር ማንን መቼ፣ እንዴት እንደሚጠራ ስለማናውቅ፥ “ኢአማኒ ነኝ” ላለ ሰው የማርያም መንገድ በሚከለክል መልኩ ሆ ብለን እንነሳለን። ከዚህም ባሻገር “እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል።” (የሉቃስ ወንጌል 15፥7) ተብሎም ተነግሮናልና ኢአማኒ ሰው ንስሐ ሊገቡ ከሚችሉ ሰዎች መደብ ነውና፥ ከጻድቃን ይልቅ በእርሱ መጠራት በሰማይ ደስታ ይሆናል።

የሆነው ሆኖ፥ ይሄ ሁሉ ሲሆንስ ምን ላይ ቆመን ነው ሌላውን ሰው የምንዘልፈው? እኛ “አማኝ” መስለንና በስሙ ክርስቲያን ተብለን በጓዳም ባደባባይም ስንት ዓይነት ጽድቅ ሰርተን ጣታችንን ለመጠቆምና ድንጋይ ለማንሳት እንረባረባለን?

“ነኝ እንዳልል፥

የት ቆሜ መሆኔን አየሁ” እንዳለው ነው ጋሽ ሰለሞን ደሬሳ።

“አሁንም ያ ቆሜአለሁ ብሎ በራሱ የሚታመን ሰው እርሱ እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ።” (1ኛ ቆሮንቶስ 10:12) ተብሎም ተነግረናልና ሁሉም ነገር እንደ እኛ ሳይሆን እንደቸርነቱ ይፈጸምልን ዘንድ እንማጸናለን።

————

ትናንት በዕውቀቱ ስዩም ላንዲት ሴትዮ አስተያየት ለጥፎ የነበረው ምላሽ ላይ “Don’t waste your time with explanations: people only hear what they want to hear.” የሚለውን የPaulo Coelho ንግግር አስተያየት መስጫው ላይ አስፍሬ ነበር። (አስተያየታቸውንም አንብቤው፥ ቁጣውና ተግሳጹ እንዲሁም ነገር ፈልፋይነቱንና የማጋጨት ፍላጎታቸውን ብቻ ነበር ለማየት የታደልኩት።) በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ እርስ በርስ ማብራሪያ መሰጣጠትና መማማር እንዳለብኝ ስለተሰማኝ ነው ይህን ሁሉ መዘብዘቤ።

የሆነው ሆኖ ሰው መርጦ ማንበብና መርጦ መረዳት ይችላል። መፍረድና መወገን ግን በፍላጎት እና በስሜት ብቻ የሚወሰን አይመስለኝም።

ሰላም!

 

በረከታቸው ይደርብን!

10173731_1089352547747892_2394650342772072445_n

የአድዋ ድል፥ ባሰብኩት ቁጥር ህልም ህልም የሚመስለኝ ክስተት ነው። ከጦርነቱ አጃኢባትና ከድሉ ትሩፋቶች ባሻገር፥ የጀግኖቹ ደግነት ልቤን ይሰረስረዋል። ክቡር የሰውን ልጅ ሕይወት ለሀገር መስጠት የሚያስቀና ምግባር ነው። አድዋ የጦርነት ጉዳይ ብቻም አይደለም፤ ድንበር አልፎ የተዳፈረን ባለጌ የመመለስ ኃላፊነትን የመቀበል ተግባር ጭምር እንጂ። ሰው በመሆን ብቻ የሚያስቆጣ ሁኔታ ነው።

በተለይ፥ ቁስ ሳያታልላቸው፣ የመሰልጠን ተስፋ ሳያማልላቸው (ቅኝ በተገዛን ኖሮ ባደግን፥ የሚሉ ጣባ ራሶች እንዳሉ ልብ ይሏል)፣ ወላ የ“እንግዳ ተቀባይነት” ምግባራቸው እንኳን እንደ ክፉ ጥላ ሆኖ ሳያዘናጋቸው… ጠባቃ አንጀታቸውን ሸብ አድርገው፣ ሆ ብለው ጠላትን ለመመለስ የከፈሉት መስዋዕትነት የሚደንቅ ነው። ድልን መሻታቸው ፅኑ ስለነበር፥ አፍረው አልገቡም።

እርግጥ ነው፥ የተከፈለንን ነገር ለከፋዮቹ እንዳንመልስ ሁኔታዎች ላይፈቅዱልን እንደሚችሉ ይታወቃል። ነገር ግን፥ …ለቀጣዩ ክፈል (pay it forward)… የምትል፥ ፍቅራዊና ደግነታዊ አዛዥ ሀረግ አለች። ወደእኛ ሀገር ስናመጣው፥ “በረከታቸው ይደርብን” የምንለው ነገር ነው። በረከታቸው ይደርብን ስንል፥ እነርሱ ሰርተው ያለፉትን ነገር እኛም ለሌላው እናድርግ የሚል በጎ ምኞት ነው።

ታዲያ ግን፥ የአድዋ ድል በረከት አድሮብናል ወይ? ብዬ ስጠይቅ ከራሴ ጀምሮ የምታዘበው ነገር ብዙ ነው። እንደ ምሳሌ ባነሳ፥ ደጃፋችን ላይ ሰው ሲደበደብ “ወገኔ ተጠቃ” ብለን አሞን ለማስጣል እንሞክራለን? ምን ያህል የ“ድረሱልኝ” ጥሪዎች ጆሮዎቻችንን አግኝተዋል። ምን ያህል የሚፈሱ እንባዎችንና ደሞችን አይተን “ጎመን በጤና” ብለን ሸሽተናል? አፍንጫችን ስር ግፎች ሲፈፀሙ አይተን “ውሻ ምን አገባት ከሰው እርሻ”ን ተርተን ባላየ እንኖራለን? በነገሮች ላይ፥ በ“እንግዳ ተቀባይነት” ሽፋን፥ ለሌሎች ሰዎች ስናሽቋልጥ ራሳችንን ዝቅ ዝቅ አድርገናል? ስንቴስ በቁስ ተደልለናል?

“የሰው ልጅ ክቡር
ሰው መሆን ክቡር
ሰው ሞቷል – ሰው ሊያድን፣
— ሰውን ሲያከብር
በደግነት፣ በፍቅር፣ በክብር ተጠርቶ፣
በክብር ይሄዳል፥ ሰው ሊኖር — ሰው ሞቶ፤”

የአድዋ ጀግኖች በረከት ይደርብን።

ስለደግነታቸው ሁሉ እ ና መ ሰ ግ ና ለ ን!

❤ ❤

 

I would rather go blind than to see the corpse of the massacred children, mothers, and youth; I would rather go deaf than hearing the groans, the wails, and the sobs here and there; I would rather go palsy than standing helplessly and hopelessly in the middle of nowhere. May the souls of the deceased rest in peace, may the wounds of the injured heal fast, and God comfort the grieving souls 😦
 
May the Almighty intervene in the #OromoProtest, and the vain blood sheds of civilians.
 
“To speak of this is painful for me:
to keep silence is no less pain.
On every side is suffering.”
 
— Aeschylus’ Prometheus Bound (as cited on Tower in the Sky)

ስለአገራዊ ለውጥ ስናስብ: “የዘገየችበት ምንድን ነው ምክንያቱ?”

የእኛ ነገር…

“ስለለውጥ፥ ሌላ ሰው እና ሌላ ጊዜ የምንጠብቅ ከሆነ፥ ፈፅሞ አይመጣም። ለዘመናት ስንጠብቅ የኖርነው እኛው ራሳችንን ነው። የምንፈልገው ለውጥም ያው እኛው ነን።” (“Change will not come if we wait for some other person or some other time. We are the ones weve been waiting forWe are the change that we seek.”) ሴናተር ባራክ ኦባማ በፕሬዝዳንታዊ ምርጫ እንቅስቃሴያቸው ወቅት፥ በታላቁ ማክሰኞ (Super Tuesday) አድርገውት ከነበረው መሳጭ ንግግራቸው መካከል ተቀንጭቦ፥ በጠንካራነቱና አነቃቂነቱ ሲታወስና በየቦታው ሲጠቀስ የኖረ ሕዝባዊ እውነት ነው።

በተለይ “ስንጠብቅ የኖርነው እኛው ነን” የሚለው ሀረግ፥ በየሰዉ አእምሮ እና አንደበት ተደጋግሞ ሲሰማ፥ ቁጭትንም፣ ተስፋንም፣ ጉልበትንም እኩል ይሰብካል። ከዚያም በፊት፥ በተለያዩ የማኅበረሰብ መብት እንቅስቃሴዎች ወቅት፣ ኪነጥበባዊ ስራዎችና ንግግሮች ውስጥ ሲጠቀስ የነበረ በመሆኑ፥ የሰዎችን ልብ በማሞቅ ረገድ የራሱን ሚና ተጫውቷል። ሆኖም፥ ባነቃቃባቸው ቦታዎች ሁሉ ጉልህ እርምጃዎችን አስወስዷል አያስብልም። በተለይ ወደ እኛ አገር ሲመጣ፥ ለነገር ማሳመሪያ፣ አልያም የድብርታም ቀንን ብርድልብስ መግፈፊያ ተብሎ፥ ተጠቅሶ የሚተወው ነገር ብዙ ነው።

