ልዩ የኢድ በዓል ዝግጅት! አሚን በይ በቃሉ | የረመዳን ጾም | ልጅነትና የረመዳን ጾም ትዝታ | የጁምአ ጀነት | Ethio Teyim | Episode 30

የቀጠለ… (ከዴቪድ ጋር)

ነገሩንም ለማብሰልሰል እየሞከርኩ፥ ሳቅ ብዬ “ይገርማል! እና ከሚስትህም ጋር እንዲህ የድሮ ነገር እያስታወሰችብህ፣ መግባባት እያቃታችሁ ነው የተጋጫችሁት?” ብዬ ጠየቅኹት
 
“አይ እሱን እንኳን ነገሩን ቀድሜ ስለማውቀው ብዙም አያጣላንም። ማወቅ ረጋ እንድትል ይረዳል። ስለምረዳት አልፋታለሁ።”
 
“ታዲያ ምንድን ነው? የሚነገር ዓይነት ከሆነ ነው የምልህ… ካልሆነም አትጨነቅ”
 
“ችግር የለውም። እነግርሃለሁ። ዋናው ነገር እኔም እሷም ትንሽ እረፍት ፈልገናል መሰለኝ። አንዳንድ ጊዜ በአንዱ መኖር የሚሸፈንልህን ነገር፣ ያ ሰው ጎድሎ ካላየኸው አታመሰግንም። ሁሉንም ነገር እንደ ተራ ጉዳይ ትቆጥረዋለህ። እሷም እኔም ዋጋችንን እርስበርስ እንድንተዋወቅ ይጠቅመናል። በዋናነት የግጭት መንስኤ የነበረው፣ ተራ ነገር ነው። ምን መሰለህ፥ ያዋጣናል ብለን የሆኑ እቃዎችን ሸጠን ነበር። ሀላፊነቱ ለእኔ ነበር የተወሰነው። ልክ እኔ ከሸጥኩት በኋላ ዋጋው ተወደደ።
 
መጀመሪያ ሳማክራት በስራ ስለምትጠመድ አንተ እንደፈለግኽ አድርግ ብላኝ ራሷን ገለል አድርጋ ነበር። እኔ ደግሞ የራሴን ጥናት አድርጌ፣ ሰዎች አማክሬ ሸጥኩት። በኋላ የተሻለ ዋጋ ማውጣት የሚችል ነገር መሆኑ ተገለጠልን። እና ጭቅጭቅ ጀመረ።
 
“ሳማክረሽ ችላ ብለሽው። ልብሽ ሁሉ ስራሽ ላይ ነው ያለው።” እላታለሁ፤ “አንተ ነገሮችን እንደፈለግኽ ነው የምታደርገው፣ ግድ የለህም” ትለኛለች።
 
ነገሩ ምክንያት ነው የሆነን እንጂ ጊዜ የሚጠብቅ ነገር ነበር። ያንን አጋጣሚ ተጠቅማ እሷ ከእኔ የተሻለ አሳቢ እና አዋቂ መሆኗን ለማሳየት ትፈልጋለች። እኔም አጋጣሚውን ተጠቅሜ፣ ልቧ ስራ ላይ ብቻ መሆኑን በማስታወስ የእኔን በደል እዘረዝራለሁ።
 
ታውቃለህ፥ በስራ በጣም ስለምትጠመድ ብዙ ነገሮች ያልፏታል። ደግሞ የቤተሰብ ሀላፊነቱ፣ እናትነቱ ስላለ አያስችላትም። ቤት መሆን መሳተፍ ትፈልጋለች። ታሳዝናለች።” አለኝ ሀዘኔታ እና ግራ መጋባት የተደባለቀበት ፊት እያሳየኝ
 
“ስራዋ ምንድን ነው?”
 
“ሀኪም ናት። ኦንኮሎጂስት ናት። ከባድ ሀላፊነት አለባት። ህክምና ስራውም ይበዛል፣ እሱ ላይ ደግሞ፥ እሷ በጣም ስራ ወዳድ ናት። አሁን እኔና አንተ እያወራን ብደውልላት እንኳን ኮምፒዩተሯ ላይ ተጥዳ የታካሚዎቿን መረጃዎች ስታስተካክል፣ ወይ የነገ ኬዞችን ስታደራጅ ነው የምታመሸው። እኔ ሁሌም ልረዳት ነው የምሞክረው። በስራዋ ደስተኛ ነኝ። ህክምናውን ባውቅና፣ ብችል ባግዛትም ደስ ይለኝ ነበር። ግን ደግሞ የስራ እና የኑሮን ጉዳይ ሚዛን መጠበቅ አለብህ።”
 
“እውነት ነው”
 
“ቀላል ምሳሌ ልንገርህ። ብዙ ጊዜ የሚከሰት ነው። ከምሽቱ 12 ሰዓት አካባቢ ቴክስት ተደራርገን ወይ ተደዋውለን እየመጣሁ ነው። ትለኛለች። እኔም እሺ ብዬ ምትበላውን አዘጋጅቼ፣ ምትጠጣውን አዘጋጅቼ እጠብቃታለሁ። 1 ሰዓት፣ ወይ 2 ሰዓት ያልፋል። በመሀል መሄድ የምፈልግበት ቦታ ካለ ወይ ወዳጆቼ ከጠሩኝ የጽሁፍ መልዕክት ትቼላት እወጣለሁ። ታብዳለች። እሷን ለማናደድ ያደረግኩት ያህል ይሰማታል። እሷ ጉዳይ ካለባት ሌላ ሰው ጉዳይ የሌለበት ይመስላታል። ራሷን ብቻ ነው የምታዳምጠው። ብዙ ነገሮች እሷ ስታደርጋቸው ልክ ሆነው ይኖሩና፣ ልክ እኔ ሳደርጋቸው ስህተት ይሆናሉ።” ብሎኝ ሳቀ። በፈገግታ አጀብኹት።
 
“እህ…” አልኩኝ የምሰጠው አስተያየት ነገር ያግል፣ ነገር ያብርድ ስላልገባኝ፤ ጨዋታው እንዲቀጥል በመፈለግ፥
 
“ሌላ ምሳሌ ልስጥህ፥ ከልጆቼ ጋር ባለኝ ግንኙነት ትቀናለች። ቅድም ተደዋውለን ራሱ አንድ ሁለት ተባብለናል። ልጃችን ከኒውዮርክ ነገ ትመጣለች። ቀድመን ሁለታችንም እናውቃለን። ነገር ግን ከአውሮፕላን ማረፊያም እንድቀበላት ስለምትፈልግ ዛሬ እኔ ጋ ደወለችልኝ። ቅድም ስደውል መደወሏን ነገርኳት።
 
“ለምንድን ነው እኔ ጋር ያልደወለችው?” አለችኝ። ለምን ልበላት?
 
እኔ የስራ ፀባዬም ጊዜ ስለሚሰጠኝ፣ በተፈጥሮዬም እንደዚያ ስለሆንኩ ልጆቼ ጋር በየቀኑ አንድ ደቂቃም ቢሆን እደውላለሁ፤ ያንን ለምደው ሳልደውል ስቀር ደግሞ እነሱም ይደውላሉ። እሷም ጋር ይደዋወላሉ። ግን ያለባትን ጫና ስለሚያውቁ፣ ብዙምም ፊት ስለማትሰጣቸው አጥሯን ያከብሩላታል።
 
እኔ አብሬያቸው መሬት ላይ ስንከባለል፣ ትራስ ስወራወር፣ ስላፋ፣ ቴኒስ ስጫወት ነው ማሳልፈው። እሷ ያንን ለማግኘት እድሉም የላትም። ከስራ ጸባዩዋ አንጻር ይህንን ማድረግ ለእሷ ቅንጦት ነው። በዚህም የተነሳ ልጆቻችን እኔን የበለጠ ይቀርቡኛል። የምልህ እሷንም ይቀርቧታል፣ ግን እኔ ጋር ይበልጥ ይሆናሉ። እሷን ይረዷታል። ዝም ብለው ሄደው አይረብሿትም። ነይ እንውጣ፣ ገበያ እንሂድ፣ ሜዳ እንሂድ አይሏትም። ትልልቆች ስለሆኑ ያውቃሉ።
 
