እነሆ ሁለተኛ ልጃችንንም ወልደን ከእናንተ ጋር እንደባልቃት ዘንድ ጊዜው ቀረበ። “ምነው ከመጀመሪያው መጽሐፍህ በ3 ዓመታት ዘገየህ?” ላላችሁ ወዳጆች፥ ያው ያን በኦፕራሲዮን (C/S) ስለነበር የተገላገልነው፥ ጊዜውን አሳልፈን ብንባጠስም ለመቋጠር ትንሽ እምቢ ስላለን ነው። ሄሄሄ…
የምር ግን፥ ልክ እንደ “የብርሃን ልክፍት” ይኼም ከእርግዝናውና ከወሊዱ በላይ፥ ቀባብቶ እና አሽሞንሙኖ ከማኅበረሰብ ጋር የመደባለቁ ሥራ የበለጠ አድክሞኛል። ግን ሁሉም መለገምን ባለመሻት እና ወዳጆችን በማክበር ነው። እነሆ ሁሉም አልፎ፥ “በቅርብ ቀን” በማለት የሽፋን ምስሉን ቀብድ አስይዣለሁና እፎይታው ልዩ ነው። የበለጠው ደግሞ፥ ሰብሰብ ብለን በደመቀ ድግስ ስንመርቃት እንደሚኖረን ይሰማኛል።
የቀድሞው መጽሐፌ ላይ የተሰጡኝ አስተያየቶች እና አብሮነታችሁ ለዚህኛው ሥራ እንደረዳኝ አለመናገር ነውር ይሆናል። የብርሃን ልክፍት ካሰብኩት በላይ ተቀባይነት ማግኘቱ ለአዲስ ሥራ ያነቃቃኝ ቢሆንም፥ ይኼም ልክ እንደዚያኛው… “ከእኔ ይውጣልኝና ልገላገል”፣ “ወዳጆቼን ላስደስትና ጥያቄያቸውን በትህትና ልመልስ” “ተጨማሪ መጽሐፍ ቢኖረኝስ?”… ምናምን በሚል ተራ ስሜትና ሞቅታ ሳይሆን፣ ለስነጽሁፍ ዘርፍ ሊሰጠው የሚገባውን ክብርና ፍቅር በላቀ ለመረዳት በመጣር ነው። እናም “ይሁኑ” ያልኳቸውን ሰብስቤ፣ ከዘርፉ ባለሞያዎች እና ወዳጆች ጋር ተወያይቼ፣ “ይሆናል” ባልኩት አቀራረብ “የብርሃን ሰበዞች”ን አዘጋጅቻለሁ። በዚህም ላይ የሚኖሩትን አስተያየቶች ለቅሞ በመጠቀምና፣ በንባብና በልምድ በመታገዝ ደግሞ ወደፊት (እድሜና ጤና ከሰጠን) የተሻልኩ እንደምሆን አውቃለሁ።
ከህብረተሰብና ማህበረ-ባህላዊ ጉዳዮች ጋር ከማቀራረብ ባለፈ፥ ለብዙ የታፈኑ ድምጾች ልሳን በመሆን እያገለገለ ነውና ፌስቡክን ማወቅ ደስ ይላል። ብዙ ጊዜ ይፍጅ እንጂ፥ ፌስቡክን ቀርቦ አውቆ፥ ኗሪዎቹን ማስተዋልና እርስበርስ ተቀራርቦ በነፃ መማማር ደግሞ ይበልጥ ደስ ይላል። ያው ከነድክመትና ጉዳቱ ጋር! በጊዜ እየተሻሻሉና በአጠቃቀም ረገድ እየጎለመሱ ሲመጡ ደግሞ፥ ድካሙም ጉዳቱም አብሮ ይቀንሳል። (ይህን ያኔም ብዬው ነበር። ወደፊትም እለዋለሁ።) ታዲያ የ”3 ዓመታት” ያህል አድጌያለሁና፥ ድካምና ጉዳቱ ቀንሰውኛል ብዬ አስባለሁ። (ጊዜው ግን እንዴት ይሮጣል?)
ያኔ የእግዚአብሔር ሞገስ በፊቴ እንዲሆን ብቻ ተማጽኜ በጨበጣ የነበር የገባሁት። ይኸው ጸሎቴ ተሰምቶ ብዙ ሰው አተረፍኩኝ። ብዙ የመኖር ብልሀቶችን ለመድኹኝ። ያኔ ያልነበሩኝ ብዙ ነገሮችና ልምዶች አሁን አሉኝ። ዛሬ የሌሉኝ ደግሞ ነገ ይኖሩኛል። ሕይወቴ ላይ ብልጭ ብለው ድርግም ያሉትም፥ መቼም ባይረቡኝ ይሆናል። ዛሬም ዘወትርም የእግዚአብሔር ሞገስ በሁላችንም ፊት ይሁን። አሜን!
በጽሁፍና በመጽሐፍ ዝግጅት መንገዴ ላይ፣ በአንድም በሌላም መልኩ መልካም አስተዋፅኦ አድርጋችኋልና፣ በደግነትም በክፋትም፣ በንጹህ የወዳጅነት ስሜትም፥ በሽንገላም፣ በፌስቡክም በአካልም፥ ዙሪያዬ ለነበራችሁ ሁሉ ምስጋናዬ ከልብ ነው። እንኳን አወቅኋችሁ! …እንግዲህ “ይሁን” ስትሉ የ”በቀርብ ቀን“ ወሬውን በዙሪያችሁ ሁሉ አዳርሱት። ለወዳጆቻችሁ ንገሩ። የምረቃውን ቀንም ከበፊቱ በበለጠ ሁኔታ እና ስሜት እናሳልፈው ዘንድ፥ ጉጉት፣ በአሞራ፣ በጭልፊት እና በመሰል አእዋፍ አብረን እንጠብቃለን 🙂
ከበዛ ፍቅር እና ከበሬታ ጋር!
Push the news spread!