እንገንባ ሲሉን ግድቡን ነው ብዬ
ቦንድ ግዙ ሲሉን ለልማት ነው ብዬ፣
ለካስ ለምሽግ ነው፥ ለሚሸጎጡበት…
ሲያጥለቀልቃቸው ጎርፍ ሆኖ ዕንባዬ!
ይኸው ደግሞ ወደንም ኾነ ተገደን፣ ላባችንን ጠብ አድርገን እያስገነባን ባለው “የአባይ ግድብ” ማስፈራራት ጀምረዋል። እንደምናየው እያስፈራሩን ያሉትም በራሳችን ንብረት ነው። የሕዝብ ብሶት ጦር ኾኖ ሲንቀለቀልባቸው፣ አባይን ተጋሸን (ጋሻ ሁነን) እያሉት ነው።
አሁን ነው “ወንድምና ወጥ ማስፈራሪያ ነው።” ብለው ሚሸልሉት። ግን እንጀራው ሲሻግት ወጡ በስትራው አይመጠጥ! እንጀራው ሲደርቅ ወጥ ትሪ አያስፈራራ! ደግሞ ተገንብቶ ኃይል ሲያመነጭስ ለእኛ ይትረፍ አይትረፍስ በምን እናውቃለን? እኛን በጨለማ “የሽንብራው ጠርጥር”ን እያስዘፈኑ ለሌሎች አፍሪካ አገራት መብራት እየቸበቸቡትም አይደል?
እኛ ቁርበት ላይ ስንቆራፈድ በስንትና ስንት ሚሊዮን ብር ቪላ አንጣለውም አይደል? ለቀድሞው ፕሬዝዳንት አቶ ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ሳይቀር በወር 450 ሺህ ብር ቤት ኪራይ እየከፈሉ፣ ሰውዬውን ገዳም ገብተው ንስሀ እንዳይቀበሉ (እሳቸውን እንጥቀም ብለው ይሁን አከራዩን፥ እነሱ ያውቃሉ።) የከለከሏቸው በሕዝብ ገንዘብ አይደል?
ከዘፍጥረት አንስቶ፣ ገነትን ያጠጣ የነበረ፣ ከኤደን የፈለቀው የጊዮን ወንዝ እንደው ከአምባገነኖች ጋር ሕብረት አይኖረውም። ጩኸታችንንም ይዞት ይሄዳል። የምናምነው ያየናል። እንኳን ባሮቹን ሊፈጅ የመጣ መሰሪ ስርዓት፥ ይኹን ሲባል የኢያሪኮ ቅጥርም ከመውደቅ አልዳነም። ፈርኦን ከነጭፍሮቹም አልተረፉም። መልከ ጼዴቃዊ ሹመት ለግፈኞች ቃል አልተገባም።
የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ሁሉም ሂሳቡን ያወራርድ ዘንድ ግድ ነው!