ከማዕበሉ ባሻገር…

እንደሚታየው፥ ሁላችንም በፍስሀ እና በእርካታ፣ በስሜት ማዕበሉ ላይ ጡዝ ፍንጥዝ እያልን ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። ይኽን ያሳየን አምላክ ክብር ምስጋና ይግባው!
 
ሚዲያዎቹም፣ አክቲቪስቶቹም፣ ፖለቲከኞቹም፣ ጋዜጠኞቹም… ሁሉም በአንድ ዓይነት አጀንዳ ተወስዶ፣ በአንድ ዓይነት ግብር ተጠምዶ …ደፈር ብሎ የህግ የበላይነት ይከበር የሚል እና ስለፍትህ የሚጮኽ፤ ስሜታችንን ደርዝ በማስያዝ፥ ለነገ የጋራ ጉዳዮች እንድንዘጋጅ አቅጣጫ የሚጠቁም፤ የንግግር ባህላችን እንዲሻሻል የተለያዩ ዝግጅቶችን የሚያቀርብ፤
 
ቢያንስ ፍቅርን እና አንድነትን በሚያደረጅ መልኩ፥ ድሮ እነ ሂሩት መንግስቴ በ”ከሴቶች አድማስ” በ”ከያቅጣጫው” ዓይነት ፕሮግራሞች ዙሪያ ገባውን ያስቃኙን እንደነበረው፣ የገጠር እና የከተማ ማሕበረ – ባህላዊውን መስተጋብር፣ እና የጋራ እሴቶቻችንን ዓይነት እንኳን በማሳየት፥ የእርስበርስ ትስስራችንን በማውሳት፣ ለውጡን የሚያቀላጥፉ ተግባራትን የሚያደርግ ጠፍቶ፥ ሁላችንም በውዳሴ ላይ የማተኮራችንን ምክንያት ሳሰላስል እኒህን 3 ምክንያት መስለው ታዩኝ።
 
1) አጀንዳውን ሁሉ ኮካዎች ያረክሱታል!
 
በተወሰነ መልኩ ከውዳሴ መስመር ወጣ ተብሎ የሚሰጥ አስተያየት፣ ለሕወሃት ኮካዎች የሰርግና ምላሽ ያህል የሚያስቦርቅ መሆኑን ታዝበናል። በዚህም የተነሳ ምንም ዓይነት አጀንዳ ቢነሳ፣ ምንም ዓይነት ነቀፋ እና ትችት ቢከናወን ‘ይደሰታሉና’፣ ብሎ የመፍራት ነገር አለ። ለዚህ አስተዋጽኦ የሚያደርገው፥ የለውጥ ፈላጊው ወገን መካከል፥ አንዳንዶች ከሌሎቻችን የተሻልን አገር ወዳድ፣ አጋዥ፣ ሰላም እና ለውጥ ፈላጊ መስለን በመታየታችን በምናሳየው የተሟጋችነት እና አፋችሁን ዝጉ ባይነት መታገላችን ነው። ፍሬ ሀሳቡ ቀርቶ፣ ብሽሽቁ ላይ እናተኩራለን።
 
ሆኖም ግን፥ ማገዝ ፈርጀ ብዙ ነውና፣ የተሰራውን በማድነቅ ከመደሰት እኩል (ወይም በላቀ ሁኔታ) ለተራማጅ መንግስት፥ ነቀፋ ትልቅ እገዛ ያደርጋል።
 
2) አሁን ከጊዜው ጋር የሚዜመውን ካላዜምኩ፣ የሚጣጣለውን ካላጣጣልኩ፥ ኋላ ተከታይ/አድማጭ/ተመልካች ባጣስ የሚል ነገር ሊኖርም ይችላል!
 