እሷ ለመታቀፍ እና ለመሳም “እኔስ” ብላ ጠይቃ ነው እንጂ ዝም ብለው ሄደው አይጠመጠሙባትም። እሷም ያን ያህል ጊዜ መስጠት ብትፈልግም አትችልም። ስራዋ በጣም ይፈልጋታል። የብዙ ሰዎች ሕይወት እጇ ላይ አለ። እና ከእኛ ጋር መሆኑ ቅንጦት የሚሆንበት ጊዜ ብዙ ነው።
 
ሀኪም ማግባት ቀላል ነገር አይደለም። በጣም ከባድ ነገር ነው። ሀኪም ካላገባህ ወይ ሀኪም ካልሆንክ አይገባህም። ከሀኪም ጋር ጓደኝነት እንኳን ከባድ ነው።
 
በብዙ ውጣ ውረድ ነው የምታልፈው እሷ። የተለያዩ ታካሚዎች ይመጣሉ። የተለያዩ ታሪኮችን ትሰማለች። በመሀል ቆዳዋ ጠንክሯል። ሞት አይደንቃትም። የምልህ፥ በግዷ ትጠነክራለች። ጠንካራ ተመስላለች። ብዙ ጊዜ ሰው ሲሞት አይታለች።
 
የረዳችው ሰው፣ ለክፉ አይሰጥህም ያለችው ሰው፣ ተስፋ የሰጠችው ሰው፣ የተላመደችው ሰው ሲሞት አይታለች። ለቤተሰብ ዓይናቸውን እያየች የሟቹን ወሬ ማርዳት አለባት። ስራዋ ያስገድዳታልና አብራም ማልቀስ አትችልም። ዓይናቸውን እያየች፣ ፊትለፊታቸው ቆማ “ስነግርህ አዝናለሁ። ሚስትህ ሞታለች” ትላለች። ቀላል አይደለም። በሀዘኑ ብዛት ድብርት ውስጥ ገብተው መልሰው እሷ ጋር ይመጣሉ። መርዳት፣ ሪፈር መጻፍ አለባት። ነገ ያንን ወሬ ከአንዱ ለማስቀረት ስትል ዛሬ ብዙ መስራት እንዳለባት ታስባለች። ቀላል አይደለም። እና አንዳንዴ ትንሽ የራሷን ቦታ ልትፈልግ ትችላለች። በአንድ መልኩ እሷንም እኔንም ለመርዳት ነው ለጊዜው ገለል ማለት እንዳለብኝ የወሰንነው።”
 
“አይዞን! (የአይዞንን ትርጉም አስረድቼው ቃሉን እሱም ይጠቀማታል) ሁሉም ጥሩ ይሆናል። በቅርቡ ሁሉም ተስተካክሎ አብራችሁ እንደምትሆኑ ተስፋ አደርጋለሁ።” አልኩት።
 
“ይመስለኛል! በቀጣዩ ወር የጋብቻ አማካሪ (marriage counselor) ጋር ለመሄድ ቀጠሮ ይዘናል። ነገሮች ጥሩ መሆናቸው አይቀርም።”
 
መልካም ምኞቴን ተመኝቼለት ሌላ ጨዋታ ቀጠልን።

“ሴቶች አስቂኝ ናቸው”

ከ2 ሩም ሜቶቼ ጋር፥ ፒንች ውስኪ በ3 ብርጭቆ ቀድተን አጋጭተን ተጎነጨን። ከጥቂት ቆይታ በኋላ አንደኛው ‘ኖርዝ ካሮላይና የሚሄድ ልጄን አውሮፕላን ማረፊያ አደርሳለሁና ልሂድ’ ብሎ ተሰናብቶን ወጣ። ሬሜ ይባላል። ስለእሱ ሌላ ቀን እንጫወታለን።
 
ከዴቪድ ጋር ለጥቂት አፍታ ዝም ተባብለን ስለሚስቱ ጠየቅኹት።
 
“ታውቃለህ ዮሐንስ፥ ሴቶች በጣም የሚያስቁ ፍጥረቶች ናቸው” ቀጥሎ ያለውን ለመስማት በመጓጓትም፣ በደምሳሳው የደመደመው እንደው ለመከላከል በመሻትም
 
“እንዴት?”
 
“ናቸዋ!”
 
“ቀላል ነው? እንዲህ ብለን ማጠቃለል እንችላለን ዴቪድ?”
 
“ታውቃለህ? በጣም ነው የሚያስቁት። አስቂኝ ፍጥረቶች ናቸው። የዛሬ 20 ወይ 25 ዓመት ያደረግኸውን ነገር በፈለጉት ጊዜ ያስታውሱታል። ከወሸቁበት ያወጡታል። መቼም ቢሆን ነገሮችን አይረሱም። ባልጠበቅኸው ጊዜ፣ ባላሰብኸው ሰዓት አሳቻ ቦታ ላይ አንተን ለማጥቃት ወይ አሸናፊ ለመሆን ይጠቀሙበታል።”
 
ከት ብዬ ሳቅኹኝ!
 
“ሳቅ! ጊዜው እስኪመጣልህ ሳቅ!” ብሎ አብሮኝ ሳቀ
 
“የምር ግን ነገሩ ስላልገባኝ ነው”
 
“ለምሳሌ እኔ የሆነ ጊዜ የሆነ ነገር እላለሁ። ለምሳሌ በጭቅጭቅ መሀል “ገደል ግቢ” እላታለሁ። ከ15 ዓመት በኋላ ‘በእንዲህ በእንዲህ ጊዜ፣ እንዲህ እንዲህ ስናወራ፣ እንዲህ ስል ገደል ግቢ ብለኸኝ ነበር። እህ?’ ትለኛለች። እኔ አላስታውሰውም። ዛሬ ብለኸው በመነጋውም ትዝ ላይልህ ይችላል። በዚህ በጣም ተናደህ ‘እና ምን ይጠበስ ያልኩ እንደው?’ ትላታለህ። ነገሩ ጭራሽ ይግላል…”
 
“ለሁሉም ሴቶች ላይሰራ ይችላል” አልኩኝ ነገሩን ለማስቀጠል እና ትንታኔውን ለመስማት በመጋበዝ
 
“ቀልዴን አይደለም። ሴቶችን ለማሳነስ ብዬ አይምሰልህ። በዚህ ዙሪያ ያለኝን ግንዛቤ እና ልምድ እነግርሃለሁ። እረዳቸዋለሁ። በአብዛኛው የራሳችን የወንዶቹ ችግር ነው፤ ግድ እናጣለን። ስለሚስቴ ወይ ቀድመው ስለነበሩ ሴቶች አይደለም ማወራው። ማነጻጸሪያዬም እነሱ ብቻ አይደሉም። ከእህቶቼ ጋር፣ ከእናቴ ጋር፣ ከአያቴ ጋር፣ ከሚስቴ እናት ጋር፣ ከአጎቶቼ/አክስቶቼ ልጆች ጋር ያወራሁበት እና ያየሁት ነገር ነው። 4 እህቶች አሉኝ። ሁሉም በዚህ ጉዳይ ይስማማሉ።”
 
“ይገርማል። ግን ለምን እንደዚህ ይሆናል?”
 
“በአብዛኛው ነገሮችን በግል እንደተደረገባቸው ነው የሚወስዱት (they take things personally)። እንዲህ ስልህ ሴቶችን ከወንዶች ላሳንስ ወይ ልክ አይደሉም ልል አይደለም። ግን ተፈጥሮአቸው ይመስለኛል። በርግጥ ስለሁሉም ሴቶች እያወራሁ አይደለም። ላወራም አልችልም። ግን ከጓደኞቼም ከቤተሰቦቼም ከስራ ባልደረቦቼም ጋር በተለያየ ጊዜ አውርተነዋል። ወንዶችም ሴቶችም እንስማማበታለን። ብዙ ምርምር አድርጌያለሁ። (ሳቀ)
 
እድሜህ ሲገፋ ከሴቶች ጋር ብዙ ግጭት ስታስተናግድ፣ ምንድን ነው ችግሩ ማለትህ አይቀርም። ዙሪያህን ስታጤን ይገባሃል። ችግሩንም ስታወሩ ማወቅህ አይቀርም። አንተ ብዙ ስላልኖርክ ብዙ ላይገጥምህ ይችላል። ከፍቅረኛህ ጋር ተጋብታችሁ 10 ወይ 20 ዓመት ስትኖሩ የምለው ይገባሃል። ለምን አሁን አትጠይቃትም? ትነግርሃለች። ደግሞ ሲወዱህ እና አንተ አሪፍ ስትሆን ድብቅ አይደሉም።
 