“ነገር ከስሩ ውሃ ከጥሩ” (“Rome wasn’t built in a day”)

ያኔ ኦባማ ምርጫውን የማሸነፋቸው ወሬ ለዓለም ሲበሰር፥ የመገናኛ አውታሮች በሳም ኩክ “A Change Is Gonna Come” ሙዚቃ ሲናጡ ነበር። ታዲያ እንዲህ ነው፥ “Rome wasn’t built in a day” በሚል ሙዚቃ ታጅቦ፥ እያንዳንዱን ቀን ለትልቅ ለውጥ ክምችትነት ተጠቅሞና የለውጥ ግብአቶችን አጠራቅሞ፤ ላይ ታቹን አሳልፎ፣ ሜዳው ላይ ሲደርሱ የድል ሙዚቃዎችን መኮምኮም። አለዚያ ግን ዜማው ሁሉ “እንቦጭ… እንቦጭ” እና ወቅታዊ ሆኖ ይቀራል።

ለውጥ ዝግመታዊ እንደመሆኑ መጠን፥ ምሰሶዎቹም (the pillars) ብዙ ናቸው። ወደ ስራ ከመግባት በፊት፥ የምንፈልገው ለውጥ ምንድን ነው? አቅማችን ምን ያህል ነው? የትኛውን ምሶሶ ብንነቀንቀው ሌላውን ያናጋልንና ስራችንን ያቀልልናል? የትኛውን ምሶሶ ብናጠናክረው ሌላውን ይደግፍልናል? የትኛውን ክር ብንስበው፥ የምንፈልጋቸውን ነገሮች ሰብስቦ ያፈርጥልንና ከህልማችን ጋር ያቀራርበናል? (“ሀረጉን ብስበው ደኑን ሰበሰበው” እንዲሉ) እኔ የቱን ማድረግ እችላለሁ? ዙሪያዬ ያሉ ሰዎችስ ለውጡን በማቀላጠፍ ረገድ የትኛውን ተግባር ቢይዙ ያዋጣል? ትዕግስታችንስ ምን መምሰል ይኖርበታል? መግባባቶቻችን እና ኅብረተሰባዊነታችንስ? የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳት ያስፈልጋል።

ካለጥቃቅን ለውጦች ትልልቅ ለውጦችንና የጋራ መሻሻሎችን ማሰብ፥ ትርፉ ጉንጭ አልፋነት ይሆንና፤ ችግሮችና ጭቆናዎች እየበዙና እየረቀቁ ሄደው፣ እኛም ለቅሶ እና እሮሮ አርቃቂዎች ሆነን እንቀራለን። ለምሳሌ፥ የትልቅ ኩባንያ ባለቤትነት ህልም ያለው ሰው፥ ከትንሽ ቁጠባ አንስቶ ቁርጠኝነቱን ማረጋገጥ ይኖርበታል። ስለነገው ህልሙ፥ ከዛሬው ፍላጎቱ ላይ የሚከፍለው መስዋዕትነት ይኖራል። ሳንቲም በመቆጠብ ውስጥ የሚያዳብረው ልማድና በምናቡ የሳለው “የተሻለ ኑሮ” ተደምረው፥ የሕይወት መመሪያውን ያረቁለታል እንጂ ከሰማይ አይወርድለትም።

የዚህ ጽሁፍ ዓላማ፥ ለውጥን በማዘግየት ረገድ በራሳችን (በለውጥ ናፋቂዎች) የሚደረጉ አፍራሽ ተግባራት ዙሪያ መጨዋወት ነውና የተወሰኑትን (በተለይ ከማኅበረሰብ ድረገጽ አጠቃቀም ጋር ተያይዞ ስር የሰደዱትን) እንይ።

“ከራስ በላይ ነፋስ”

ብዙ ነገሮችን መለወጥ እንፈልጋለን። ነገር ግን ሁሌም ራሳችንን እንጎትተዋለን። ልንላቀቃቸው የምንፈልጋቸው ሱሶች፣ ልንዛመዳቸው የምንፈልጋቸው ሞያዎች ቢኖሩም፤ ከቀደመውም ሳንራራቅ፣ ከኋለኛውም ሳንቀራረብ ዓመታት ይቀያየራሉ። አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር የእቅድ ዝርዝሮቻችንን ስንፈትሽ አምና ያቀድነው ላይ ተለጥጦ እንጂ ቀንሶ የሚሆን ነገር የለም። የምንናፍቃቸውን ለውጦች እንዳናይ የሚያራርቁን ብዙ ምክንያቶች ይኖራሉ። ታዲያ ግን፥ ለውጦቹ እኛ ነን ካልን፣ ለዘገዩ ለውጦችም ዋና ተጠያቂዎች እኛው እንሆናለን ማለት ነው።

ተደጋግሞ የመነሳቱን ያህል ብዙ ያልተተገበረውም “የራስን የአስተሳሰብ አድማስ መለወጥ” ነው። የራሳችንን አስተሳሰብ ለመለወጥ በማንፈቅድበትና በማንጥርበት ጊዜ፥ “እኛ ስንጠብቅ የኖርነው ለውጥ ነን” ብንል ከንግግር ያለፈ የሚሆን ነገር አይደለም። በመርህ ደረጃ፥ ብዙ ነገር በእኛ ቁጥጥር ስር ባልሆነበት ሁኔታም፥ ለመቀየር ቀላሉ የራሳችንን ጉዳይ ነው። የጥፍሩን ንጽህና መጠበቅ የማይችል ሰው ስለአካባቢ ንጽህና ላውራ ቢል ሰሚ አያገኝም። ሰሚ ቢያገኝ እንኳን፥ ኅሊናም ይጮህበታል። ሰዎችን የማያዳምጥ ሰው፥ ስለማዳመጥ ጠቀሜታ ላውራ ቢል ተመዝኖ ይቀላል።

ሁኔታዎች ላይ ያለን አቅም ውሱን ሲሆን፥ ራሳችን ላይ ልንበረታ ይገባናል። ዘለን የሰው አጥር ገብተን እናጽዳ ባንልም፥ የራሳችንን በማፅዳት ሂደት ውስጥ የምናጋባው እና የምናስተምረው ነገር አይጠፋም። ስለለውጥ ስናስብና የሰዎችን ግንዛቤ አስፍተን የለውጥ ደቀመዛሙርትን ለማስከተል ስንነሳም፥ መጀመሪያ የራሳችንን የግንዛቤ መጠን መፈተሽና ማጠናከር ያስፈልገናል። ሆኖም ግን፥ ነገሮችን እንደሚገባቸውና ለውጤት እንዲሆኑ ለማድረግ እንቅፋት የሚሆኑብን ውጫዊም (በባለጊዜዎች ክፋት የሚደረጉ) ውስጣዊም (ከእኛ የሆኑ) ጫናዎች አሉ። ውጫዊ ጫናዎቹን ለመቋቋምና የታሰርንበትን የባርነት ገመድ ለመፍታት ግን፥ መጀመሪያ ውስጣዊ ጫናዎችን በማስወገድ ኅሊናችንን ከገዛ ስጋችን ባርነት ማስወገድ ይኖርብናል። የነፋሱን አቅጣጫ ማስቀየስ በማንችልበት ሁኔታ፥ ራሳችንን የማጠንከር እና እንደ ሰርዶ ወደፈለግነው አቅጣጫ በብልሃት ተለምጦ ነፋስ የማሳለፍ ጥበብን ልናዳብር ይገባናል።

ለራስ የሚሰጥ አጉል ግምት (ego)

ጠቀሜታ ቢኖረውም፥ የብዙ ችግሮቻችንም ስር ነው። ለራሳችን የምንሰጠው ቦታ፥ በችሮታ የምንቀበላቸውንም ለሰዎች የምንሰጣቸውንም ነገሮች በመወሰን በኩል የራሱን ሚና ይጫወታል። ‘ego’ ጨቋኞችንም ተጨቋኞችንም እኩል ጠምዶ፥ ሰዎች በችግር አረንቋ እንዲኖሩ የሚያደርግ የትውልድ ትብታብ ነው።  ምናልባትም ከዚህ በታች የሚጠቀሱት “ለውጥ አናቃፊዎች” ስር መሰረትም ‘ego’ ነው።