ሲሆን፥ ማህበራዊውንም ሆነ መደበኛውን ሚዲያ ተከታታዮች ከምንቃኘው ይልቅ፣ ሚዲያው የሕብረተሰቡን ስሜት በመቃኘት ረገድ ሚና መጫወት ይጠበቅበታል። አሁን እየሆነ ያለው ግን በተገላቢጦሽ ነው። ከሕዝብ ጋር ለመቆም፤ ሰው ስለሚከፋ በሚል፣ በይፋም ባይሆን ውስጥ ውስጡን ማባበል/ማስመሰል/መመሳሰል አለ። ይህም በተለይ የኢመደበኛው ሚዲያ መሰረት አድማጭ/ተመልካቹ ስለሆነ ነው። በዚህ የተነሳ፣ ደፈር ብሎ ሀሳቡን የመግለጽ ነጻነቱን ለመጠቀም የሚሞክረውን ሳይቀር በማሸማቀቅ የምንጫወተው አሉታዊ ሚና አለ። ስድብ አስታጥቆ በብሎክ የሚያሰናብተውም ብዙ ነው።
 
ይህ ደግሞ ጭራሽ የለውጡን ጽንሰ ሀሳብም የሳተ ነው!
 
3) ፍቅራችን እና ፈንጠዝያችን መሰረት ያደረገው፥ ምሬትና ጥላቻን እንጂ፣ እውነተኛ የለውጥ ፍላጎትን አይመስልም! ስለዚህም፥ ስለምንነቅለው እንጂ ስለምንተክለው ነገር ቸልተኞች ነን።
 
ይህንን ለማለት ያስደፈረኝ፥ ገና ካሁኑ የሰለቹን ነገሮች በዝተው በማየቴ ነው። ገና ካሁኑ ትናንት ከሕዝብ ጋር ሆነው ድምጻቸውን በማሰማታቸው ክብርና ተቀባይነትን ያተረፉትን ሀጫሉን እና ቴዲን በራሳችን የልብ ምት መዝነን “ዐይናችሁ ለአፈር” ለማለት በመውተርተራችንም ፍንትው ብሎ ይታያል። አምባገነኑን ኢሳያስን ባቆላመጥንበት ዕለት እና መድረክ ላይ መሆኑ ደግሞ ይበልጥ ያስገምተናል። እንደሚነዳ ፍሪዳ ለዛሬው የስሜት ነውጥ መስዋዕት ልናደርጋቸው ስንንጋጋ ፍጹም ቅሬታም ያለብን አይመስል። ስንደመር ለመቀነስ የምንሯሯጠው ነገር ብዙ ነው።
 
ይህችን አንጻራዊ ሰላም እና ነጻነት ለማግኘት የፈሰሰውን ደም፣ የጠፋውን ሕይወት፣ የተዘጋውን ልሳን፣ የተሰደደውን ሕብረተሰብ፣ የጎደለውን አካል፣ የጨለመበትን ሕይወት፣ የወረደውን እንባ በማጣጣል ውስጥ ብዙ ርቀት መጓዝ እንደምንችል እንጃ።
 
ባለፈው “ቀሪ የፖለቲካ እስረኞችም ይፈቱ” ሲባል፥ “ኸረ ባካችሁ ዘንድሮም እስረኛ ይፈታ ፖለቲካ ላይ ናችሁ። ተደመሩ” የሚሉ አፍላ ካድሬዎች አይተን በግነናል። ሶማሌ ክልል ውስጥ ሕዝብ ሲያልቅ፣ ጌዲኦ ተፈናቅሎ ሲያልቅ፣ ሀዋሳ እርሰበርስ ተባልቶ ሲያልቅ፥ ካፉ ቃል ሳይወጣ በፌሽታ ውስጥ የነበረ “ቂሊንጦ እስረኞቹ አመጹ” ሲባል፣ “ለምን እርምጃ አይወሰድም” ሲል ታዝበናል። ሰው በላው አብዲ ኢሌ ጌታቸውን አማው ብለን “ጀግና” ሲባል ሰምተን “ቦ ጊዜ ለኩሉ” ብለን ተገርመናል።
 
(የሆኑት ነገሮች ሌላ ጊዜ ቢሆን ኖሮ ፕሮፋይል ምስል የሚያስቀይሩ፣ ዘመቻ የሚያስደርጉ ነበሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩም ትናንት ያስተላለፉትን የማረጋጋት ተግባር፥ ቀደም ብለው በማድረግ በመካከል የጠፉት ሕይወቶች የመትረፍ እድል ነበራቸው) የኢትዮ ኤርትራ ሰላም ወሬ እንኳን ገና ካሁኑ የሰለቸው አለ።
 
ቸልተኝነታችን ዋዛ ቢመስልም፣ ውሎ አድሮ ስር ከሰደደ አሳሳቢ ነውና እስኪ ሀሳብ እንጨዋወትበት!
 
ሰላም!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s