አንዳንዴ…

በሰላሙ ጊዜ የሆድ የሆዳችንን እንጫወት ነበር። ያኔ እኔና አንቺ አፍ አፋፍ፥ ሚስጥር የባቄላ ወፍጮ ነበረ። ሁለታችንም ጋር የሚያድር የለም፤ ጨጓራችን እስኪወቀር፣ ምላሳችን ከረጢቱ እስኪራገፍ ድረስ ተናዘን፥ በወሬ ዱቄት የታጨቀ ከረጢት ከረጢታችንን ሸክፈን እንሄድ ነበር።

ነገር ያጋጨን እለት ያቆርሽውን ሁሉ አውጥተሽ ትነቁሪኝ ጀመረ። (ማቆር መቻልሽ የልብ ልብ ሳይሰጥሽም አልቀረ።)

መጣላታችን ልብሽ ውስጥ ሲነደፍ አገር በምስጢሬ የወሬ ስንጥቁን፥ ኩታ ሸምኖ አለበሰ።

ወዳጅ ያፈራኹበትን ነጻነትና፣ ያኔ ያወራሁት ነጻ ወሬ ሰንኮፍ ሆነው ሰውነቴ ላይ ተሰኩ። ተራማጅነትንም እረፍትንም ነሱኝ። ወዳጁን እንደቀበረ ሰው ቁም ለቁም ጢሜን ነጭቼ አገጬን ተገጠብኩ።

ቆጨኝ።

ክፉኛ ቆጨኝ።

ማውራቴ ቆጨኝ።

መስማትሽ ቆጨኝ።

ማወቄ ቆጨኝ።

ምን ነበር ባላውቅሽ ኖሮ? አንቺን ከማውቅሽ ምን ነበር ሌሎች ሌሎች ሰዎችን ባውቅ?

ማመኔ ቆጨኝ።

መጣላት የለም ያስባለኝ አፍቃሪ ሞኝነቴ ቆጨኝ።

ጆሮ ስላለሽ ቆጨኝ።

አልዋሽሽም፥ አፍ ስላለኝም ቆጨኝ።

“የሽንገላ አንደበቶች ዲዳ ይሁኑ” ይላል መጽሐፍ። እኔ ደግሞ ቅልብልብ አንደበቶችም ዲዳ ይሁኑ አልኩኝ።

“ቆይ ለስንጣላ” ብለሽ የሰማሽኝ ይመስል ስንጣላ የሰማሽኝን ሁሉ ቃል በቃል ለማሳጣት ተጠቀምሽበት።

ሚስጥሬን አሸሞርሽበት። ገመናዬን ወዳጅ አፈራሽበት።

የቅርብ ነበርሽና አንቺ ብለሽ ማን ሊጠራጠር?

ባለጊዜ ገድ የሰመረለት አትራፊ ነው። ቢጨምርም ቢቀንስም ገዢ አያጣም።

የፈለግሽውን ጨመርሽ። የፈለግሽውን ቀነስሽ።

“አወራሽ። ለፈለፍሽ። ሞላ አገሩ ሰማ።

ግደይኝ አንቺ ልክ ከጠላሽኝማ” አልልሽም።

እሱ ዘፈን ነው። “እዬዬም ሲደላ ነው” ይባላል፥ እሱ ፍቅር ነው። እሱ የ”እፍታው” ውጤት ነው። የእፍታው ጊዜ እንኳንና ገድለሽ ሄደሽ “ግደይኝ”፣ ሌላ ሌላም ይባላል። “ተባብረን ካልገደልን”ም ይባላል።

“ቆዳዬ ተገፎ፣ ይሁንልሽ ጫማ፣
ስጋየም ይደገም፣ ላንቺ ከተስማማ”

ይሄን ያለው ዘፋኝ መቼም “ይቅር ይበለኝ” ብሎ ጣቱን ስንቴ ነክሷል? ፍቅር እፍታው ላይ ደስ ይላል። የጅንጀናው ሰሞን ዓለም ነው። እንደህጻን ባለ ንጽህና ቅድስናን ያስናግራል። “ይድፋሽ” እስኪመጣ ድረስ “ልደፋ፣ ልሙት” ያለ ነው። “ወይ አምላኬ” ብሎ ማማረር እስኪተካ ድረስ “I am lucky” ማለት ደንብ ነው።