ዛሬ የምትላትን ሁሉ የምትመዘግብበት ቦታ አላት። አስባው አይመስለኝም። እንዲሁ ተፈጥሮዋ ነው። ታውቃለህ ሴቶች ከወንዶች የበለጠ ስሜት (feelings) አላቸው። መኖር ይፈልጋሉ። ቁም ነገር እንጂ ቀልድ አይፈልጉም። ያምኑሃል። በቁም ነገር ይሰሙሃል። ስለዚህ አይረሱትም።
 
አንተ በ30 ቀናት 30 ጊዜ ፋክ ዩ ትላለህ። ብርጭቆው ሲወድቅ፣ ቀጠሮ ሲረፍድብህ፣ ጓደኛህ ሲያስቀይምህ በተለያዩ አጋጣሚዎች ተናደህ ምታወጣው ቃል አለ። ጓደኞችህን ሃምሳ ጊዜ ትላቸዋለህ። ጉዳያቸውም አይደለም። ሚስትህን ግን ልትሸውዳት አትችልም። ለእሷ ያልክበትን አጋጣሚ አትረሳውም። በግጭታችሁም ጊዜ ሁሉ ወደ ኋላ የሆነ ዓመት ተጉዛ የሆነ ትውስታ ትመዛለች።”
 
አሁንም ከት ከት ብዬ ሳቅኹኝ።
 
“ሳቅ አንተ። አሁን ሳቅ።” ብሎኝ ሳቄን ተቀብሎኝ ቀጠለው።
 
አባባሉ አስቆኝ እንደገና ሳቅኹኝ።
 
“ምሳሌ ልንገርህ” ብሎ ቀጠለ። በሚያወራው ነገር ሁሉ ምሳሌ አያጣም። የእናቴን በነገር ሁሉ የሚነገሩ ተረቶች ያስታውሰኛል።
 
“አንዴ የሚስቴ እናት ጉዞ ነበራት እና አውሮፕላን ማረፊያ እንዳደርሳት ጠየቀችኝ። ለጉዞዋ መገኘት ያለባት ከሰዓት 8 ሰዐት ነው። ላደርሳት ከተስማማሁ በኋላ ከሰዓቱ እንዳላረፍድባት አስጠንቅቃ ነግራኛለች። እንደተቀጣጠርነው ከቀኑ 6 ሰዐት ተኩል ላይ ቤቷ ደረስኩ።
 
‘እንሂድ’ ስላት፥
 
‘ቆይ አንዴ፣ እንዲህ ተዝረክርኬ እንዴት እሄዳለሁ?’ ብላ መኳኳል መቀባባት ጀመረች (በእጁ ፊቱ ላይ አቀባቧን እያሳየኝ)
 
‘በቃ ምንም አትሆኚ እዚያ ስትደርሺ ሆቴልሽ ትስተካከያለሽ፣ ይረፍድብሻል’ ብላት
 
‘እምቢ አሻፈረኝ! እኔ ነኝ ተጓዧ አንተ?’ አለች። ሰዐቷን አይታ ችግር የለም እንደርሳለን አለችኝ።
 
በመከራ ሰባት ሰዐት ላይ ወጣች እና ጉዞ ጀመርን።
 
የባለቤቴ እናት በሁሉም ነገር ላይ አውቃለሁ ባይ ናት። ምንም ነገር ብታደርግ አስተያየት ትሰጥሃለች። ምንም ነገር!
 
እንደልማዷ ገና ስነሳ፥ “ኧረ ቀስ!” ብላ ጀምራ አነዳዴን መተቸት ጀመረች። በርግጥ ሰዐቷ እንዳይረፍድ ብዬ እየተዋከብኩ ነበር። ፈጥኜ ለመንዳት ሞክሬያለሁ።
 
መሀል ላይ ምንጭቅ ብላ ደጋግማ ቀስ እንድል ትነግረኛለች፤ ‘መድረስ አለብሽ በሰዐትሽ’ ብዬ ላስረዳት እሞክራለሁ። በጣም ጨንቆኛል ለእሷ።
 
እሷ ደግሞ ዘና ብላ ‘ገና ነው እንደርሳለን’ ትለኛለች።
 
መሀል ላይ ጭቅጭቋ ከአቅም በላይ ሆነብኝ። ካላስቆምኳት አደጋ ላይ ሁሉ ልትጥለኝ በምትችል መልኩ ትናገራለች።
 
ዳር አቁሜ ‘የእኔ እናት፥ ካልፈለግሽ ውረጂና ታክሲ ጠርተሽ ሂጂ።’ አልኳት።
 
አበደች። እንዴት ብትደፍረኝ አለች።
 
‘ነግሬሻለሁ ምርጫው ያንቺ ነው።’ አልኳት። የምር ተናድጄ ነበር።
 
አማራጭ ስለሌላት የግዷን ተሳፍራ አፏን ዘግታ ሄድን። ስንደርስ 20 ደቂቃ አርፍደናል። እድለኛ ሆና ግን አውሮፕላኑ አረፈደና ተሳፈረች።
 
ከዚያ ምን ቢሆን ጥሩ ነው? ከ10፣ ልክ ድፍን 10 ዓመት በኋላ የሆነ ክርክር ይዘን መሀል ላይ፥ ‘ግን ለምን ነበር ወደ ፈረንሳይ ስሄድ ከታክሲ ላይ እንዲያ ያበሻቀጥከኝ?’ አለች። (አብረን ሳቅን)
 
ምን አገናኘው? ምን ልበላት? እኔ ከዚያ ቀን በኋላ ትዝ ብሎኝም አያውቅም። ያልኩትን ብያት አብቅቷል። ያን ያለችው የተነሳውን ክርክር በባሌም በቦሌም ለማሸነፍ ስለፈለገች ነው። የሚስትህ እናት ስለሆንኩ፣ እንዲህ ስለሆነ፣ ያኔ ታክሲ ያዢ ስላልኸኝ ብላ ልታሸማቅቀኝ ስተፈልግ ነው።
 
አይገርምም? እንደዚህ ዓይነት ነገሮች ይገጥሙሃል። የፈለግኸውን ባለትዳር ጠይቅ ይነግሩሃል።”
 
ሳቅ ብዬ፥ “ይገርማል፤ ግን…” ስለው
 
“ሌላ ምሳሌ ልንገርህ፥ እናቴ እስክትሞት ድረስ ከአንድ ወንድሟ ጋር እስከዚህም ነበሩ። 20 ዓመታት ተደባብረው ነው ያሳለፉት።
 
ምክንያቱን ገምት! እናታቸው በጣም ውድ የሆኑ ዘርፍ ያላቸው፣ የእምፑል ማቀፊያዎች ነበሯት። እጅግ በጣም ውድ ነበሩ። እና ለእናቴ እንድትወስዳቸው ቃል ገብታላት ነበር። እናቴ ስትሞት ወንድሟ ልቡ እያወቀ በጉልበቱ ወሰዳቸው።
 
የእርሷ እንደሆነ ነግራው ልታስረዳው ሞክራ ነበር። ግን ብዙም ግድ ያለው ዓይነት አልነበረምና ዝም ብሏት ወሰደው። ተቀየመችው። ግንኙነታቸውም እስከዚህም ሆነ። እሱ ለምን እንደሆነ አያውቅም ነበር። አይገባውም።
 
ከ20 ዓመታት በኋላ እሱም በሰል ብሎ፣ እሷም ደከም ብላ ግድ ሲነጋገሩ አስታወሰችው። ፀፀቱ ሊገድለው ደረሰ። በጣም አዘነ።”
 
ነገሩንም ለማብሰልሰል እየሞከርኩ፥ ሳቅ ብዬ “ይገርማል! እና ከሚስትህም ጋር እንዲህ የድሮ ነገር እያስታወሰችብህ መግባባት እያቃታችሁ ነው?” ብዬ ጠየቅኹት
 
ይቀጥላል…
 
እውነት ነው ወይ? 🙂

ከአዲሱ ክፍል ተጋሪዬ ጋር

በሬ ተንኳኳ።
 
የከፈትኩትን ሙዚቃ አስቁሜ፣ “ማነው?” እያልኩ ተነሳሁ፣ ከሩምሜቶቼ (ክፍል ተጋሪዎቼ) ውጭ ሌላ ማንም እንደማይሆን ልቤ እያወቀው።
 
