ለሚመለከተው ብቻ

በትጥቅ ትግል አምናችሁ አባል የሆናችሁበት ወይም በተግባር የምትደግፉት ፓርቲ ለሌላችሁ ከኢትዮጵያ ውጪ የምትኖሩ ዲያስፖራ ወዳጆች… የኢትዮጵያ ምድር እንዲህ በደም እና በእንባ ቅይጥ እየታጠበች፣ ሰላማዊ ሰው እንደቅጠል እየረገፈ፣ ሰላም ፍለጋ የወጣው ሰው ደሙ ፈስሶ የትም እየቀረ፣….
 
“የአገሬ ወጣት ሆይ ስማኝ። ሀይልህ በእጅህ ነው። እንዳትመለስ። በለው። ፍለጠው። እስከመቼ ሲገድሉህ ዝም ትላለህ? በል ተራው ያንተ ነውና ግደል! ሊመታህ የመጣውን ቀድመህ ምታው።” ብሎ መምከር የምትጽፉትን ያህል ቀላል ነው? እንደኳስ፥ በስልክ ተቀርጾ በተላለፈ ‘ወጣቶች ከፖሊስ ሲሸሹ የሚታይበት’ ቪዲዮ ላይ፥ – “አዪ… በለው! በለው! ወደ ግራ፣ ወደ ቀኝ… ለምን ሸሸህ? ባትሮጪ እኮ ፖሊሱ ይስትሽ ነበር። ስለዚህ ዱላውን ትቀሚው ነበር።” ዓይነት የኮሜንታተር ሚና መውሰድ አይከብድም?
 
ያንን ለምን እዚያው በአካል ያለው ሰው እርስበርሱ አይባባለውም? ነው እንጂ፥ ልክ ነው ልክ አይደለም እያልኩ አይደለም። እነሱ ወደው ፈቅደው ሲያደርጉት “አታድርጉ” ማለት አይሆንም። ነገር ግን፥ የሁኔታውን ምስል ለመከሰት እንኳን ምቹ ባልሆነበት ርቀት ላይ ሆነው፥ እንዲህ ያለ አዝማችነት አይከብድም ወይ?
 
ሰው አገር ስትኖሩ፥ የአገራችሁ ጉዳይ ሥራ አስፈትቷችሁ፣ ቀኑን ሙሉ እሱን ስታስቡና ስታሰላስሉ ለመዋል እንደማትችሉ ግልጽ ነው። ረጋ ባለ ምድር ላይ ንጹህ አየር ስትተነፍሱ እና ስትንሸራሸሩ ውላችሁ፥ እንደ መደበሪያ ፌስቡክ ላይ ብቅ ስትሉ ብቻ…… “አትነሳም ወይ! ድል የሕዝብ ነው። ሕዝቤ ሆይ ስማኝ፥ ተጋፈጣቸው። አውሬዎቹ ቢገድሉህም ታሪክ ይፋረድሃል።” ብሎ የታጋይ እንቅልፍ መተኛት አይከብድም? ቀኑን እንዴት ነው የምታሳልፉት? ምሽቱንስ?
 
ደሙ ሲንዠቀዠቅ ፎቶ ተነስቶ፣ በማኅበራዊ ትስስር ድረገጾች ላይ ደሙ ደግሞ ደጋግሞ ሲፈስ የሚውለውን ሰው ፎቶ ከማጋራት ባሻገር፥ “ቁስሉን መጠገኛ።” የሚሆን እንኳን “ምን ላድርግ?” ሳይሉ፥ የሞተውንም እንዲሁ፣ ለቤተሰቦቹ ክብር ተብሎ እንኳን ፊቱ ሳይሸፈን፣ እንዲሁ ብቻ ከሩቅ ሆኖ እየተቀባበሉት ሆይ ሆይ ሲሉ መዋልና፣ እሱን ‘አክቲቪዝም ነው’ ብሎ ማለፍ ብቻ ከባድ አይሆንም?
 