የእፍታው ጊዜ፥ አመሉም፣ ቋንቋውም ጉራማይሌ ነው።

“ጉንፌን አውልቄ ለበስኩኝ ቦላሌ”

በፍቅር ስንነፋረቅ አንቺን እመስል ብዬ ልቤ ላይ ያደረግኩትን ጉንፍ አውልቄ፥ የልቤን ቦላሌ ጥለሽው ከሄድሽበት አንስቼ ለብሼዋለሁ። ውሰጅልኝ የልብሽን ጉንፍ!

ደግሞ ራቁቴን ስታስቀሪኝ የቦላሌና የጉንፍ ወግ ቀርቶ አገለድምበት የነገር ሽርጥ ፍለጋ ተፍጨረጨርኩኝ።

ቀን አስማምቶን ተዋውቀን ስንኖር የመሰለኝ፥ ውሸት መሆኑን ቀን አጋጭቶን ስንተዋወቅ ገባኝ።

በነገርሽ ላይ፥ ይህን ይህን ሁሉ ያወቅኹት ዛሬ አይደለም። ነገር ባጋጨን ቅጽበት ነው።

እናቱን ነገር!

ስጉ አደረገኝ። ቤቴ እንደተዘረፈ እንዲሰማኝ አደረገኝ። ራቁቴን አስቀረኝ። ሳይሞላ የሞላ ያስመሰለውን ጎኔን ሁሉ ገላልጦት አንዘፈዘፈኝ። ያለኝን ሁሉ ይዘሽብኝ ስትሄጂ ተሰምቶኝ “ሂጂ” ስልሽ አነባሁ። ሂጂ-አትሂጂብኝ መሳቂያ አደረገኝ።

ግን ውሸት ምን ይሰራል? “አትሂጅብኙ” እርቃኔን ለመጠበቅ ነበር። ሰው የሚስጥር ተካፋዩን ደፍሮ “ሂጂ” አይልም። ቢል ወየው ለራሱ! ሚስጥር መካፈሉ ቢቀርም ልማድ አለ። ልማድ አጉል ነው። “ለገና የገዛኸው በግ፥ ስጋ ስላለ ለጥምቀት ይሁን ብለህ ብትተወው፣ ለጥምቀት ለማረድ ያሳሳህና በግ አርቢ ሆነህ ትቀራለህ” ይላል ወንድሜ። የግጭት ማግስቱ ነጻነት የመስጠቱን ያህል፥ ከነገ ወዲያው ወፍራም ማቅ ያለብሳል።

ያኔ “ሰዶ ማሳደድ ካማረህ ዶሮህን በቆቅ ለውጥ” ነው ጨዋታው።

ይሄን ተረት የቀመረው ሰው፥ የእኔ ቢጤ ይመስለኛል። ሳይቸግረው ሰዶ ሚስጥሩን ጥበቃ ሲያሳድድ የኖረ የኔ ቢጤ።

ምን ታረጊዋለሽ?

እጣ ፈንታ ነው!

አንቺ ሳትኖሪ በፊት… ድሮ ድሮ ግን ሕይወት እንዴት ነበር? ውሎ ገባው የት የት ነበር? ላንቺ ሳልነግርሽ በፊት ሚስጥሬን የትኛው ቋቴ ውስጥ ነበር የምሸሽገው? ወይስ ካንቺ በፊት ሰማይና ምድሬ ላይ ሚስጥር አልነበረም?

ሚስጥር ማጋራትን ካንቺ መምጣት ጋር ተማርኩኝ።

ሚስጥር መጠበቅን ካንቺ መሄድ ጋር ቀሰምኩኝ።

ይብላኝ የሸራረፍኩትን ለምታገኘኝ ለባለተራዋ ውዴ! ይብላኝ በተንሸዋረረ ዐይን እያየሁ፥ በተሸራረፈ ልቤ ውሃ ለምጣጣ እኔ!

