ሀበሻን ሁሉ አይቶ የጨረሰ፣ ፈረንጅን መርምሮ ደህናነቱን ለክቶ ያወቀ ይመስል፥ “ውይ ከሀበሻ ጋር! …ሀበሻ ክፉ ነው! …ከሀበሻ ጋርማ በሩቁ ነው!” ምናምን እያሉ ራስ ሀበሻ ሁነው ሳለ በራስ ላይ መሳለቅ ያሳቅቃል። ሀበሻንም ሆነ ፈረንጅን፥ ማን አይቶ ጨርሶት ነው?
* * *
አንዲት ምስኪን ኢትዮጵያዊት እናትን፣ ከአንዲት ፈረንጅ እናት ጋር አንድ ላይ አድርጎ፥ ከላይ ‘ልጅ ብርጭቆ ሲሰብር’ የሚል ጽሁፍ ከላይ አስፍሮ:
Foreign mom: “Son, are you okay??” ትላለች፥
ኢትዮጵያዊቷ ደግሞ “አንተ ከይሲ ብርጭቆው ተረፈ??” ትላለች ተብሎ የቀረበ ለዛዛ የፌስቡክ ፖስተር አለ።
ምስሉ ላይ ሲታይ፥ የውጭ አገሪቱ እናት ደንግጣ፣ ኢትዮጵያዊቷ እናት ደግሞ ዘና ብላ እንደተናገሩ ሆኖ ነው የቀረበው።
በርግጥ ያስቃል። ግን ያሳቅቃል። “አቦ አታካብዳ” የሚለው ብዙ ነው። ግን አልችልም። ወግ አጥባቂ አለመሆን የማልችልባቸው ጉዳዮች አሉ!
ኢትዮጵያዊ እናቶች ሲሉን የምናስታውሰው ነገር ስለሆነ፣ ኢትዮጵያዊቷ አለች ተብሎ የቀረበው ካለምንም ንጽጽር እና አጀብ ብቻውንም ቢቀርብ፣ የብዙ ሰው ትዝታ ነውና የማሳቅ አቅም አያንሰውም። በንጽጽር ሲቀርብ ግን ‘foreign mom’ ለተባሉት (ከኢትዮጵያውያን ውጭ ላሉ እናቶች በሙሉ) የተሻለ የተንከባካቢነት፣ ለልጅ አዛኝነት እና ሰብዓዊነት ካባ እያላበሰ፥ ለኢትዮጵያውያን እናቶች ደግሞ ግድ የለሽ እንደሆኑ ያስመስላል። ይሸክካል!
ማሳቁ ብቻውን ጋርዶን እንዲህ ያሉ አደገኛ ድንጋዮችን በራሳችን ላይ የምንወረውር ከሆነ “ስም ይወጣል ከቤት ይከተል ጎረቤት”ን እንተርታለን እንጂ ምንም አናመጣም። በበኩሌ፥ ይህንን ቀልድ ለአንድ ነጭ ወዳጄ ከማስረዳ፣ ዲዳ ብሆን እመርጣለሁ።
ማነው the so called ‘foreign moms’ን አይቶ የጨረሰ እና ከልጆቻቸው ጋር የነበራቸውን ግንኙነት የሰማ/የፈተሸ? እናቶቻችንስ ቢሆኑ፥ በእኛ ፊት እንጂ፣ በዓለም ፊት እና በልባቸው ባላሉት ነገር ከሌላ ጋር ተመዝነው ለቀልድ ሲውሉ አይከብድም? ልብ አርጉ፥ አያስቅም አላልኩም። ያሳቅቃል እንጂ!
“አያ በሬ ሆይ
ሳሩን አየህና ገደሉን ሳታይ” ነው የሚተረትብን፥ ከእኛው ለእኛው!
