ሴትን አንኳስሶ የሚናገር ከራሱ ነው ክህደት የሚፈፅመው። ያ ባይሆን ደግሞ፥ አለማወቁን ነው የሚገልጠው። ይገልጠው አለማወቅ ባይኖረው፥ አውቆ ቸል ማለቱን ያሳያል። ወይም፥ ከእውቀቶቹ ሁሉ “ሴት”ን በአግባቡ ማወቅ ጎድሎት ሳይሆን አይቀርም። ወይ ደግሞ፥ ያልተጣራ የውስጥ ችግር ይኖራል። – እንጂማ፥ “ካላበደ በቀር ዱባ ቅል አይጥልም” እንዲሉ፥ ማንም ስለፆታው ያደረገው አስተዋፅኦ በሌለበት ሁኔታ፥ ፆታው ከርሱ የተለየውን ዝም ብሎ አይፈርጅም።
 
ሴት የሚለው ቃል እንደ ቅፅል፥ ፆተኝነትን አቀንቃኝ ያልተገባ ልማዳዊ አጠቃቀም እንዳለው ቢታወቅም፥ እንደ ስም፥ የወል መጠሪያ ነው። …እንደ ወል ስም፥ ሴት: ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ከመሀይም እስከ ምዑር፣ ከቤት እመቤት እስከ ድርጅት እመቤት፣ ከምንዝር እስከ አለቃ፣ ከወላድ እስከ መሀን፣ ከወታደር እስከ ጦር መሪ፣ ከአገልጋይ እስከ እመ ምኔት፣ ከፀሐፊ እስከ አንባቢ… ሌላም ከ—እስከ ተብሎ ተዘርዝሮ የማያልቅ የተለያዩ የኑሮ እርከኖች ላይ የሚገኙ፣ በተፈጥሮአዊ ባህርያቸው እንስት የሆኑ ሰዎች ተለይተው ይታወቁበታል።
 
“ሴት” ብሎ በጅምላ የሚዘልፍ፣ የሚሰድብና ደምሳሳ ድምዳሜ (hasty generalization) የሚያደርግ ፆተኛ፥ የስኬት መሰረት የሆኑ የታፈሩና የተከበሩ ሴቶችን ታሪክ አያውቅም። ወይም እያወቀ እንዳላወቀ ሆኗል። …እያወቁ እንዳላወቁ መሆን ደግሞ ካለማወቆች ሁሉ የከፋና በራስ ጥመት የሚመጣ በመሆኑ፥ ይበልጥ የማህበረሰብ እና የጋራ ግንዛቤዎች ጠንቅ ይመስለኛል።

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s