ሴት ነሽና

ሴት ነሽና፥
ሰውነቱን፣ ክብሩን ትቶ፣
ቀሚስሽን ወንድ ይለካል
ደግሞ ሲለው ተንጠራርቶ
ተጠራርቶ… ደፍሮ ይነካል፤
 
ሴት ነሽና፥
“ተው” ብትዪው፥ እንደመብቱ
“ዝም በይ” ይላል በአንደበቱ፤
ማንም የለም “ተው” የሚለው፣
ሁሉም አጋዥ አበርቺው ነው፤
 
ሴት ነሽና፥
የሀሳብሽን ቁመት ልቀት
የህልምሽን ስፋት ርቀት
ወንድ ሰፍሮ ይመዝናል፣
በእርሱ ገበያ ይተምናል፤
 
ሴት ነሽና፥
በአውሬነቱ እርቃን ቀርቶ፣
ሀፍረት ጥሎ፣ ሱሪ ፈትቶ፣
ሰው ገላ ላይ ይፈነጫል፣
“አሳስታኝ ነው” ብሎ ይጮሃል፤
 
ሴት ነሽና፥
ለእርሱ ስሜት ለአውሬነቱ
ጥጋት ሆኖ ለነውሩ፣ ለሴሰኛ ሟችነቱ
አንቺን ያማል ሁሉም ወጥቶ ከየቤቱ፤
 
ሴት ነሽና፥
እሱ ሰፍሮ አጥሯል ብሎ
የደፈረሽን ተንጠላጥሎ፣
ሁሉም ወጥቶ ያጸድቅለታል
“ማን ተራቆች” አላት ብሎ፤
 
ሴት ነሽና፥
ሰዓት እላፊሽ በሰፈሩ ይተመናል
መውጫ መግቢያሽ በጎረምሳ ይሰፈራል
 
በየት ገባሽ?
በየት ወጣሽ?
ከማን ታየሽ?
ማንን አየሽ?
ሁሉም ጣቱን ይቀስራል፤
 
ሴት ነሽና፥
አትስሚያቸው!
እኔ እኔ ነኝ በይ ንገሪ፣
ብርቱነትሽን ለዓለም አውሪ፤
ለጉልበታም ጉልበትሽን
ለብልሁም ብልሃትሽን
አሳያቸው፣ እንዳጸሚ!
አንቺ ላንቺ፣ በርቺ ቁሚ
 
ቆሞ ሄደሽ ስትልቂ፣
ያኔ ይመጣል ማሪኝ ብሎ
ሂስ ቅጣቱን ተቀብሎ፣
የሰው ሁሉ ቁም ነገሩ፥
ሴት ነሽና!
ሴት ሴታታ…
ምታበሪ በቀን ማታ!
 
/ዮሐንስ ሞላ/

ስለሀሳብ ልዕልና ሲወራ…

ምርጫውን ፍትሀዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የተደረገው የቃል ተስፋ መልካም ነው። እግዚግዚአብሔር ፈቅዶ ምርጫው ነጻ ሆኖ ቢከናወን ግን፣ ኢህአዴግ በምን ቁመናው ሊቀጥል ይችላል? 🤔
 
በርግጥ “ከማያውቁት መልዐክ የሚያውቁት ሰይጣን” በሚል ብሂል የሚገብርላቸው ሊኖር ቢችልም ቅሉ፥ ለክፋታቸው ሲነዙት የኖሩት የብሄር አጀንዳ መልሶ እነሱኑ ሳይሰለቅጥ የሚመለስ በማይመስል መልኩ ተቀጣጥሏልና፥
 
“ምርጫው በነጻ እና ፍትሀዊ መንገድ እንዲደረግ ፈቃደኞች/ቁርጠኞች ነን” ማለታቸውን በራሱ፣ በሰላም እንደሚለቁ ቃል የገቡ ያህል እቆጥረዋለሁ።
 
(የሚነደው ግን፥ የነጻ እና ፍትሀዊ ምርጫ ወሬ እና ምኞት እንኳን ካለነሱ ፈቃድ የማይቻል የነበረ መሆኑ ነው። ይኽንንም ውለታ እንደዋሉ እንጂ መሆን እንዳለበት አይቆጥሩትም።)
 
ኢህአዴግ “ሀሳብ ሸጠን ነው የምናሸንፈው” ሲልና ስለሀሳብ ልዕልና ሲያወራ መስማት ይገርማል። እንደው ምናልባት በታምራት ደስታ (ነፍስ ይማር)
 
አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ
“አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ”
 
ብለው ይጀነጅኑን እንደው እንጂ ምን ቀራቸው?
 