አዲሱ ክፍል ተጋሪዬ ዴቪድ ነው። ጠርሙስ እና ሲኒ ይዞ፣ ፈገግታ ተሞልቶ “ሰላም” አለኝ።
 
“ሰላም ዴቪድ። እንዴት ዋልክ?” አልኩት
 
በቀኝ እጁ የአረቄ ጠርሙስ፣ በግራ እጁ ሲኒ ይዞ እንደመቅዳት እያቀባበለ፥
“ምናልባት አረቄ ትፈልግ እንደው ብዬ ነው? ትወደዋለህ። አሪፍ የስፔይን ረም ነው።”
 
“ኦህ፥ መልካም ነህ። አልጠላም። ለነገሩ እኔም ወይን እየጠጣሁ ነበር።” ብዬው የቀዳልኝን አረቄ ተቀብዬው፣ አመስግኜ ገባሁ።
 
ሳልቀመጥ ተጎነጨሁለት። የምር አረቄ ነው። ቁንዱፍቱዬ። ጵጣ ጵጣ እያልኩ አንድ ሁለት ጊዜ ከተጎነጨሁለት በኋላ፣ ምናልባት ሰው ፈልጎ ይሆናል እኮ፥ ጠርቼው ወይኑን አብረን የማንጠጣው? የሚል ሀሳብ አደረብኝና ውጥቼ በተራዬ በሩን አንኳኳሁ።
 
“ሰላም ዴቪድ። ወይን አብረን እንድንጠጣ ትፈልግ እንደው ታች እየወረድኩ ነው፣ መምጣት ትችላለህ” ብዬው ወደ ሳሎን ሄድኩኝ።
 
ይሁንታውን ስለገለጸልኝ ሁለት ብርጭቆ አለቅልቄ ተሰየምኩ።
 
እጅ ነስቶ ተቀላቀለ። ከአፍታ ቆይታ በኋላ መጥቶ ቀዳሁለት እና አጋጭተን ተጎነጨን።
* * *
በ60ዎቹ መጀመሪያ የሚገመት ነጭ ነው። ደልደል ያለ ሰውነት፣ መልከ መልካም ገጽታ ያለው፣ መላጣ ነው። ፊቱ ላይ የሚታይ እርጋታ እና ብስለት አለ። ያለው ጥቁር ፀጉር የቅንድቡ ብቻ ነው።
 
የእኛን መኖሪያ ከተከራየ ገና ሳምንቱ ነው። ከ3 ቀናት በፊት እንዲሁ፣ ለምሳ ቤቴ ስገባ፥ “ሰላም ዮሐንስ፣ ቡና ትፈልግ እንደው አታፍላ። እኔ ያፈላሁት አለ።” ብሎኝ ሲያስደንቀኝ ነበር። ያልተለመደ ጸባይ ነው። የእናቴን ጓደኞች፣ የአገሬን አኗኗር ያስታውሰኛል።
 
እንደሚታየው ሰው ይወዳል። ሰው ይፈልጋል።
 
ቀድሞም ቡና አለ አታፍላ ሲል፣ የቀደመ ታሪኩን የማወቅ ፍላጎቴን ቀስቅሶት ነበር። የአረቄ ግብዥ ማንኳኳቱ ደግሞ ይበልጥ አባሰብኝና፣ ጥያቄዎችን አግተለትልለት ዘንድ ወሰወሰኝ።
 
“እሺ ባክህ። ብዙ ቆየህ እዚህ?”
 
“አዎ። ከአርባ አመታት በላይ።”
 
“ከየት ነህ?”
 
“ከስፔን ነኝ”
 
“አንተ ከየት ነህ?”
 
“ከኢትዮጵያ። ይገርማል። ብዙ ቆይተሃል። ብቻህን ነበርክ ይሄን ሁሉ ጊዜ?”
 
“ቤተሰብ መስርቻለሁ። ልጆች አሉኝ። ሁለት ልጆች አሉኝ። አንደኛው ልጄ እንደውም ኦሀዮ ዩኒቨርስቲ አሁን እየገባ ነው። እናቱ ናት ልታደርሰው አብራው የሄደችው። እዚያው ኦሀዮ ናት። ትልቋ ልጄ ሬዚደንሲ ላይ ናት።”
 
“ደስ ይላል። አብራችሁ አትኖሩም ማለት ነው?”
 
“ያው እንደምታየው እኔ ከእናንተ ጋር ነው ምኖረው ከዚህ በኋላ” ብሎ ሳቀ
 
“ይቅርታ ዴቪድ። ዝርዝሩን መጠየቄ ሳይሆን፣ ነገሩን እያሰብኩት ስለነበር ነው።”
 
“ገብቶኛል። አትጨነቅ። ሳምንት ሆነን ከተለያየን።”
 
“አዝናለሁ። በሰላም? ልትፈቱት የማትችሉት ጉዳይ ሆኖባችሁ ነው?”
 
“እንፈታዋለን። ግን ትንሽ የየራሳችንን ቦታ ፈልገናል መሰለኝ። እንደምንመለስ ተስፋ አደርጋለሁ።”
 
“እኔም አብራችሁ ትሆኑ ዘንድ ምኞቴ ነው። እርግጠኛ ነኝ በአጭር ጊዜ ወደቀደውም ሕይወትህ ተመለሳለሕ”
 
“አመሰግናለሁ። ጥሩ ሰው ነሕ። እኔም ተስፋ አደርጋለሁ።”
 
እንዲህ እየተባለ ብዙ ነገሮች ስናነሳ ስንጥል፣ ስንጎነጭ አመሸን።
 
ያልለመድኩት፣ ያልጠበኩት ዓይነት ሰው ነው። የኑሮን ብልሀት ያውቅበታል። ስለብዙ ነገሮች ተጨዋወትን። ብዙ ቦታዎችም ሊያሳየኝ ፍላጎት እንዳለው ነገረኝ።
 
አፀፋውን ለመመለስም ተቅበዝብዤ፥
 
“ዴቪድ፥ ምናልባት የምታወራው ሰው ትፈልግ እንደው በሬን ማንኳኳት ወይ ቴክስት ማድረግ ትችላለህ። ከሞቀ ቤት ስለወጣህ ሊከፋህ ይችላል። ግን አደራ፣ ብቻህን እንደሆንክ እንዳታስብ።” አልኩት
 
ደስታ ስሜታዊ አደረገው። “እንደዚህ መባል ነበር የናፈቀኝ። በጣም አመሰግናለሁ። አሁንም አሁንም እየመጣሁ አልረብሽህም። ግን አሁን ቢያንስ ሰው አለ፣ ብቻህን አይደለህም ስትለኝ ደስ አለኝ። እዚህ ስቆይ ያንን ስለማስብ እኔም ጥሩ እሆናለሁ፣ አንተንም አልረብሽህም”
 
“ኧረ ችግር የለም። እንደ ልጅህ ልታየኝ ትችላለህ። ምንም ዓይነት እርዳታ ስትፈልግ አለሁ። ባልረዳህ እንኳን፣ ቢያንስ አንተን ሳልፈርጅ እሰማሃለሁ።”
 
“ይሄ ከእርዳታ በላይ ነው ለእኔ። ሰው ትናንት ላይ ተቸንክሮ ይቀራል። አልረባም ይላል። እኔ በአንድ ጊዜ አንድ ቀን ለመኖር እየታገልኩ ነው የኖርኩት። አሁን ደግሞ ባላሰብኩት ጊዜ እዚህ መምጣት ነበረብኝ። ልትቆጣጠረው አትችልም። ቢያንስ ግን ርቄም ሰው እንዳለ ማወቄ ደስ ብሎኛል። ከባለቤቴ ጋር የምንታረቅ ይመስለኛል።”
 
“መች ነው ለመጨረሻ ጊዜ ያወራሃት?”
 