እንዲህ ባለ ቀውጢ ሰዓት፥ የስጋ ወንድሞቻችሁ/እህቶቻችሁ ጋርስ ደውላችሁ “በሉ ሰብሰብ በሉ። አርፋችሁ ቁጭ በሉ። የወያኔ ሲሳይ እንዳትሆኑ። መቼስ እግዚአብሔር ያመጣውን እሱ እስኪመልሰው ድረስ።” ብላችሁ ታስጠነቅቃላችሁ? ወይስ እንደፌስቡኩ ሁሉ “አንተ ሽንታም! አትወጣም ወይ? ሂድና ግደል ወይም ለነጻነትህ ሙት” ብላችሁ ታጀግናላችሁ?
 
እሺ ይሄም ይቅር። ያላችሁ የነጻነት ጥማት “በለው በለው” ከሚለው ድምጻችሁ ውስጥ ፈልገን እንስማው። ታዲያ ግን፥ በትጥቅ ትግል ማመናችሁ ካልቀረ፣ እንዲህ በሩቁ “በለው በለው” ከማለት ቀረብ ብሎ ትግሉን መቀላቀል እንዴት አላሰባችሁም? ከፌስቡክ ታጋይነት ባለፈ ማለቴ ነው። ለምሳሌ፥ ወደአገር ቤት ሄዶ፣ ራሱን መስቀል አደባባይ ላይ አቃጥሎ ዜና እንዲሰራለት የማድረግ ዓይነት ታጋይነት? ወይ ደግሞ፥ ጠቅልሎ ሄዶ ባገኙት አጋጣሚዎች ሁሉ ከፌደራል ፖሊሶች ጋር ፊት ለፊት የመመታታት ዓይነት ታጋይነት? “ሽንታም” ማለቱ እንደሚቀላችሁ ሁሉ፥ የእናንተን ጀግንነት ደማችሁን እያፈሰሳችሁ ማሳየት?
 
እንደውም፥ ዲያስፖራው ሰብሰብ ብሎ ሄዶ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰልፍ አድርጎ ሲተኮስበት ድንጋይ ወርውሮ የተወሰነው ደም ቢፈስ፣ ለሚዲያ ሽፋኑም ጠቅሞ ከፍተኛ የለውጥ ስትራቴጂ ሊሆን ይችላል እኮ! (አንድ ሰው ብቻውን ሰልፍ ቢያደርግ ትኩረት እንደሚስበው ሁሉ።) ለማታገሉም ቢሆን እንዲህ ከሩቅ ሆኖ አቅጣጫ ሲቀይስና አሰላለፍ ሲተች የነበረ ሰው ውጤታማ ሳይሆን አይቀርም።
 
ባጭሩ፥ ለምንድን ነው ወደ ኢትዮጵያ የማትሄዱት?? ምንድን ነው የቸገራችሁ? – የአውሮፕላን ቲኬት መግዣ?? እንዳትሞቱ/እንዳትታሰሩ ፈርታችሁ እንዳይባል፥ እዚያ የሚሞተውን ሰውም እየገፋፋችሁት ነውና እንደዛ አላሰብኩም። ማለቴ፥ ሕይወቱን ለነጻነት አሳልፎ ለመስጠት ዝግጁ ያልሆነ ሰው፥ እንዴት ሰዎች የራሳቸውን ሕይወት አሳልፈው እንዲሰጡ ከሩቅ ሆኖ ጥሪ ያቀርባል??
 
ሌላ በጣም በሚደንቅ ነገር ደግሞ አክቲቪዝሙን ስታደርጉ፥ አሁን ላይ እንኳን፥ “እኔ አገሬ መግባት እፈልጋለሁ ባክህ” ብላችሁ በራሳችሁ ስም ሳይሆን፣ በanonymous ስም የምትጠቀሙ መኖራችሁ ነው። ጥቃት መርሮት የወጣን ሰው ፎቶ ለአክቲቪዝም መጠቀም አግባብ ከሆነ፥ የራስን ስም ለአክቲቪዝም መጠቀም የሚከብደው ለምንድን ነው??
 
