…ዝናሽ ለምን ተሰደደች?

“እንደምን ነሽ ሸገር
የእነ ሮቤል ኪሮስ፣ የኮካዎች አገር”

ካለነገር አይደለም ሮቤልን (aka the whale) ጠቅሼ ነገሬን መጀመሬ። ስለስፖርት እና ስለዓለም አቀፍ ውድድሮች ውክልና ሲወራ፥ ያለውን የተበላሸ አሰራር መልክ በሱ ልክ ለዓለም ያሳየ የለምና ነው። ያው ኮካ ኮካ ነው። ድራሹ ይጥፋ!

ሰበቤ ደግሞ ፈረንሳይ ውስጥ በምትኖርበት አፓርትመንት ውስጥ በኤርትራዊ ወጣት በትራስ ታፍና፣ በተሸለመችው ዋንጫ ጭንቅላቷን ተመትታ የሞተችው የ27 ዓመቷ ኢትዮጵያዊት ዝናሽ ገዝሙ ናት። ሞቷ/አሟሟቷ እጅግ በጣም ያንገበግባል። 😥 ነፍሷን ይማረው! ለቤተሰቦቿም መጽናናት ይኹን!

ግን ለምን ተሰደደች?? እሷ ብቻ ሳትሆንም ብዙ አትሌቶች ለምን ተሰደዱ/ይሰደዳሉ? አሸንፈው በቴሌቪዥን እስኪታዩ ድረስስ እንዲህ ባለ ውጣ ውረድ ውስጥ እንደሚያልፉ ስንቶቻችን አስበነው እናውቃለን? አገር ውስጥም በሶ መበጥበጫ ካቅሙ ብርቅ ሆኖባቸው በታጠፈ አንጀት ልምምድ የሚያደርጉ ስንት ተስፈኛ ወጣቶች አሉ!? እንደዜጋ ቢቀር፥ መንግስት እንደ ኢንቨስትመንት ቆጥሮት፥ ከድሀው ሕዝብ የተሰበሰበውን፣ ከገደላ ገደሉ ቀፈቴ ቆንጥሬ እንዴት “ቀለብ ልስፈርላቸው” አይልም?

24129742_2033573766659094_7074890654497629838_n.jpg

 

(ሌላ ሞያ ላይ ያሉትን ዜጎች ትቼ ስለአትሌቶቹ መጠየቄ፥ ዕድሉን ካገኙ፣ የልፋታቸው ውጤት የትም ተሁኖ በንጹህ ላብ የተጠራቀመ ጠቀም ያለ ገንዘብ፣ ክብርና ዝና መሆኑ ስለሚታወቅ ነው። እንዲህ ያሉ ለሀገር ሀብትም፣ ክብርም መሆን የሚችሉ ብርቅዬዎች፥ የውጭው በር የሚከፈትላቸው የውስጡ በር እንዴት እንዴት ተዘግቶባቸው ውጭ ውጭ ቢያሳያቸው ይሆን? ብዬ ነው።)

በርግጥ እንደ ፈይሳ ሌሊሳ ያሉ ግልጽ በሆነ ፖለቲካዊ አመለካከታቸው የተነሳ የሚሰደዱ አሉ። አብዛኞቹ ግን ችሎታ እያላቸው፥ ዘመድ ስለሌላቸው ውድድሮች ላይ የመሳተፍ በሮች እየተዘጉባቸው እንደሆነ ይፋዊ በሆነ መልኩ ባይሆንም በገደምዳሜ ይሰማል። ሯጮቹ ገጽታ ላይም የሚታይበት አጋጣሚ ብዙ ነው። በተለይ ውድድሮችን አሸንፈው ለሽልማት ሲበቁ የሚጎርፈው እንባቸው ዝም ብሎ የደስታ ብቻ አይመስለኝም።

ከጀርባ የነበረው መገፋት እና ትግል፣ ልፋትና ጥረት ሁሉ ተደራርቦ ድል ማድረግ እንደ ደራሽ ወንዝ የሚፈጥረውና፣ ቁጭት የሚያባብሰው ይመስለኛል። (የመሰረትን የለንደን ኦሎምፒክ ዕንባ ያስታውሷል።) ከጥረታቸውና ልፋታቸው ጎን ለጎን ደራርቱና እልፍነሽ ቀድመው ከቤተሰቡ ባይኖሩ ኖሮ ገንዘቤ እና ጥሩነሽን የመሰሉ ብርቆች ላናውቃቸው፣ ወይም ደግሞ ተሰደው የሰው አገር ጌጦች ሆነው ልናውቃቸው… በነሱ ምትክ ደግሞ ቦርጫም ሯጮች ልናይ እንችል እንደነበር አስበነው እናውቃለን?

