“ለ24 ሰዓታት ሴት” (ምናባዊ ልብወለድ)፣ ተማሪዎቹስ? ግን እስከመቼ? | Ethio Teyim | Episode 19

ሰው ነው የናፈቀኝ፣ ፍቅፋቂ፣ የጥሩንባ ነፊው መልእክት፣ እና የልጅነት ጊዜ ትውስታ… | Ethio Teyim | Episode 6

አንዳንዴ…

በሰላሙ ጊዜ የሆድ የሆዳችንን እንጫወት ነበር። ያኔ እኔና አንቺ አፍ አፋፍ፥ ሚስጥር የባቄላ ወፍጮ ነበረ። ሁለታችንም ጋር የሚያድር የለም፤ ጨጓራችን እስኪወቀር፣ ምላሳችን ከረጢቱ እስኪራገፍ ድረስ ተናዘን፥ በወሬ ዱቄት የታጨቀ ከረጢት ከረጢታችንን ሸክፈን እንሄድ ነበር።

ነገር ያጋጨን እለት ያቆርሽውን ሁሉ አውጥተሽ ትነቁሪኝ ጀመረ። (ማቆር መቻልሽ የልብ ልብ ሳይሰጥሽም አልቀረ።)

መጣላታችን ልብሽ ውስጥ ሲነደፍ አገር በምስጢሬ የወሬ ስንጥቁን፥ ኩታ ሸምኖ አለበሰ።

ወዳጅ ያፈራኹበትን ነጻነትና፣ ያኔ ያወራሁት ነጻ ወሬ ሰንኮፍ ሆነው ሰውነቴ ላይ ተሰኩ። ተራማጅነትንም እረፍትንም ነሱኝ። ወዳጁን እንደቀበረ ሰው ቁም ለቁም ጢሜን ነጭቼ አገጬን ተገጠብኩ።

ቆጨኝ።

ክፉኛ ቆጨኝ።

ማውራቴ ቆጨኝ።

መስማትሽ ቆጨኝ።

ማወቄ ቆጨኝ።

ምን ነበር ባላውቅሽ ኖሮ? አንቺን ከማውቅሽ ምን ነበር ሌሎች ሌሎች ሰዎችን ባውቅ?

ማመኔ ቆጨኝ።

መጣላት የለም ያስባለኝ አፍቃሪ ሞኝነቴ ቆጨኝ።

ጆሮ ስላለሽ ቆጨኝ።

አልዋሽሽም፥ አፍ ስላለኝም ቆጨኝ።

“የሽንገላ አንደበቶች ዲዳ ይሁኑ” ይላል መጽሐፍ። እኔ ደግሞ ቅልብልብ አንደበቶችም ዲዳ ይሁኑ አልኩኝ።

“ቆይ ለስንጣላ” ብለሽ የሰማሽኝ ይመስል ስንጣላ የሰማሽኝን ሁሉ ቃል በቃል ለማሳጣት ተጠቀምሽበት።

ሚስጥሬን አሸሞርሽበት። ገመናዬን ወዳጅ አፈራሽበት።

የቅርብ ነበርሽና አንቺ ብለሽ ማን ሊጠራጠር?

ባለጊዜ ገድ የሰመረለት አትራፊ ነው። ቢጨምርም ቢቀንስም ገዢ አያጣም።

የፈለግሽውን ጨመርሽ። የፈለግሽውን ቀነስሽ።

“አወራሽ። ለፈለፍሽ። ሞላ አገሩ ሰማ።

ግደይኝ አንቺ ልክ ከጠላሽኝማ” አልልሽም።

እሱ ዘፈን ነው። “እዬዬም ሲደላ ነው” ይባላል፥ እሱ ፍቅር ነው። እሱ የ”እፍታው” ውጤት ነው። የእፍታው ጊዜ እንኳንና ገድለሽ ሄደሽ “ግደይኝ”፣ ሌላ ሌላም ይባላል። “ተባብረን ካልገደልን”ም ይባላል።

“ቆዳዬ ተገፎ፣ ይሁንልሽ ጫማ፣
ስጋየም ይደገም፣ ላንቺ ከተስማማ”

ይሄን ያለው ዘፋኝ መቼም “ይቅር ይበለኝ” ብሎ ጣቱን ስንቴ ነክሷል? ፍቅር እፍታው ላይ ደስ ይላል። የጅንጀናው ሰሞን ዓለም ነው። እንደህጻን ባለ ንጽህና ቅድስናን ያስናግራል። “ይድፋሽ” እስኪመጣ ድረስ “ልደፋ፣ ልሙት” ያለ ነው። “ወይ አምላኬ” ብሎ ማማረር እስኪተካ ድረስ “I am lucky” ማለት ደንብ ነው።

የእፍታው ጊዜ፥ አመሉም፣ ቋንቋውም ጉራማይሌ ነው።

“ጉንፌን አውልቄ ለበስኩኝ ቦላሌ”

በፍቅር ስንነፋረቅ አንቺን እመስል ብዬ ልቤ ላይ ያደረግኩትን ጉንፍ አውልቄ፥ የልቤን ቦላሌ ጥለሽው ከሄድሽበት አንስቼ ለብሼዋለሁ። ውሰጅልኝ የልብሽን ጉንፍ!

ደግሞ ራቁቴን ስታስቀሪኝ የቦላሌና የጉንፍ ወግ ቀርቶ አገለድምበት የነገር ሽርጥ ፍለጋ ተፍጨረጨርኩኝ።

ቀን አስማምቶን ተዋውቀን ስንኖር የመሰለኝ፥ ውሸት መሆኑን ቀን አጋጭቶን ስንተዋወቅ ገባኝ።

በነገርሽ ላይ፥ ይህን ይህን ሁሉ ያወቅኹት ዛሬ አይደለም። ነገር ባጋጨን ቅጽበት ነው።

እናቱን ነገር!

ስጉ አደረገኝ። ቤቴ እንደተዘረፈ እንዲሰማኝ አደረገኝ። ራቁቴን አስቀረኝ። ሳይሞላ የሞላ ያስመሰለውን ጎኔን ሁሉ ገላልጦት አንዘፈዘፈኝ። ያለኝን ሁሉ ይዘሽብኝ ስትሄጂ ተሰምቶኝ “ሂጂ” ስልሽ አነባሁ። ሂጂ-አትሂጂብኝ መሳቂያ አደረገኝ።

ግን ውሸት ምን ይሰራል? “አትሂጅብኙ” እርቃኔን ለመጠበቅ ነበር። ሰው የሚስጥር ተካፋዩን ደፍሮ “ሂጂ” አይልም። ቢል ወየው ለራሱ! ሚስጥር መካፈሉ ቢቀርም ልማድ አለ። ልማድ አጉል ነው። “ለገና የገዛኸው በግ፥ ስጋ ስላለ ለጥምቀት ይሁን ብለህ ብትተወው፣ ለጥምቀት ለማረድ ያሳሳህና በግ አርቢ ሆነህ ትቀራለህ” ይላል ወንድሜ። የግጭት ማግስቱ ነጻነት የመስጠቱን ያህል፥ ከነገ ወዲያው ወፍራም ማቅ ያለብሳል።

ያኔ “ሰዶ ማሳደድ ካማረህ ዶሮህን በቆቅ ለውጥ” ነው ጨዋታው።

ይሄን ተረት የቀመረው ሰው፥ የእኔ ቢጤ ይመስለኛል። ሳይቸግረው ሰዶ ሚስጥሩን ጥበቃ ሲያሳድድ የኖረ የኔ ቢጤ።

ምን ታረጊዋለሽ?

እጣ ፈንታ ነው!

አንቺ ሳትኖሪ በፊት… ድሮ ድሮ ግን ሕይወት እንዴት ነበር? ውሎ ገባው የት የት ነበር? ላንቺ ሳልነግርሽ በፊት ሚስጥሬን የትኛው ቋቴ ውስጥ ነበር የምሸሽገው? ወይስ ካንቺ በፊት ሰማይና ምድሬ ላይ ሚስጥር አልነበረም?