እርሳት እርሳት አሉኝ እንዴት እረሳለሁ፥
ሞኝነቴን ብንቅ፥ ወዴት እበልጣለሁ?!

Celebrating wo/men…

Celebrate wo/men, celebrate yourself, live well…
 
We all should empower women that it means empowering ourselves; it is empowering the society; it it utilizing all our resources and excelling life; it is living life to the fullest; it is rationality; it is humanity; it is how it should gonna be. Come on!, how is life thinkable without wo/men? We should know this properly, we should tell the sky and the earth, and practice it duly.
 
Taking the lion share, no wonder, women should uplift themselves; they should uplift men; they should uplift the society; they should cooperate in the process of generation replacement, and nurture uplifted children as an already determined fate, with the God’s will; that they should say “NO” for any oppression by their most intimate men, by people that they plan and commit their life with; …nor they should oppress anyone, and be civilly and intellectually arrogant.
 
They shouldn’t expect a miracle to come their ways to triumph over life, nor wait for someone else to work for them; no one should expect of course! …we all should struggle rather; we all should get together, make comfortable ways and go through altogether. Then, the legacy for children will be a decent place, where life will be cherished, and death will be celebrated.
 
By the way, I’m not a feminist… I even am against its very inception (the way I understand it); though it is driven by an androist world, the concept irritates me at all. I’m a humanist rather. (…but, if being ‘feminist’ means, being an activist for gender equality, proudly, I’m one hell of it.) I can’t think segregating human fellows into women and men. Apparently, no one has contributed any for the gender s/he has, nor s/he has done fault to be born having the sex s/he has.
 
Wake up brother! “brother Jacob 😉 “, and uplift your home!, empower the executive of your home; never undermine her power, nor take her for granted; respect yourself and never objectify your woman, as saying ‘I love you’ for someone that yourself has dared to objectify is foolishness at its worst level. Never do that my man; never ever, even, when you think, on her foolishness.
 
Wake up sister! “sister 😉 “, and uplift your home and the lives inside it!, fortify your abilities, unleash the potentials in you, utilize resources, dig for opportunities to come your ways, be respectful, be responsible and trusted, …and meet your soul truly! …that you will give birth for &rear an uplifted, other things being equal!
 
To respect each one another, and to contribute for the construction of a better place to bring neonates to, ‘the sky is the limit’.
 
– I think!
 
Lots of love!
 
#makeithappen #internationalwomansday #IWD2016

እንዳለመታደል…

12767525_991101850982528_2078982365_nአያቶቻችን፥ ደፍሮን የመጣን የጠላት ጦር ስለሰውነት ዋጋ ከፍለው በድል መልሰውት ዛሬም ድረስ አንገታችንን ቀና አድርገን የምንሄድበትን፣ በየትኛውም ቦታ “ኢትዮጵያዊ ነኝ” ስንል፥ ዝም ብሎ ሰው እንዳልሆንን የሚያስመሰክርልንን የድል ታሪክ አበረከቱልን።

ኢትዮጵያን ጠርተን ዓድዋን ያስታወስነው የውጭ አገር ዜጋ፥ በልቡ “ኖር” ብሎ ጎንበስ ቀና ይልልናል። – ይሄ ቁመቱ ነው።

ወገን፥ “ጨርቄን፣ ማቄን፣ ልጄን፣ ቤቴን” ሳይል፥ እስካፍንጫው ከታጠቀ ዘመናዊ ጦር ጋር በጦርና በጎራዴ ገጥሟል። አፍሮም አልገባም፤ በድል እንጂ! – ይሄ ጀግንነቱ ነው።

የአገር ሉአላዊነት እንጂ ብልጭልጭ ስልጣኔ አላጓጓውም። የሰው ልጆች ነጻነት እና ክብር እንጂ፥ ቁሳቁስ አላታለለውም። እኛ እንድንኖር እሱ አለፈ። እኛ እንድንቆም እሱ ወደቀ። – ይሄ ምስጢሩ ነው።