እንዲህ በትጥቅ ትግል እና በፈለገው ደም መፍሰስ ለውጥ የምትፈልጉ ከሆነ፥ አገር ቤት መግባት ምንም ዓይነት ስጋት አያጭርባችሁም መቼም። (ከለውጥ በኋላ የምትኖረውን የተረጋጋች አገር ከመናፈቅ ወይም ዓለም ከማማለሉ በቀር? ወይ ደግሞ ከምትወዷቸው ቤተሰቦቻችሁ የመለየት ስጋት?) ታዲያ ለምን አትመለሱምና ትግሉን አትቀላቀሉም? ይህን ለማድረግ ጠብታ ሀሞት ካጣችሁ ደግሞ፥ ወይ ደግሞ ኤርትራ ሄዳችሁ ግንቦት ሰባትን ለምን አትቀላቀሉም? …በነገራችን ላይ፥ ቢያንስ እነሱ ጋርስ አባል ናችሁ? በገንዘብ ትደግፏቸዋላችሁ? ወይስ እንደተለመደው “ሁሉንም ማቃለል! የዕለቱን እሳት አይቶ ማቀጣጠል!” ነው መመሪያችሁ?
 
ክብር አገር ቤት ሆናችሁ ለመብታችሁ እና ለነጻነታችሁ መከበር ቆርጣችሁ ለቆማችሁ፣ በምትችሉት ሁሉ ግፍን ለምትቃወሙ! የደማችሁ መፍሰስ በከንቱ እንዳይሆን፥ ፈጣሪ ያግዛችሁ! ሰላማችሁ ይብዛ!
 
ክብር ሰው አገር ሆናችሁ በምትናገሩት የለውጥ መንገድ ሁሉ በተግባር ለምትኖሩ!
 
#Ethiopia #EthiopiaProtests #OromoProtests #AmharaProtests #StopKillingCivilians

አለማወቅህን ለመጋረድ…

ስትቀልድበት አብሮ መሳቁ የልብ ልብ ሰጥቶህ ከሆነ እዚህ ያደረሰህ ተሳስተሃል። የሚጎዳውን እና የሚጠቅመውን መርምሮና ለይቶ ተገቢውን ምላሽ ይሰጣል እንጂ፥ የጉራጌ ማኅበረሰብ በንቃት (consciously) ኗሪ ነው። ለዚያም ነው ሥራን ካለመናቅና በኅብረት ከመንቀሳቀስ አንስቶ፣ ሰብአዊ መብቱን ተጠቅሞ፥ ገና ድሮ በየክፍለ አገራቱ ተንቀሳቅሶ እስከመኖር የደረሰው።
 
አርአያ የሚሆን የቁጠባ ባህሉም፣ በነጻነትና በስርዓት የመኖሩ ውጤት ነው። የዚያኑም ያህል ደግሞ፥ በየደረሰበት በፍቅርና በሰላም ተቻችሎ በመኖሩ ይወሳል እንጂ በክፉ አይነሳም። ባለማወቅ ቢያንጓጥጡበትና የሕይወት መመሪያውን ባለመገንዘብ ቢቀልዱበት፣ አብሮ እየሳቀ ዝም ብሏቸው ኖሮ፥ ውሎ አድሮ በክፉ በደግ ማንነቱን በሥራው ነው የሚያሳየው።
ግፍና ጭቆናን ማንም አይወድም። የበደልን ቀንበርም ማንም እስከዘላለሙ ችሎ አይሸከምም። የጉራጌ ማኅበረሰብም ሥራ የመውደዱን እና ሰላም የመሻቱን ያህል አምባጓሮ ውስጥ ራሱን ለማግኘት አይፈልግም እንጂ፥ “በሰላምና በሽምግልና ማኅበራዊ ችግሮቻችንን እንፍታ” ሲል እምቢ ብለውት ሲረግጡት ይረግጣል። ረግጬህ ልግዛህ ሲባል አሻፈረኝ ይላል። ሕግና ስርዓትን ዘርግቶም ባህሉን አክብሮ ኗሪ ነው።
 