በዚህ “ምን ታካብዳለህ?” የሚለኝ ቢኖር፥ ብሔር ላይ የተቀለዱ ቀልዶችስ ያስቃሉ እና ብንቀባበላቸው፣ ብንለጥፋቸው ምን ችግር አለው ታዲያ የሚል ጥያቄ አለኝ። አንዲት ኢትዮጵያዊት እናትን ከሌላ እናት ጋር አነጻጽረን መቀለድ ሞራላችን ከፈቀደ፣ አንዱን ብሔር ከሌላው፣ አንዱን ሀይማኖት ከሌላው ጋር ለማድረግስ ታዲያ ለምንድን ነው ሞራላችን የማይፈቅደው?
* * *
ዓለማቀፍ ዝና ያለው ሰው ሲሞት ጠብቆ፥ በረሀብ ከተጠቁ ህጻናት ፎቶ ጋር አድርጎ፥ “ሚሊዮኖች ሲሞቱ ማንም አላለቀሰም፣ 1 ሰው ሲሞት ዓለም አለቀሰ” ብሎ ትዝብት ሲለጠፍ ይጨንቀኛል። ያሳክከኛል። ሰውን ከመርዳት ይልቅ ይበልጥ ጨካኝ ያደርገዋል እላለሁ። የተራቡት ትዝ እንዲሉን ታዋቂ ሰው መሞት ነበረበት? ለምን የሰዎችን ኀዘን እንቀማለን?
* * *
አንድ ሰው በቅንጡ ሰርግ ሲጋባ፥ “ለምን ድሀ አይረዳበትም ነበር?” ብሎ ንጽጽር ይበላኛል። ድሀ መርዳት እንዳለ ሰው በውድ ሰርግ ሲያገባ ትዝ የሚለን ጉዳይ ነው? ለምንስ የሰውን ደስታ እንቀማለን?
* * *
“ተክሉ የተባለ ሳክስፎኒስት ለአሸናፊ ከበደ ገቢ ማሰባሰቢያ በተደረገ የሙዚቃ ዝግጅት ላይ፥ ሁሉም በነጻ ሲሰሩ እሱ ግን አሸናፊን ከማንም በላይ እየቀረበው፥ 200 ብር ተቀበለ። ሆዳም ነው። እንዲህ ነው፣ እንዲያ ነው። ኅሊናው ይፍረደው።”
ብሎ ከሌሎች ጋር በንጽጽር አውርቶ፣ አንድን ባለሞያ ወደሞያው ለመመለስ በተደረገ ዝግጅት ላይ፣ ሌላኛውን ባለሞያ ከሞያው መግፋት ያሳስባል። አንድን ሰው ለመርዳት ተብሎ ሌላን ሰው አደጋ ላይ የሚጥል ስርዓት ለምን እንፈጥራለን? እሱ ያለበትን ወጪ እና የኑሮ ስንክሳር ያውቃልና ለሰራበት ስራ ከተከፈለው በኋላ ስም ማንሳት ለምን ያስፈልጋል?
አሸናፊ ከበደ ጥሩ ድምጽ እና ችሎታ እያለሁ፣ መስራት ባለመቻሉ ምክንያት እርዳታ እየተሰበሰበለት ነው። ተክሉም ቢሆን ሳክስፎኒስት ስለሆነ ብቻ እና ቆሞ ስለሄደ ስላለበት የኑሮ ጫና መናገር አይቻልም። አልሰረቀም ይኼ ልጅ፣ ወሰደ ማለትን ምን አመጣው? የገንዘብ ችግር እንደሌለበትም ተፍተፍ ሲል ስላየን ብቻ መፍረድ አንችልም። ያለበት የሕይወት ጣጣ (commitments) ይኖራሉ።
ያንን እንዳያደርግ ያስቻለውን ምክንያት ራሱ ብቻ ነው የሚያውቀው። እነኧከሌ በነጻ ስለሰሩ እሱም በነጻ አልሰራም ብሎ እያነጻጸሩ መዝለፍ ያስጨንቃል።
ነገሮች ስለሚነጻጸሩ ብቻ ሳይሆን፣ የመነጻጸራቸውን አስፈላጊነት በማወቅ ብናነጻጽር ይሻላል እላለሁ!