በለውጥ ሂደት ውስጥ ዕውቅናን ማሠስ

ይሄ አደገኛው ማኅበረሰባዊ ችግራችን ነው። ከሽንፈትና ከአቅመቢስነት የሚመጣም ይመስላል። ሰዎች ትልቁን እና በልባቸው ያለውን ምስል ደርሰው እንደማይነኩት ሲያስቡና፣ “ካሰብኩት ባልደርስስ” የሚል ስጋት ሲያድርባቸው፥ “እየሰሩ ናቸው” እንዲባል በሂደቱ ውስጥ እውቅናን ይፈልጋሉ። አልያም፥ ለውጡን ከልባቸው ፈልገውት ሳይሆን፥ ‘ሀዋርያነቱ’ እንዲያስደንቃቸው አልመው ሲነሱም፥ በሂደት ውስጥ ውዳሴን ያስሳሉ። “እየሰሩ ነው” መባሉን ይፈልጉታል። ይህኔ ሚስጥረኝነትና ወዳጅነት አፈር ይበላሉ። አካሄዶችና ትልልቅ ጉዳዮች ፀሐይ ይመታቸዋል። ወዳጅነት ይጎለድፋል። እምነት ይጫጫል። ወዳጆቻችን እንዲያሙን ሽንቁር እናበጃለን።

ግልብነትና ትኩስ ትኩሱን ቃርሚያ… (አፍሮጋዳዊነት)

“እውነተኛ የሂስ መንፈስ የሌለበት ቦታ የህዝቡ ሂስ የጥበብ ደረጃን ያወጣል። ያወጣው ይፀድቃል። ህዝብ የወደደው ሁሉ እውነተኛ ነው።” (ሌሊሴ ግርማ (2004), ‘አፍሮጋዳ’) ይሄ እየኖርን ያለንበት ግልብ ዘመን ሀቅ ነው። በተድበሰበሱ እውነቶች ተከብበን በብዥታ እንመላለሳለን። ብዥታንም እንፈጥራለን። ብዙ ነገር ስላየን ብዙ ነገር ያወቅን ይመስለናል። ብዙ ሰው ስላደነቀን ጠቃሚ ነገር ያደረግን ይመስለናል። ብዙ ነገራችን የለብለብ ነው። የተጠበሰና የበሰለ ነገር አናውቅም። ብናውቅም ዙሩን ያጠነክርብናልና አንፈልግም። ሌሊሴ ዘመኑን በአንድ ቃል ሲጠቀልለውም “አፍሮጋዳ” ይለዋል። “ለእኛ የዘመኑ ታዋቂነት መንፈስ “አፍሮ” እና “ጋዳ” ተጠቃሽ ናቸው። የአፍሮጋዳ አስተሳሰብ የሚመነጨው ጥልቅነትን ከማለዘብ ነው።” በማለት እያብራራ።

ሰድቦ ለሰዳቢ መስጠት

በንግግር ወቅት ያልተገቡ ቃላቶችን መጠቀም፥ የግልጽነት ንግግራችንን ልባዊነት ላይ የሚያጠላው ነገር ይኖረዋል። ሰዎች በወዳጅነት ስሜት ሲያወሩም፥ በርዕሱ ላይ እንጂ በግል (personally) እንደማይጋጩ ያሳይ ይሆናል። ሆኖም ግን፥ ያንን ለማሳየት ከቁልምጫና ‘ወዳጄ ወዳጄ’ ከመባባል ጎን ለጎን ቃላት መረጣም ወሳኝ ነው። (ያው ዘንድሮ “ወዳጄ” ተብለን ነው የሚቀረቀርልን) ከምንናገርበት መንገድና ዘዬ ባላነሰ፥ የምንናገርበት ቦታም ለንግግራችን ፍሬያማነት ግብአት ይሆናል።

ጉራጌዎች “በመደረንዳ” የሚል የተለመደ ጠንካራ ቃል አላቸው። ትርጉሙ “በቦታችን” ማለት ነው። ብዙ የጉራጌ ወላጅ፥ ልጅ ያልተገባ ነገር ማድረጉን ቢመለከት፥ …ምናልባት፥ ገላጋይ ገብቶ እንደሚገባው ሳይቀጣው እንዳይቀር፣ ወይ ደግሞ ሰው ፊት አሳፍሮት ልጁ በእልህ ተበላሽቶ እንዳይቀር፣ ወይም ‘ነገ ለሚለወጥ ነገር ልጄን ሰድቤ ለሰዳቢ እንዳልሰጠው ከሚል አባታዊ ስስትና ስጋት የተነሳ፥… “ኧክስ በመደረንዳ!” (ጠብቅ በቦታችን) ብሎ ጥርሱን ነክሶ ያልፈውና ብቻውን ይቀጣዋል እንጂ፥ ጥፋቱን እዚያው ዘክዝኮ ለመገሰፅ አይሞክርም።

እርስበርሳችን የምንዘላለፍበት፣ ቅሬታ የምንገልፅበትና የምንወቃቀስበት አግባብነትና መንገድ፥ ስለመረጋጋትና ሀላፊነት የመሸከም አቅማችን የሚነግረን ነገር የለውም?  ለውጥ ፈላጊዎችስ እርስ በርስ ገመና ሸፋኞች መሆን የለብንም?

ሽ ቡድንተኝነት

በተለይ “ያወቁ፣ የነቁ” ናቸው ተብለው ቦታ የሚሰጣቸው ሰዎች፥ አውቀውም ይሁን ሳያውቁ ርካሽ ቡድንተኝነት ውስጥ ሲጠመዱ ይስተዋላል። የቡድንተኝነቱ ርኩሰት፥ ሌሎችን ለመጉዳትና ለማግለል፣ ፊትና ዕድል ቢሰጣቸው የለውጥ ምሶሶ አጠናካሪ ሊሆኑ የሚችሉ ሰዎችን ስለሚያጠቃ ነው። ባነበብናቸው አንድ ሁለት መጽሐፍት ውስጥ ተከልለን፥ ሌሎች ሰዎች ላይ ስነልቡናዊ ጥቃት እናደርሳለን። ጥራዝ ነጠቅ የእውቀት ጋሻችንን ይዘን፥ የጥፋት ጦራችንን እንመዛለን። ለመነሳት የሚጥሩ ነፍሶችን፣ ለማወቅ የሚታትሩ ልቦችን፣ ግንዛቤያቸውን ለማስፋት የሚታገሉ ብላቴናዎችን ብቅ ሲሉ ጠብቀን፥ አቁስለን ጥልቅ እናደርጋቸዋለን። “ወፌ ቆመች” ላይ ያሉ ሰዎችን በደረት እንዳይድሁ ሳንካ እንሆንባቸዋለን። ሀሳባቸውን ሊገልጹ ሲሞክሩ፥ “እስኪ ዝም በሉ” ይባላል። የሆነ ነገር ለመጻፍ ሲጭሩ እንኳን፥ “ዘንድሮ ማንም እየተነሳ ይፈነጭበታል” ብለን የማሸማቀቅ ስራ እንሰራለን። ያው ጉዳዩም ርካሽ፣ ቡድንተኝነቱም ተራ ነውና፥ ደቀመዛሙርቶቻችን ያቀነቅኑልናል። በዚያ ሂደት ውስጥ፥ የለውጥ ሀዋርያት ቁጥሮችን እንቀንሳለን።

እኔ ያልኩት ካልሆነ… (ፍረጃ)

ጥቃቅን መንግስተኝነትም ሌላው ችግራችን ነው። በየቅያሱ ከመንግስት የምንጠይቃቸውን መብቶች እኛው ከወዳጆቻችን እንገፋ’ለን። “እኔ ብቻ ላውራ። የእኔ ብቻ ነው ልክ።” የሚል ሰው፥ መንግስትን “የመናገር መብቴን አትንጠቀኝ። አስተያየት ልስጥበት።” ይለዋል። ደግሞ በመንግስት ቂመኝነት የሚማረር ሰው፥ ወዳጁ ላይ ስር ሰደድ ቂም ይቋጥራል። …ደግሞ ወዲያ “ለውጥ፣ የሀሳብ ነፃነትና የምርጫ መብት” ጃዝ ገለመሌ እንላለን። ወዲህ ሰዎች የወደዱትን ስለመረጡ፥ ቅሬታን ከመግለፅ ባለፈ… በራስ የመስተሀልይ ልክ፣ በቀደመ ታሪክና በግል ፍላጎት ብቻ መዝነነው ተመራጮቹንም መራጮቹንም ባንድ ላይ እንወቅጣለን። ወቀጣችንን የሚወቅሱ ቢኖሩም የነገር ሰንኮፋችን እጥፉን ይዘረጋል። የሀሳብ ነፃነትም ሆነ ለውጥን መናፈቅ በመከባበር መታጀብ እንዳለበት! አለዚያ ይሄድ ይሄድና አንገቱ ጋር ሲደርስ ሲጥ ብሎ፣ እምነት ማጣት ተከትሎት፣ ‘ብዬ ነበር’ መባባልና እርስበርስ መወቃቀስን እንጂ ምንም አያስተርፍም።