“አሁን ከ20 ደቂቃ በፊት፣ አንተ ሳትጠራኝ። የልጁን ዶርሚታሪ አልወደደችውም። እና ስለሱ እየነገረችኝ ነበር። በፊት አብሬ ላይ ታች እል ነበር። አሁን ብዙም ያንን የምትፈልግ አልመሰለኝም። ሃኒ፥ አይዞሽ፣ የምትፈልጊው ማድረግ የምችለው ነገር ካለ ንገሪኝ አልኳት”
 
“ሃኒ ትላታለህ አሁንም?” ተገርሜ ጠየኩኝ
 
“አሁንም እወዳታለሁ። ታወደኛለች። ልጆች አሉን። በህግ አልተለያየንም። አብረን ነን ማለት ነው። ያላስማማን ትዕቢት ነው። ኢጎ።”
 
“አብራችሁ እንደምትሆኑ ተስፋ አደርጋለሁ” ብዬ መልካም ምኞቴን ተመኝቼ ወደሌላ ጨዋታችን ቀጠልን።

ከአዋላጅ ነርስ ወዳጄ ጋር ገጠመኝ

ጊዜ ሳገኝ ስለህክምና ባለሞያዎች የማስታውሰውን እጽፋለሁ ባልኩት መሰረት፥
 
ጎሮ የሚባል ጤና ጣቢያ ስር ያሉ የጤና ኬላዎች (health posts) የCHIS (community health information system) የሥራ ላይ ስልጠና ለመስጠት ከአንዲት አዋላጅ ነርስ የስራ ባልደረባዬ ጋር እንሄድ ነበር።
 
ነገሩ፥ የትራንስፖርት ችግርም ስለሚኖርብን በአንድ ድንጋይ ብዙ ወፍ ለመግደል ተሰብስበን ነበር የምንሄደው። እዚያ ደርሰን ሁላችንም በየሚናችን እንሰማራለን።
 
የዚያን ቀን ግን ጤና ኬላው አንዲት ነፍሰጡር እናት ምጥ ላይ ሆና፣ የጤና ኤክስቴንሽኖቹም ሊረዷት እየሞከሩ ግራ ተጋብተው ሲጯጯሁ ነበር የደረስነው። እርግዝናው ከመደበኛው ትንሽ የተወሳሰበ (complicated) ነገር ነበረው።
 
“ለምን አምቡላንስ አልጠራችሁም ቀድማችሁ?” ብላ ጮኸች ባልደረባዬ
 
“ከትናንት ማታ ጀምሮ ስንሞክር ስልክ እምቢ ብሎን ነው። በትራንስፖርት ልንወስዳትም ብለን አልቻልንም።” አለች የጤና ኤክስቴንሽኗ በጭንቀት በሚቆራረጥ ድምጽ።
 
ባልደረባዬ ቀጥታ ወደ ስራው ገብታ
 
“በይ ቶሎ ጓንት አምጪልኝ፤ እናንተስ ቆማችሁ እያያችኋት ነው እንዴ ምትረዷት?” አለች
 
“ጓንት እኮ አልቆብናል። በስልክ እነግርሻለሁ ብዬ ኔትዎርክ እምቢ ስላለኝ ነው። ግራ ሲገባን ስስ ፌስታል ገዝተን ነበር፤ ፌስታል አለ።” ብላ ሁለት አዳዲስ ፌስታሎች ነጥላ ሰጠቻት።
 
(እንግዲህ አልቋል የተባለውንም ጓንት መንግስት አይደለም የሚልክላቸው። እኔ እሰራ የነበረበት መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ነበር። አምቡላንሱንም የገዛው የእኛው መ/ቤት ነበር።)
 
ፌስታሉን እጆቿ ውስጥ አጥልቃ፣ “እሰርልኝ” አለችኝ።
 
ነገሩ ትንሽ ይጨንቅ ስለነበር አስተያየትም ሳልሰጥ የደመነፍሴን አሰርኩላትና፣ “በሉ ፀልዩ ሂዱ” ብላ ከጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኛዋ ጋር ገብታ፣ ከብዙ ከፍ ዝቅ፣ ፀሎት እና ጩኸት በኋላ በሰላም አዋለደቻት።
 
ስትመለስ ድካም፣ እርካታ፣ መሰልቸት፣ ብዙ ነገር ነበር ፊቷ ላይ።
 
እየተመለስን “ትቀልጂያለሽ እንዴ? እንዴት እንዲህ ይሆናል? ካለጓንት እንዴት ታዋልጃለሽ? ፌስታሉስ ግን ያመቻል?” አልኳት
 
ግራ የገባው የእንትን የማይባል ሳቅ ስቃ (የፌስታሉን ነገር ማንሳቴ መሰለኝ ያሳቃት)፥
 
“ምን ላርግ? የኖርንበት ችግር ነው። ትዝ የሚልህ ራሱ መሀል ላይ ነው። ቀድሞስ ትዝ ቢልህ ምን ታመጣለህ? እንኳን እኔ አዋላጇ፣ አንተስ ብትሆን በእንዲህ ሁኔታ ላይ ሆና አግኝተሃት በማታውቀውም ገብተህ ቢሆን ለመርዳት አትሞክርም ነበር? ሕይወትህን አደጋ ላይ ጥለህ ነው የሰው ሕይወት ለማዳን ምትጥረው።”
 
እሷ ረሳችው። የሁልጊዜ ገጠመኟ፣ እንጀራዋ ነውና ብዙም አይደንቃትም ይሆናል። እኔ ግን እዚያ በሄድኩ ቁጥር የማልረሳው ገጠመኜ ነበር። ካለማጋነን ንግግራችንን ቃል በቃል የማስታወስ ያህል አእምሮዬ ላይ ታትሞ ቀርቷል።
 
አስታውሼ ስጽፈውም ትዝ እያለኝ ዘግንኖኛል። ምናልባት ይኽን ሲያነብ የሚዘገንነውም ይኖራል።
 
ለእሷ ግን ሕይወቷ ነው። የአርበኝነት ሕይወቷ። ራሷን አደጋ ላይ ጣል፣ ሌላን የመርዳት፣ የማዳን፣ የማዋለድ ሥራ።

ከዚያስ…?

“እሺ፥ እንዴት ነው? ሁሉ ሰላም?” አልኩት አፍሪካ አሜሪካዊውን አዲስ ወዳጅ

“ማለት?” እኔ ከዝምታዬ ጋር ስደራደር፣ በሀሳብ ጭልጥ ብሎ ስለነበር ተደናግጦ ጠየቀኝ

“አይ፣ እንዲያው ሁሉ ሰላም ነው ወይ? ቤተሰብ? ኑሮ እንዴት እየወዘወዘህ ነው? ለማለት ያህል ነው።” ቀልጠፍ ብዬ በፈገግታ ታጅቤ መለስኩ። የምሸሸው ጭንቀት ስለነበረብኝ ዝምታውን አልፈለግኩትም።

“ኦህ፥ ሁሉም ሰላም። ሰላም ነው። …እሁድ የትልቁ ልጄ 29ኛ ዓመት ልደት ነበር።”

“እየቀለድክ መሆን አለበት። 29? አንተ ራስህ ከዚያ የምታልፍ አትመስልም እኮ።”

“አዎ። ሁለተኛዋ 26 ዓመቷ ነው።”

“በጣም ደስ ይላል። እጅግ በጣም ደስ የሚል ነገር ነው። ይኽኔ ከኮሌጅም ወጥተው ቦታ ቦታ ይዘውልሃላ…”

“አይ አይ! ቢሆን በምን ዕድሌ። ግን አይደለም። የቀድሞዋ ሚስቴ ዕድላቸውን መወሰን ነበረባት። ሲጥልብህ ልጆቿ ላይ ክፉ ፍርድ የምታሳልፍ እናት ጋር ያጋባሃል።”

“እንዴት ማለት? የማይሆን ርእስ ካነሳሁ ይቅርታ” ራሴን ስለቀለብላባነቴ እየወቀስኩ ጠየኩት።

“ግድየለም ኧረ። ….እናታቸው ከገንዘብ ጋር ያላት ቁርኝት እጅግ የተለየ ነበር። በእርሷ የብድር መክፈል ታሪክ የተነሳ ልጆቼ ብድር ማግኘት አይችሉም ነበርና ወደ ኮሌጅ አልሄዱም።”

“አዝናለሁ።”

“ተመስገን ነው። ይኽችኛዋን እናታቸውን ይወዷታል።”

“እንዴት? ከእሷ በኋላ አግብተሀል?”

