
ሰሞኑን አገር ቤት ኢንተርኔት ከመቋረጡ ጋር ተያይዞ፥ ወዳጆች የፌስቡክ እና የሌሎች ማኅበራዊ ድረ ገጾች “ናፍቆት” እንዴት እንዴት እንዳደረጋቸው እያየን ነው። እኔም “መቼም የሸገር ጓዶቼ በሰፊው ብትን ያላሉበት ፌስቡክስ ቢቀር ይሻላል” ብዬ፥ ከፌስቡክ ለመራቅ ያደረግኩት ሙከራ ባጭሩ ሲከሽፍብኝና፣ ጣቴን እየበላኝ በባዶ ሜዳም… “ሄድኩ” ስል ስመለስ ከራሴ ጋር እየተሳሳቅኹኝም
“ኧረ ይኼ ነገር የከፋ ሳይሆን አልቀረም።” ብዬ “ከፌስቡክ ሱስ መላቀቂያ መንገዶች”ን በመፈለግ፣ በዚያውም ስለፌስቡክ እና ስለሱሱ ማንበብ ቀጠልኩ። (ሱስ የመሆኑ ብዛት፥ ሰው ሁሉ መጠቀም ቢያቆም እንኳን ብቻችንን መጥተን እንድናውደለድል የሚገፋፋን ስሜት አለ።) የሚገርመው ነገር ግን፥ መላቀቂያ መንገዶቹን እያነበብኩ ራሱ፣ በየመሀሉ ስንት ጊዜ ፌስቡኬን ቼክ እንዳደረግኩ እኔና እግዜሩ እናውቃለን። ሃሃሃ…
የተጠቆሙትን መንገዶች ሁሉ ሳነብ፥ በልጅነት “እስክሪብቶዬ የዛሬን ጻፊልኝ፣ ለነገ አስገዛለሁ” ብለን ቁልቁል ዘቅዝቀን እንደምናራግፋት፣ “ቆይ አሁን፣ ቆይ በኋላ፣ ቆይ ነገ” ስል፥ ባህሩ እሹሩሩ እያለኝ እንደሆነ በደንብ ገባኝ። “ወደ ሲዖል የሚወስዱ መንገዶች በማስተባበያ የተጠረጉ ናቸው።” (the road to hell is paved with excuses) እንዲል ፈረንጅ፥ ሳልቦዝን፥ ለማስተባበያዎቼ ሳይቀር ማስተባበያ ስፈልግ ቆየሁ።
በንባቤ መሀል “ድረ ገጾቹን ብሎክ ማድረግ” የሚል ጥቆማ ሳገኝ፥ “wow, this must be working” ብዬ blocksiteን ተጠቅሜ ብሎክ አደረግኩት። ችግሩ እየረሳሁት ብቅ ስል፥ አውቶ ፖፓፑ ሲያላግጥኝና ስስቅ ዋልኩ። ስቄም አላባራሁ። ከዚያም ቆይ የፌስቡክን ሱስ ለማስታመም እና ቀስ በቀስ ለመተው ብዬ፣ ተያያዥ ነገሮችን እያየሁ ለመቆየት ወሰንኩና፥ ‘how to unblock a site blocked by a blocksite’ ብዬ ፈለግኩና ማብሪያና ማጥፊያዋን (the switch) አገኘኋትና፥ ይኸው ቀጥታ ከመጠቀም በማብሪያና ማጥፊያ ወደመጠቀም ተዘዋውሬያለሁ።
“ሲጋራም ቢሆን ባንዴ ማቆም ጥሩ አይደለም። ከፓኬት ወደ 10፣ ከ10 ወደ 5 ነው” የሚሉትን አስታውሼ፥ ብሎክሳይቷን በፈረቃ አብቃቅቼ ለመጠቀም ወሰንኩና “ቆይ የዛሬን” ብዬ off አደረግኩት። 🙂
ታሪኩ በአጭሩ ሲነገር፥
“አልሆንልህ አለኝ እጄ፥
እናንተን ጥዬ ሄጄ
ጉድ ብሆንስ አብጄ” ነው (በ“አልሆንልህ አለኝ እግሬ” ዜማ)
እያጨስን ነው ወዳጄ! ፈተናው ከባድ ነው! እየተጨሰብን ነው!
ለአፍታ ዞር ስል፣ መንግስት ተገልብጦ፣ ጓደኞቼ ተድረው፣ የማይዳሩት ፂማቸውን ላጭተው ጨርሰው ቆዳቸውን ጨርሰው፣ ሰማዩ ዝቅ ብሎ፣ ምድሩ ከፍ ብሎ፣ የሆኑ የሆኑ ዓይነት ብርቅዬ እና ድንቅዬ እንስሳዎች ተፈጥረው… የሚጠብቀኝ፣ ዓለም የሚያልፈኝ እየመሰለኝ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። ሃሃሃ… ሰሞኑን በኢንተርኔት መቋረጥ የተነሳ “ናፍቃችሁኝ ነበር” የምትሉትንም አንሰሜክስ ብለናል። ሱስ ነው፥ ታከሙት! 😀
እስኪ የዛሬውን በግጥም እንዝጋውና፥ “ካለፌስቡክ ስንት ቀን መኖር እንደሚቻል” እንፈትሽ! ሃሃሃ…
እትት እያስባለ ሲያናውዘኝ
የደረብኩለትን ማታ፣
በል አሁን ጣል ኩታ ሲለኝ
ከሙቀት ጋራ ሊፋታ፣
መስሎኝ የነበረ ናፍቆት
ነፋስ ሽቶ፣ ገላ ሞቆት፥
ላህብ አጥልቆ ወብቆት
ለካስ ኖሮ ከራስ ስርቆት፣
ለስራ ፈትነት ግምጃ
ለባተሌነት መጋረጃ፥
የተጠመቀ ደረቆት፣
የመራቋቆት ሱስ ቆት።
/ዮሐንስ ሞላ/
ቆት: በትግራይ ጨለቆት አውራጃ ውስጥ ይገኝ የነበረ/የሚገኝ ትልቅ ዛፍ ስም ሲሆን፣ በስልጥኛ ደግሞ “ኃይል” ማለት ነው።
ሰላም!