የትልልቅ ምስሎች ልክፍት

ትንንሽ ሁኔታዎችንና የለውጥ መንደርደሪያዎችን አናደንቃቸውም። ልባችን ትልልቅ ለውጦችን በማሰብ ተጠምዶ፣ በመንገዱ ላይ የሚያገኛቸውን ትንንሽ ለውጦች ስለማይደነቅባቸው ሀሞቱ ቶሎ እንዲፈስ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ። የማመስገንን እና የመደሰትን ጉልበት ብዙዎች እንስተዋለን። ስለዚህ ቶሎ ይደክመናል። ልባችን ትልቁን ነገር ብቻ ነውና የሚያየው፥ እዚያ ለመድረስ ያደረግናቸው ጥረቶች ምን ያህል ፈቅ እንዳደረጉን ሳናስብ፥ እዚያ አለመድረሳችንን እንረግማለን። በንጽጽር ውስጥ ሆነን ራሳችንን እንወቅሳለን። ሌሎች ሰዎች የነበሯቸውን እድሎችና፥ የማርያም መንገዶች ሳናውቅ፣ ቀድመውን ስለሆኑት ነገር እንገረማለን። ራሳችንን እንረግማለን። በአንጻሩ ደግሞ፥ ትንንሽ ምስሎችን ብቻ ይዘን እየተንቀሳቀስን በትንሽ ውጤቶች ብቻ ልባችን አርፎ ቁጭ ካለም ሌላ ችግር ነውና ሚዛኑን መጠበቅ ያሻል።

ውሻ በቀደደው…

ሌላው ማኅበረሰባዊ ችግራችን፥ በተቀደዱልን ቦዮች ሁሉ የመፍሰስ አባዜዎች ነው። ያም ይመጣል አጀንዳ ያቀብለናል፣ ተቀብለን እናቀነቅናለን። ደግሞ አጀንዳ ሲቀየርልን ቀይረን እንቀባበለዋለን። ተደጋግሞ የሚጠቀሰው “አስማተኞች እና ፖለቲከኞች የሰዎችን ትኩረት ከሚያከናውኑት ነገር ላይ ትኩረቶችን ማስቀየስ መፈለጋቸው ያመሳስላቸዋል” የሚለውን የናይጄሪያዊውን ደራሲ ቤን ኦክሪን አባባል ደጋግመን ብንጠቅሰውም፣ ጭራሽ አናስተውለውም። ስለዚህ በአስማተኞች እና በፖለቲከኞች አጀንዳ ማስጠምዘዝ መርሀ ግብር ሰለባ እንሆናለን። ሌሎችን የመከተል አባዜም አለ። “እነ ኧከሌ ካሉማ” ብለን ልክነትን በሰዎች እንመዝንና እንደናበራለን።

ዘርፈ ብዙ ማኅበረሰባዊ “ሳቦታጆቻችን”

የጎረቤት ዛፍ ጥሩ እያደገ፣ ቅርንጫፉ እየሰፋና እያበበ ሲሄድ… ከመደሰትና ያለውን የጋራ ጥቅም ከማሰብ ይልቅ፣ በጋራ ለሚቆጋን ፀሐይ ጥሩ መላ መሆኑን ከመገንዘብ ይልቅ፥ “ቅርንጫፍሽን ሰብስቢልኝ። የልጆቹን ዐይን እየጠነቆለብኝ ነው።” ….“ማነሽ… አበባሽ ደጄን አቆሸሸው። ዛፉን ቁረጪልኝ።” ….“ግንዱ ግድግዳዬን ሊሰብረው ነው። ተኛብን እኮ! ኧረ ይሄ ነገር ባጭር ይቆረጥ።” ….“ስሩ ወደቤቴ ገብቷል። ቤቴን ያፈርስብኛል ንቀይልኝ ይሄን ዛፍ።” እሪሪሪ… ይባላል። የፈረደበት ቀበሌ አለ፥ ነጠላ ጎትተው ለነገር ቅያስ ያካልላሉ።  “ምናምን አርጋበት እንጂ፥ ሰው ሲጫጫ ዛፏ ብቻውን የሚወዛ” የሚሉ ሀሜቶች ሊሰሙ ይችላሉ። – አገሩ የእኛ ነው! የተተከለው የምች መድኃኒት ቢሆን እንኳን፥ “ነገ ታምሜ እፈልገውም ይሆናል።” ብሎ መራራትም የለም።

ሰው ስራው ጥሩ ከተቀላጠፈ፣ ፍላጎቶቹን ማሟላት፣ ለውጡ ፊቱ ላይ መታየት ሲጀምርና “ስራ እንዴት ነው?” ሲባል፥ ረገጥ አድርጎ “ተመስገን” ማለቱ ሲሰማ፥ ዞር ተብሎ፥ “በጤናው ነው ብለሽ ነው? ጠንቋይ ቤትማ ሳይሄድ አይቀርም።” ይባላል። ደም ያቃቡ፣ ጉቦ ያቃበሉ ይመስል፥ “ጉቦኛ ነው ስልሽ።” …“በሰው ደም ነው ቤቱን የሰራው።” ይባላል። ሌላም ሌላም …ሀሜቱ ብዙ ነው። ማነፍነፉና መሰለሉም አይቀሬ ነው። ሀሜቱ መሰረት ያለው ሲሆን፥ ደህና። ማነፍነፉና መሰለሉም የወንጀልን ጫፍ ለመያዝ ሲታለም ሸጋ ነው። ነገር ግን፥ በእለት ተእለት ኑሮ ሀሜቱ የሚቆሰቆሰው የምንጠረጥራቸውን ተግባራት እኩይ መሆናቸውን በማሰብ የተነሳ ሳይሆን፥ ወዳጃችን ቀና ቀና ማለት ከመጀመሩ ጋር ተያይዞ መሆኑ ነው የሚያሳዝነውና ለውጥ የሚያዘገየው።

አብረን ትምህርት ቤት ያልሄድነው ሰው፥ ስለሚያውቀን ብቻ፥ በትምህርት ሲሳካልን ቅር ይለዋል። ራሱን እየወቀሰ በንጽጽር ይለፋል። አምላኩን ሲያማርር ውሎ፥ ፀሎቱም “የኧከሌ አምላክ” ይሆናል፥ – የተሳካለትን ጎረቤቱን/ወዳጁን ስም ጠቅሶ። (ይህም በቅንነት ሲሆን ክፋት የለውም።) የምንሰራው አጥተን፣ ሰማይ ምድሩ ዞሮብን ስንንከራተት፥ መላ ያላማታን ሰው፣ “ምን በልተው አደሩ?” ብሎ ያልተጨነቀና ለእርጥባን ያላግደረደረን ሰው፣ ነቃ ነቃ ማለት ስንጀምርና የበለጥነው ሲመስለው ይበግናል።

በተለይ ግቢ የሚጋሩት ከሆነ፥ የጎረቤት ቤት መታደስ ለጸብ በቂ ምክንያት ነው። ከ “አሸዋው ግቢውን አቆሸሸው” እስከ “ድንበር ነክታችኋል” ድረስ ጸብ ለመጫር በተጠንቀቅ የሚቆመው ብዙ ነው። አንድ ሚስማር ሲመታ፥ ቀበሌ ተንጋግቶ ይመጣል። መቼም ቀበሌው ጎረቤት ሆኖ አይደለም… ጎረቤት ተሯሩጦ ሄዶ ጠቁሞ እንጂ። ለክፉ ጎረቤት የእኛ ቤት አለማደስ እንጂ፣ በእኛ ቤት ማደስ ተነሳስቶ የእርሱን እንዴት ሊያደርገው እንደሚችል ማሰብ ሞቱ ነው።

እንበልና፥ ግቢ ከሚጋሩ ሰዎች መካከል፣ አንደኛው በገቢ የማይጨነቅ ቤተሰብ ለውጥ ፈልጎ “ሙሉ ግቢውን ሲሚንቶ ላድርገው። መቼስ ከልኩ አያልፍም።” ብሎ ገንዘቡን አፍስሶ ሲሚንቶ ሲያስደርግ፥ ከጎረቤቶቹ መካከል ያንዱ አባወራ ልጁን ጠርቶ፥ “ካለሸር ሲሚንቶ ላድርገው አላለም። ምን እንደሚካሄድ ነቅተህ ተከታተል። እስኪ ዛሬ እንኳን ቁም ነገር ስራ። ነፈዝ!” ብሎት ሊሄድ ይችላል። ንፍገትን እንረግማለን። ስጦታዎችን እንጠራጠራለን።

ደግሞ የሚሰራና ጥሩ ላይ ያለ ወዳጃችንን፥ በመቆርቆር ስሜት፣ ስራውን ያቃናል፣ ለመልካምነቱ ሳንካ ነው ብለን ያሰብነውን ነገር ስንነግረው፥ ቅናት ነው፣ ምቀኝነት ነው፣ ይለናል። ቀና አስተያየት መስጠትም፥ ከምቀኝነትና ከተንኮለኝነት የሚያስደምር ነገር ነው። – አይገርምም፥ የእኛ አገር እንዲህ ነውና!