“አዎ። ጥሩ ሰው ናት። 12 ዓመታት አብረን ቆየን።”

“ደስ ይላል። በተለይ ልጆች እንጀራ እናታቸውን ሲወዱ ማየቱም ያጽናናል።”

“በጣም። አፍሪካ አሜሪካዊት ናት እሷም። ግን ጀርመን ነው የተወለደችው። ያደገችው ደግሞ ጣልያን። ሆኖም ዓያቶቿ ከሜክሲኮ እና ስፔይን አሉ። ድብልቅልቅ ሲል ሆደ ሰፊነት ይጨምራል መሰለኝ።”

“ኦህ ደስ ይላል።”

“በጣም። ይገርምሀል፥ እኔ ቤተሰብ ውስጥ ስብጥሩ የተለየ ነው። አሜሪካ፣ አፍሪካ፣ ኢስካሞ፣ ፣ ብራዚል፣ ፣ ጀርመን፣ ኢትዮጵያ፣ ማሊ… የተባበሩት መንግስታት በለው” ብሎኝ አብረን ሳቅን።

“ኢትዮጵያዊም ቤተሰብ ካለህ እኔም ዘመድህ ነኝ ማለት ነው” አልኩት እንደጨዋታ።

“እንዴታ፥ የአጎቴ ልጅ ኢትዮጵያዊት በጉዲፈቻ ያሳድጋል።”

“አሃ…ደስ ይላል።”

“በጣም። ዓለም ላይ ካለው ሰላም የተሻለ እኛ ቤተሰብ ውስጥ ሰላም እንዲኖር እንሞክራለን።”

“ጥሩ አድርጋችኋል። ሰዉ ሰው ለመበደል ምክንያት ሲፈልግ ነው የሚመሽ የሚነጋለት።”

“አዎ። ሁሉም ጋ የዘረኝነት እና ሌላውን የመናቅ መንፈስ አለ። ሰው ለምን እንደዚህ እንደሚያደርግ አላውቅም። እናንተ ጋ አንድ ነው ብሄራችሁ?” አለኝ።

“ኧረ ብዙ ነን። 80 ምናምን ነን።” አልኩት። ምናምኗ ሁሌም ታስቀኛለች።

“ሰዉ ስለብሔሩ ብዙም ግድ አልነበረውም። ግፉም በጅምላ ነበር። አሁን ያለው መንግስት የዘውግ ፖለቲካ ስርዓት ነው የሚከተለው። በዚያ የተነሳ መታወቂያ ካርድ ላይ ሳይቀር ከመጻፍ ይጀምራል። በየቦታውም ሰዎች እርስበርሳቸው እንዲጋጩ በማድረግ ለራሳቸው እድሜ ይፈልጋሉ። እኛም ሞኝ ሆነን አጀንዳቸውን እንቀበላቸዋለን።” ብዬ ቀጠልኩ።

“ያው እንደሁሉም አፍሪካ መንግስታት ነው። ያሳዝናል።”

“በጣም”

“ይገርምሃል ባለቤቴ ከሜክሲኮም ትዛመዳለች ብዬህ የለ። እሷ ያለችው ሰሜኑ ክልል ላይ ነው። እዚያ የሀብታም እና የድሀ ስም በሚል ከባድ የሆነ የዘረኝነት ስሜት አለ። ሰዎች ስማቸው የድሀ ስለተባለ ብቻ ለጋብቻ እስከመከልከል ይደርሳሉ።”

“እየቀለድክ መሆን አለበት።”

“እንደዚያ ነው። እኔም በጣም ገርሞኝ ነበር። በጣም ይገርማል።”

“እንዴ በጣም እንጂ። ስም ሊቀየርም ይችላል እኮ። ቢያንስ ደግሞ አዲስ ለሚወለዱት ልጆች የሀብታም የተባለውን ስም በመስጠት ትውልድን ማቅናትም ይቻላል።” አልኩኝ።

“አዪ። እሱንማ አንተ ነህ የምታስበው። ትውልድ ስለማቅናት ቢያስቡ ቀድሞስ በስም ይጣሉ ነበር?”

“እሱስ ልክ ነህ።”

“ደግሞ አለልህ። ፊሊፒን ውስጥ በቁመታቸው ነው ጥቃት የሚፈጽሙት። አጭር ከሆንክ አለቀልህ። ትገለላለህ። ስራ ማግኘት አትችልም፣ ለጋብቻ አይፈቀድልህም፣ ብዙ ነው በደሉ።”

“ኧረ ሰውዬው እየቀለድከኝ ነው የሚሆነው።”

“እውነቴን ነው። ፈላልገህ ልታነብም ትችላለህ። ለማመን የሚከብድ ነው። ግን ያው እንደዚያው ነው። ሰዎች እርስ በርስ ለመበዳደል ሰበብ ነው የሚፈልጉት። በጾታ ለመበዳደል አላመች ሲል፣ በሀይማኖት፣ እሱ ሲያቅት በቆዳ፣ እሱም እምቢ ሲል በቁመትና በስም ሁሉ መበዳደል አለ።”

“በጣም የሚገርም ነገር ነው። ውስብስቦች ነን።”

“በጣም። እኔ በዚህ እድሜዬ የደረስኩበት ነገር ሁሉም ነገር ዝም ብሎ ተራ ሩጫ እንደሆነ ነው። የእኔ ወንድም ልንገርህ አይደል? ዝም ብለህ ኑር። ሕይወት ያሉህን መልካም ነገሮች ለማጣጣምም አጭር ናት። በፍጹም ሌላን ሰው ስለመናቅ አታስብ።” ብሎ ሌላ የሀሳብ መስኮት ከፈተልኝ።

የእሱን ወሬ እና ምክር ይዤ ያለንበትን ሁኔታ ማውጣት ማውረድ ጀመርኩ። ግን ለምን እንደዚህ እንሆናለን? ያሉንን መልካም ነገሮች እንዳንቋደስ ማን አዚም አደረገብን?

እሺ ከዚያ በኋላስ?

‘የአስተማሪ ምግብ…’

ዩኒቨርስቲ አስተምር የነበረ ጊዜ…
 
ከእለታት ባንዱ ቀን ቡና ልጠጣ ወጥቼ ጠረጴዛ የተጋራኋቸው ሁለት ባልደረቦቼ ብስጭትጭት ብለው ሲያወሩ ሰማኋቸው።
 
“ምንድን ነው እሱ?” አልኩኝ ከመቀመጤ።
 
“እንዴት እንዴት እንደጠገቡ እኮ…” አለኝ አንዱ።
 
(በኋላ ግራ ቀኙን ስቃርም የገባኝ ሁሉም በየጠረጴዛው ያወራ የነበረው ይህንኑ ጉዳይ ነበር።)
 
“እነማን ናቸው ደግሞ?”
 
“ሌላ ማን ይሆናል? እነዚህ የተረገሙ ናቸዋ”ብሎ ተማሪዎች ወደሚራመዱበት አቅጣጫ አገጩን ቆለመመው።
 
“ተማሪዎቹ? …ምን ተባለ ደግሞ?” አልኩት እንዲህ መነጋገሪያ የሆነውን ጉዳይ ለመስማት አቆብቁቤ።
 
“እዚህ ላውንጅማ ድርሽ አይሏትም። እንደውም በዲሲፕሊን ኮሚቴ መከሰስ አለባቸው።” አለኝ።
 
“ጋይስ እኛም እኮ መምህራን ነን። እንስማውና አብረን እንቃጠል።” አልኩ።
 
“ምን ባክህ፥ ሁለት ሴቶች ከውስጥ እየወጡ፣ አንዲት ጓደኛቸውን… ‘ተመለሽ ተመለሽ፥ ምግብ አልቋል’ አሏት። ‘ምንም’ ስትል፥ ‘አይ ያለው ለአስተማሪ የሚሆን ብቻ ነው’ አሏት። እንዲሰማ ጮክ ብላ…” አለኝ።
 
አተራረካቸውና አበሰጫጨታቸው ዘና አድርጎኝ ስለነበር፥ “እንግዲህ ተማሪዎች ላውንጅ ሄዶ በልቶ፣ የተማሪን ምግብ የመግዛት አቅም አለን ማለት ነው። በፊት እንኳን፥ አንዱ ጋ ለትምህርት ሲኬድ የፈረደባት ካሪና ተገዝታ “እኔም ተምሬ መጣሁ” አስብላ ታስሸልል ነበር።” ብዬ እንደመሳቅ አልኩ። አልሳቁልኝም። ተናደዋል።
 
እንግዲህ “ለአስተማሪ የሚሆን ለተማሪ የማይሆን” (that teachers can’t afford, but students) የምግብ ዓይነት መኖሩ ነበር እንዲያ ያተከናቸው።
 
ቀን ተቆጥሮ ተማሪዎቹም ተከሰሱ አሉ።
 
“ሁለተኛ እንዳይለመዳችሁ” ተብለው በማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ሳይቆነጠጡም አልቀሩም። ወዲያውም፥ የካፌው በራፍ ላይ “ለተማሪዎች አይፈቀድም” ዓይነት ትኩስ ማስታወቂያ ተለጥፎ ነበር።
 
ይኸው ባለፈው ወር የመምህራን ደመወዝ መጨመሩን ሰምተን
 
“እኛ ማስተማር ስናቆምማ የማይሻሻል ነገር የለም” የሚል ቅናት ባይሸነቁጠንም፥… 🙂
 
መንግስት የሆነ ያህል መቶ ብር “ጨመርኩ” ያለ ጊዜ፥ ከወሬው እኩል፥ የቤት አከራዮቻችን የጨመሩብን ብር ትዝ ብሎኛል። በዚያ ሰሞን ነጋዴዎች እንዴት እንዴት እንደሆኑም አይረሳኝም።
 
እና ጓዶች ጭማሪው ከወጪ ቀሪ እንዴት ነው?
 