ግን ዝናሽ ለምን ተሰደደች??

ዝናሽ በዋናነት፥ ለመኖር እና፣ ወላጅ እናቷን ለመጦር ተስፋ ያደረገችው አትሌቲክሱን እንደነበርና፥ የአትሌቲክስ ልምምዷን ላለማቋረጥ እና፣ እሳቸውንም ለመደገፍ በሳምንት እስከ 270 ዶላር ድረስ የምታገኝበትን ሆቴል የማጽዳት ሥራ እየሰራች፣ ከሌሊቱ 11 ሰዓት እየተነሳች ሥራ ከመሄዷ ቀድማ፣ እንዲሁም ምሽት ከሥራ ስትመለስ ጧትና ማታ ልምምድ ታደርግ እንደነበርና፥ ይኽ ጥረቷ እና ጥንካሬዋም ቡድኗ ውስጥ ከነበሩ በርካታ አትሌቶች ለየት እንደሚያደርጋት ጠቅሶ ስለልዩ ጥንካሬዋ የቀድሞ አሰልጣኟ ኒኮላስ ቫላት ተናግሯል።

አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ በጀርመን ድምጽ ሬድዮ ላይ በሙስና እና የዘመድ አሰራር ዙሪያ ተጠይቆ ሲናገር “የዝምድናው፣ የሙስናው፣ የመሳሰሉት በየትም ቦታ አሉ፤ ግን ልዩ የሚያደርገው በስፖርቱ የምታየው ሙስና እና የዝምድና የመሳሰሉት ነገር ሜዳ ላይ ቁልጭ ብሎ ለሚሊዮኖች ይታያል። ያ ደግሞ ያጋልጥኻል ማለት ነው። ምንም የፖሊስ ምርመራ ሳያስፈልገው የሚጋለጥ ነገር ነው። እኔ የምጥረው ያ እንዳይኾን ነው።” ማለቱም ይታወሳል።

እንግዲህ እሱ ከውስጥ ሆኖ በዚህ ደረጃ ከገለጸው፥ በውጭ ያለነው ሰዎች ስለአትሌቶች ስደት ሲወራ፣ እንደ ዋና ምክንያት የአሰራሩ ብልሹነት ነው ብንል ልክ አይደላችሁም አንባልም ማለት ነው።

ሆኖም “ሞተች” የተባለችን ምስኪን “ለምን ተሰደደች?” ብሎ መጠየቁ፥ ሌሎች የሞያ አጋርና እኩዮቿ እንዲጠበቁ ጥሪም ጭምር ነውና፥ በእሷ ሞት የተነሳ አንድ እንኳን ተስፋ ያለው አትሌት፣ አገሩ ላይ ተለማምዶ አገሩን ወክሎ መወዳደር እየፈለገና እየቻለ፥ ባለጊዜ ካለመሆን የተነሳ ብቻ ዕድል እንዳይነፈገው ቢቻል፣ ለከርታታ ነፍሷም ጥሩ እረፍት ይሆን ይመስለኛል። መታሰቢያዋም ሁሌ ይኖራል።
.
.
ከልፋቷ ለማረፍ ላይ ታች ስትል መቀጨቷ ያሳዝናል። እግዚአብሔር ነፍሷን ይማረው። ለቤተሰቦቿም መጽናናት ይስጥ። አገዳደሏም በጣም ያሳዝናል። ገዳይዋም ተገቢውን ፍርድ እንደሚያገኝ እናምናለን። ዝናሽ በዋናነት የማራቶን ሯጭ ብትሆንም፥ በ10ሺ፣ ግማሽ ማራቶን እና ሌሎች የቤት ውስጥ ውድድሮች ፈረንሳይ ውስጥ ብዙ ጊዜ ማሸነፏ ተገልጿል።

ነፍሷ በሰላም ትረፍ!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s