ሁልጊዜ አንጻር እንፈልጋለን። እኛ ማድረግ የማንችላቸውን ነገሮች፣ ወይም ለማድረግ እየቻልን ችላ ያልናቸውን ነገሮች፥ ሌሎች ሰዎች ሲያደርጉ ስናይ ዐይናችን ደም ይለብሳል። ደስታችንን ስንገልጽ እንኳን ካንገት በላይ ነው። ከዚህ በፊት፥ አንድ ወዳጄ “ሊስትሮ፥ ‘እኔም ሰፊ እሱም ሰፊ’ ብሎ ሰርጅን ላይ የሚቀናበት አገር” ብሎ ነበር። የችግሩን ስር ሰደድነት፥ ይህ ንግግር ፍንትው ያደርገዋል።

ብዙ ጊዜ ሰው ወዳጁን የሚለካውና የሚያዳንቀው በሐዘኑ ጊዜ ከጎኑ በመኖር ባለመኖሩ ነው። በእርግጥ ስናጣ አብሮን ያለ የክፉ ቀን ወዳጅ የልብ ነው። ስናዝን የሚያጽናናም ከየትም አይገኝም። መጽሐፍ ቅዱስም ቢሆን “ወደ ግብዣ ቤት ከመሄድ ወደ ልቅሶ ቤት መሄድ ይሻላል እርሱ የሰው ሁሉ ፍጻሜ ነውና፥ ሕያውም የሆነ በልቡ ያኖረዋልና።” የሚል ት/ት አለ። (መጽሐፈ መክብብ 7፥2) ሆኖም እዚህም ላይ ቢሆን፥ ለቅሶ ደራሹ ስለሚማረውና በልቡ ስለሚያኖረው ነገር እንጂ፣ ለቀስተኛው ላይ ስለሚፈጥረው በጎ ነገር ብቻ ተጨንቆም አይመስልም። ያ ለቅሶ ደራሽ፥ በግብዣችን ወቅትም፥ ድግሱን ታድሞ ከመሄድ ባለፈ ‘የደስታችን ተካፋይነቱ’ ሊፈተሽ ይገባዋል።

ምሳሌውን ነው ‘ቤት፣ ጎረቤት፣ ጓደኛ’ ያልኩት እንጂ፥ ችግሩ በየዘርፉና በየሁኔታው ውስጥ የሚስተዋል ነው። ስለለውጥ ስናስብ ‘የደስታ ተካፋይነታችንን’ ልንፈትሸው ይገባል።

እንዴት ይሻላል?

“ላለፉት 33 ዓመታት፥ ሁልጊዜ ጠዋት ራሴን በመስታወት ውስጥ እየተመለከትኩ፥ እጠይቃለሁ ‘ዛሬ የሕይወቴ የመጨረሻው ቀን ቢሆን ኖሮ፥ ዛሬ ልሰራ ያሰብኩትን ነገር ነበር የምሰራው’ ብዬ ራሴን ደጋግሜ እየጠየቅኩኝ፥ ደጋግሜ ያገኘሁት መልስ ‘አይ! አልነበረም!’ ሲሆን፥ የሆነ ነገር መለወጥ እንዳለብኝ አውቅ ነበር።” ብሎ ነበር የአፕል ካምፓኒው ስቲቭ ጆብስ። የምር፥ ዛሬ የሕይወታችን የመጨረሻው ቀን ቢሆን ኖሮስ? ታላቁ ማርቲን ሉተር ኪንግም፥ “ሰዎች እንዲጋልቧችሁ፥ ጀርባችሁን ለምጣችሁ አትመቿቸው።” ብሎ ነበር። (በረከታቸው ይደርብንና!)

በማርቲን ሉተር ኪንግኛ እንሰነባበት! – “Change does not roll in on the wheels of inevitability, but comes through continuous struggle. And so we must straighten our backs and work for our freedom. A man can’t ride you unless your back is bent.

እስኪ ጀርባችንን ቀና እናደርግና ጋላቢ ጨቋኞቻችንን እናንሸራትታቸው ዘንድ፥ አቋቋማችንን እንፈትሽ፣ ለውጦቻችን ስለዘገዩበት ጉዳይ እንጨዋወት።

ሰላም!

 

 

 

 

 

 

ፍካሬ ንቅሳት

ድሮ ነበር…
አንድ በጊዜና በጥረቱ ብዛት ከድህነቱ ተላቅቆ ባለፀጋ የሆነ ሰው ነበረ። ቤቱ ውስጥ በአሽከርነት እንድታገለግለው ከገጠር ያመጡለትን ሴት ገና ሲያያት ይደነግጣል። በወቅቱ ሴቲቱ የለበሰችው አዳፋ ልብስ ነበር። እሱም በዝቶ ገላዋ ላይ ተበጫጭቋል። ለእግሯም ባዶ እግር ከመሆን የማይሻል የተበጣጠሰ ላስቲክ ጫማ (ኮንጎ) ነበራት። ስትራመድ እየጎተተችው፣ ጣቶቿም ወጣ ገባ ይሉ ነበር። እየሮጠች ያስጎነጎነችው የሚመስለው ፀጉሯም ተክበስብሶና አዋራ ተሰግስጎበት ለዓይን አይማርክም። ከጉዞ ብዛት ፊቷን ያወረዛው ላብም ውበቷ ላይ አጥልቶባት ይጨንቃል።
 
እድሏ ሆኖ ግን በዚህ ሁሉ መሀል የአዲሱ ጌታዋን ልብ ማቅለጥ አልተሳናትም ነበር። ነፍሱ እስክትበር ተከይፎባት ነበር። ባለፀጋው ከሀብቱ ብዛትና ከኑሮው ጥራት የተነሳ ቤቱ የሚቀጠሩ አገልጋዮችን ልብስ በአዲስ እንዲቀየር ትዕዛዝ ያስተላልፍ ነበርና፥ እንደልማዱ ያን ቀንም በአስቸኳይ እንዲፈፅሙ ለነባር አገልጋዮቹ ትዕዛዝ አስተላለፈ። ሴቲቱ ልብሷ በአዲስ ተተካላት። ታጥባም ፀጉሯን በአዲስ ተጎነጎነች። ውበቷም በአዲስ እንደተሰራ ሁሉ ሽልቅቅ ብሎ ወጣ። …ደስም አለው። አፈቀራት። (ማለት ክየፋው ባሰበት)።
 
አዲስ ለባብሳ ገና እንደተመለከታት “ኦ የማስባት ሴት…. እስከዛሬ ድረስ የጠበቅኋት የጎን አጥንቴ…” ሲል ለራሱ አጉተምትሞ፥ እርሷ ሳትሰማ ሌሎች አሽከሮቹን (ነባሮቹን) ቅያሪ ልብሶቿን እንዲያመጡለት ጠየቀ። እነሱም “እንዴ ጌታችን እንዴት ይሆናል? ልብሶቹ ከመንተባቸው ማደፋቸው? ያዩዋቸው ዘንድ አመጥኑዎትም! ስለምን ፈለጉዋቸው?” ብለው ቢያቅማሙ ገስፆ ላካቸው። (ባርነታቸውን እንደማስታወስ…. ያው ነው አለቃና ምንዝር።)
 
ከዚያም ብር ብለው ወጥተው ብር ብለው አመጡለት። ድርቶዋን። እርሱም ተቀብሎ አሰናበታቸው። ምንጉድ እንደሆነ ለማጣራት ቢጓጉም የጌታ ትዕዛዝ ነውና ካለልባቸው በሽቅድምድም ወጡ። ካለወትሮው (ለሌላ እንደማያደርገው) ቤቱን ሲያስጎበኛትና የስራ ድርሻዋን ሲያስረዳት ቆይቶ፣ መኝታ ክፍሉ ደረሱና እዚያ ያለ ያማረ ሳጥን እየጠቆማት የስራ ጉዳዮችን የተመለከቱ ነገሮች ስላሉት ከቦታው እንዳታንቀሳቅሰው።… እርሷም ታማኝ፤ ከዚያ ወዲያ ጭራሽ ሳጥኑን ለዓይኗም ረስታዋለች። (መቼስ የዛሬ ብትሆን እንዳትነካው ‘ንኪው’ ማለት ነበር።)
 
እናም ሲኖሩ ሲኖሩ… (ሲኖሩ ሲኖሩ ለመባል የማይበቃ ጊዜ ቆይተው) ስሜቱን መቋቋም አቃተው። በትህትናም ዘከዘከላት። ደስም አላት። (የዛሬን ቢሆን በፍቅራዲስ ነቅአጥበብ ‘ልዑል አስወደደኝ’ ዜማ ታጅባ ትቀውጠው ነበር።) ብቻ የሚቀልድባትም መስሏት ነው መሰል ተሽኮረመመች። ‘ኧረ እንዴት ይሆናል?’ ስትል እያልጎመጎመች! በልቧ…. ‘ባንዳፍ! የኔ ንጉስ! የኔ ጌታ! ኧረ እንዴት ተባርኬያለሁ አያ?!’ ስትል… ደግሞ አፍ አውጥታ ‘ኧረ አትቀልድ አንተው!’ ብላ ጌታዋን ልትሳፈጥ እየዳዳት….
 
