የምር መንግስት ቢኖረን ኖሮ፥ ይህኔ በሬድዮና በቴሌቪዥን የሚታጀብ፣ ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ የሚደረግበት ብሔራዊ ኀዘን ላይ ነበርን። ግን ያው፣ ሕዝቡ ራሱ ብሔራዊ ሐዘን ተጠራርቶ ቁጭ ብሏል።
“የገደለው ባልሽ
የሞተው ወንድምሽ፣
ሐዘንሽ ቅጥ አጣ
ከቤትሽ አልወጣ” ሆኖ አላመች አላቸው እንጂ፥ ለራሳቸው ፍጆታ ሲሉ እንደከዚህ በፊቱ ሁሉ እኛ የጠራነውን ብሔራዊ ሐዘን ያዳምቁ ነበር።
አሁን እንደው የመለስ ሞት በምን ሚዛን ተሰፍሮ ነበር፣ “በመንግስት ጥበቃ ስር ናቸው።” ተብሎ ሲታሰብ፣ በጥይት እና በእሳት ተጠባብሰው ከሞቱ ወገኖች ልቆ በዋሽንት ስንደነቁር የነበረው? ሲሆንስ አዲስ ዓመትን ጠብቆ እስረኞችን መፍታት የሚጠበቅ ነበር።
እሺ እሱም ቅንጦት ሆኖ ይቅር። የቤተሰብን ልብ ሰቅሎ ማሰቃየት ምን ይባላል? ባገራችን ደንብ እንደው የሰው ክቡርነት በሞት ደምቆ ይገለጻል። እርም ሳይወጣ ምግብ አይበላም። የከፋ ቅያሜ ቢኖር እንኳን አስከሬን ቆመው ያሳልፏል።
የሟች ወገኖች እናቶች እንዴት ሆነው ይኾን? የእናት እና የልጅ ተፈጥሯዊ ትስስር ጥልቅ ስለሆነ፥ የሞቱት እስረኞች እናቶች ይኽኔ ቁርጡን ሆዳቸው ይነግራቸዋል። (እናቴ በሌለሁበት ጠንከር ያለ እንቅፋት ቢመታኝ ታውቃለች።)
ታዲያ ግን ምን ብለው “ልጄ ሞቷል” ብለው ለቅሶ ይቀመጡ? ስሜቱን የማያውቅ ሰው እንደአሟራች ቢቆጥራቸውስ ይፈረድበታል። ምን ብለውስ “ልጄ ደህና ነው” ብለው ይረጋጉ። ስሜቱን የማያውቅ ሰው እንደግብዝ ቢቆጥራቸውስ ይፈረድበታል? ልጆቻቸው ሞቱ/ኖሩ ቁርጡን ሳያውቁ እንዴት ያንቀላፋሉ? ወዳጅ ዘመድ ጓደኛስ እንዴት እህል ይወርድለታል?
ሕዝብ በመንግስት በዚህ ልክ ይጠላል? “የድሃ ድሃዎች” አሉ ቃል ሲያሳምሩ እና ወሬ ለመቀሸር ሲሯሯጡ።
የክፉ ክፉዎች!!
ሕዝብ
——-
የእምቧይ ድርድር ካብ፥ እሾህ የማያጣ፣
ንጉሥ ሲደብረው፣
¬ ጭቃ ሹም ሲከፋ፣ ባለሟል ሲቆጣ፣
እንኳን ወሬው ቀርቶ፥ ዝምታው ‘ሚያስቀጣ፤
ኩራቱ ‘ሚያስጨንቅ — እንደ እመቤት ኩርፊያ፣
መቻሉ ‘ሚያስገፋ፣ ‘ሚያስደምር ከትቢያ፤
ወንበር ‘ሚያነቃንቅ፥ — የሰላሙ ዜና፣
መንግሥት የሚያሸብር፥ — የነፍሱ ጽሞና፤
ሳቁ ‘ሚያጠራጥር፤ ትንፋሹ ‘ሚያስገምት፣
እርምጃው ‘ሚለካ፤ ሩጫው ‘ሚያስፎትት፤
ሕዝብነት—
— ከንቱነት!
/ዮሐንስ ሞላ (2005) የብርሃን ልክፍት/