ሴት ነሽና

ሴት ነሽና፥
ሰውነቱን፣ ክብሩን ትቶ፣
ቀሚስሽን ወንድ ይለካል
ደግሞ ሲለው ተንጠራርቶ
ተጠራርቶ… ደፍሮ ይነካል፤
 
ሴት ነሽና፥
“ተው” ብትዪው፥ እንደመብቱ
“ዝም በይ” ይላል በአንደበቱ፤
ማንም የለም “ተው” የሚለው፣
ሁሉም አጋዥ አበርቺው ነው፤
 
ሴት ነሽና፥
የሀሳብሽን ቁመት ልቀት
የህልምሽን ስፋት ርቀት
ወንድ ሰፍሮ ይመዝናል፣
በእርሱ ገበያ ይተምናል፤
 
ሴት ነሽና፥
በአውሬነቱ እርቃን ቀርቶ፣
ሀፍረት ጥሎ፣ ሱሪ ፈትቶ፣
ሰው ገላ ላይ ይፈነጫል፣
“አሳስታኝ ነው” ብሎ ይጮሃል፤
 
ሴት ነሽና፥
ለእርሱ ስሜት ለአውሬነቱ
ጥጋት ሆኖ ለነውሩ፣ ለሴሰኛ ሟችነቱ
አንቺን ያማል ሁሉም ወጥቶ ከየቤቱ፤
 
ሴት ነሽና፥
እሱ ሰፍሮ አጥሯል ብሎ
የደፈረሽን ተንጠላጥሎ፣
ሁሉም ወጥቶ ያጸድቅለታል
“ማን ተራቆች” አላት ብሎ፤
 
ሴት ነሽና፥
ሰዓት እላፊሽ በሰፈሩ ይተመናል
መውጫ መግቢያሽ በጎረምሳ ይሰፈራል
 
በየት ገባሽ?
በየት ወጣሽ?
ከማን ታየሽ?
ማንን አየሽ?
ሁሉም ጣቱን ይቀስራል፤
 
ሴት ነሽና፥
አትስሚያቸው!
እኔ እኔ ነኝ በይ ንገሪ፣
ብርቱነትሽን ለዓለም አውሪ፤
ለጉልበታም ጉልበትሽን
ለብልሁም ብልሃትሽን
አሳያቸው፣ እንዳጸሚ!
አንቺ ላንቺ፣ በርቺ ቁሚ
 
ቆሞ ሄደሽ ስትልቂ፣
ያኔ ይመጣል ማሪኝ ብሎ
ሂስ ቅጣቱን ተቀብሎ፣
የሰው ሁሉ ቁም ነገሩ፥
ሴት ነሽና!
ሴት ሴታታ…
ምታበሪ በቀን ማታ!
 
/ዮሐንስ ሞላ/

ስለሀሳብ ልዕልና ሲወራ…

ምርጫውን ፍትሀዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የተደረገው የቃል ተስፋ መልካም ነው። እግዚግዚአብሔር ፈቅዶ ምርጫው ነጻ ሆኖ ቢከናወን ግን፣ ኢህአዴግ በምን ቁመናው ሊቀጥል ይችላል? 🤔
 
በርግጥ “ከማያውቁት መልዐክ የሚያውቁት ሰይጣን” በሚል ብሂል የሚገብርላቸው ሊኖር ቢችልም ቅሉ፥ ለክፋታቸው ሲነዙት የኖሩት የብሄር አጀንዳ መልሶ እነሱኑ ሳይሰለቅጥ የሚመለስ በማይመስል መልኩ ተቀጣጥሏልና፥
 
“ምርጫው በነጻ እና ፍትሀዊ መንገድ እንዲደረግ ፈቃደኞች/ቁርጠኞች ነን” ማለታቸውን በራሱ፣ በሰላም እንደሚለቁ ቃል የገቡ ያህል እቆጥረዋለሁ።
 
(የሚነደው ግን፥ የነጻ እና ፍትሀዊ ምርጫ ወሬ እና ምኞት እንኳን ካለነሱ ፈቃድ የማይቻል የነበረ መሆኑ ነው። ይኽንንም ውለታ እንደዋሉ እንጂ መሆን እንዳለበት አይቆጥሩትም።)
 
ኢህአዴግ “ሀሳብ ሸጠን ነው የምናሸንፈው” ሲልና ስለሀሳብ ልዕልና ሲያወራ መስማት ይገርማል። እንደው ምናልባት በታምራት ደስታ (ነፍስ ይማር)
 
አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ
“አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ”
 
ብለው ይጀነጅኑን እንደው እንጂ ምን ቀራቸው?
 
አብረው ተባብረው ዘረፉ፣ ገረፉ፣ ደፈሩ፣ አባረሩ፣ ጣት ቀሰሩ፣ ጣት እንቆርጣለን ብለው ፎከሩ፣ ከፋፍለው አባሉ፣ ቀለም ጠልተው ቀለም ደፍተው፣ የቀለም ቀንድ ሰባብረው፣ ሕዝቡን በድንቁርና አጥረው አኖሩት፣ (ከርሞ ማመናቸውም ተመስገን ነው)፣ ምኑ ቅጡ ተሰፍሮ ተዘርዝሮ ያልቅና?
 
በተጭበረበረ ምርጫ ገነው፣ አሁንም በየመሀሉ በሊቀመንበራቸው በኩል “ተፎካካሪ” ያሉትን ይወቅሳሉ። ያስጠነቅቃሉ። ላይ ላዩን ገር ሆነው፣ ውስጥ ውስጡን አሁንም በሚዛን ሲቀመጡ እነሱ እንደሚሻሉ ያስባሉ። ያሳስባሉ።
 
በምርጫ ምክንያት ለተፈጠሩ ቀውሶች በሙሉ ዋናው ድርሻ ኢህአዴግ እንጂ ማን ሆኖ፣ አሁን “ወደኋላ ሄዶ ያለፈውን ማንሳት እና በትናንት መኖር አያስፈልግም” ካሉ በኋላ፣ በጨው መታጠብ ካልሆነ በቀር፣ መለስ ቀለስ እያሉ ሌላውን ለመውቀስ እና አበክሮ ለመውቀስስ ምን አቅም ያገኛሉ?
 
የኢህአዴግ ነገርማ
ያልጠፋነው፣
ከእግዚአብሔር ምህረት የተንሳ ነው”ን
እያስዘመረን የሚኖር ጉዳይ ነው!
 
እግዜር ቸር ቸሩን ያድርግልንማ!