ከተማሪ ጋር ያጋፋል?
 
የተማሪን የምግብ ምርጫ ያስቀምሳል?
 
የገቢ ግብር ማሻሻያ አዋጅም ከሀምሌ 1 ጀምሮ በሚገኝ ገቢ ላይ ተፈጻሚ እንዲሆን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባስቸኳይ በጠራው ስብሰባ ላይ አዋጅ አጽድቋል አሉ። ምን አስቸኮላቸው? 🙂
 
በነገራችን ላይ፥ ዜናው ላይ የተዘገበው ከቅጥር እና ከኪራይ ለሚገኙ ገቢዎች ነው። ከንግድ ስለሚገኙ ገቢዎች የተባለ ነገር የለም። የተጨማሪ እሴት ታክሱ እንደው ዞሮ ሸማቹ ላይ የሚጨመር ነውና በተዘዋዋሪ ተቀጣሪውን ነው የሚመለከተው። #Ethiopia
ሰላም!

የወዳጅን ሞት ሰምቼ ስባዝን…

ማኅበራዊ መዋቅራችን አጓጉል ነው። ከደስታ ይልቅ ኀዘንን ለማስታመም ይቀለናል። ከእልልታ ይልቅ ለከንፈር መጠጣ የሚያፈጥነን ይመስላል። በሰው ደስታ ከምንደሰተው ይልቅ፣ ሰዎችን ለተሻለ ፍላጎታቸው ከምንገፋቸው ይልቅ፣ በኀዘናቸው የምንማቅቀው ይበዛል፤ ከፍላጎታቸው ምንገፈትራቸው ይልቃል። በደግ ቀን፥ ስም ስንሰጣጥ፣ ስንፈራረጅ ነው የምንውለው። ደሞ ትንሽ ችግር ሲደቁሰን፥ “ወንድሜ እህቴ” ስንባባልና ስንረባረብ ለጉድ ነው የምናስቀናው።
 
ለምሳሌ፥ አይበለውና እግሬ ቢቆረጥ ሳር ቅጠሉ ያዝናል። ያየ የሰማም ከንፈር መምጠጡ አይቀርም። ደግሞ፥ ይበለውና ዘናጭ መኪና ብገዛ በጣም ጥቂቶች ናቸው የደስታዬ ተካፋይ የሚሆኑት።
 
ከማስታውሰው…
 
ሳልጠይቀው፣ አንድም ቀን… ‘ሞካሪ’ እና ‘የትርፍ ሰዓት ሞንጫሪ’ ነኝ እንጂ፥ አፌን ሞልቼ እንደ ማዕረግ (title) እንኳን ‘ጸሐፊ’ ነኝ የማልልበትን ጉዳይ አንስቶ ሲያንቆለጳጵሰኝ የኖረ ሰው፣ የሆነ ቀን… ከጀርባዬ በመጻፍ ባህርዬ የተነሳ፣ በክፉ በደግ ሲያነሳኝ ከርሞ፣ የሰማሁ ሲመስለው ደግሞ፥ ነገሩም ውኀ እንዲያነሳለት እኔን ማጣጣልና ማንቋሸሽ ተጨማሪ ሥራው ያደርገዋል።
 
“ይሄን ያህል ምን አጠፋሁና ነው? እርሱ ቦታ አልሄድኩ። ሀሳቡን ካፉ ነጥቄው አልጻፍኩበት። መጻፍ እንደው ክህሎት (skill) ነውና፥ ፍላጎቱ እና የተወሰነ ተሰጥኦው ካለ ያድጋል። ደግሞ ባይሆንስ፥ እኔ ሀሳቤን ብገልጽና ያመንኩበትን ብናገር ኑሮውን አላዘባርቅበት። “በርታ…ይሄን ደግሞ እንዲህ አሻሽለው” ቢል ምናለ?” ምናምን እያልኩ ከራሴ ጋር አወራ እና እተወዋለሁ።
 
እሱ አይተወውም።
 
ሌላ ላስታውስ…
 
ስለ ሥራ ማጣት እየተወራ ነው። እኔም ሥራ ፍለጋ ላይ ነበርኩ። የደረሰባችሁና የደረሰላችሁ እንደምታውቁት፥ አብዛኛው ሥራ በዝምድና እና በፖለቲካ አቋም ሁኔታ ነው የሚወሰነው።
 
ከወዳጆቼ ጋር ሰብሰብ ብለን፥ እኔም የራሴን ልምድ ተናገርኩ። “ለስንትና ስንት ጊዜ የሥራ ማመልከቻ ባስገባም፥ ማንም ጠርቶኝ አያውቅም። ግን…” አልኩ። ሲስተሙንም መኮነኔ እና ምሬቴን መግለጼም ጭምር እንጂ፥ በዋናነት ስለራሴ ማውራቴ፣ ወይም የሚታዘንልኝን ናፍቄም አልነበረም።
 
“ግን” ያልኩበትን አፍም ሳልሰበስብ፥ “ኦህ… እንደዛ ነው እኮ። ምን ታረገዋለህ?” ምናምን ተባለ። ወዲያውም “ወዳጄ” የምለው ሰው፣ ለኪነጥበቡ ቅርብ የሆነ (እንደመፍትሄም ጭምር መሆኑ ነው) “ግን ለምን ጽሁፉን seriously አትወስደውም። የሙሉ ጊዜ ጸሐፊ ብትሆን ነው ሁሌ የማስበው። በእጅ ያለ ወርቅ አታርገው። እንግሊዘኛም ጥሩ ነህ። You know, እንደዛ ቢሆን እኮ…”
 
እንደማላደርገው ስለማውቅ፥ “ኧረ እኔ እኮ ለሙሉ ጸሐፊነት የሚያበቃ አቅሙ የለኝም። ጭራሽ እንግሊዘኛ።” ምናምን ብዬ ላሽ አልኩት።
 
የእርሱን ምክር ጋብ አድርጌ፥ “ግን ተመስገን ነው! እስካሁን የምሰራው አላጣሁም። በራሴው ጥረት ተነጋግሬ እና ተደራድሬ በተሻለ ደመወዝ ነው የምሰራው። እኔው ነኝ እንዲቀጥሩኝ የማግባባው። ነገሩ ይገርማል እንጂ ምንም አላጣሁ።” ስል፥
 
“እስኪ ስለራስህ ሌላ ሰው ያውራ።” ብሎ ኩም ሊያረገኝ ይሞክራል። (በጣም ግልጽ ከሆነ ነው ይሄ።) ካልሆነ ደግሞ፥ “ኡፍ እሱ ደግሞ ጉራው መከራ” ምናምን ተብዬ ጫት ማባያ እና ቡና ማጣጫ እሆናለሁ።
 
“ቆይ ግን እኔው ራሴ ስለተንከራተትኩትና ስላወጣሁት ጥረት ማን ነው ማውራት ያለበት? ራሴን ሸጬ ሳበቃ አሻሻጤን በተመለከተ ልምድ ቢቀስምስ እርሱ ነገ የኔን መንገድ ተከትሎ በተሻለ ዋጋ ለተሻለ ቦታ ራሱን ይሸጥም አልነበር? እሱም ቢቀር ስለሆነልኝ ባመሰግንስ ምን አለ? ወይስ ወዳድቄ ሥራ ፈትቼ ብኖር ደስ ይለው ነበር? ስንገርም” ብዬ ተውኩት።
 
ኖርን ኖርንና… በራሴ ገንዘብ፣ በራሴ ትርፍ ጊዜ የጫርኳቸውን ሰብስቤ መጽሐፍ ማሳተሜን ተከትሎ፥ “ኑ ጸበል ቅመሱ” ብዬ የምረቃ ድግስ መጥራቴ ሲወራ፥
 