ሚስጥር ማጋራትን ካንቺ መምጣት ጋር ተማርኩኝ።

ሚስጥር መጠበቅን ካንቺ መሄድ ጋር ቀሰምኩኝ።

ይብላኝ የሸራረፍኩትን ለምታገኘኝ ለባለተራዋ ውዴ! ይብላኝ በተንሸዋረረ ዐይን እያየሁ፥ በተሸራረፈ ልቤ ውሃ ለምጣጣ እኔ!

እርሳት እርሳት አሉኝ እንዴት እረሳለሁ፥
ሞኝነቴን ብንቅ፥ ወዴት እበልጣለሁ?!

ባቡር፣ መንገድና የሰው ጠባይ

IMG_5433_zps75glabjg

ተመርቆ የቆየው የባቡር መንገድ ስራ የጀመረ ጊዜ “ከተማችን ዘነጠች” ተባለ። “ዓለሟን አየች” ተባለ። በየልቡ “አሁን ደመቅሽ አዲሳባዬ” ተዘፈነላት። ሰው ደስታውን በተለያየ መንገድ ገለጸ። የትናንት መልካም ታሪኮችን ስለዛሬ መስዋዕት ያቀረቡ አሽቋላጮችም ነበሩ። አንዳንድ የአዲስ አበባ ኗሪዎች እጅጉን ተመጻደቁ። በነዋሪው ግብርና፣ ነገ ላቡን ጠብ አርጎ በሚከፍለው (አልያም ሞልቶ ከተረፈው ተፈጥሯዊ ሀብት በዓይነት በሚከፈል) ብድር መሰራቱን የማያውቁ ይመስል ብሽሽቅ ጀመሩ። የስልጣኔ አልፋ መሆኑን አወሩ። “የ24 ዓመቱ ልፋት አፈራ” አሉ።

ለባቡር መንገድ ስራ ጫካ የተገባ ይመስል “የታጋዮች ደም ፍሬ እያፈራ ነው።” ተባለ። ሬድዮና ቴሌቪዥኑ ሌላ ስራውን ትቶ፥ ከሞላ ጎደል ባቡሩን ማውራት ጀመረ። ከባቡሩ በሚተርፈው ጊዜ ባለጊዜውን “ሞላ” ያቀነቅናል። ሰልፌዎች በየሰዉ ግድግዳ ተለጣጠፉ። ወሬው ባቡርና ባቡር ብቻ ሆነ። ጋዜጠኞቹ ከምን ጊዜውም በላይ መበጥረቅ ጀመሩ። አንዱ “ይሄን ታሪካዊ ትኬት አልበም ውስጥ አስቀምጬዋለሁ” ሲል ገረመኝ። ለወሬ ሲቸኩል፥ “ትልቅ ዋጋ ያለውን አረንጓዴ ትኬት ቆርጬ ረዥሙን መንገድ ነው የሄድኩት።” አለ። (ትልቅ ዋጋ ያለው ትኬት ቀዩ ነው እንጂ አረንጓዴው አይደለም።)

ወዲህ ከፒያሳ ተነስቶ ቃሊቲ፣ ወዲያ ደግሞ ከጦር ኃይሎች ተነስቶ ሀያት የሚዘልቁ ሁለት መንገዶች ተዘረጉና ከተማችን ቄንጠኛ ሆነች ተባለ። ሰዎች ደግሞ መውረጃቸው ጋር ሲደርሱ ወደጉዳያቸው ቶሎ እንደመሄድ ወገባቸውን ይዘው እዚያው ቆመው ወሬያቸውን ሲሰልቁ ይውላሉ። የባቡሩ መንገድ ሊሰራ ሲቆፈርና በልምምድ ወቅት፣ ከብበው ይመለከቱ ከነበረው በላይ ሰዎች የባቡሩን ማለፍ ቆመው ይመለከታሉ። ያወራሉ። ምን እንደሚያወሩ ግን አይገባኝም ነበር። ፖሊሶችና ትራፊኮች የባቡር ጣቢያዎች ላይ ፈሰሱ። በቻይኖች እየተዘወረች ባቡሯ ብቅ ስትል (በየ6 ደቂቃው ነው ተብሏል) ሰዉን ያዋክቡታል። ከድንዛዜው የተነሳ ሀዲዱ ላይ ሲሰጣ፣ ተገርፎ የሚወጣም ነበር። (ሲያንሰው ነው።)

እንዳያያዛቸው፥ የባቡሩ መንገድ ስር፣ እና ጎንና ጎን፣ አንድ ቀን እሳት አንድደው፣ ጀበና ጥደው ቡና ሳይጠጡም አይቀር። ዳስ ጥለው ጠላ ሳያንዶቆድቁም አይቀር። የእድር ስብሰባዎችም እዚያ ሳይካሄዱም አይቀር። መጀመሪያ ሰሞንማ ባቡሩን ለማየት ከቤት ተቀሳቅሰው የሚወጡ ነበሩ። እንደ ቤተ አምልኮ ሊሳለሙት ይመስል ነጠላ ጎትተው ዋናው መንገድ ላይ የሚውሉ ጎልማሶች ተበራከቱ። ጎረምሶችና ኮረዶች ደግሞ መቀጣጠሪያቸውን የባቡሩ መንገድ ያለበትን አቅጣጫ ብቻ አድርገውታል።

በየስልኩ “ሃሎ! እሺ… አልቆይም ኧረ። ባቡሯን ይዤ ነው የምመጣው።”፣ “ውይ ባቡሯ አመለጠችኝ። በቃ ቀጣይዋን እይዛለሁ።”፣ “ባቡር አትይዥም? አቦሉ ላይ ድረሺበት…”፣ “ለትንሽ አረንጓዴዋ ትኬት አለቀችብኝ። በቀይዋ መጥቼ አቆራርጣለሁ። አልቆይም…” የሚሉ የስልክ ወሬዎች መሰማት ጀመሩ። “ችግር ያቅልል ተብሎ ችግር ሆነ እኮ። ታያለህ መንገዱን እንደዘጋጋው?” የሚሉ አሽከርካሪዎች በዙ። ።

የባቡሩ መጫኛና ማውረጃ ቦታዎች ሁልጊዜ ትርምስ ሆነ። መንገድ መዘጋጋት ጀመረ። በተለይ ባቡሩ ዝቅ ብሎ፣ ከመኪና ጋር እየተጠባበቀ በሚያልፍበት ቦታዎች ላይ የትራፊኩ ጭንቅንቅ በዛ። ታቦት እንደሚሸኙ ሁሉ ተሻጋሪዎች ተከትረው ቆመው ይጠብቃሉ። የመርካቶ በራፎች ትርምስ በዛባቸው። ወትሮም ግር ብለው ሲወጡና ሲገቡ ቀብር የሚሄዱ የሚመስሉት የመርካቶ ሰፈር ነዋሪዎች መውጫና መግቢያ ላይ፥ አስከሬን ቆመው የሚያሳልፉ ይመስል… አልቃሽ ያዙኝ ልቀቁኝ ብላ ስትፈጠፈጥ ቆመው እስክትነሳ ይጠብቋት ይመስል…መውጫና መግቢያው ላይ መገደብ ጀመሩ። ትራፊክና ፖሊሶች ላይም ጭንቅ ሆነ። መጀመሪያ ሰሞን፥ ሰዉ ጉዳይ ሳይኖረውም ለሙከራ ይሳፈር ነበር። “እስኪ ሽርሽር እንውጣ” ይላሉ። ለሙከራ የሚሳፈሩት ሰዎች ፊት የመገረም ፈገግታ ፊታቸውን ሞልቶት ይታያል።

ትንሽ ከርሞ ከተማዋ በዚህ ባቡር ከዘነጠች በኋላ እናቴ አንድ ሀሳብ ተከሰተላት። ካልጠፋ ነገር ባቡሩ ጣቢያ ጋር ቆሎ የማዞር ሀሳብ ተከሰተላት። መንገድ ሲሄዱ መኪና ተበላሽቶ ወርደው የሚተራመሱ ሰዎችን ሲያይ፥ “እዚህ ጋር ሻይ ቤት መክፈት ነበር” እንዳለው ስራ ፈጣሪ ጉራጌ እናቴም የስራ ሀሳብ ተከሰተላት። በቆሎ ጀምረነው፣ የሰዉን ፍላጎት እያየንና እንደ ወቅቱ ድንችና በቆሎም እንጨምራለን አለች። በፕላስቲክ የተለበጠ “ሞባይል ካርድ አለ” የሚል ወረቀት አንገቴ ላይ አንጠልጥዬ፣ ማልጄ ቆሎዬን ይዤ እንድወጣ ተፈረደብኝ።

ባቡሩ እንቅልፌን ቀማኝ። ባቡሩ ልጅነቴ ላይ ተደራደረ። እንደፈረደብኝ ባቡር ለሚጠብቁ ሰዎች ቆሎዬን መስፈር ጀመርኩ። እንደ ስራ ሳይሆን እንደቅጣት ስለምቆጥረው በደስታ አድርጌው አላውቅም። ባቡሯ እንዳታመልጣቸው ሲዋከቡ መልስ ጥለው የሚሄዱ ሰዎች ሲያጋጥሙኝ ደስ ይለኝ ጀመር። እንደዛ ሲሆን “ስትመጣ ትከፍላለህ… ቅመሳት” እያልኩ መቀናጣትና ገበያተኛ ማማለል ይቃጣኛል።

አንዳንዴ ደግሞ የፋጤ እድል ይገጥመኛል። ማንጎ ሸጣለት “ሽልንጌን” እያለች የጮኸችው የሀረሯ ፋጡማ ትዝ ትለኛለች። አንዳንዱ ቆሎዬን ሰፍሬለት ሳይከፍለኝ ባቡሯ ውስጥ ይገባል። እንዲህ ሆነ ስራዬ። ባቡሯ በመጣች ቅጽበት እንደ ሀይለኛ ዝናብ ሿ ይልና፣ ወዲያው ቀጥ ብሎ ያባራል። ሰፌዴን ይዤ እንደነገሩ ትከሻዬ ላይ ጣል አድርጌው እወጣና ባቡር መንገዱ አካባቢ በፀጥታ ገዢ እቃርማለሁ። ባይኖቼ እለማመጣለሁ።

ባቡር ጠባቂው “መጣች መጣች” ይባላልና አንገት ሁሉ ሰግጎ ባይኑ አቀባበል ያደርግላታል። እሪ ይባላል፣ ይጮሃል፣ ይገፋፋል። ጨዋ የሚመስሉ ሴቶች እንኳን ቀሚሳቸውን ሰብስበው ይሯሯጣሉ። ቆሎዬን ሽጬ እቤት ከተመለስኩ በኋላ ሌላ ቆሎ ከሌለ፣ የሞባይል ካርዶቼን ይዤ ሰፌዱን አስቀምጬ እወጣለሁ። ከዚያ ለተባራሪ ፈላጊ ሞባይል ካርድ እየሸጡ ወሬ መስማት ነው።

ባቡሩ መጀመሩ አንድ ትልቅ የወሬ ለውጥ አመጣ። ሕዝቡ ለታክሲ መጋፋቱን በባቡር መጋፋት ተካው። የሚሄድበት መንገድ አጭር የታክሲ ወይም የእግር መንገድ ቢሆን እንኳን፥ እንደምንም ብሎ ባቡሩ በሚሄድበት አቅጣጫ ሄዶ፣ በታክሲ ማቆራረጥ ጀመረ። ባቡሯን ለመጠቀም ቀደም ብሎ እየወጣ ራሱ ላይ መከራ ከመረ። ወሬው በየቦታው በየቤቱ በየቅያሱ ስለባቡርና በባቡር ስለመሄድ ሆነ። ቃሊቲና ቂሊንጦ ያሉ እስረኞችን የሚጠይቅና መንጃ ፍቃድ የሚያወጣው ሰው በዛ። ባቡሯን ቃሊቲ ድረስ ለመጠቀም ብሎ ወጥቶ ደብረ ዘይት ሄዶ የሚዝናናውም ሰው ጨመረ።

“ፍጥነቱ ደስ ሲል። ደግሞ የሚሄድም አይመስልም… ”

“መንገጫገጭ የለ… ታክሲው እኮ ሲንጠን እንዴት ገድሎን ነበር?”

“አንቺ ባቡሩን ሞከርሽው? ወደ ሀያት ስትሄጂበት ደግሞ ከቃሊቲው ይለያል።” ትንታኔዎች ተደሰኮሩ።

“ትላንት ለቅሶ ሄጄ… እንዴት ፈጥኜ መጣሁ መሰለሽ።” (ሰው ሲሞቱና ትልልቅ ጉዳዮቹ እንዳያልፉት ባቡሩ መንገድ ተከትሎ ያሉ ዘመዶቹ ጋር ዝምድናውን አጠበቀ።)

“ደግሞ ከታክሲው ሲናጸር ዋጋው መርከሱ… ታክሲዎቹማ ሲበዘብዙን ኖሩ እኮ።”

“ኧረ የረዳቶቹን ስድብ መጠጣቱና የጣሉትን ቂጥ ማየት መቅረቱስ”

“’ድመት መንኩሳ ዐመሏን አትረሳ’ …አሁን ምንድን ነው መስገብገብ። ሆዱ እኮ ሰፊ ነው። ሁላችንንም ይችለናል። ኧረ ተዉ ቻይኖቹም ይታዘቡናል…”

“ኧረ ደቂቃው እንዳይሞላብሽ ፍጠኚና ውጪ”

“ለትንሽ ጥሎኝ ሊፈረጥጥ። ሀዲዱ ላይ መዳመጤ ነበር…ብቻ ብረቱን ይዤ ተረፍኩ።”

“ባቡር ላይ እያስቸገረኝ ነበር። ስልኬን ወስዶ…”

“እንዴ ባለቤቴ እኮ ባቡሯ እንዳታልፈው ስለሚጣደፍ ማምሸቱም ቆሟል። ይኸው በጊዜ፣ መጥቶ ስንላፋ ነው የምናመሸው ስልሽ…”

ጨዋታው ባቡርና ባቡር መንገድ ሆነ።

ባቡር ባቡር የሚሉ ዘፈኖች፣ የድሮ የዘፈን ክሮች እየተራገፉ ወጡ። አዳዲስ ግጥምና ዜማዎችም ተቀመሩ። ችኮላው አላደርስ ያላቸው የቀድሞ ዘፈኖችን ግጥሞች አድሰው ሬድዮዎቹን አጨናነቁ።

ባለጋሪው ባለጋሪው፣
ቶሎ ቶሎ ንዳው…

የሚለው ዘፈን ግጥም ተቀይሮ…

ባለባቡሩ ባለባቡሩ፣
ሸገር ሆኗል ሀገሩ!

ተሳፋሪ ሁሉ ባለ ጉዳይ ነው
ታክሲና አቶቢሱን አሻግሮ ሚያየው
የሞላ የሞላ ባለና በፊቴ
ባሳፈረኝና እፎይ ባለ ስሜቴ፤
እፎይ ባለ ስሜቴ፤

ተብሎ በየኤፍ ኤሙ ተሰማ።

በባቡር በፍቅር መንገድ ላይ በባቡር
በባቡር በመውደድ መንገድ ላይ በባቡር
መጓዝስ ካልቀረ ካንቺ ጋር ነበር

የሚለው ሙዚቃ እንዳንዲስ መጠባበሻ ሆነ።

በባቡሩ መንገድ የቆምኩት አሁን
ስንቱን አሳልፌ ልዘልቀው ይሆን?

የሚለው የሜሪ አርምዴ ዘፈን ከነክራሩ ከተሰቀለበት ወረደ።

በየታክሲው ጭቅጭቁ፣ ማስፈራራቱና ዛቻው በዛ።

“ኤጭ አትጨማለቅ እንግዲህ! ባቡር እኮ…” እያሉ የሚያስፈራሩ፣ “’እጸድቅ ብዬ ባዝላት…’ አንተ በባቡር መሄድ አቅቶኝ አይደለም።” እያሉ የሚመጻደቁ፣ “እንደውም ተወው ባቡሯ ብቅ አለች” ብለው የሚያኮርፉ ተሳፋሪዎች በረከቱ።

“ታክሲ ጥንቡን ጣለ” ተባለ።

ስጋቶችም አልጠፉም።

“መብራት ቢጠፋስ?”፣ “ደግሞ ሲዘንብ ቢነዝረኝስ?”፣ “ይሄ ደንባዛ ቻይና ቢያስነጥሰውና ዐይኑ ጭራሽ ድርግም ቢልስ?” የሚሉና ሌሎች የፍርሃት ወሬዎች በሹክሹክታና በየሰዉ ልብ ውስጥ ይብላሉ ጀመረ።

“ባቡር ጣቢያው ጋር ጠብቂኝ” “ምስጢራዊ የባቡር ጉዞዎች” “መሀልየ መሀልይ ዘባቡር” “የባቡሩ ጉዶች” “ባቡር ላይ ያየሁት ወንድ የወሰደው ልቤ” “ባቡር ተሳፍሬ” “የዘገየው ባቡር” “ከባቡር አደጋ ለመትረፍ የሚያስችሉ 8 ነጥቦች” “ባቡርን ወደ ቢዝነስ የመቀየር ጥበብ” “የባቡር ኬሚስትሪ” “ባቡሩ” “ከባቡር የወጣች ነፍስ” “ባቡር መንገዱ ዙሪያ ያሉ የወሲብ ሕይወቶች”…የሚሉ የተለያዩ ከተፋ መፅሐፍትና ፊልሞች በዙ። ሙዚቃዎችም ባይነት ባይነቱ ሆኑ። ገጣሚያንም ወገባቸውን ቋጥረው ስለባቡር ተቀኙ። ናፍቆትና ጥበቃ በባቡር ተሰማመሩ።

“የከሸፈው የአሸባሪዎች ሴራ በባቡሩ መንገድ ላይ”፣ “እንደ ባቡራችን ፈጣኑ ኢኮኖሚያችን”፣ “ባቡር ላይ በሻዕቢያ ተላላኪ ፀረ ሰላም ኃይሎች የተቀነባበረው ፍንዳታ ምስጢር ተጋለጠ”፣ “አቶ አንዳርጋቸው እንደ ኤክስፕረስ መንገዱ የባቡሩንም ጎበኙት። ይህኛው የባቡር ጉዞዬ ከእስከዛሬው ሁሉ ለየት ያለ ነው አሉ።” እና የመሳሰሉ ዶክመንተሪዎችና የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ርዕሶች በብዛት መታየት ጀመሩ።

እኔ ግን ኑሮ ባቡር ላይ ተጭኜ ቆሎ እሰፍራለሁ እንጂ እስከዛሬ ባቡር ተሳፍሬ አላውቅም። ባቡሩ ሆዴን እያሰብኩ ባቡር ተሳፋሪን አሳድዳለሁ። በቆሎና ስለቆሎ ያየሁት ጉድ ይበዛል። ሳድግ ግን “ባቡር መንገድ ላይ ያሳለፍኩት ልጅነቴና ትዝብቶቼ” ወይም “ባቡር መንገድና የሰው ልጅ ጠባይ” ወይም “ባቡርና ሕይወት” ወይም “ባቡር ጣቢያ ላይ የተረሳው የትንሹ ልጅ ሕይወት” የሚል መጽሐፍ ብጽፍ ደስ ይለኝ ነበር። ትምህርት ቤት አልሄድኩም እንጂ መጻፍ ብለምድና መጽሐፍ ብጽፍ ደስ ይለኝ ነበር።

‘ግን ሰው ከባቡር መሳፈርና ስለባቡር ማውራት ምን ጊዜ ተርፎት ያነብልኛል?’ ስል አስባለሁ።

ማስታወሻ
ይህንን የጻፍኩት የአዳም ረታ “ግራጫ ቃጭሎች” ላይ ገጽ፥ 127-128 ባለው “ቧንቧ፣ ልብስና የሰው ጠባይ” በሚል ንዑስ ርዕስ በተጻፈው ታሪክ መቆስቆስና ቅርጽ ነው። አንዳንድ አረፍተ ነገሮችንም በቀጥታ ከግራጫ ቃጭሎች ላይ ገልብጫለሁ።

አንድ አፍታ፡ – ነገረ ቆሎ. . .

ህይወት ቆሎ ናት… ስንዴ ቆሎ ¬ ገብስ ቆሎ -¬ በሽንብራ የተደባለቀች ቆሎ -¬… ጎኗ ሱፍ ቁጭ ቁጭ ብሎ የሚያጅባት ቆሎ…. ሱፍ ለብሰው የሚከኳት ቆሎ… ¬ ሰነፍ ቆሎ፣ ጎበዝ ቆሎ… ¬_ ‘ፓ ቆሎ!’ እያሉ…. እየሰፈሩ የሚቸረችሯት…. የሚቆረጥሟት! የሚቀጯት! እየቆነጠሩ የሚቀጨቅጯት —

— ቀጭ ቀምቧ…. ቀምቧ ቀጭ…. ቀጭ ቀምቧ….

…..ቆሎ በአፉ ሞልቶ ቆንጆ ሴት ማለም – ለፈለገ – ቀላል ነው። ወይ ማስቲካዋን፣ ወይ ሂል ጫማዋን አርጋ…. በሊሾው ወለል ላይ፥ ቀጭ ቀንቧ ስትል በሀሳቡ እየሳለ – – – ሂል ቶፕስ – ዳሌዋን ማለም ይችላል። ¬ ‘የ – ኔ – ቆ – ን – ጆ– ’! ግን ከቻለበት ነው።…. ከፈለገ።…. ታዲያ እንዲያም ቢሆን ህልም አይታለፍም፤ የማይጨበጥ የማይዳሰስ ህልም…. – ህልም እልም!

ህይወትም እንዲህ ናት! እየቆረጠሟት የፈለጉትን ዓይነት ህልም መከለም ነው። ያው የስሜት ጉዳይ ነው! የፍላጎት ዓይነት።…. ጉልት እየተቸረቸሩ ቤተመንግስት ንጉስ ፊት የሚቀርቡ ቆሎ እንደሆኑ መመኘት…. ፆም የማደርን ያህል ቀላል ነው፤…..ዓለም ላይ ቁጭ ብለው፥ለመጠጥ ቤት እየተቸበቸቡ፥…. ከዳቤ ጋር የሚቀርብ የገዳም ቆሎነትን መመኘት ይቻላል፤… የለቅሶ ቤት ቆሎ ሳሉም የሰርግ ቤት ኮክቴል አጃቢነትን መቋመጥ መብት ነው። ግን ማሰብ ብቻ!

ኳስ ሜዳ ዙሪያ ቢቸበቸቡስ ቀላል ነው እንዴ? …. “እስኪ ከሽንብራው! ….ከሱፉ ጨምሪ እንጂ። …..ኤዲያ አንቺ ልጅ እጅሽ አ ይደለም የቆላው።…. ይሄማ ቤት አልተቆላም! የገበያ ነው።…” ቢባልለት!….. የገበያው ዱር ይቆላ ይመስል። የገበያ ሲሆን እግር ይቆላው ይመስል። ….ዝም ብለው ሲቀናጡ! አቅም ማሳየት! — የመግዛት አቅም። የመክፈል አቅም። — ገንዘብ የመክፈል?! ሁለት ቦታ የመክፈል?! ….የማዘዝ አባዜ። የመተቸት ፍቅር። የእልቅና ታናሹ….

እንዲህ ሲሆን ግን ህይወት ቆሎዋም ደስ ይላታል። ሰርክ በመታመስ ላይ እንዳለ አካሏን ታገላብጣለች። ዳሌዋን ሸሽጋ ሽንጧን ታተራምሳለች።…..የህይወት ሂልቶፕስ የት እንደሆነ ችለው ሲወጡ ብቻ ነው የሚታየው።…. ባላዩዋት ቁጥር ደግሞ ስታሳሳ! ሂልቶፕሷን እያቁለጨለጨች ኗሪዋን ማሴሰን ነው። እየተማረሩባት ብዙ የምታስመኝ። አልቆረጠም ብላ ጥርስ እየፈተነች ብዙ የምትፈለግ። ጥርስ ገብታ እያመመች የምትናፈቅ። ለዝዛም፣ ፈዝዛም፣ አደንዝዛም፣ አስተክዛም….

“ሂልቶፕሴን ያያችሁ?
– አላየንም….
ኗሪዎች እባካችሁ…”

ህይወት ቆሎ…. እንደ ዱቤ ቆሎ…. በዱቤ የሚኖሯት…. በዱቤ ገዝተው በዱቤ የሚበሏት…. የተኮናተሯት ዓይነት! በብዙ ጨው ተለውሳ ውሀ የምታስጠማ። ከዚያ ብዙ የምታስጠጣ። መጠጥ የምታሻሽጥ። የምታሳክር። ….ህይወት ቆሎ። ጨው የበዛባት ቆሎ።…..“ማን ነሽ… ትንሽ አፌ ላይ አንቀዋልዬው የምመልስልሽ ቆሎ ካለሽ አውሺኝ። እንግዳ መጣብን የእኛው ቆሎ እስኪቆላ ድረስ….” የሚባልላት።

“ምነው እቴ? አይሟሟ!….ምነው ሰሰተች?…. ይዋጥባት ይመስል።…..” ተብሎ የሚገበዙባት….. እርሷን እየቆረጠሙ፣ “ባዶ ቤት በክረምት”ን የሚያንጎራጉሩባት። እየፈጯት በትዝታ ነጉደው መንገዱን የሚፈጩባት። ይገርማል! ….ከቆሎ ጋር ሆነው “ባዶ ቤት” ይባልባታል።….. ቆሎ ይዘው ቆሎ መመኘት ቅንጦት ነው። ሙቅ እንደማላመጥ ያለ ቅንጦት፤…አሻሮ ይዞ ከቆሎ መጠጋት ግን ከዚያም ይብሳል። — ሰገብጋባ ቅንጦት!

…. ያሻው ደግሞ ኑሮውን ሊደጉምባት በእንቅብ ሞልቶ የሚቸረችራት ቆሎ። -ህይወት፤

ስንዴ ቆሎ፣….
አጃ ቆሎ፣….. ቆሎ ቆሎ
ያቺን ትተህ ይችን ቶሎ!

ተብሎ በልጅ ኩልትፍትፍ አንደበት የሚዜምላት!

ጎረምሳ በእንካ ሰላምታ የሚረታባት! ረትቶ “እንካ ቆሎ” የሚባልበት….የሚሸለምበት… – የቆሎ ሽልማት! ደስ ሲል!!

“እንካ ሰላምታ
– በምንታ
በቆሎ…
– ምናለ በቆሎ?
ነይ ልቃምሽ ቶሎ”

…. እርሱ ጠይቆ፣ ልቃምሽ ብሏት ማን ቆሎ ችላ ልትቀር? ትሸለመዋለች! በሽልማት መልክ ላላማጯ ትበረከታለች!!

…. ጠጅ ቤት፣ መንገድ ዳር፣ መጠጥ ቤት፣….የምትንከራተት። — ቆርጣሚ ፍለጋ። ገዢ ፍለጋ። አሳዳሪ ፍለጋ። – አሳዳሪ ሆድ። ቆርጣሚ ጥርስ።…….. ቆርጣሚዎቿም ይፈልጓታል። ያለችበት መጥተው ይገዟታል። ዓይናቸውን እያንቀዋለሉ…. እያንከባለሉ…. እርሷን ቆርጥመው “ጠማኝ” ሊሉ። ሰበበኞች…. ጠማኝ ብለው ጋኑን ሊገለብጡ። ሲጠጡ ደግሞ ይናፍቋታል። ታጫውታለች። ታስቆዝማለች። እያሉ……..ከዚያም ፍለጋ መውጣት….

ዓይኗ ቆሎ፣ ጥርሷ ቆሎ፣ የወለዱ እንደሆን፣
ታመጣለች አማች ብረት መዝጊያ የሚሆን…

ይሉላታል በዜማ! ለእነሱ ኤልያስ ተባባል ኮልታፋ ነው። ኮልታፋ ስለሆነ… “ቆሎ” ለማለት ነው “ኮሎ” ያለው። በቃ — ካሉ አሉ ነው። – ህይወት ገብሷ አስክራቸዋለቻ!

ህይወት ቆሎዋ ጢንቢራቸውን ታዞረዋለች!….ታባክናቸዋለች። ሲሻት ደግሞ ትቆላቸዋለች። እንደራሷ አድርጋ እርር…. እርሷን እንደቆላት ቁልት ታደርጋቸዋለች። በምድር ምጣድነት በኑሮ መቁያነት ታምሳቸዋለች። ታገላብጣቸዋለች። ቢያርሩም ለአመል ነው። በዪ አያጡም። ጨው ስታበዛባቸው ደግሞ ተከታይ ውሀ ይቀዳላቸዋል።… የማታ ማታ ግን የአፈር ሲሳይ ናቸው።…. እሳት እራት ወደ እሳት፣ የተቆሉት ወደ አፈር፣ ያልተቆሉት ወደ እሳት….

….ግብአተ መሬት….

ወይኔ ቆሎ…. ቆሎ ቆሎ.
አልሰማሁም ነበር አልሰማሁም ነበር፤
ለእኔ ያርገው ቆልዬ ለእኔ ያርገው።
ይሄ ጅብ መሬት ሊቆረጥምሽ….

.
.
“እምቢ…. እምቢ ለቆሎ…. እምቢ ለጥርሴ ጌታ….በወንፊት ሞልታ፣ በሰፌድ መጥታ፣….. አጫውታ አማሽታ….. እምቢ ቆሎ! ተይ አታድርጊኝ ከርታታ….”

ዥዋ – ዥዌ —
— ከሙሾ ወደ ቀረርቶ…. በቃ ህይወት ስትቆላ እንዲህ ነው!

እስከዚያው ድረስ፣ ግብአተመሬቷ እስኪፈፀም ግን ትሰፈራለች። ትኩስ ትኩሱን ያዞሯታል። በእንቅብ ሞልተው ይሰፍሯታል። ልጅ ያለው ልጁን አስይዞ…. የሌለው ራሱ ይዟት…. ይሰፍራታል። በየጠጅ ቤቱ። በየቡና ቤቱ…. ጉልበተኛ መጥቶ እስኪበትናት። የጠገበ መጥቶ እንቅቧን አንገጫግጮ እስከሚደፋት።…. ሰካራም በጥፊ እስኪወለውላት።

… ከተደፋች እንቅቡ ይቀራል። እንቅብ ካለ ቆሎ፣ ቆሎ ካለ እንቅብ ምንም ናቸው። እንቅብና ቆሎ ከሌሏት አዟሪዋስ ምን ትሰራለች? እነሱ ኖረው እርሷ ባትኖርስ?…. ከተደፋች መስፈሪያውም ተሽቀንጥሮ የጎማ ሲሳይ! ኦ መሰፈር ከንቱ። ኦ መስፈር ብላሽ።…. ሰዎች እንደመልቀም ሆነው፣ ከንፈር እየመጠጡ ክንብል ክንብል፣ ድፍት፣ ክብልል፣ ክብብ… ከዚያ ያሟታል። ፊት ለፊቷ።… ‘ኧረ ባክሽ ይሄን ልትሸጭው?!’ ብሩን እንደሚሰጥ እየተግደረደሩ…
.
.
.
ውይ ያቿት…. መጣች እንቅቡን ይዛ! ማነሽ ባለቆሎ…?! ውይ እብድ መጣላት! ስትዞርም እንቅቧን በካልቾ ሲልባትም እኩል ሆነ። ውይይ…

ዝ – ር – ግ – ፍ—-
—-እ – ር – ፍ!

ከመታፈሪያ፣ ከመሰፈሪያ እንቅቡ ወጥቶ እንግዳ አስፓልት ላይ….

ብ ¬
ት ¬ ን –
ት ¬ ን ¬ ት ¬ ን…
– ት ¬ ን ¬ ት ¬ ን -!

¬ – , ..
¬ _ – – =
ብ ¬ት ት ¬ ን ¬ ት ¬ ን — ሜዳ ላይ!!

ህይወት ቆሎ ¬__
¬ – , ..
¬ _ –
¬ _ – – =

/ዮሐንስ ሞላ/

አንድ አፍታ 2

ዙረታም ነች! — የለየላት…!! ኡመቴ ዙረታም!
[‘ኡመቴ ምንድን ነው?’ አሃ… በቃ የድሮ የመንደራችን ቃል ነበር። እንደ’ሷ ያለ የሚጠራበት ቃል።]
ሰው ኡምት ሲል፣ መላ ቅጡን ሲያጥ ‘ኡመቴ ነው’ ይባላል።…እናም ‘ኡመቴ ናት!’…
አገር ምድሩን ስትዞር ነው የምትውለው…
ልክ መሬት እንደምትዞር፣ አታርፍም!

ዝም ብላ ስትዞር… ዝም ብላ!
…… እያወራች ስትዞር… — ሰሚ ፍለጋ!
…… እያላወራች ስትዞር….– ወሬ ፍለጋ!
…… እየበላች ስትዞር… — ‘እንብላ’ ምትለው ፍለጋ!
…… እየራባት ስትዞር….– ምግብ ፍለጋ!
…… ሲበሉ ስታይ ስትዞር…–ቅልውጥና!

ስታሳዝን!

ደግነቱ እንደ’ሷ መዞር አይደለም፤….ከተማው አዙሪት የለውም።
— ሲራዳት! ሲረዳት! ሲያረዳት! ሲያርዳት! ለርሷ ቤቷ መመለስ መርዶዋ ነው…
… ዞራ ቤቷ ትመለሳለች። ሲቀናት! ሲያቃናት! አሃ… ማለት የሚያቃናት ስታገኝ! የሚያቀናናት! — ከኑሮዋ! ከራሷ! ከጎረቤቷ!…
ግን ሁሉም ነው የሚቀናባት…

ታድላ!

ሴቶቹ — ‘የባቷ ውበት ከመዞር የመጣ ነው።’ ብለው ይቀናሉ።
— ቀንተውም ይዞራሉ። – ተደብቀው! እንደሷ ለመሆን! አልሆነላቸውም እንጂ ቢሆን በባታቸው መታወቁ ላይቀር….
ወንዶቹ — በርሷ አይደለም! ስትዞር በሚለክፏት ወንዶች ይቀናሉ።
— ቀንተውም አይቀሩ! ያለፈች ያገደመችውን ይላከፋሉ! እንደውሻ… ያንንም… ይሄንንም… — ልክፍ፣ ልክፍ! ቀን ጥሏቸው ‘ክፍ’ እስኪባሉ ድረስ መላከፍ…
ፀጉራቸውን ለውጣው፣ እንደ ጭን ገረድ አብረዋት ቢዞሩ ደስ ባላቸው….
ግን ኦሆ…
— ማን ያስጠጋል? ማን ይጠጋል?

ሰዉን እንጀራ ነው የሚያዞረው። አመል አይደለም። የርሷንም ‘አመል ነው’ ይሉታል እንጂ አይደለም። — ታውቃለች! ይገምታሉ! – እንጀራ ነው….
— አዳሜን እንጀራ በቆመበት ጭውውውው…. አርጎ ይመልሰዋል።
— ሄዋኔንም! እንጀራ ያዞራታል… እንጀራ ያዞራቸዋል…
ታዲያ ለምን ይቀኑባታል?
ሴት ስለሆነች? ወንድ ስለሆኑ? እና ምን ይጠበስ?
ሁሉም ዘዋሪ ነው። ሂያጅ።
— ‘ ♫ አዙረኝ አታዙረኝ’ እያለ ሲዞር የሚውል።
ሲንቀዠቀዠ…. ሲቅበዘበዝ….የሚውል! — እንደ ባጃጅ!

ያው ባጃጅ ነው!
… ባዶውን ወጥቶ፣ ሰው ጭኖ ይመለሳል።
… ሰው ጭኖ ወጥቶ፣ ባዶውን ይመለሳል።
እሷም!
ዙረት…
ባጃጅ ግን ሰው ከመጫን ከማራገፍ ሌላም ጥቅም አለው። ሲዟዟር ለድድ አስጪዎች ገቢ ያመጣል። የገቢ ምንጫቸው ነው። በቃ እንትን ይጫወታሉ! — ሞላ… ጎደለ…
ቁማር!

እርሷም ትጫወታለች! የርሷ ቁማር ግን ከመንገዱ ጋር ነው… ከቀናት ደግሞ ካሳራፊዋ ጋር፤ ካሳፋሪዋ (ላልቶ)፤ ካሳፋሪዋ (ጠብቆ)… ዞራ ዞራ ሲደክማት! ዞራ ዞራ ስታገኘው!…
እስከዚያው ግን፥ ዝም ብሎ መዞር፣
መዟዟር፥
የሰው ናላ ማዞር፣
‘♫ mአዙረኝ አታዙረኝ….
… አሽከርክረህ፣ ከሱ ጣለኝ! ♬’
የዙረት ዜማ…!
ማይክ ይዞ ማዜም!
ካለማይቅ ማዜም!

ዜማ!

ዜማ… ዝሙት… ዘማዊ… ዘመናዊ…
… ‘♫ አዙረኝ አታዙረኝ….
… አሽከርክረህ፣ ከሱ ጣለኝ! ♬’
ግን እሱ ማን ነው?….አሃ! ማንም ነው። ማንም!
ለርሷ ሰው እኩል ነው። ዟሪ ማሳረፍ የሚችል መደብ ካለው ሰው እኩል ነው። ማለት ሲደክማት ደረቱን ተደግፋ ካረፈችበት ወንድ እኩል ነው።
እስክታርፍ ድረስ ካሳረፋት! አስክትደርስ ድረስ ካሳፈራት!

እኩልነት!

እርሷና እርሱ ግን ይበላለጣሉ….
— በመዞር ትበልጠዋለች!
— በማሳረፍ ይበልጣታል!
— በማሳፈር ትበልጠዋለች!
—- በመሳፈር ይበልጣታል!

አይ አይ… ያው ናቸው። — አይበላለጡም! — እኩል ናቸው!
— መዞሯን ፈልጋው ነው!
— መፈለጓ ቢፈልገው ነው!
— ማሳረፉ ብታርፍለት ነው!
— ማረፏ ቢያሳርፋት ነው!
— መሰፋፈራቸውም ቢሰፋፈሩ ነው!

እና?!

የመጀመሪያ ልጇን ስትዞር አርግዛው፣ ስትዞር ነበር የወለደችው…
…ከዚያ ግን ስትዞር ሞተባት። ‘ኧረ ሞት ያንሰዋል እሷ እየዞረች ማን ያጥባው?’ – ብለው ያሟት ነበር። – በሰፈሯ፤
ግን አይደለም!
የመጀመሪያ ልጇን ስትዞር አስረግዟት፣ ሲያዟዙር ነበር ያስወለዳት….
… ከዚያ ገደለባት። ‘እሱ እያዞረ ጡቷን እየተሻማት ልጁን ማን ያጥባው?’ – ብለው ያሙት ነበር። – በሰፈሩ፤

ሀሜተኞች!

ግን አሁንም እየዞረች ነው። ደግሞ ነፍሰ ጡር ነች።
እየዞረች አርግዛለች…
እየዞሩ…
ግን ንጉስ ይሁን ቄስ ማን ያውቃል? – ያቺ የቁርጥ ቀን መጥታ ትለይላታለች እንጂ። እስከዚያው ግን ትዞራለች… ይዞራሉ… — ‘አዙረኝ፣ አታዙረኝ’
— ሰው ስትጭን፣ ሰው ስታራግፍ!
— ወላጅ ስታድን፣ አዋላጅ ስታስስ!
— ሰው ሲጫናት፣ ሰው ሲራገፋት!
— ወላጅ ስታገኝ፣ ወላጅ ስትሸኝ!
— ስታሳፍር፣ ስታፍር!

ለምዳዋለች!

ጭው ብሎባት…. ጭው የምታደርግበትን ትፈልጋለች….
እጅና እጅ ተቆላልፈው….
‘♫ ♬አዙረኝ አታዙረኝ፣
አሽከርክረህ ከዚያ ጣለኝ!♫ ’
ከመደቡ… ከማስወለጃው… ከመውለጃው…. አሃ! እርጉዝ ናት! – ሁለት ነፍስ!

— ማርያም ትቅረባት! እስከዚያው ግን…

♫ ♬አያዙራት አያዙራት፣
ከመደቡ ያሳርፋት! ♫ ♬

/ዮሐንስ ሞላ/

አንድ አፍታ 1

አያት…. አየችው….
አሳቀው… አሳቃት….ተሳሳቁ…. ተሳቀቁ….
አለ አይደል? — እንዲሁ ማስፈገግ! ፈገገገገግ…
ተፋገጉ!
ፈገገላት…. ፈገገችለት….
ፍግግግግ…
!!
አሃ!
ተፈላለጉ! ዐይን ላይን… ትይትይት….
ፈለጋት….. ፈለገችው….
ፍልግልግ…..
ውይ ፍጥነቷ! – እጇ ላይ የወጣውን ፈለግ ከምኔው አሳየችው….
እህ፥ ወይስ አየባት? አዎ አየባት!
!!
አይቶም አላበቃ ድፍት ብሎ ፈለገገላት!
ያው በጥርሱ ፍልግግግ አረገላት…
በስታይል እየሳማት!
ሳያስቀይስ፣ እንደፈለግ ነቃይ…
ሳያስጠጣ…
ሳያስጠጣ ከእጇ ላብ ጥጥት! — ጥሙን ቁርጥ! — እርክት!
እርክትክት!
እርሷም ኩርት! እርክት!… አልደበራትም!
አስፈለገገችው!
!!
ታክሲ ውስጥ ነበሩ!
እርሱ ሲወርድ፣ እርሷም ወረደች!
ማለት ተያይዘው ወረዱ….
ውርድ፣
ርድ…
ርድርድ…
ውርድርድ….
ውርድርድርድርድ…
ድርድርድርድርድር….
ሸኟቸው! በዜማ ሸኛቸው…
“ሲሄዱም አንድላይ፣ ሲለያዩ እንዳናይ!”
!!
ደግነቱ አስወረዳቸው እንጂ፥ ማንም አልተወራረደም ነበር፤
እንጂማ ውርዱ ከራስ ነበር።
ያው መዋረድ አይቀር!….
…..ማለት “አብረው አይወርዱም” ብሎ የተሟገተ ቢኖር ይዋረዳት ነበር።
አቦ የምን ማካበድ ነው? ተዋረደም፣ ብሩን ተበላም፣ ያው ናቸው!!
!!
ከዚያ በኋላ…
እህ…. ሲሄዱ ሲሄዱ…
ከዚያ በኋላ….
በቃ አለ አይደል? ከዚያ….
አሃ! ይሸምማል እኮ፤
ከዚያ በኋላ እነሱም አያውቁትም…
!!
መኝታውን እርብሽ!
ራሱም እርብሽ!
እርብሽብሽ!
ብሽ…
ብሽ ብሽ…
እርብሽብሽብሽብሽብሽ….
የሰው መኝታ ረበሹ!
ተራበሹ!
!!
ባለቤቱ የባለሆቴሉ ነው፤
አቦ ባለቤት ምን ይሰራል?
ከፍለው የለ?!….
በቃ ዝም ብሎ መረበሽ፣ መፈረሽ፣ መረበሽ፣ እንደገና መፈረሽ
ፍርሽርሽርሽርሽ…
ርብሽብሽብሽብሽ…
!!
እስከዚያው፥
ጨዋታው ፉርሽ እስኪሆን ድረስ…
ፉርሽ!
ፉርሽርሽ!…
ፊሽካው ተነፋ!
ጨዋታው ፈረሰ…
ዳቦው ተቆረሰ…
ቁርስርስርስ…
ጲርርርር..!
!
!
ውይ…ሆነ!
ፉርሽ ሆነ…
ፉርሽ!
አሃ! አልተጣሉም።
ግን አለ አይደል? እርሷ ቤት ይመሽባታል! ከመሸ ደግሞ ይቆጧታል፤
‘ከነገሩ ፆም እደሩ’ ነው… ‘ደህና እደሩ!’ ብላ ሄደች።
ተጣድፋ ሄደች…
ሂድት ሂድት ሂድት…
ቋ ቋ ቋ….
ቂሊው ቂሊው ቂሊው….
(እሱ ቤት ስለማይቆጡት ቆይቶ ነበር፣ ወንድ አይደል? ወንደላጤ! ተቆጪ የለበትም…)

ወዲያው ትዝ አለው!
እርሷም ትዝ አላት!
ማለት ስቅ አለው…
ስቅ ሲለው– ‘ትዝ ብያት ነው’ አለ!
አወቀባት!
ከመቅፅበት አወቀባት!!
ከመቅፅበትም ልጅነቱ ትዝ አለው…ልጅነታቸው…
— ማለት የልጅነቱ መዝሙር፥

♫ ♬ ♫ ♬

አሰበ! ተፅናና! እንዲሁ መፅናናት! አለ አይደል?!
— ‘እርሷም እየዘመረችው ነው’ ብሎ ማሰብ ከዚያ መፅናናት።
ጲርርር… ፊሽካውን ነፋው!
መዝሙሩን ጀመረ!!

♫ ♬
“አንቺ ልጅ አንቺ ልጅ
ስምሽን ንገሪኝ፣…
በዚያ በተራራ፣ ተክያለሁ ሙዝ♫
የሚበላ ሳይሆን የሚወዛወዝ፣
አረንጓዴ ለብሶ ይደንሳል አሳ
ምነው ተለያየን ፎቶ ሳንነሳ?!♫”
የርሷንም ገመተ – እየዘመረ!
♫ ♬

ልክ ነበር!
እንደውም ስሙን ልትጠይቀው፣ ‘ፎቶ እንነሳ’ ልትለው ከጅላ ልትመለስ ነበር፥
— ግን ቤት እንዳይቆጧት ትታው ነው።
ብቻ ግን እየዘመረች ሄደች…

♫ ♬ ♫ ♬
“አንተ ልጅ አንተ ልጅ
ስምህን ንገረኝ ♫ ♬
በዚያ በተራራ ተክያለሁ ሙዝ
የሚበላ ሳይሆን የሚወዛወዝ፣
አረንጓዴ ለብሶ ይደንሳል ዓሳ፣
ምነው ተለያየን ፎቶ ሳንነሳ?!♫
♫ ♬ ♫ ♬ ♫ ♬

አረንጓዴዋን ለብሳ ነጎደች….
እርሱም አረንጓዴው ጠፍቶ ተነሳ።
— ሲገባ የነበረው የፊቱ አረንጓዴ። ድክም… ጥውልግ…ቅልጥ…
ምናልባት ነገ በታክሲ ሲዞር ነው የሚውለው። በፀሀይ ሲቀልጥ። ምናልባት ካገኛት….
ዛሬ ታክሲ ላይም አልነበር የተገናኙት?
ማን ያውቃል?!
ግን ማን ይላት ይሆን?!
“ለነገ ነገ ይጨነቃል።” አሁን መዝሙር ነው….

“አንቺ ልጅ አንቺ ልጅ
ስምሽን ንገሪኝ፣…
“አንተ ልጅ አንተ ልጅ
ስምህን ንገረኝ ♫ ♬

/ዮሐንስ ሞላ/

የመጨረሻው ኑዛዜ

አድናን አሊ
e-mail: adnan2000free@yahoo.com

አሞራዎቹ ከበውናል። ነብሳችን ሳትወጣ ስጋችንን በጫጭቀው ሊበሉ አሰፍስፈዋል። ጉልበቶቻችን በጠኔ ዝለዋል፤ በረሃብ ደክመናል። ያረፈብንን ዝንብ እንኳ ‘እሽ’ ለማለት እጃችንን ማወናጨፍ አቅቶናል። ደክመናል። መንገዶቻችን ሁሉ ወደ አዘቅት ወስደውናል። አሁንስ የትኛው ተስፋ ቀረን? . . . . . . . . በአሞራዎቹ ከመሰልቀጥ በቀር።

እንዲህ ይሆናል ብለን እንዳንናገር አፋችን በሴራ ተተብትቦ ልሳን አልባ ሆነን ኖረናል። ከዝምታችን ብዛት አፋችን ላይ ሸረሪት ድሯን አድርታብናለች። በዚህች እንኳ የሞት ሽረት ትንቅንቅ ውስጥ ልሳናችን ተለጉሟል።
“ማን ያውጋ? . . . የነበረ
ማን ያርዳ? . . . የቀበረ” . . . ነበር ድሮ። የነበርነውም አላወራን፤ የቀበርነውም አላረዳን . . . . . ታዲያ ምን ይበጀን ይሆን? . . . . . ሞት በቀር። ‘በሞት አፋፍ ብሆን እንኳ ስለእውነት እመሰክራለሁ’ ያለው አንደበታችን ዛሬ ምን ዋጠው? ሳንናዘዝ አሞራዎቹ ሊቦጫጭቁን እኮ ነው። ለንሰሃ ጊዜ በሌለን ሰዓት . . . . . . ምነው ሐጥያታችን በኑዛዜ ቢቀልልን?

ማነህ? . . . . . . . . ፀሐፊ!
እስኪ ብዕርና ብራና ይዘህ የያንዳንዳችንን ጓዳ ጎድጓዳ እውነት ከትበህ አስቀረው። በአሞራዎቹ ከመበላታችን በፊት ኑዛዜያችንን አኑረው። በሞት አፋፍ ላይ ሆነው እውነት ይደብቃሉ ብለህ አትስጋ። ለመኖር ነው ሰው አድርባይ ውሸታም የሚሆነው።

አሁን ግን ደክመናል። በጠኔ፣ በረሃብ ደቀናል። እኛ የምንበላው ሳይኖረን የሰማይ አሞራዎች በኛ ስጋ ሊጠግቡ ነው። ይህ ነው እንግዲህ የሕይወት ሚዛን! Survival of the fittest!

ዓለም እኛን ከመመገብ ይልቅ የሰማይ አሞራዎቹን እና ጥንብአንሳዎቹን ለመመገብ መርጧል። “This Is Natural Selection!” እኛ አቅም አጥተናል። አቅም ያለው የኛን ስጋ ይበላል።

የወረወርናቸው ቀስቶች መልሰው እኛኑ ይወጉናል። የደማችን ዥረት ሆዳቸውን አሳብጧል፤ ልጆቻቸው እንደ ቅልብ ጫንቃቸው ወፍሯል። ይህ የዚች ዓለም ሚዛን ነው!

አሁን ደከመን የመጨረሻው እስትንፋሳችንን እየጠበቅን ነው። አሞራዎቹ ወደ መሬት ማዘቅዘቅ ጀምረዋል። ከቀይ መስቀል እርዳታ ቀድመው ይደርሱልናል።

አንተ ፀሐፊ!
ወረቀቶችህ በሌሉ የፍቅር ቃላት ውዳሴ እና በቅንዝረኞች ፈንጠዝያ ከሚሞሉ . . . ና . . . የኛን የሰቆቃ ኑዛዜያችንን ፃፍበት። ና! . . . አሞራዎቹ ስጋችንን እየቦጨቁ ሲሄዱ በካሜራህ ቅረጸን። የውዳቂ መጽሔትህ የፊት ሽፋን ባይሆን . . . ገጽ ማሟያ ወሬ ይሆንሃል። ሞዴሎቻችን በተጥለቀለቁበት የፊት ሽፋን ገጽ ጀርባ የኛን የጠኔ ክርፋት አትምበት።

እንዲህ ሆነው ነው የሞቱት ብለህ ዘግበን። አርሰው፣ ዘርተው፣ አጭደው መብላት አቅቷቸው በረሃብ ሞቱ ብለህ ዘግበን። አንተን ለሚሰሙ ጥራዝ ነጠቅ ሊቆች።

ካሜራዎች እያንዳንዷን ቅጽበት ያንሱ፤ እንዳንዷውን ቅጽበት ይቅረጹ።

አሁንስ ምን ቀረን? . . . ከገማው ስጋችን፤ ከከረፋው ማንነታችን በቀር። እንደ እባብ አፈር ልሶ መነሳት አልተማርን። የሌለንን ዛሬ ከየት እናምጣ?

አሞራዎቹም የሳር ጎጆዋችን ክዳን ላይ አርፈዋል። እኛን ለመቦጨቅ አሰፍስፈዋል። ከመሬት ተንጋለን ሰማዩን እናማትራለን። እግዜር ከሰማይ ወርዶ እንዲያስጥለን እንማጸናለን። ተማጽኖዋችን በበረታ ቁጥር አሞራዎቹም ወደኛ ይቀርባሉ።

ማናችሁ? . . . እናንት ፀሓፊያን!!!
የሕብረተሰቡ ችግር የኛ ችግር ነው ትሉ አልነበር? በስራዎቻችን ሕብረተሰቡን እናንፀባርቃለን ትሉ አልነበር? . . . ምነው ታዲያ የኛ ችግር ችግራችሁ አልሆነም?

************************************

ተቀበል አዝማሪ
ተቀበል ግጥሜን
ና ወዲህ ጠጋ በል

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የሚነጥቁ’

ብለህ አንጎራጉር
አንት አዝማሪ ዘምር
ጮክ አርገው ድምጽህን
ከጫፍ ጫፍ ይሰማ
ንጠቅ ከኔ ዜማ
ውሰድ የኔን ስንኝ
ድገመው እንደ ሞኝ

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የሚነጥቁ’

ድገመው አንድ ጊዜ
ማሲንቆህ ሳይበቃ
የፈዘዘች ነፍሴ፣ ባንተ ጩኸት ትንቃ።

ተቀበለኝ ግጥም
እንደማር እንደጠጅ
እንደወይን የሚጥም
ተቀበለኝ ግጥም
አንጎራጉር ዜማ
አለም ሁሉ ይስማ

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የነጠቁ’

ብለህ አሳምረው
አንተ ደሃ አዝማሪ፣ የምጮኽ ላንተው ነው።

‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የነጠቁ
ከረሃብ ጋር ታግለው ተረተው ወደቁ
በአሞራዎቹ፣ በጥንብ አንሳዎቹ፣ ተበልተው አለቁ’

 

. . . . . . . . ‘ካንበሳ መንጋጋ ስጋ የሚነጥቁ’

ብለህ ዘምርልኝ
አንተ ቂል አንተ ሞኝ

* * *

ና አንተ ፀሐፊ. . .

አዝማሪው ከብዶታል
የኔን ስንኝ ማለት
እስኪ በብራናህ
ፃፈው የኔን ውድቀት

. . . . . . . . ‘ከተራሮቹ ጫፍ እስከ ሸለቆዎቹ
. . . . . . . . ምንም ማይበግረው፣ ጠንካራ ክንዶቹ
. . . . . . . . ዛሬ ከመንገድ ዳር
. . . . . . . . ወድቆ ይማፀናል
. . . . . . . . ወደ ሰማይ ያያል . . .’

ፃፈው የኔን ውድቀት
ሳትጨምር እብለት

አዝማሪው ደክሞታል
አዝማሪው ከብዶታል
አንተ ትጉህ ሰው ነህ
ፃፍልኝ እባክህ
እባክህ . . . እባክህ
ከመሞቴ በፊት
ክተብ ይሄን እውነት

****************************

አሁን አሞራዎቹም ወርደዋል። የሞት ሽረት ትግል ሊጀመር ነው። አሞራዎቹ ከኛ ስጋ የሚያገኙ መስሏቸዋል፤ ካገጠጡ አጥንቶቻችን በቀር። እስትንፋሳችን በቀጭኗ መውጫ ተወጥራለች። ቁስሎቻችን ላይ ዝንቦች ካረፉ ሰንብተዋል። እነሱን ለማባረር ክንዳችን ዝሏል።
አሁንስ ምን ቀረን? . . . ታፋችን ሲዘነጠል ከማየት በቀር። በመንቁራቸው የዓይኖቻችንን ብሌን ሲያፈርጡ ከምንሰማው የፃር ድምጽ በቀር።

ምነው ቶሎ ጀምረው በገላገሉን። የሞት መንገድ እንዲህ ይርቃል እንዴ? . . . ለምን ስቃያችንን ያራዝሙታል? . . . ለምን በድምፆቻቸው ያሸብሩናል?
ድምጽ!
ድምጽ!!
ድምጽ!!!
የአምቡላንስ ድምጽ!
ማነው ቀድሞ የሚደርስልን???

“ላነስተስልም! . . . ላነስተስልም! . . . ላነስተስልም!”