እንጉርጉሮ 2

አዬ ስጋ ክፉ፣ አይ ሰውነት ብላሽ፣
ቆሻሻም ነፈገሽ፣ ዛሬስ አፈር በላሽ።
* * *
እዚያ ስርመሰመስ፣ የነበርኩት ጌጡ
ነፍስ የምዘራበት፥ ፈልፍዬ ከውስጡ
አድቦልቡዬ ቅርሻ፣
ትርጉም አወጣለት፣ አበጅቼ ጉርሻ
ከተረፈ ኗሪው፣ ለአኗኗሪው ድርሻ
 
በእኔ ገጽ፣ በእኔ አምሳል፥
ሙሰኛ ጅብ ሆዳም የኖረበት ዋሻ
ላዬ ላይ ተደፋ፣
ይኸው እንደሰዉ፥ ሰለቸኝ ቆሻሻ።
 
ገባሁለት ካፈር፥
ይቀኙ ይጻፉለት፣ ስሄድለት ይክበር።
* * *
ከቆሻሻው ክምር
ከሰው ተራራ ሥር
ነበረኝ ቀጠሮ፣
ለቅሜ ምፈታው የረሀብ ቋጠሮ፤
ከተማ ብመንን ቀን ቢነሳኝ ኑሮ
ሞት ሰው አገናኘኝ አዙሮ ዟዙሮ።
* * *
“እኔን እኔን እኔን፥ እኔን አፈር ይብላኝ”
ብሎ ያበላ ነበር
በቀን ጣ’ይ ተበልቶ፣ ሕዝቤ ባይቸገር
በረሀብ ጥም ተቀጥቶ፣ እጁ ባይጠፈር
ባይቆስል፣ ባይገደል፣ ባይሰደድ ኖሮ፥
ከሰው ጅብ ለመሸሽ፣ ባህር ባይሻገር፤
 
ይጽፈው ነበረ የልቤን እሮሮ
ሽንቁራም አንጀቴን ሚጥፍበት ቢያጣ፥
ተነቅፎ ባይጣል፣ እግር ተወርች ታስሮ
ስለተነፈሰ በአዋጅ ባይቀጣ።
* * *
ከወንዝ ወዲህ ማዶ፣ ከጠነባው ትቦ፣
ማማ ከሰራበት፣ ሰው ቆሻሻ ክቦ
መልክ፣ ሕይወት ነበረኝ
ኑሬ የማላውቀው፣ ኑሮ ሰድቦኝ በአግቦ
በሞት ተጠቁሜ፣ ጎበኘኝ ሰው ከብቦ፤
 
እብለት በደም ረቅቆ
ከተሰደርኩበት፣ ከቆሻሻ መስኩ፣
የጣለው ላይ ደምቆ
በሚጥለው መዓት ከሚታየው መልኩ
የሰውነት ሚዛን፣ የኗሪነት ልኩ
የግፈኛው ሽፎን፣ በዕድገት ማላከኩ
ዐይን ጆሮዬ ሞላ፥
 
ቆሻሻ ጭንቅላት ተለቅሞ ተለቅሞ፣
በየወንበሩ ላይ፣ በየህንጻው ከትሞ
ለስሙ መጠሪያ፣ ለልጆቹ መኩሪያ
ድንጋይ ሲደረድር፣ ሲያንገዋልል ትቢያ
ብርጭቆ ሲያገጫጭ፣ በውስኪ ሲረጫጭ፥
ድሀን ቸግሮት ሳቢያ
ቁንጫ ማስረሻ፣ ሆዱን መመቅነቻ
ሲድህ ሲንከላወስ፣ ልቡ ኑሮ ዛቢያ
ሲተክዝ ለብቻ፤
 
ከዳኝ ሆድ ማከኩ፣
በቃኝ መብሰክሰኩ
ምች አጠናገረኝ፣ አጣሁ ድንገተኛ
ከህንጻው ግም የመጣ ጠለዘኝ መጋኛ
ስሞት ወግ ደረሰኝ፥ እንደሰው ልተኛ።
 
/ዮሐንስ ሞላ/
 
የሞቱትን ነፍስ ይማር! ያዘኑትንም ያጽናና! ለአገራችን እና ለሕዝቡ የተሻለ ቀን ያምጣልን!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s