ሴት ነሽና፥
ሰውነቱን፣ ክብሩን ትቶ፣
ቀሚስሽን ወንድ ይለካል
ደግሞ ሲለው ተንጠራርቶ
ተጠራርቶ… ደፍሮ ይነካል፤
ሴት ነሽና፥
“ተው” ብትዪው፥ እንደመብቱ
“ዝም በይ” ይላል በአንደበቱ፤
ማንም የለም “ተው” የሚለው፣
ሁሉም አጋዥ አበርቺው ነው፤
ሴት ነሽና፥
የሀሳብሽን ቁመት ልቀት
የህልምሽን ስፋት ርቀት
ወንድ ሰፍሮ ይመዝናል፣
በእርሱ ገበያ ይተምናል፤
ሴት ነሽና፥
በአውሬነቱ እርቃን ቀርቶ፣
ሀፍረት ጥሎ፣ ሱሪ ፈትቶ፣
ሰው ገላ ላይ ይፈነጫል፣
“አሳስታኝ ነው” ብሎ ይጮሃል፤
ሴት ነሽና፥
ለእርሱ ስሜት ለአውሬነቱ
ጥጋት ሆኖ ለነውሩ፣ ለሴሰኛ ሟችነቱ
አንቺን ያማል ሁሉም ወጥቶ ከየቤቱ፤
ሴት ነሽና፥
እሱ ሰፍሮ አጥሯል ብሎ
የደፈረሽን ተንጠላጥሎ፣
ሁሉም ወጥቶ ያጸድቅለታል
“ማን ተራቆች” አላት ብሎ፤
ሴት ነሽና፥
ሰዓት እላፊሽ በሰፈሩ ይተመናል
መውጫ መግቢያሽ በጎረምሳ ይሰፈራል
በየት ገባሽ?
በየት ወጣሽ?
ከማን ታየሽ?
ማንን አየሽ?
ሁሉም ጣቱን ይቀስራል፤
ሴት ነሽና፥
አትስሚያቸው!
እኔ እኔ ነኝ በይ ንገሪ፣
ብርቱነትሽን ለዓለም አውሪ፤
ለጉልበታም ጉልበትሽን
ለብልሁም ብልሃትሽን
አሳያቸው፣ እንዳጸሚ!
አንቺ ላንቺ፣ በርቺ ቁሚ
ቆሞ ሄደሽ ስትልቂ፣
ያኔ ይመጣል ማሪኝ ብሎ
ሂስ ቅጣቱን ተቀብሎ፣
የሰው ሁሉ ቁም ነገሩ፥
ሴት ነሽና!
ሴት ሴታታ…
ምታበሪ በቀን ማታ!
/ዮሐንስ ሞላ/