አብረው ተባብረው ዘረፉ፣ ገረፉ፣ ደፈሩ፣ አባረሩ፣ ጣት ቀሰሩ፣ ጣት እንቆርጣለን ብለው ፎከሩ፣ ከፋፍለው አባሉ፣ ቀለም ጠልተው ቀለም ደፍተው፣ የቀለም ቀንድ ሰባብረው፣ ሕዝቡን በድንቁርና አጥረው አኖሩት፣ (ከርሞ ማመናቸውም ተመስገን ነው)፣ ምኑ ቅጡ ተሰፍሮ ተዘርዝሮ ያልቅና?
 
በተጭበረበረ ምርጫ ገነው፣ አሁንም በየመሀሉ በሊቀመንበራቸው በኩል “ተፎካካሪ” ያሉትን ይወቅሳሉ። ያስጠነቅቃሉ። ላይ ላዩን ገር ሆነው፣ ውስጥ ውስጡን አሁንም በሚዛን ሲቀመጡ እነሱ እንደሚሻሉ ያስባሉ። ያሳስባሉ።
 
በምርጫ ምክንያት ለተፈጠሩ ቀውሶች በሙሉ ዋናው ድርሻ ኢህአዴግ እንጂ ማን ሆኖ፣ አሁን “ወደኋላ ሄዶ ያለፈውን ማንሳት እና በትናንት መኖር አያስፈልግም” ካሉ በኋላ፣ በጨው መታጠብ ካልሆነ በቀር፣ መለስ ቀለስ እያሉ ሌላውን ለመውቀስ እና አበክሮ ለመውቀስስ ምን አቅም ያገኛሉ?
 
የኢህአዴግ ነገርማ
ያልጠፋነው፣
ከእግዚአብሔር ምህረት የተንሳ ነው”ን
እያስዘመረን የሚኖር ጉዳይ ነው!
 
እግዜር ቸር ቸሩን ያድርግልንማ!

ችግር ወልዶ ያሳደገውን ፍቅር፣ ማግኘት ይቀብረዋል!