ብቻ ምንስ ብትሆን ያው ሴት ነችና ወግ የባህሉን ተግደርድራ ሆኑ። ተግባቡ። ተዋደዱ። ተኙ። ተነሱ።…. እንደ ገና ተኙ። እንደ ገና ተነሱ። ከዚያም ከናካቴው አልጋ ለመወራረስ (ለዘለዓለሙ ለመጋራት)፣ በነገር ሁሉም ‘አንተ ትብስ አንቺ’ ተባብለው ሊኖሩ፤ እግዚአብሔር ልጆች ቢሰጣቸው ደግሞ ምድርን ሊሞሏት…. ተስማሙና ተፈጣጠሙ። አሳዳሪዋ ባለቤቷ ሊሆን ነውና ሽማግሌ ላኪም ተቀባይም ሆኖ ጉድ ተባለላቸው። – ለሰሪና ላሰሪው። ድል ባለ የባለፀጋ ድግስ ተዳሩ። ላልከዳሽ፣ ላትከጂኝ ተባብለው። በወግ በማእረግ ቃል ተገባቡ።
 
ሲኖሩ ሲኖሩ… ልጆች ተወልደው፣ ቤቱ ውስጥ ተድላ ፀጋው ከነበረው በላይ በዝቶ፣ እንግዶች የሚያርፉበት – የዓለም የሲሳይ – የሚባል ቤት ሆነ። እርሷ ግን የመጣችበትን ስትረሳው ብዙም አልቆየ። ወዲያው ከንጉስ ቤት አኗኗር ጋር ራሷን አጣጥማና አስማምታ መኖር ጀመረች። ቋንቋውን፣ ስርዓቱን፣ ባህሉን፣ ዘመዱን፣ ቀዳዳውን፣ ድፍኑን… ሁሉን በአጭር ጊዜ አበጥራ አወቀች። አውቃም ልቧ አበጠ። መዝለል፣ ውጭ ውጭ ማለት አማራት።
 
ባል ነገሩን ሁሉ እየተመለከተ ይታዘባል። በዘዴ ፀባይዋን ታርም ዘንድ ሸንቆጥ ያረጋታል። እሷ እቴ… መስሚያዋ ጥጥ ሆኖባት ነበር። ጭራሽ ከአንዴም ሁለቴ ከሌሎች ሰዎች ጋር መሄዷን ይሰማል። በሰማበት ቅፅበት እሳት ይለብስ፣ ይጎርስና ወዲያው ደግሞ መለስ ይላል። ከልቡ ሳይቀዘቅዝ እንደበረደለት፣ ምንም እንዳልተፈጠረበት ሰው – ዝም። ጭጭ። ድራማውን መስራት።…. የሆዱን በሆዱ አድርጎ ‘እንዴት ዋልሽልኝ እመቤቴ?’ ይላታል። መልሷም ስርዓት ያጣ ጀመር።
 
ምሬቱ ሲደራረብ ለቅርብ ጓደኞቹ፣ ከዚያም ለቅርብ ጓደኞቿ፣ ከዚያ ደግሞ ለተከበሩ ሽማግሌዎች ተናገረ። ይመክሩ ይዘክሩለት ዘንድ ጠየቀ፤ አሳሰበ። ነገሩ መላ ቅጡን ማጣቱን የተረዱት ሰዎች ሁለቱንም ቀን ቆርጠው ሰበሰቧቸው። ከዚያም ሁለቱም አሉ ያሉትን ችግር እንዲናገሩ እድል ሲሰጣቸው፣ እርሱ እንደሚወዳትና ፀባይዋን አስተካክላ … እግዚአብሄር እስከፈቀደላቸው ጊዜ ድረስ ከርሷ ጋር አርጅቶ በተድላና በደስታ መኖር እንደሚፈልግ ተናገረ።
 
እርሷም በባልነት ምንም እንዳልበደላት ገልፃ በትዳር ታስሮ ቤት መዋሉ ስለመረራት ንብረት ተካፍላ ልጆቿን ማሳደግ እንደምትፈልግ ተናገረች። ሁሉም ተገረመ። ባሏም። ሽማግሌዎቹም። እርሷ ግን ምናልባት መገረማቸው እንዳስገረማት እንጃ…. ሽማግሌዎቹ ለዳኝነት ተቸግረው እየተቅበዘበዙ….. አንዴ ባልን አንዴ ሚስትን ቀና ብለው በ ‘እንዴት እናድርገው’ እየተመለከቱ ቆዩ።
 
እርሱም ነገራቸው ገብቶት ኖሮ ‘ፈቃዷ ይሁን’ ሲል መለሰላቸው። “ንብረት ከመከፋፈላችን በፊት ግን እስከዛሬ ስለነበራት መልካምነት አንድ ስጦታ አለኝ።” ሲል ተናገረ። እነሱም በትህትናውና በመረጋጋቱ ተገረሙ። እርሷም ግራ ገባት። ‘ምን ይሆን?’ ብለው በጉጉት ጠበቁ።
 
አላትም… “እመቤቴ ሂጂና ከመኝታ ክፍል ስትመጪ አትንኪው ያልኩሽን ሳጥን አምጪው አላት።” እርሷም የመጣችበትን ጊዜና ቦታ እንደዘነጋ
“ከየት ስመጣ?” አለችው።
እርሱም “ከገጠር።” …..የረሳችው ነገር ስለተቆሰቆሰባት ተናዳ እየተመናቀረች ከመኝታ ቤት ሳጥኑን ይዛው መጣች። ፓ! ያማረ ነበር። በወርቅ ቅብ የተለበጠ ሳጥን። ልቧ እንደ አታሞ ድም ድም ይል ያዘ። ምን የሷ ብቻ? የሽማግሌዎቹም። ከዚያም ቁልፉን ሰጥቷት ከፍታው ውስጥ ያለውን እንድትወስድ ነገራት።…..
“ምናልባት የጉዞሽን አቅጣጫ ትለዪና ትወሲኝ ዘንድ ይረዳሽ ይሆናልና ነገም በጥንቃቄ አስቀምጪው አላት።”
 
ከፈተችው። ስትመጣ የለበሰቻቸው ልብሶች ነበሩ። ቆራጣ ኮንጎዋም አለ። የተሸነጣጠቁ እግሮቿን በኮንጎው፤ ቆስቋላ ገላዋን በቡትቶዎቹ አየቻቸው። ሀዘኑ ፀፀቱ ደቆሳት። ከፋት። ግራ ገባት። ግራ ገባቸው። ግራ ተጋቡ። እግሩ ላይ ወድቃ አለቀሰች።ስቅስቅ ብላ… በእድሏ፣ በሰራላት። ባፈጣጠሯ። በመርሳቷ። በጥቃቧ። በበደሏ። በሁሉም ነገር ምርርርርር ብላ ምህረት ጠየቀች።
 
ከዚያም አብረው መኖር ቀጠሉ። ልብሶቹና ሳጥኑ ግን ቦታ ቦታቸው ተመለሱ።
 
የነገን ማን ያውቃል? 🙂
 
‘የመጣንበትን እንዲያስታውሰንና የምንሄድበትን እንዲጠቁመን፣ ላለፉት ታሪኮቻችን ሁሉ ንቅሳት ቢኖረን (ያሉንን እንዳይጠፉ ብንንከባከባቸው)’ ስል አሰብኩ። 🙂
 
******
ከላይ የፃፍኩት በልጅነቴ የሰማሁትን አንድ ተረት፥ የዛሬ 3 ዓመት፣ ሙሉው ቢጠፋኝ ጊዜ እንደመጣልኝ በራሴ ያሰፋሁት (እንጀራ አሰፋች እንዲሉ) ታሪክ ነው። ያኔ ታሪኩን እንዳስታውሰው ቆስቋሽ የነበሩኝ የሶሊያና ሽመልስ እና የዮሐንስ ኃይሉ ገጠመኞች (በንቅሳት ዙሪያ) ነበሩ።
 

189I have captured this photo while the youth are collecting a dispersed cereal (perhaps just a kilo) of an old woman, through a perforated plastic bag. Showing such kinds of courtesy for community elders is common in the residence side of Merkato area. As a reward, the youth get showered by blessings.

Dignity for the elders; they have given us out of their penury, their pride about us and our achievements is an ocean deep, and their blessings are relentless.

