የንፍገት ጥግ

ከእለታት ባንዱ ቀን አምባገነን ገፍተው፣ ከጫካ ብቅ አሉ… ለመላ ለዘዴ፥ በሽለላ ብዛት፣ በዲስኩር ጋጋታ፣ ባዋጅ አጥር ብዛት፥ የሚሻል መሰሉ… ‘ዴሞክራሲ ሰፍኗል፣ ተናገሩ… ጻፉ፣ ተከራከሩ’ አሉ…
 
ገና በማለዳው፥ እንኳን የጻፈውን፣ ሊጽፍ ያሰበውን በፀረ ሽብር ህግ በቁም አሸበሩ… ‘በሽብርተኝነት ጠረጠርኩኝ’ ብለው ማለፊያውን ለቅመው፣ ሰብስበው አሰሩ፣…. ለተጠርጣሪው ሰው ማስረጃ ፍለጋ፣ ማስረጃ ቅመራ ላይ ታች ተባረሩ… በሰማይ በምድሩ ቧጠጡ፣ ዳከሩ… ወለሉን ቆፈሩ፣ ግድግዳውን ጫሩ… አልበቃ ብሏቸው ጊዜ ለፈጠራ፣ ለክስ ቅሸራ፥ በቀጠሮ መዓት፣ ገነቡ ተራራ… በእግረ ሙቅ እጅ አስረው፣ ከሰሩት አቀበት እያመላለሱ፣ አሳዩ መከራ…
 
ሲኖሩ ሲኖሩ…
ከእለታት ባንዱ ቀን፥ ‘እሳት ተነሳ’ አሉ ከእስር ቤት ምግብ ቤት… ‘ሊያመልጡ ሲሉ ነው’ ብለው በመተኮስ፣ የቻሉትን ጣሉ… አማራጭ በማጣት፣ የቀረውም ሸሸ ወደ ላንቃሙ እሳት… ‘ይህን ያህል ሞተ’ ተብሎ ተወራ፣ ከተጠቂውና ካጥቂው መንግስት ጎራ፣ ተዛብቶ ቆጠራ… ‘ከሞቱ ተረፉ’ የተባሉትንም ጭነው አጋዟቸው እስር ቤት ቀየሩ… በቤተሰብ ለቅሶ፣ በወዳጆች ዋይታ ታፈነ አየሩ… ቆዘመ መንደሩ…
 
ሳይነገር መርዶ… አስከሬን ሳይሰጥ… ከጥቃቱ የዳነም እንደተጨነቀ ሰላሙን ለማውራት… ተቆጠሩ ቀናት… ‘ቄሱም ዝም፣ መጻፉም’….. እርም ሳይወጣ፣ ያለው ሳይታወቅ ልብ እንደሰቀሉ… ‘አገሩ ሰላም ነው… በእውቀት ተቃወሙን’ ብለው አላገጡ፣ የቀለም ቀንዶችን፥ የቻሉትን አስረው፣ የቻሉትን ገፍተው እንዳላቀለጡ።
 
#Ethiopia
 
ምንም እንኳን የማውቃቸው ታሳሪዎች ባይኔ እየዞሩ እረፍት ቢነሱኝም፥ በሀቅ ሲመዘን ተጎጂው ሁሉ እኩል ነው። እግዚአብሔር ለተጨነቁትና ላዘኑት ሁሉ ብርታት ይስጥ። መርዶአቸው ባይሰማም፥ የሞቱትም በሰላም ይረፉ! የሰማዕትነትን አክሊል ያቀዳጅልን!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s