46765716_1937122056408818_3712700478056824832_n

ችግር ወልዶ ያሳደገውን ፍቅር፣ ማግኘት ይቀብረዋል!
በአንድ ትሪ ማቅረብ ያመጣው ችግር ቢሆንም (ሲመስለኝ)፥ ለልጆች መተሳሰብን፣ አንተ ብስ አንቺ መባባልን አስተምሯል። ሁሉም ሰው ታጥቦ እስኪሰየም ድረስ እንጠባበቃለን።
ከአንዱ ቦታ እንጀራው ሲሳሳ፣ ከአንዱ ቆርሰን እናሳልፋለን። “አንቺ ብዪ፣ አንተ ብላ እንባባላለን። “ይኸው የኔን አታይም? ጥርግ አድርጌ በልቼ እኮ ትሪው ታየ። አንቺ አልበላሽም።” መባባሉ፣ ጨዋታው ሁሉ የሚገነባ ነገር ነበረው።
በአንድ ትሪ ሲበሉ ሁሉም ነገረ ስራው እንደእናት ይኾናል። ማቀራረቡም የጋራ ርብርብ አለውና መተጋገዝን ያጠናክራል።
በአንድ ትሪ በሚቀርብበት ዘበን፥ “ቤት ራት ይጠብቁኛል” ብሎ መሯሯጡም ነበር።
ማባያው ወጡ እንዲብቃቃ፣ ሌላውን ሰው ከግምት አስገብተን እንመገባለን እንጂ ጣፈጠኝ ብሎ መስገብገብ የለም። ሽሚያው ሲጀመርም በጋራ ነው። ከተሻማው ላይ ከአፉ ነጥቆ የሚያጎርስም አለ።
ደግሞ የተጎዳ የመሰለንን ጠቅልለን እናጎርሳለን። እየበሉ ሰው ሲገባም፣ “በሞቴ አንዴ ላጉርስህ” ይባልና ተጠቅልሎ ይላክለታል። ደግሞ “አንድ ያጣላል” ይባላል። “ኸረ በዛ” ቢል “ፍቅርና ጉርሻ ሲያስጨንቅ ነው” ይባላል።
መጎራረስን የወለደው ግን ማጣት፣ ወይም “አልጠገበም ይሆናል” የሚል ልባዊ ስስት ነበር። በትሪ ማቅረብን ያመጣውም የሳህን እጥረት ወይ ደግሞ የማጠብ ስንፍና ነበር። እንጂማ አሁን የት ይጠፋ ነበር?
ማጣት እየተቀረፈ፣ አንጻራዊ ማግኘት ሲመጣ፥ ትሪው ቀርቶ የቁርስ ሳህን መግዛት፤ እንጀራ መቁረጥ መጣ። ሁሉም የየራሱን ይበላል። ሁሉም የየራሱ ላይ ይደፋል።
ከፊት ለፊት እንጀራ ቆርሶ ማሻገር የለ። መጎራረስ የለ። እንግዳ ቢገባም “አቅርቡለት” ይባላል። “አንድ ቁርጥ እንኳን ያዝ እባክህ” ይባላል።
ታዲያ ሕይወት ካለትሪ አይሰለችም?
ይኽን የምዘበዝበው አብረን፣ አተራምሰን የበላን ወዳጆቼ ናፍቀውኝ ነው። ትሪ የተካበብኩባቸው ብዙ ወዳጆች ያሉኝ ዘመደ ብዙ ነኝ። የብዙ ሰው ጉርሻ ያሳደገኝ ነኝ።
በተለይ “የምስጋና ቀን” ላይ፣ ነጭ ከጥቁር ተሰባስቦ በአንድ ገበታ ቀርቦ በመተሳሰብ በሚመገብበት፣ ዘመድ በሚጠይቅበት፣ አቅመ ደካማውን በስጦታ እጅ በሚነሳበት ወቅት ወዳጅ ዘመድ ይናፍቃል።
ስንቱን ነገር ስንቀዳ የምስጋና ቀንን ያለመቅዳታችን ነገር ግን ይገርመኛል። ነው ወይስ ለጎጂ ቀረብ ካለው ጋር እንቀራረብ ሆኖ ነው?
ለማንኛውም መልካም ሰንበት!
ብትችሉስ በትሪ አቅርቡ! 😉
ፎቶ፡ ከፌስቡክ መንደር የተገኘ!

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ…

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ ነው ስንል በምክንያት ነው። የጥቅም እና ዝርፊያ ተካፋይነቱን ሕወሃት የበላይ ሆኖ ቢሰፍርበትም፥ ትናንት ሁሉም በተመቸው እና ጊዜው በፈቀደለት ልክ ዘግኗል፣ አንገላቷል፣ በየፈርጁ እና በየደረጃውም፥ የግፉም የዝርፊያውም ተካፋይ ነበር። የሚደርሰው ወንጀል እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሁሉ እንዳይታወቅ በመሸፋፈን ረገድም ሁሉም አባል ይኽ ነው የማይባል ሚና ተጫውቷል። ምንም እንኳን በሕወሃት የበላይነት ቢዘወርም፥ የሰብአዊ መብት ጥሰቱን እና ንጹሐንን የማፈኑን ሥራም በድርጅት ደረጃ አቋም እና አተገባበር ይዘው ሲያደርጉት የነበረው ነውና፣ የጭንቀት ቀን ሲመጣ ጣት መቀሳሰሩ በኅሊና ዳኝነት ፊት የትም አያደርስም። ማናቸውም አሸባሪውን ድርጅት ሲያገለግሉ እንጂ፣ ገዳም አልነበሩም።

ሁሉም ደርሶ በድል አጥቢያ አርበኝነት ስሜት እና በለውጠኝነት ሽፋን ጣት ቀሳሪ ይሁን እንጂ፣ ለመዛኝ እና ለፈራጅነት የሚያበቃ ንጽህና ያለው ያን ያህል አይደለም። ምንም አያውቅም የሚባለው አባል እንኳን፣ ቢያንስ ዝም በማለት እና ንጹሐን ሲንገላቱ ባለመከላከል፣ ድሀ ሕዝብ ሲመዘበር የምዝበራው አበል ተካፋይ በመሆን እያመሰገነ እና፤ አባል ያልሆኑና ያገባኛል ያሉ ሰዎችን በጠላትነት እየፈረጀ ኖሯል። የኢትዮጵያ አምላክ ራቁት እሲያስቀር፣ የጊዜ ፈረስ እንዲህ በአፍጢም እስኪፈጠፍጥ ድረስ!

