ግን ምን ያጣድፈናል?

አንዳንዴ ነፍሴ ሽማግሌ ነገር ትሆንብኛለች። በዚህም ራሴን እታዘበውና ብቻዬን እስቃለሁ። በቀላሉ ሊማርከው ይችላል፣. . . አጓጉቶት ይመርጠዋል. . . ተብሎ የሚታሰብ ነገር ልክ ደጃፌ ሲደርስ ራሱን በዜሮ ያባዛል — አንዳንድ ጊዜ በልማድ (tradition). . . — አንዳንዴ ደግሞ እንዲያው በደመነፍስ (instintct)። ጎጂ ያልሆነ ልማድ ካለምንም አሳማኝ ነገር ሊቀየር ሲል (ወይም ሲቀየር) ይደብረኛል፤. . . ደመነፍሴን ደግሞ ህይወቴ ላይ እንዲወስንልኝ ፊትና እድል ባልሰጠውም በደንብ አምነዋለሁ። ችላ ስለውም በሙሉ ልቤ አይደለም።

ዘመናዊ እውቀትና የኑሮ ወከባ፣ እንዲሁም ትእቢትና ትምክህት ባይጋርዱንብ ኖሮ ደመነፍስ የሚነግረን ብዙ ነገር እንዳለ አስባለሁ። አንዳንዴም ደመነፍሳችን ጮሆብን. . . ሳንሰማው ቀርተን፣ የጠረጠርነው (ግን ደግሞ ችላ ያልነው) ነገር ሲደርስ — ‘ውይ! ታውቆኝ ነበረ. . . ፊቴ ላይ ነበር. . . እያሰብኩት. . .’ ምናምን ብለን የፀፀት ሀረጋትን እንደረድራለን። የራሳችንን ማሰላሰልና ማወቅ በማይጠይቁ ነገሮች ላይ ግን ደመነፍስን ማዳመጥ ሊያተርፍ የሚችል ነገር ይመስለኛል። በርግጥ የሚያከስርበት ጊዜ ሊኖርም ይችላል። – ማን አይቶት፥ ማን እቅጩን ያውቃል?

በአዲስ መስመር ወደ ጥድፊያው ስንመለስ ደግሞ . . . ቦታ ቀይሮ ፈታ ለማለት ረዥም መንገድ 801589መሄድ በጣም ያስደስተኛል። የጉዞ ጣጣዬን ቶሎ ጨርሼ፣ ካሰብኩበት ቦታ በጊዜ መድረሱንና እንዳሰብኩት መዝናናቱን ባልጠላውም፣ የመንገዱ መርዘምና መጎተት ብዙም አያስጠላኝም። ወይ ደግሞ ለምጄው ተስማምቶኛል። እንደውም ደስ ይለኛል። እንደ ጥሩ ትርፍ. . . ከመኪና መንቀራፈፍ ጋር በተያያዘ መንገድ ላይ የማንበብ ልምድ አዳብሬያለሁ። ብዙ ጊዜም መሄዴን ሳላውቀው ነው የምደርሰው።

በፍፁም ትኩረት፣ ርጋታና አለመሰልቸት ውስጥ ሆኜ ካነበብኩባቸው ቦታዎች መካከል የክ/አገር አውቶቢሶች ዋናዎቹ ናቸው። የምሄደው በአዲስ መንገድ ከሆነ ደግሞ በመስኮት በክል ግራ ቀኙን እያየሁ ተፈጥሮን አደንቃለሁ። በሀሳብ እነጉዳለሁ። ምናምን ምናምን . . . ካለምርጫና ካለማቋረጥ ማንበብ መቻሉ ቀድሞም ለነበረኝ የጉዞ ፍቅር ተጨማሪ ቅመም ሆኖልኛል። ስለሆነም ረጅም መንገድ ስጓዝ እንደ ሚኒባስ ያሉ ፈጣን የሚባሉ የትራንስፖርት አማራጮችን ለመጠቀም አላስብም።

አያዝናኑኝም። መፅሀፍት አያስገልጡኝም። ፊት ለፊቱን እንጂ ግራ ቀኙን በመስኮት እንዳይminibus-accident1 እድል አይሰጡኝም። ነፍሴን ካለአግባብ ያዋክቧታል። በጭንቀትና በስጋት ወጥረው ካለ ቅጥ ያርገበግቧታል። ያንገበግቧታል። መጨረሻዋ ለማይታወቅ እርሷ. . . መጨረሻዋን ለቅፅበት ያሳይዋታል። በፈጣሪ ስልጣን ገብተው፥ ወስደው ይመልሷታል። ካለልቧ ዥዋዥዌ ያጫውቷታል። ከዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ የብዙ ነፍሳት መጨረሻ በሚኒባስ ሲወሰን ተመልክቻለሁ። ‘ኧከሌ/ኧከሊት. . .’ ብዬ በስምና በግብር በቅርብ የማውቃቸው ሰዎች በሚኒባስ ተሰናብተዋል። ቅዳሜ ለመገናኘት ቀጠሮ የነበረኝ ሰው በዋዜማው አርብ በሚኒባስ ተፈፅሞ በጣም አዝኜ አውቃለሁ። በየቦታውም ብዙ ዓይነት ታሪክ አለ። ብዙ ሰው እንደወጣ መንገድ ላይ ቀርቷል። ቶሎ ለመድረስ ሲጣደፍ በአጣዳፊው ተሰናብቷል። – በሚኒባስ!

ብቻ ግን ረጅም መንገድ በሚኒባስ መጓዝ አልፈልግም። አልጓዝም። ከሚኒባስ ውጭ አማራጭ መጓጓዣ በማይገኝበት ቦታ ካልሆነ በቀር አማራጭም አላደርገውም። ይልቁንስ በጣም ትልቁን አውቶብስ ነው የምመርጠው። ጉዞው በህብረት ከሌሎች ወዳጆች ጋር በሚሆንበት ጊዜ ወይ ደግሞ ስለአካሄዴ ተናግሬ ሚኒባስ እንድጠቀም ሲያግባቡኝ አልሰማቸውም። እሞግታቸዋለሁ። ሲስማሙ – አብረን እየተጫወትን በትልቋ እንሄዳለን። ላይ ወርጄ ታች ወጥቼ በሀሳቤ አልስማማ ሲሉኝ ደግሞ እነሱም – በፈጣኗ፤ እኔም – በተምዘግዛጊዋ እንለያያለን። – ሰላም ከደረስን ለመገናኘት ተቀጣጥረን።

የምቀርበው ሰው መንገድ እንደሚሄድ ሳውቅም፥ የወጪ ስንቄ – ‘በናትህ/ሽ በሚኒባስ ethiopian-busrides09እንዳትሄድ/ጂ’ የምትል የጭንቀት ሀረግ ናት። ብዙዎች ይገርማቸዋል። ‘ነፍስህን አንተ ተብቀሃት አይሆንም። በትልቅ መኪናም ሄደህ አደጋ ካለ አይቀርልህም። ከቀንህ አታልፍም’ ምናምን ምናምን. . .። አይገባኝም። የእኔ ሃሳብ አደጋ ማስቀረት ሳይሆን አለመሳቀቅ ነው። ሞትማ ምናባቱ! በጉርሻ ትንታም ሲቀራርብ አይተን እናውቃለን። ቀኑ በተመደበበት ህይወት ነው የምመላለሰው ብዬ ግን አላስብም።

ረጅም ርቀት በሚኒባስ በተጓዝኩባቸው አምስት በማይሞሉ ጊዜያት ውስጥ ሳስታውሰው (አንዳንዴም በጉዞው መሀል) እስቅበት ