
በነገራችን ላይ፥ ጉራጌ ካለው ነገር አንዱ፣ ምናልባትም በደንብ ያልተነገረለት፣ የመስጠት ባህሉ ነው። የምርቃት ባህሉም ሌላው ነው። ግፍ፣ ነውር ይፈራል። ቀመጥ ይሰርፍ ይባላል።
እንደ ጥሩ ምሳሌ፥ በመውደድ ክብሩ “ያዊዌ” ዘፈን ላይ፣ ሽምግልና ተልኮ ልጅቷ ትሰጠው ወይ?” ተብሎ መጠያየቃቸው፣ እሱም እሷን አይቷት ልቡን ከጣለ በኋላ መጨናነቁ፣ በኋላም ሲሳካለት ሰዉን በግብዣ ሲያንበሸብሽ ነው ታሪኩ ማጠንጠኛው። (“ያዊዌ” ማለት “ይሰጠው ወይ?” ማለት ነው።)
ተፈቃሪዋ ቆንጆም፣ ለትዳር የሚሆናት የማይሆናት መሆኑን ለማወቅ ሶስት ጥያቄዎች ነው የምትጠይቀው
1) ንቅ ቃር ትረምዴ ዌ? (በጣም ትወደኛለህ ወይ?)
2) ሜና ትረምድ ዌ? (ሥራ ትወዳለህ ይ?)
3) ቀመጥ በሰረፍከ (ነውር፣ ግፍ ከፈራህ) …መውደድ እናቴርኸ (አታርፍድ ውሰደኝ) ነው የምትለው።
እንጂ እንደተለመደው “ቤት አለው ወይ? ስራው ምንድን ነው? ንብረቱ ምንድን ነው?” የሚሉ ባህላዊ የሽምግልና ጥያቄዎች አይደለም የሚነሱት። ግፍ ከፈራ፣ ከወደዳትና ሥራ ከወደደ በቂዋ ነው። ሁሉንም ሰርተው እንደሚያገኙ ታውቃለች።
በልምድ ገኖ የሚወራው ቋጣሪነቱ፣ ከምክንያታዊነት ጋር የሚያያዝ ነው። እንጂ ስስት አያውቅም። በነገራችን ላይ ጉራጌን ቋጣሪ የሚሉት፣ የሰው ንብረት የሚመኙ ወይም ቁጭ ብለው መቀለብ የሚፈልጉ ናቸው። ለሰው በሙሉ እጁ ቁም ነገር የሚሰራበትን ይሰጣል እንጂ፣ እንዲመላለስ የሚያደርግ ቁጥ ቁጥ አያውቅም። ሰው በልቶ የሚጠግብም አይመስለውም። የገንዘብን ጥቅም እና አመጣጡን ያውቃልና ካላግባብ የሚወጡ ብሮች ያናንዱታል።
ጋብዞ፣ ድግስ ጥሎ፣ ወይ ሰው ለመርዳት በአግባቡ የሚያወጣው 100 ሺህ ብር እና እንዲሁ ተሸውዶ ወይም ያላግባብ የሚያወጣው 100 ብር ስሜት ሲነጻጸሩ፣ የ100 ብሩ ያበግነዋል። አዲስ ሰው ወይም የከሰረ ወዳጁን ስራ ለማስጀመር ያለውን ከማዋጣት አንስቶ፣ እቁብ ሰብስቦ አንደኛ እጣ በመስጠት ባህሉ ይታወቃል። በሀዘን እና በደስታም አብሮ ተካፋይ ነው እንጂ የዳር ተመልካች አይደለም።
በአካባቢ በጎ ፈቃደኝነት ስራም (voluntarism) ጉራጌ ስመ ጥሩ ነው። በየደረሰበት አካባቢውን ምቹ ለማድረግ ይተጋል። ሁሉም ጋር ይዞራልና ሁሉም ቤቱ፣ ሁሉም አገሩ ነው። መንግስት ሳይቀሰቅሰው ኮሚቴ አዋቅሮ፣ በሰንበት አካባቢውን ያያል። ጉብታውን ሜዳ ያደርጋል። ገደሉን ይሞላል።