ይኸው እኛ ደግሞ “ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ?” በማስባል ዝንታለም የሚያስደንቀውን የአድዋ ድል ታክከን በዘር ተከፋፍለን እርስ በርስ ስለጥላቻ እና ስለዘር፥ ዋጋ ከፍለን እንዋጋለን። ታሪክን ከባለታሪኩ መንጥቀን ለማላቀቅ ላይ ታች እንላለን። ሁኔታችን ሁሉ አዟዙሮ እንደማያይ ነው። ነገራችን ሁሉ ዋጋ እንዳልተከፈለበት ነው። ቆም ብለን የምናደርገውን ብናይ ኖሮም እንኳን በሌላ ሰው፥ በራሳችን ትዝብት ውስጥ መውደቃችንን እንገነዘብ ነበር። እውን፥ የአድዋ ድል የሌላ አገር ድል ቢሆን ኖሮና፣ ታሪኩ ተዘርዝሮልን ብንሰማው ኖሮ፥ አለመደነቅ እንችል ነበር?

አንዳንዴ፥ “ብዙ ያልተደረገልን ሰዎች ብንሆን ኖሮ፣ ብዙ ታሪክና ቅርስ ባይኖረን ኖሮ፣ ተፈጥሮ ለእኛ ባያዳላ ኖሮ፥ ምናልባት ዛሬን ወደ ስልጣኔ ለመሸጋገር እንበረታ ነበር ይሆን?” እላለሁ። ይህም የሞኝ ሀሳብ ነው፤ እንጂ፥ እንዲህ ያለ ድንቅ ታሪክ፥ ዓለም ሲሰማው ሲደነቅበት የኖረን ነገር ማን “የእኔ ባይሆን ኖሮ እበረታ ነበር” ይላል?

የጀግኖቹ በረከት ይደርብን!

#VictoryOfAdwa #Adwa120 #Ethiopia #የአድዋ_ድል

Graphics: Ashu

አ ድ ዋ

ልዩ፣ ንዑድ፣ ፅሩይ ፅዋ፥
የደግነት ጥልቅ ጣዕሟ፥
የመስዋዕት ጣሪያ፣ ማማ፤
የክብረት ጫፉ፣ ከተማ፤
የኩራት፥ የድል ፏፏቴ
የመውደድ፥ ሰፊ ገበቴ፤

“ትናገር…
ትመስክር!”

“አድዋማ ጦርነት ነው!”
በባለጌ ደፋር ግብዣ፥
ሰው ስለሰው የቀመሰው፣
ሰው ስለሰው ያፀደቀው፤
ነጻነት፣ ክብረት ኀሰሳ፣
ሰው ስለሰው የከፈተው፣
ሰው ስለሰው የከተተው፤
ቀን አሻግሮ፥ ሩቅ አይቶ…
ተንኮል ሴራ፣ ግፍ ለይቶ፣
በባርነት ዳፋ ግምት…
ያልወደቀውን ሊደግፍ፥
ያልዘመመውን ሊያነሳ፣
ሰው ስለሰው የገጠመው፣
ሰው ስለሰው ያሸነፈው…
ሰው ስለሰው አይቶ ፍዳ፣
ሰው ስለሀገር ቆጥሮ አበሳ፤
አድዋማ ብድራት ነው፥
ሰው ስለሰው የከፈለው።

“ሰው ሞቷል ሰው ሊያድን፥
ሰውን ሲያከብር!”

አድዋ ሰደድ ቁጣ ነው፤
የሰው ንብረት ተመኝቶ፣ ግዛት ሊያሰፋ ሽቶ፥
በድፍረት ልጥ የታሰረ፥ ተስፋ ሸክፎ መጥቶ፣
ከታፈረች መሬት ጥሎ፥
በዘመናይ ፍጭርጭሪት፥ ደቃቅ ልቡ አጉል አብጦ፣
ሰውነት ላይ ሊረማመድ፥ ሲንቆራጠጥ ወጥ ረግጦ፣
በቀቢጸ ወኔ ሲርድ፥
ለታየ ቅብዝብዝ ደፋር፣ ለነበር ከንቱ ሶላቶ፥
የተመለሰ አጸፋ፥ የተከፈለ ዋጋ ነው፤
ይኸው፥ ከያኔ አንስቶ…
ሰው በሰው ቁጣ ተረትቶ፣
ሰው በሰው ሕይወት ተገዝቶ…