በርግጥ፥ አንድም ይሁን ሁለት፣ ያጠፋ ሰው መጠየቅ መጀመሩ አግባብ ነው። ሆኖም ግን፥ የሌላው ነውረኝነት አለመጋለጥ፣ የተጋለጡትን እና በህግ ለመጠየቅ መንገድ የተጀመረላቸውን ሰዎች ጉዳይ ስህተት አያደርገውም። ዛሬ ጊዜው ፈቅዷል፣ ትናንት አልፏል በሚል ቀመር፥ አብረው ሲፈተፍቱ፣ የሕዝብ ደም ሲገብሩ እና ነውሩን ሲጋርዱለት፣ በታማኝነት እና ቁርጠኝነት ሲያገለግሉት የነበሩትን ድርጅት “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ” በሚል ጲላጦሳዊ ግብዝነት ሲነዛ ግን፥ አሁንም ህሊና ካለ ይፈርዳል።

እንደማሳያ፥ ሰሞኑን በድፍረታቸው እና አጋላጭነታቸው ተደንቀን፣ አፋችንን ከፍተን ሀቀኝነታቸውን የመሰከርንላቸውን አምባሳደር ሱለይማን ደደፎን የትዊተር ገጽ በጊዜ ወደ ኋላ ተመልሰን በመቃኘት ነገሬን ልቀጥል።

አቶ ሱለይማን ዛሬ ፓርቲአቸው ኦህዴድ የበላይ ባይሆን እና ሕወሃት ቢቀጥል ኖሮ፣ ሰጥ ለጥ ብለው የሚገዙ እንጂ “ግፍ አንገፈገፈኝ” ብለው የሚለቁ አይነት ነበሩ የሚያስችል የጀርባ ታሪክ እንዳላቸው የሚያሳይ ማስረጃ የለም። በርግጥ እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ሌሎች አባላቶችም እንዲሁ ከመጣው ጋር ቀጥለው፣ በጥሎ ማለፍ ድርጅታቸውን እያሽሞነሞኑ ይቀጥሉ እንደነበር መገመትም ከባድ አይደለም። ድርጅታቸው ኢህአዴግን በታማኝነት ከማገልገል ባለፈ፥ ሲያደርግ የኖረውን ነገር በመሸፋፈን እና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በማሳጣት የተጫወቱት ሚና ብዙ ነው።

በኦክቶበር 2013 የአፍሪካ አገራት በኢትዮጵያ መንግስት አዘጋጅነት፣ እነ ኡሁሩ ኬኒያታ የሰው ልጆች ላይ ወንጀል በመፈጸማቸው  በሚል መከሰሳቸውን ለመከላከል፥ በአዲስ አበባ አስቸኳይ ስብሰባ አድርገው ነበር። አጀንዳቸውም የዓለማቀፉን የወንጀል ፍርድቤት International Criminal Court (ICC) ለመቃወም ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በተባበሩት መንግስታት ስብሰባ ተገኝተውም ፍርድቤቱን መተቸታቸውን ተከትሎ፥ የአፍሪካ መሪዎችን ስብሰባ ጠርተው ነበር። ነገሩ “ነግ በእኔ”፤ “አፍንጫ ሲመታ አይን ያለቅሳል” ነበር። በተለይ ደግሞ የነገሩ ጠንሳሽ ኢትዮጵያ መሆኗ “ፈስ ያለበት ዝላይ አይችልም” ዓይነት ነበር።

ታዲያ ያንን ተከትሎ፥ ከሁለት ወይም ከሶስት ሳምንታት በኋላ በኦክቶበር 28 ቀን፥ አቶ ሱለይማን

I am skeptical on the very intention to create the ICC. Why doesn’t it open its eyes on the whole globe than giving excess attention to Africa?