በማኅበረ ፖለቲካው በጉራጌዎች የተደረጉ እምቢባይነቶች ሞልተዋል (እንዲህ እንደዛሬው ሰው በጎጥ ተከፋፍሎ ‘የአማራ’ ‘የጉራጌ’ መባባል ሥር ሳይሰድ በፊት፥ በ’ኢትዮጵያዊነት’ ስምና ስሜት። በአገራዊ አጀንዳ ‘የጉራጌ ተቃውሞ’ የሚባል ኖሮ አያውቅም። ያው ሀሳቡም መጤ ነው)። ከኢትዮጵያዊነት ጉዳዮች ባሻገር ከድል በኋላ ወደ ሥራ ስለሚሄድ፣ ታሪክም በባለጊዜዎች ስለሚመዘገቡ እንጂ ብዙ ታሪኮች አሉ። የተጻፈውም ቢሆን በበቂ ሁኔታ መስካሪ ነው። ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴስ ጨቦና ጉራጌ አውራጃ አይደል ተወልደው ያደጉት! በየዘርፉ ዞር ዞር ብለህ ታዘብ፥ የሕይወት ታጋዮች ሞልተውልሃል፡
 
ከቤትህ ዙሪያ ልስማ ካልክ የአባቴ አባት በጣልያን ተሰቃይቶ መገደሉን እናቴ ትተርክልሃለች። ተተኩሶበት ሳይሆን፣ ተይዞ፣ ዐይኑ ተጎልጉሎ እና ሌላ ሌላም ስቃይ ደርሶበት መሞቱን የነበረ ያህል ታወራልሃለች። (አባቴ “ያኔ 12 ዓመት ብሆን ነው” ይላል።)
 
ልብ አድርግ! ስለአባቴ አባት ነው፥ እናቴ እሷ ሳትወለድ ስለሞተው አያቴ የተነገረውን ታሪክ የምትተርክልህ። እንጂማ አባቷም ቀላል አልነበሩም። ደርሼባቸው ከአንደበታቸውም ሰምቻለሁ።
 
“መድፍና መትረየስ ጥይት ሲጓረሱ
አሳላፊ ነበር የማሩ ገረሱ” ስለተባለለት ደጃዝማች ገረሱ ዱኪ፣ አባ ቦራ (አያቴ አገልጋዩ ሆነው አሳልፈዋል) እና ስለጀግኖች አርበኞች ተጋድሎ፥ የታሪክ መጽሐፍ ማንበብ ሳልጀምር በፊት ከእርሳቸው ነበር የምሰማው።
 
በቅርቡ ታሪኳ በሰፊው የተነገረላት ሴታዊት (feminist)፣ የቃቄ ውርድወትን ተመልከትና ያልተዘመረላቸውን ሌሎች ብዙዎችን አስብ። ‘አይ ዘመኑ ወዲህ ይቅረብልኝ’ ካልክ፥ የተደላደለ ኑሮውን ትቶ በረሀ የገባው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋም አለልህ። (እንግዲህ ጉራጌ ጥርስ ከነከሰብህ፣ “ከፈለግክ ዱላም እንማዘዝ” ካለህ፥ ምን ክፉ ብትሆን እንደሆነ ራስህን መፈተሽ ነው።) “ቆይ እስኪ እንየው” ብሎ ተስፋ ባለመቁረጥ በሰላም የሚማጸን ከፈለግክ ደግሞ፥ ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም ይጠቀሱልሃል። (እንግዲህ ልብ አድርግ፣ ጫፍ ጫፉን ነው የማወራልህ። መሀል መሀሉን ገምተው።)
 
ወዳጄ፥ አለማወቅህንማ በከንቱ ዘለፋ አትጋርደው!
 
Stop your racist remarks against the Gurage people!, or die now with it!
 
#Ethiopia #StopKillingCivilians