“በክብር ይሄዳል…
ሰው ሊኖር፥ ሰው ሞቶ”

ቡርቂ ጡርቂያሙን ሆዳም፥
ስልጣኔ ያልደገፈው፥ ያልበረታን ከንቱ ፈሳም
አሳድዶ የተቀዳጀው፥
ሰው ስለሰው ያስተረፈው፥
ሰው ስለሰው ያወረሰው፥
አድዋማ ነጻነት ነው፤

“የተሰጠኝ ሕይወት ዛሬ በነጻነት፣
ሰው ተከፍሎበታል፣ ከደምና ካጥንት”

አድዋ ልዩ “መንፈስ ነው”
ሰውን ከሰው ጋር አጠራርቶ፣
ሁሉን በፍቅር አንጠራርቶ፣
እርስበርሱ አደራርሶ፥ አንዱን ካንዱ አለካክቶ፤
ከየእምነቱ፣ ከየቋንቋው፣
ከየቤቱ፣ ከየቀዬው…. ከየአስተሳሰቡ ጎራ፣…
ሆ ብሎ ተነስቶ፣ ከትቶ፥
በፍቅር ትዕዛዝ ተጠርቶ፥
“ማርያምን” ተብሎ ዘምቶ፣
በድል ያመላለሰው…
አድዋስ ቋንቋ ሰዋሰው፣
አድዋስ የክብር ጫፍ ነው፣
የአንድነት፣ የኩራት፥ ሙላት፣
ቀና አስብሎ አረማማጅ፥
ከዳር ዳር ሁሉን አዛማጅ፤

“በደግነት በፍቅር፣ በክብር ተጠርቶ፥
በክብር ይሄዳል… ሰው ሊኖር፣ ሰው ሞቶ።”

አድዋ ኧረ ሌላ ናት…
‘ከሶላቶ ጋር ክርክር፣ የእንካ ሰላንቲያ ጨዋታ፥
በተገጠመበት ቅጽበት፥ በተጀመረበት አፍታ፥
የምትሰማ ውብ ነገር’
ልብን ውርር… ጆሮን ኩርር…
የምታደርግ፥ ውድ ስሜት፣
ጫፍ አልቦ፥ እሷ ራሷ ጫፍ፣
የመርቀቅ አናት ከፍታ፥
የመቅለል ዳር፣ የማነስ ቋፍ፤
የአጃኢባት ሜዳ፥ ጉብታ።

“ትናገር አድዋ፥ ትናገር ሀገሬ፣
እንዴት እንደቆምኩኝ ከፊታችሁ ዛሬ።”

ፍቅርን የፈተሉበት፣ ኩራትን ያለቀቁበት፣
ድርና ማጉ ተስማምቶ፥
የሀበሻነት ልዩ ጋቢን፥ “መንፈሱን የሸመኑበት”
ለነፍስ ግዥ፥ ነፍስ ሸጠው…
ስጋን ለስጋ ገብረው፥ ወገንን የታደጉበት፣
ሀገርን የከለሉበት፣ አህጉር ያስታፈሩበት፣
ግዞትን የሸቀጡበት፣ ነጻነት የሸመቱበት፤
የማዕዘን ክቡር ድንጋይ፥ ወሰን ነው አድዋ ማለት፤

“አፍሪካ፣ እምዬ፣ ኢትዮጵያ፥
አዪዪ… ተናገሪ፣
የድል ታሪክሽን አውሪ።”

አድዋማ…
ጥቁርን ያስፈለቀቀ፣ ከነጭ ጥርስ ያስለቀቀ፣
ትምህተኛን ያሳፈረ፣ ሰውን በሰው ያስቆጠረ፣
የማይበጠስ ክር ነው፥ ነፍስን በዋጋ ያሰረ፥
የሰዋዊነትን ጉዳይ፥ በደም ዋጋ ያስከበረ፤
“አድዋ ይጮሃል እንጂ፥ ከቶ ማን ሊሰማው ችሎ?”
ከዘመን ዘመን ይጓዛል፥ ካ’ጥናፍ አጥናፍ ያስተጋባል፥
ብርቱ ድምፁ ልቆ፣ አይሎ።