“አበደ ፈረሴ” አለ። ከጀርባዬ ዘለዘለኝ። ሚስቱን እንደቀማሁበት ሁሉ ጉዳዩ እኔው ሆንኩኝ። አንዳች አገራዊ ጉዳይ እንደተስተጓጎለ ሁሉ በየሄደበት፣ በየወዳጆቻችን ፊት አማኝ። የአጻጻፌን አስጸያፊነትና የባህርዬን መጥፎነት አተተ። አልሰማሁትም እንጂ፥ ወላ “ይቅርብህ” ሊለኝም ዳዳው። …እንግዲህ በትርፍ ሰዓት የሞከርኩትን የማያደንቅ “ወዳጄ” ነው “የሙሉ ሰዓት ጸሐፊ ሁን” ሲለኝ የነበረው።
 
“ምነው ይሄን ያህል፥ ግፋ ቢል ያለመነበብ እጣ ፈንታ ቢገጥመኝ፣ ወይ ደግሞ ጥሩ መጽሐፍ እንዴት እንደማይጻፍ መማሪያ ብሆን ነው እንጂ… የአገር ሀብት መዝብሬ አላሳተምኩ። እሱ ግን ብዋረድ ብቻ ነው ሚደሰተው?” ብዬ ሥራዬን ቀጠልኩ።
 
ፕሮግራሙ ያማረ ሲሆንም፥ እንዲህ ሆነ።
 
ተነቦ ገንቢ feedback ሳገኝም፥እንዲህ ሆነ።
 
አያርገውና፥ “ተበድሬ አሳትሜው ነበር። እና ሙሉ ለሙሉ ከሰርኩኝና የሰው ገንዘብ እንዴት እንደምመልስ ቸገረኝ።” ብለው ኖሮ፥ እርግጠኛ ነኝ “እናዋጣለት” ባይልም ገንዘቡን መልሼ የማገኝበትን መንገድ ለመጠቆም ይሞክር ነበር።
 
‘እንዲህ ያለውን ነገር ብናሻሽል የተሻለ እንኖርና ኀዘናችንም ይቀል ነበር’ እላለሁ።
 
====
 
አቡኪ ሞት ሰቅጥጦኝ ስባዝን ነው ‘randomly’ ይሄን ይሄን የማስበው።
ብልጭ ድርግም አለ። በወጣትነቱ ሄደ። ሞት አዲስ ሆኖ በመጣ ቁጥር ቢያስደነግጥም፥ ነገም እንዲሁ ነን እኛ።
ነፍሱን በአጸደ ገነት ያኑራት!
13342971_646994268791366_2197683848191752176_n
ልበ ቀናው ወዳጃችን ይህ ነበር። 😥 

ወይ ጉድ…

ከዓመት ከምናምን በፊት…
 
“አብሬያቸው ብሰራ” ከምላቸው፣ ጥሩ ስሜት ካሉኝ መሥሪያ ቤቶች መካከል በአንዱ የሥራ ማስታወቂያ መውጣቱን ጋዜጣ ላይ ተመልክቼ ለማመልከት አሰብኩና የትምህርት እና የሥራ ማስረጃዎቼን አደራጅቼ ሄድኩ። (መቼም አብዛኛው ቅጥር በፖለቲካ አቋም፣ በትውውቅና በዝምድና እንደሆነ ባላጣውም፥ በምናልባት ነበር ሙከራው።)
 
ከወጡት ሶስት የሥራ መደቦች እኔ ለማመልከት የፈለግኩት “managing director” ይል የነበረውን የሥራ መደብ ነበር። (ቀሪዎቹ ሁለቱ Data Encoder እና Secretary ነበሩ።) መስፈርቱን በበቂ ሁኔታ ስለማሟላ “ለቃለ መጠይቅ ፈተና ቢጠሩኝ እንኳን…” የሚል ጉጉት ነበረኝ።
 
ቢሮው ደረስኩኝና የሰው ሀብት አስተዳደሯን (መሰለችኝ) “ጤና ይስጥልኝ፣ የሥራ ማስታወቂያ አይቼ ለማመልከት ነበር።” አልኳት።
 
“Data encoder ነው?” አለችኝ። (ሶስተኛው መደብ ‘secretary’ ስለነበረ ሴቶችን ብቻ መጠበቋም አብሽቆኝ ነበር።)
 
“አይ ለማኔጂንግ ዳይሬክተር መደብ ነው።” አልኳት።
 
ገለማመጠችኝ አይገልጸውም።
 
“ማስታወቂያውን በደንብ አይተኸዋል? መስፈርቱ ብዙ ነው።” አለችኝ።
 
“አዎ! ስለማሟላ ነው የመጣሁት። ዶክመንቶቼን ይዣቸዋለሁ።” አልኳት።
 
“ማስተርስ ዲግሪ ነው የሚጠይቀው።” አለች።
 
“Sure, አለኝ” አልኩ።
 
“በአስተዳደር መደብ የሰራም ይላል…” አለች
 
“አዎ ሰርቻለሁ። እንደውም አሁን የምሰራውም በአስተዳደር መደብ ነው።”
 
አልተዋጠላትም። ዶክመንቶቼን እየተቀበለችኝ፣ “ብዙ ሰው አመልክቷል። ባትደክም ግን ጥሩ ነበር” ብላ አጉተመተመች። ማኅተሞቹን አፍጥጣ መመርመር ያዘች።
 
“ቆይ ግን ምን ዓይነት ሰው ጠብቀሽ ነበር?… ለማኔጂንግ ዳይሬክተርነት የሚያመለክተው ሰው እንዴት መሆን አለበት ብለሽ ነው?” አልኳት።
 
መልስም አልሰጠችኝም።
 
ተናድጄ ቀጠልኩ። “ሁኔታሽ ደስ አይልም። ብቀጠር እኮ ምናልባት አለቃሽ ነው የምሆነው።” አልኩ።
 
እርሷ እቴ ምንም አልመሰላት። (በልቧ “ኡኡቴ” ሳትልም አይቀር)
 
‘ስወጣ የቅርጫት ሲሳይ ታደርገዋለች።’ ብዬ ባስብም የተቀበለቻቸውን ዶክመንቶች ዝርዝር መመዝገቢያዋ ላይ መዘገበችኝ እና ፈረምኩ።
 
“ሳስበው ስራውን ብዙም አልፈልገውም። ለፈተና መጠራቴን ግን እፈልገዋለሁና ዶክመንቴ ቅጥር ኮሚቴው እጅ መድረስ አለመድረሱን እከታተላለሁ። ደህና ይዋሉ።” ብያት ሄድኩኝ።
 
* * *
 
ከወራት በፊት ደግሞ…
 
ለአንድ የአደራ መልእክት… የቤትና የቢሮ እቃዎች ሱቅ ሳይ፥ ተልኬ የነበረውን መግዛት የነበረብኝ እቃ ትዝ ብሎኝ ገባሁና ዞር ዞር ብዬ አይቼ፥
 
“ይሄ ስንት ነው?” አልኳት።
 
“ለቤት ነው የሚሆነው” አለችኝ።
 
በልቤ “ሆ” ብዬ… “አዎ እኔም ለቤት ነው የፈለግኩት።”
 
“ማለቴ ለመኖሪያ…”
 
“አዎ እኮ ለመኖሪያ። ቤት ያለውና የሌለው በድምጽ ይለያል እንዴ?” እንደጨዋታ ነበር ያሰብኩትና ያልኩት።
 
የተጋነነ ብር ነግራኝ… አያይዛ፥ “ግን ከዚህ ወረድ ብሎ አንድ ቤት አለ። ጠይቀሃል እዛ። ይረክስልሃል።” ብላኝ እርፍ።
 
* * *
 
በዚህ ሰሞን…
 
የሰው አገር ጠብ እርግፍ ሲታይ ደግሞ፥ የሚገዛውን እና የማይገዛውን፣ የሚመጥነውን እና የማይመጥነውን ሰው በዐይን አይተው የሚለዩት የአገሬ ልጆች በዐይኔ ዞሩ። የአገር እና የአገር ልጅ ነገር እንደው ባሰቡት ቁጥር ግርም ይላል፤ …ይኼ ይኼም እንደ ደህና ቁምነገር ይናፍቃል!
 
አልኩኝም… ወይ ጉድ!!!