 

ተስፋዬ ገብረአብ እና የበዕውቀቱ ስንኞች

ውብሸት ታደለ

ተስፋዬ ገ/አብ በዕውቀቱ በስም ዙሪያ የፃፈውን ፅሁፍ በማጣቀስ በዕውቀቱን የማንነት ቀውስ ውስጥ እንዳለ የሚገልፅ ፅሁፍ ፅፏል፡፡ከበዕውቀቱ ፅሁፍ ውስጥ በዕውቀቱ የግል ማንነቱን የፈታበትን መንገድ መመልከት እንደምንችል ፅሁፉም ከማንነት ጋር የሚያስተሳስረው ጉዳይ እንዳለ እኔም አምንበታለሁ፤ በቀደመው ፅሁፌም ገልጫለሁ፡፡

በመሰረቱ ማንኛውም ሰው የማንነት ጥያቄ አለበት፡፡ የማንነት ጥያቄ የሰው ልጆች ሁሉ የሚገጥማቸው የህይወት አንዱ ገፅታ ነው፡፡ ጥያቄው ያለው የማንነት ጥያቄህን እንዴት ትፈታዋለህ የሚለው ላይ ነው፡፡ አንዳንዱ ጥያቄውን በማፈን ለመፍታት ይሞክራል፡፡ አንዳንዱ ከአካባቢው አስተሳሰብ ጋር ራሱን በማላመድ በሌሎች መንገድ ማንነቱን ለመፍታት ይጥራል፡፡ አንዳንዱ የብሄር ፖለቲካ ራዲካሊስት መሆን ለመፍታት ይፍጨረጨራል፡፡ ወዘተርፈ፡፡

እንደበዕውቀቱ ያሉ ጥቂቶች ግን የማንነት ጥያቄን በዘልማድና በኋላቀር መንገድ ሳይሆን በሰለጠነ መንገድ ግለሰብ በመሆን (ሰው በመሆን ይፈቱታል)፡፡ የበዕውቀቱን ለዬት የሚያደርገው ይህን ግላዊ ጥያቄውን አደባባይ ላይ አውጥቶ መልካም ስራ ለመስራት ተጠቅሞበታል፡፡ አስቂኙ ነገር የበዕውቀቱ ግለሰብ መሆን ብዙ ብሔርተኞችን የማንነት ቀውስ ውስጥ ሳይከታቸው አልቀረም፡፡ የቆሙበትን መሰረት ንዶ እንደግለሰብ እንዲቆሙ ሲጠይቃቸው የሚያነበንቡት ተረት ሁሉ ባዶ ሆነባቸው፡፡ ማንነታቸው በቡድን ተረት ላይ የቆመ ነበርና፡፡

እንግዲህ ተስፋዬ በዕውቀቱ የማንነት ቀውስ እንደገጠመው በማሰብ የበዕውቀቱ ቀደምት የጥበብ ስራዎች ውስጥ የቡና አተላ እንደሚያነብ ሰው ሲወራጭ የነበረው ለምንድነው? የበዕውቀቱ አያት ስም ኦሮምኛ መሆኑ ብርቅና ለማንነት ቀውስ የሚዳርግ እንግዳ ነገር ስለሆነ ነው? ተስፋዬ የኢትዮጵያን ህዝብ ሁኔታ አልተረዳውም እንዳልል ቢያንስ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ስለሚከታተል የፖለቲከኞችን ስም ሳያውቅ የሚቀር አይመስለኝም፡፡ በነገራችን ላይ የማንነት ቀውሱ ተስፋዬ ገ/አብን ራሱን የሚመለከት ይመስለኛል፡፡ በትውልድ ቦታና በዘር ቆጠራ መካከል የተወጠረች ባተሌ ነፍሱን ተንኮል በመስራት የሚያሰቃያት ማንነቱን መፍታት አቅቶት ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ ተስፋዬ በዕውቀቱ የሰነዘረበትን በማስረጃ የተደገፈ ጡጫ ለመቋቋም እንዲህ ዓይነት ጭቃ ውስጥ መግባቱ በበኩሌ አቅመ ቢስነቱን ስለሚያሳዬኝ ቢያስቀኝም ያሳዝነኛል፡፡ አቅመ ቢስነቱን ለማወቅ ወደትንተናው ይዣችሁ ልግባ፡፡

በመጀመሪያ ተስፋዬ የበዕውቀቱን “ዳዊትና ጎልያድ” የተሰኘ ግጥሙን በመጥቀስ ግጥሙ ኃይማኖትን የሚያጣጥል እንደሆነ ለማሳዬት ይፍጨረጨራል፡፡ በሱ ቤት ከአክራሪ ኃይማኖተኞች ጋር ሊያጋጨው ነው፡፡ እስኪ ለዳኝነት እንዲረዳን ግጥሙን ልጥቀሰው፡-

እግዜርና ዳዊት አብረው ተቧደኑ
ብቻውን ታጠቀ ጎልያድ ምስኪኑ
አንዳንዱ ተገዶ ለሽንፈት ሲፈጠር
በጥቅሻ ይወድቃል እንኳንስ በጠጠር

ግጥም አንብባችሁ የምታውቁ ሁሉ እባካችሁ የዚህን ግጥም መልዕክት ንገሩኝ፡፡ ጎልያድን የጣለው ዕጣ ፈንታው እንጅ የዳዊት ጠጠር ኃይል ኖሮት አይደለም የሚል መልዕክት አይደለምን በዕውቀቱ ያስተላለፈው?

እንቀጥል…

ተስፋዬ እንዲህ ይላል፡ “ከሚስጥራዊ ስንኞቹ መካከል ጥቂት አገኘሁ” ይልና የሚከተለውን የበዕውቄን ግጥም ይጠቅሳል፡-

በነፍሴ ሰማይ ላይ
ቢሰርቅ ጣምራ ፀሃይ
አንዱን ጋርጃለሁ
ሌላው ደምቆ እንዲታይ

“ምን ማለቱ ነው ብዬ ሳስብ የአቶ በዳዳን ኦሮሞነት ሸሽጎ አያቱ ባልሆነ ስም እየተጠራ መቀጠሉን እየተቃወመ ይመስላል አልኩ” ይለናል ተስፍሽ ባተሌው (እዚህ ጋ እንድስቅ ይፈቀድልኝ ሃሃሃሃ… የምር ይህን ፅኁፍ ስፅፍ ሳቄ እያቋረጠኝ እንደነበር መደበቅ አልሻም)፡፡ እባካችሁ ነፍስ የስጋ ዘርን የምትወክልበትን ይህን በተቃርኖ የተሞላ የስነፅሁፍ ትንታኔ በመፃፍ ላዝናናችሁ ተስፋዬ አጨብጭቡ፡፡ ልጁ “ነፍስ” ብሎ ገጠመ፤ ተስፍሽ “ስጋ” ብሎ ተረጎመለት፡፡ ወይ ጉድ!

ተስፍሽ በማስከተል የጠቀሰው የሚከተለውን የበዕውቄን ግጥም ነው፡-

ቀንድ አውጣ ሆይ!
ውብ ዛጎልህ አማለለኝ
ከጎጆህ ላስወጣህ ነው (ይቅር በለኝ)
‘በዝግ ዓለም ሰማይ ጣራ ነው’ ይባላል
ያለውበት ነው እንጅ ያለቤት መኖር ይቻላል

እንግዲህ ለመሳቅ ተዘጋጁ፤ ተስፍሽ ይህን ግጥም ሲተነትነው እንዲህ ይላል፡-

“እነዚህ ስንኞች ለኔ የሰጡኝ ትርጉም በዕውቀቱ አቶ በዳዳን ከተሸሸጉበት ዛጎል ጎትቶ ለማውጣት መወሰኑን ነበር፡፡ በርግጥም እንደፎከረው ፈፅሞታል፡፡ ያለውበት መኖር እንደሚቻል ለማሳየት ሞክሯል፡፡”

እና ይሄ ሰው አያሳዝንም? ሃሃሃ እስኪ ተመልከቱ… በዕውቀቱ “ያለቤት መኖር ይቻላል፤ የማይቻለው ያለውበት መኖር ነው እንጅ፡፡ ስለዚህ ቀንዳውጣ ሆይ ውብ ዛጎልህን ልዋብበት፤ ያለቤት መኖር ስለምትችል” በሚል ግልፅ ቋንቋ የሰው ልጅ ካለውበት መኖር እንደማይችል በመግለፅ በተለይም ውበትን የምታስሰውን ገጣሚ ነፍሱን ሊገልፃት ሲሞክር፣ ተስፋዬ ግን አማርኛውን ፍፁም ገልብጦ “ያለውበት መኖር ይቻላል” ብሎ ተረጎመው፡፡ ይህ ነገር ግጥም አንብቦ ለማያውቅ ማንኛውም አማርኛ ቋንቋን ለሚያውቅ ሰው ግልፅ ነው፡፡ ወይ ተስፍሽ!