“በደስታ፣ በክብር፣ በኩራት፣ በፍቅር፣
በድል እኖራለሁ ይኸው በቀን በቀን፥
ደግሞ መከራውን ያን ሁሉ ሰቀቀን፤”

ከሷ ወዲያ…
ጥቁር እንቁ ዋጋው ንሮ፥
ባለም ገበያ የከበረ፣
ለመድኃኒት የቸገረ፤
የአጥንት የስጋ ደመራ፣
ጥቁር ገላ ያበራበት፥
ለሰው ብርሃን፣ ለሰው ሙቀት፣
ለሰው ንቃት፣ ለሰው ድምቀት፤
የማንነት ልዩ ጎራ፣
የልዩነት ውብ ተራራ፥
ላለም ዓለም እንዲያበራ፥
ሰው በሞቱ ያማረበት፤
አድዋማ ብድራት ነው፥
ሰው ስለሰው የከፈለው።

“ምስጋና ለእነሱ፥ ለአድዋ ጀግኖች፣
ለዛሬ ነጻነት… ላበቁኝ ወገኖች።”

/ዮሐንስ ሞላ/

P.S. ግጥሙን ያዘመትኩት በኃይል በምወደው የእጅጋየሁ ሺባባው “አድዋ” ግጥም ስንኞች ነው። በድፍረት ያደረግኹት ሙከራ ነው። እናም ክብር ቢኖር፥ ለእርሷ ይሁንልኝ። ከዚያ በተጨማሪ፣ ግጥሙ የተቆሰቆሰው (inspired by)፥ የዛሬ ዓመት ከወዳጆቻችን ጋር የአድዋ ድል በዓልን በምንሊክ አደባባይ አክብረን፣ ጣይቱ ሆቴል ቁጭ ብለን ስንጫወት፥ ከጨዋታ ርዕሳችን አንዱ አድዋ ለእኛ ምን ማለት እንደሆነ መናገር ነበር። ሁሉም ሀሳቡን ሰጠ፣ ጨዋታው ሲቋጭ፥ “ዛሬ ማታ የሁላችንንም ሀሳብ የሚዳስስ ግጥም ፅፌ እለጥፋለሁ” ብያቸው ነበርና በማስታወሻ የጫርኩትን በት/ተ ጥቅስ አኑሬያለሁ። አብረን ስላሳለፍናቸውና ወደፊት ስለምናሳልፋቸው መልካም ቀናት፥ ወዳጆቼን እጅ ነስቻለሁ።

ከዓመት ዓመት ያድርሰን! የጀግኖች እናቶቻችን እና የአባቶቻችን በረከት ይደርብን!

 

In the name of Adwa

ShuSh! You may boast harking back to any kind of history… but certainly, I’ll beat you calling ‘ADWA’, the ever amazing triumph of Ethiopia in particular, and Africa in general. It is a gift of life we’re given, the return was life; and we’re forever indebted that I can win any kind of your ‘battle of pride’ with the history of the Victory of Adwa – የዐድዋ ድል. 😉

“man is precious; …precious to be man
man has died to save man, respecting man,

The calling of sacrifice of love and honor,
with honor, one dies for the other
my freedom today paid in much blood and bone.

Let Adwa speak, let my country speak,
….how I stand before today
– in pride and honor, in happiness and love”

~ the one and only, the renown Ethiopian singer Ejigayehu Shibabaw (Gigi) in grateful memory of the #VictoryOfAdwa

Tribute to our patriots!

እንኳን አደረሰን! የጀግኖች አባቶቻችን እና እናቶቻችን በረከት ይደርብን!

#Adwa120 #Ethiopia

12814704_919738991480468_7289387146518231890_n

Graphics: by Dawit Anagaw Ain’t it awesome?