በማለት ለአምባገነኖቹ የአፍሪካ መሪዎች መቆርቆራቸውን ገልጸው ነበር።

1

ኖቬምበር 15 ቀን 2013፥ የሳውዲ አረቢያ መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ የነበረውን ስቃይ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት በማውገዝ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በሳውዲ አረቢያ ኤምባሲ ደጃፍ ላይ ለማካሄድ በጠራው የሰላማዊ ሰልፍ ላይ የወጡ ሰዎች፣ ላይ ፖሊስ የተቃውሞ ሰልፉን በመከልከል ሰዎችን ደብድቦ እና አስሮ ነበር።  ታዲያ በዚያን ቀን፥ አቶ ሱለይማን

Ethiopian Gov’t has allocated 50 million Birr to integrate Ethiopians deported from Saudi Arabia. But what do the opposition parties are doing? Ethiopian opposition parties are trying to benefit out of tears of Ethiopian migrants in Saudi Arabia as usual. Why?

ብለው በሁለት ትዊት ጽፈው ነበር።

2.jpg

በመጀመሪያ የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘቡን የመደበው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ንብረት ላይ መሆኑን ዘንግተውት እንደልግስና ቆጥረውት ተመጻድቀው ነበር። ገንዘቡ በአግባቡ ይዋል አይዋልም አይታወቅም። ሆኖም ግን፥ በወቅቱ ለወገን በመቆርቆር የተጠራን ሰልፍ ተከትሎ፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን በጅምላ ለመፈረጅ እና፣ እንደ ኢህአዴግ አባልነታቸው “ተቃዋሚዎች በሕዝብ እንባ ለማትረፍ የሚሞክሩ ናቸው” ብሎ ስም ለመለጠፍ እና፣ “መንግስት ይህን ሲያደርግ፣ እነሱ ግን ምንም እንዳላደረጉ” ለማጉላት ዳክረው እንደነበር እናያለን።

20131115163925420734_20

(እንደፓርቲ ከአባላት ከሚያገኙት መዋጮ ላይ መቋቋሚያ እንዲሰጡ ጠብቀው ነበር ማለት ነው። እንደተቃዋሚ ፓርቲነታቸውም ለዜጎች ጥቃት መቆርቆራቸውንም አቃለዋል።) ከዚህ በላይ ኢህአዴን መጋረድ እና የሰብአዊ መብት ጥሰቱን መደገፍ ከየት ይመጣል?

እነ ወ/ሮ ሚሚ ስብሀቱ፣ አቤል ተስፋዬ እና መርከብ ነጋሽ ተሳትፈውበት በነበረ “የቀለም አብዮት” ዶክመንተሪ ማግስት፥ የዞን 9 ስድስት ጦማርያን እና 3 ጋዜጠኞች ወዳጆቻችን በአፕሪል 2014 መታሰራቸውን ተከትሎ፥ አቶ ሱለይማን፣ በሜይ 1 2014፥

Zone Niners are messangers of color revolution hired by neo-liberal masters. They are instructed to create violence ahead of next election. Press Freedom is not systematic invasion or campaign to change regime by color revolution. That is what the west are trying in Ethiopia.

ብለው ንጹሀን ላይ ጣታቸውን ቀስረው፣ እና የመንግስትን ጭቆና ለመሸፈን ሞክረው እንደነበርም እናስታውሳለን።

4.jpg

የመንግስትን የተጋነኑ “የኢንቨስትመንት” ወጪዎችን በተመለከተም፥ በዲሴምበር 3፣ 2014

Where will huge state investments lead Ethiopia? Obviously to growth

ብለው ጽፈው ነበር።

6

እንግዲህ ወደ እድገት ያመራናል ያሏቸውን ወጪዎች በተመለከተ ነው፣ አሁን ያላየ፣ ያልሰማ ሆነው በጻድቅ ምስክርነት የቆሙት። ምስክርነት መቆማቸውን መንቀፌ አይደለም፣ ነገር ግን ትህትና የቀላቀለ ቢሆንና፣ ሁላቸውም መነካካታቸውን የማይክድ መንፈስ ያረበበት አነጋገር ቢሆን የሚል የከሸፈ ጉጉት እንጂ።

በሌላ ማሳያ፥ የአሁኑ የጠቅላይ አቃቤ ህግ፣ የያኔው የፍትህ ሚንስትሩ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ፥ በ2011

