የሰው ልጅ ብቻውን እንደሆነ እንዳይሰማው፣ እንዳይሰለቸውና እንዳይፈራ በነገሩ ሁሉ በዓላማ መኖሩን እንዲያውቅና እንዲረዳ፣ ፈጣሪ ዓይኖቹንና ጥርሶቹን አጎራበታቸው። ዙሪያውን በሰው ልጆች አጠረው። ስሜቶቹን አሰለፈለት። ጊዜንም በወቅት ከፋፈለ: ክረምት፣ ፀደይ፣ በጋ፣ በልግ…ጨለማ እና ብርሀን… ጠዋት እና ማታ… እርሻ እና አዝመራ… ኀዘን እና ደስታ። ትዝታን እና ተስፋንም በልቡ አኖረለት። አጢሀት እና ይቅርታንም በመንገዱ ላይ አቆመ። ከአፈርና ከአጥንት እፍ ብሎ የምድርን ጾታ አሰባጠረ። ለዘወትር ድካሙ እንዲሆን፥ ካለአጀንዳም አላስቀረውም።
“ፀሐይ ይሁን” ቢል፥ ፀሐይ ሆነ። ጨረቃና ከዋክብትን፣ ነፋስና ውሀንም እንዲህ አፀና። ሥነፍጥረት ሁሉ በቃሉ ተከናወኑ። የሰው ልጅን ከነአስገራሚ መላመዱ እና ከነጥበቡም በእለተ አርብ ፈጥሮ ፍጥረታትን አስገዛለት። መንገድንም አመላከተው። በተሰጠው ላይ የሰው ልጅ እየጨመረበት ነገር ሁሉ ይበልጥ ውብ ሆነ። ፍቅርን ምድር ላይ ዘራ። ስለመኖሩ ምልክት እንዲሆኑት፣ እንዲጽናና እና እንዲበረታበት ለሁሉም አንጻርና ወዳጅ አላሳጣውም። ሲለቀስ ለሲቃ ጥርስ ይነከሳል፣ አፍንጫም ከጥርስ የሚሰበስበው አቅም አለ። ሲሳቅም አይን አብሮ ይስቃል እንጂ የጥርስ ድርድር መታየት ብቻ ሳቅ አይባልም።
አዋራና ጎርፍ ይፈራረቃሉ። ህጻናት ያድጋሉ። ወጣትነት ሲሰሰት ያልፋል። ጉልምስና በክፋት፣ በ“ካለ’ኔ”፣ እና በራስ ወዳድነት ይጠቀረሻል። ያልለገሙበት ጊዜ ወራዙት ግን ከራስ አልፎ ዙሪያንም ያበለጽጋል። ልብ የሰበሩለት ጉልምስናም ጌጥ ለሚሆን ሽምግልና ይገነባል። ውብ አበባ፣ ጣፋጭ ፍሬ እና እሾህ ካንድ ዛፍ ላይ ይበቅላሉ። ሁሉም እንደመድረሱ ልክ እና እንደመሻቱ ይለቅማል። ዕድሉ ሆኖ፥ ካማረ መስክ ላይ መጣል የሚቀናው አይጠፋም። ለፍሬ ብሎ ተንጠልጥሎ እሾህ መያዝና መፈተንም አለ። ፀንተው ቢቆዩ ፅናት ወደፍሬው ያሻግራል። ደግሞ ‘እሾህ ነው ዕጣፈንታዬ’ ብለው ቀድመው ሲያማርሩ፥ ፍሬ ታድሎ በረከት መቁጠርም የሰው ልጅ እጣ ፈንታ ውስጥ ይገኛል። እግዚአብሔር “ይሁን” ሲል ግን፥ አንዲት ጀምበር ይበቃል!
“ነገር ሁሉ ያደክማል፤ ሰው ይናገረው ዘንድ አይችልም፤ ዓይን ከማየት አይጠግብም፥ ጆሮም ከመስማት አይሞላም።”ና ቆመን መሄዳችን እስኪደንቀን ድረስ በዓይን እና በጆሯችን አሳልጦ የገባ መአት ጉድ እንታጨቃለን። ግን እንኖራለን። ከብዶን የወደቅን እንደው፥ ጉዱም ጉድ አይሆን። …ከእናታችን ማህጸን ጀምሮ ታውቀን እስከራስ ፀጉራችን ድረስ ተቆጥረናል። ይተናነቀናል እንጂ፥ “በእምነት ሆናችሁ ተራራውን ሂድ በሉትና በመደነቅ ኑሩ” ተብለናል።
ስሜት ቦታና ጊዜው ሲገጥምለት ጽንስ ይሆናል። እናት ልጇ ቢራብ ጡቷ ላይ ህመም ይሰማታልና በዚያ ታውቃለች። አድጎ፥ እንኳን ህመም፣ ከረር ያለ ግጭት ውስጥ ቢገባ እንኳን ሳይነገራት እንድታውቅ የፈጣሪ ድንቅ ሥራ ነው። ደግሞ ሽል ሳይቀር ድምጽና ወሬ ይለያል። ተክሎችም በሙዚቃ ይፈነጥዛሉ። ጠፉ ሁሉ በልባዊ ፈገግታ ይለመልማል። የተፈጥሮ ዑደት፣ የእጽዋት እና እንስሳት እድገትና መዝናናት፣ የዘመናት መፈራረቅ፣ የወቅቶች ማለፍ፣ የእጁ ሥራ ሁሉ አይጓደልም። ሰው ሲሞት፥“ዋርካው ወደቀ” ተብሎ በሀዘን ቢረገድ፥ ሺህ ዋርካዎች ከሥር ይወለዳሉና በዚያ መጽናናት ይሆናል። “ቆሜያለሁ” ቢሉም መውደቅ አይቀርምና ልብ ብለን ብናይ ማስታወሻው ብዙ ነው። ድንቅ ነው!
ተመስገን! ፀሐይና ጨረቃን ሰው አይፈቅድም። ብርድና ሙቀትንም ሰው አይከለክልም። ፍቅርን ሰው “ይሁን… አይሁን” አይልም። ስለዚህ ካለን፥ ምን ሌሊቱ ቢረዝም፣ ሲነጋ ጠዋት መሆኑ አይቀርም። ከቆየን፥ ደመናው አልፎ ፀሐይ ይሆናል። ይኽ እውነት ነው የሚያበረታን!
ፍቅርና ማየት ምርኩዝ ሆነውኝ እኖራለሁ። ጭጋጋም ቀናትን ተሻግሬ ብርሃናቱን አቅፍ ዘንድ፣ ዳፍንታም ቀናትም እንዲሸማቀቁ የፈጣሪ ቃል ነውና አይታጠፍም። ደግሞም የቀደመ ልምድ ያበረታል እንጂ፥ ተመልሰው በቦታ እና ጊዜ ለውጥ እንደሚመጡም አውቃለሁና እግዚአብሔር መርሳትን አያድርግብኝ።
አሁን ደምና ጦር አስደንግጠው እንደሚያደነድኑት ዓይነት፥ የጠላትም የወዳጅም ቅይጥ መንፈሶች ስንቅ ሆነውኛልና በፍጹም አልፈራም! ለዚህ በሰማይና በምድር፣ ከተጻፈው እና ካልተጻፈው ብዙ ምስክር አለኝ!
ሃሌ ሉያ!