ሌላው ደግሞ የሴቶችን ነጻነት/እኩልነት ለማስከበር ያለው ታሪኩ ተጠቃሽ ነው። ዓለም ፌሚኒዝምን ማቀንቀን ሳይጀምር “እምቢ አሻፈረኝ” ብላ አምጻ፣ ሴቶቹን አሳምጻ መብት ያስከብችው ፌሚኒስት ጉራጌዋ የቃቄ ውርድወት ናት። ታሪኩ በቴአትርም ተሰርቶ ብሔራዊ ቴአትር ታይቷል። እንዲሁም የእንዳለ ጌታ ከበደን “እምቢታ” ብታነቡ ትደነቃላችሁ።
ከዚህም ባሻገር በበዓላት የወንዶች እና የሴቶች የስራ ክፍፍል አለ። ሶፋ ላይ ተጋድሞ ሪሞት እየነካኩ “አልደረሰም” ወይ የማለት ቅንጦት የለውም የጉራጌ ወንድ። ተፍ ተፍ ብሎ፣ እንጨት ፈልጦ፣ ኮባ ቆርጦ፣ ደጅ አጽድቶ አብሮ በስራ ይሳተፋል። በከተፋ ጊዜም ስጋ በመመራረጥ እና በመለየት ያግዛል። የሚከትፍም አጋጥሞኝ ያውቃል።
ከመስቀል በዓል አንድ ቀን ቀድሞ ያለው ቀን፣ ዴንጌሳት ወይም የሴቶች መስቀል ነው የሚባለው። የሴቶች መስቀል መባሉ፣ ሴቶች ሙሉ ለሙሉ ከወጪ እስከስራ ራሳቸው ችለው የደረሰውን እንግዳ ስለሚያበሉ ነው። ተራ ቢመስልም፣ እንደእኛ ብዙ በሚቀረው እና ሴት በደመወዝ ስትበልጠው በሚከፋ ማህበረሰብ ውስጥ፣ አንድምታው ትልቅ ነው።
እንደዚሁም አስተርዮ ማርያም የሴቶች ገና በመባል ይታወቃል። እንደፈለጉ አምሽተው፣ አድረው ሲጫወቱ እና ሲበሉ ቢያነጉ ማንም አይታዘባቸውም፣ አይናገራቸውም። አሁን አሁን ዘመን ሲሰለጥን ቀረ እንጂ፣ የፊቂይር ገብያ በሚባል የሚታወቅ የመተጫጨት የጨዋታ ስርዓት ነበር። እዚያ ላይ ወንዱ ብቻ አይደለም የመምረጥ መብት የነበረው። ሴቷም ልቧ የፈቀደውን በዘፈን ግጥም እየደረደረች፣ ወይም በዐይን እየተያየች ስሜቷን ታስተናግዳለች። ለዚያም ነው ገበያ መባሉ። ሸጪ እና ገዥ ካልተስማማ ነጥቆ መሮጥ የለ ገበያ ውስጥ።
በዓል በመጣ ጊዜም፥ ለቤቱ ሰንጋ ሲጥል አካባቢው ላይ ያጡ፣ ባል/ወላጅ የሞተባቸውን እና አረጋውያን ጋር ስጋ ይልካል። ወይ ደግሞ ይገዛላቸዋል። በዚህም ምርቃት እና በረከት ያገኛል። ለመመረቅ በጣም ነው የሚለፋው። ከከተማም በአቅም ማጣት መሄድ ያልቻሉ ሰዎችን እቃ ገዝቶ፣ ከራሱ ጋር አሳፍሮ ይዟቸው ይገባል እንጂ ብቻ መብላት ብሎ አይታሰብም።
ጉራጌ ወዳጅ፣ ጎረቤት ያላችሁ መስክሩ።
ብቻ በወዳጅ ቆስቋሽነት፥ don’t mess up with Gurage people ለማለት ያህል ነው! ሃሃሃ…