ተስፍሽ ስለአባ ገብረሃና የተፃፈውን ግጥም ጠቅሶ የመተንተን ሙከራ እንኳን ሳያደርግ የልጅ ተንኮል ሞክሮ አልፎታል፡፡ እንዴት ለማያያዝ እንደሞከረ ለራሱ እንኳን የገባው አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ እዚህ ላይ ጊዜ አላጠፋም፡፡

ወደሌላው እንለፍ…

“በተለይ ገዢዎች ላይ ቅሬታና ቂም እየያዘ እንደመጣ የሚጠቁሙ ከጥቂት በላይ
ስንኞቹን ታዝቤያለሁ፡፡ አንዷ እንዲህ ትላለች፡”

አልወጣም ተራራ ደመናውን ላብስ
ቀስተ-ደመናውን ሽቅብ ልቀለብስ
አልዋስም እኔ ካቡነ ተክሌ ክንፍ ከያዕቆብ መሰላል
እኔ መውጣት ሳስብ ሰማዩ ዝቅ ይላል

… ዝቅ ይላል ያለው ሰማይ ስልጣን ነው”፡፡

ሃሃሃ… ይሄ ሰውዬ ግጥም ሊያስጠላኝ እኮ ነው፡፡ ይሄን የግጥም ግንዛቤውን ይዞ ነው በየመፅሃፎቹ ግጥም የሚደነጉር? ይህ ግጥም የሰው ልጆችን የምኞት ኃይልና የማድረግ አቅም የሚያሳይ ግጥም ነው፡፡ የእኛ ፍላጎትና ኮሚትመንት ካለ ሁሉን ነገር ማድረግ እንችላለን የሚለውን የምኞት ኃይል የሚገልፅ ግጥም ነው፡፡ ሌላ ነው ትርጉሙ የሚል ሰው ካለ ያስረዳኝ፡፡ ተስፍሽ ካለው ስልጣን ቅብጥርሶ ጋር የተያያዘ እንዳልሆነ ግን ከበዕውቀቱ በሚልቅ እርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፡፡ አለበለዚያ ግጥም ማንበብም ሆነ መፃፍ ባቆም ነው የሚሻለኝ፡፡

“የበዕውቀቱ ቀደምት ግጥሞች ከአሜን ባሻገር ላይ ከተጠቀሱት አቶ በዳዳ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማዬት ሞክሬያለሁ” ይላል ተስፍሽ ተንትኖት ልቡ ውልቅ ብሏል፡፡ አንድ ጤነኛ ፊደል የቆጠረ ሰው እንዴት ይሄን ሁሉ የአንድ ገጣሚ ግጥም ከአያቱ ስም ጋር ለማያያዝ ይሞክራል? እንደዛ ማሰቡ ራሱ የጤንነት ምልክት ነው?
“በዕውቀቱ የመፅሃፉን ርዕስ ለምን ‘ከአሜን ባሻገር’ ሲል እንደሰዬመው ምስጢር አልነበረም፡፡ በቀጥታ ከአያቱ ከአቶ በዳዳ ጋር ይያያዛል”

ይሄ ሰው አቶ በዳዳን ምን አድርጉ ነው እሚላቸው? አሁን ከአሜን ባሻገርና አቶ በዳዳን ምን አገናኛቸው? ተስፋዬ ይቀጥላል፡- “እሱም (በዕውቀቱም) በዚያው ምዕራፍ ላይ የሚከተለውን ገልፆ ነበር” ይልና በዕውቀቱን እንደሚከተለው ይጠቅሳል፡- “የተለያዩ ባህሎችን በአንድ በገና ውስጥ እንደተወጠሩ አውታሮች ማስተናገድ በማይታወቅበት ጥንታዊ ማህበረሰብ ውስጥ ግለሰቦች የገናና ባህሎችን ምልክት አሜን ብለው ከመቀበል ያለፈ ምርጫ አልነበራቸውም” ይሄ ምን ማለት ነው? መልቲ-ካልቸራሊዝም ስለማይታወቅበት ዘመን በማስታወስ ያን ዘመን በአሁኑ ዘመን ዕይታ እንዳናዬው ከመናገር ውጭ ሌላ ምን ትርጉም አለው?

ተገርማችሁ ሙቱ ብሎን ተስፋዬ የበዕውቀቱን አንድ ግጥም እንደሚከተለው ይጠቅሳል፡፡ የግጥሙ ርዕስ ‘ሉላዊነት’ ሲሆን ተስፍሽ ግን ለአተላ ንባቡ እንዲጠቅመው ርዕሱን ‘ሉአላዊነት’ በሚል አቅርቧታል፡፡ ተስፋዬ ብሶት ያዘለ ነው ብሎ የገለፀው ግጥም ይሄው፡-

የጋራችን ዓለም የጋራችን ሰማይ
የብቻችን ህመም የብቻችን ስቃይ

ትንታኔው፡- “በአንድ አገር ስር ዜጎች አብረው እየኖሩ፣ አንደኛው ወገን ስቃይ እንደሆነበት ሲነግረን አልገባ ብሎን ይሆን?” ይላል የገ/አብ ልጅ፡፡ ግጥሙ የሚያወራው ስለሉላዊነት (ግሎባላይዜሽን) ሆኖ ሳለ ተስፋዬ ግን ርዕሱን ቀይሮ ጠለፈው፡፡ በዕውቄ ግሎባላይዜሽንን ሊሳለቅበት የሞከረውን ግጥም ሰውዬው በቡና አተላ ስልት አነበበው፡፡

ደከመኝ፡፡ እስኪ በቀጣይ ክፍል ልጨርሰው እሞክራለሁ፡፡ እስከዚያው ተስፋዬ እንዲህ ጭቃ ውስጥ የገባው ለተንኮል ብሎ ነው ወይስ ተስፋዬ ይህን እንኳን መረዳት የማይችል ተራ የወሬ አሰናዳኢ ነበር የሚለውን ጥያቄ አስቡበት፡፡ እኔ ደግሞ የዚህን በሽተኛ ሰውዬ ፅሁፍ ከቁምነገር ቆጥሬ ጊዜዬን የማጠፋው ለምንደነው የሚለውን ጨምሬ በቀጣይ ክፍል እመለሳለሁ፡፡

ሰናይ ጊዜ!

ቫላንታይንስ ቀን…

ፍቅርን መካፈል፣ ፍቅርን መጋራት፣ ፍቅርን መዘከር፣ ፍቅር መስጠር፣ ፍቅርን ማውራት ሸጋ ነው። ዓመቱን ሙሉ በኑሮ ዱብ ዱብ እና በየእለት ንትርክ ተጋርደው የተዘነጉ የፍቅር አጋሮች፣ ወዳጆች እና ቤተሰቦች፥ በዚህ ቀንም ቢሆን ከወደቁበት፥ ሳይረገጡ በፊት ኧፈፍ ተደርገው፣ ትቢያቸው ረገፍ ረገፍ ተደርጎ ወግ ማዕረግ ቢያዩ ደስ ይላል። የእናቶች ቀንን የቀዳን፣ የሴቶች ቀንን የቀዳን፣ የሌላ የሌላውንም ቀን የቀዳን… የወደደ የፍቅር ቀንን (valentine’s day) ቢቀዳ ክፋት የለውም። ባይሆን፥ ወግ ወጉን ብቻ ተይዞ፣ ስነስርዓታዊ (ceremonial) በሆነ ዘይቤ ስንተራመስ መጠቋቆሚያ እንዳንሆን፥ ከቀይ ልብስ ባለፈ ልቦቻችንን እና አኗኗራችንን ስለማቅላት እንምከር።
ቫላንታይንስ ቀን ማለት ማስመሰል የሚሰበክበት ቀን አይደለም።
ቫላንታይንስ ቀን ማለት ግድ ከየቤት ውጭ የሚታደርበት ቀን ማለት አይደለም።
ቫላንታይንስ ቀን ማለት፥ ወንድ ሴቷን እንደሚያዝናና እና እንደሚጋብዝ ተደርጎ የሚታሰብበት ቀን አይደለም። (ሰምታችኋል “ከወደድከኝ ግሎባል ሆቴል ውሰደኝ” የሚል አሳፋሪ ዘመኑን ያልዋጀ ማስታወቂያ?)
ቫላንታይንስ ቀን ማለት፥ ሴቶች የወንድ ጥገኛ ናቸው ብለን የምናቀነቅንበት ቀን አይደለም።
ቫላንታይንስ ቀን ማለት፥ ተለክተው ተበድረው ቀይ ቀሚስ የሚያስቀድዱበት ቀን ማለት አይደለም።
ቫላንታይንስ ቀን ማለት፥ ስጦታ ስላልተሰጠን የምንኮራረፍበት ቀን አይደለም።
ቫላንታይንስ ቀን ማለት፥ እስከዛሬ ያለው በደል እና ግፍ በዝምታ ታልፎ ለዚህ ቀን ታርቀን ከነገ ጀምሮ ወይ መልሰን የምንዘጋጋበት፣ አልያም ሁሉን ረስተን አዳፍነን የምንዘልቅበት ቀን ማለት አይደለም።
ሲሆንስ፥ ይህን ቀን ታክከን ስለሆነልን ነገር ብናመሰግን፣ እድለኛነታችንን ብናደንቅና፣ ፍቅራችን እንዴት ወደተሻለ ደረጃ እና ሁኔታ ማሳደግ/ማሻገር እንደምንችል ብንመክር ዓላማውን አይስትም።

flowers-roses-red-rose-1680x1050-wallpaper_www.wallpaperhi.com_66

Happy Valentine’s Day!
ፍቅር ይብዛልን!

To the king!

He came to earth 71 years ago, on this day; and died when he was only 36. As if ‘effectiveness’ means his life, he lived it well tho. And he is living in us forever. I wonder, how boring would life be, hadn’t it been for me to learn about music, him and his kinds?
 
Whenever I recall the goodness of life and the jewels; the hopes that everything will be alright, and the joys in my life; or whenever I feel achieved and acquainted with new things, or being on the right track towards conscience, passions and career, my heart looks like this face of him 🙂
tumblr_static_tumblr_static__640
Happy birthday the king, the one and only, Bob Marley
 
I will always love you!