ያለ ፍርድቤት ትዕዛዝ አይታሰርም። ያለፍርድቤት ውሳኔ አይቀጣም። በምርመራ ወቅት ድብደባ የለም። ግርፋት የለም። ሕገመንግስታችን ይከለክላል። እነዚህን ነገሮች ማለት ነው። ስለዚህ እንደዚህ ተደርጓል፣ እንደዚህ ተደርጓል ተብሎ አሉባልታ ካልሆነ በስተቀር በተጨባጭ እንደዚህ አይደረግም። በማረሚያ ቤት የሚገኙ፣ በምርመራ ላይ የሚገኙ፣ በፍርድቤትም የሚገኙ ማየትም፣ መጎብኘትም ይቻላል። እየተደረገም ነው። በውስጥም በውጭም ባሉት አካላት ነው። በዋናነት ለነዚህ አካላት አይደለም መንግስት እነዚህን ስራ የሚሰራው።

በዋናነት፥ ቅድም እንዳልኩት፣ ህገመንግስቱ ላይ የተቀመጡትን መብቶች የማስከበር፣ የማክበር ኃላፊነት የመንግስት ነው። ይሄም ህግ የወጣው፣ [የዜጎችን] መንግስት ሌት ተቀን እየሰራ ያለው፣ የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር ነው እንጂ ሌሎች ሶስተኛ ወገን የውጭ አካላትን ለማስደሰት፣ ወይ ደሞ ለማስቀየም አይደለም። ለዜጎች፣ የዜጎችን መብት ለማስጠበቅ፣ በአገራችን ውስጥ የዴሞክራሲ ስርዓት ስር እንዲሰድ ለማድረግ ነው እየተሰራ ያለው እንጂ፤ ለነዛ አካላት ተብሎ የሚሰራ ነገር አይደለምና፣ ጣልቃ የሚገባበት ነገርም አይኖርም።

ባሉበት አንደበታቸው፣ ባለፈው ሳምንት በቁጥጥር ሥር የዋሉ ሰዎችን አስመልክቶ የሰጡት መግለጫ ላይ፥ ይደርስ የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት የገለጹበትን መንገድ እናስታውሳለን። ቪዲዮውን እዚህ ይመልከቱ።

የበፊት ንግግራቸው መታወሱ ሲወራ፣ ወዲያውኑ ዋልታ የያኔውን ቪዲዮ ከድረ ገጹ ላይ ወዲያው ያነሳው ቢሆንም፣ ቀድመው ያወረዱት ሰዎች እየተቀባበሉት ተመልክተነዋል። (ዋልታስ ቪዲዮውን ማንሳቱ ምን ይባላል?)

እንግዲህ በደም የተጨማለቀ ስርዓትን በሀቀኝነት ማገልገል እና ሲደርስ የነበረውን ግፍ እና በደል ሁሉ፣ የሰብአዊ፣ የዴሞክራሲ እና የሕገመንግስት ሽፋን በመስጠት እንዳልነበሩ፥ አሁን ሌላው ላይ በሚናገሩት ነገር ህሊና ቢኖር ኖሮ አይሸመቅቅም ነበር ወይ?

ከላይም እንዳልኩት፥ ትናንት እንዲህ ተደርጎ ነበርና ዛሬ ዝም ይባል አይደለም። ቢያንስ ግን፥ ትናንት ተሳትፎ የነበራቸው፥ ከጋዜጠኛ እስከ ባለስልጣን፤ ከተራ አባል እስከ ፈላጭ ቆራጭ ድረስ፥ “ስላልተጋለጥን/ስለማንጋለጥ” በሚል ስሜት፥ ወይም በኖሩበት የአድርባይነት ስሜት፣ ነገሮችን ሲተርኩ፣ ፍጹም ከደሙ ንጹህ መስለው ለመታየት የሚያደርጉትን ነገር በልኩ ቢያደርጉት የሚል ነው። አሁንም ተጠያቂነት ድንበር አይኑረው!

እንግዲህ መመዘዝ የተጀመረው የሙስና እና የሰብዓዊ ጥቃት ክር የት ጋ እንደሚቆም በጉጉት እና በሌሎች በራሪ እንስሳዎች እናያለን! 😉

ዕድሜና ጤና ይስጠን እንጂ ከጊዜ ዳኝነት ማንም አያመልጥም!

ሰላም!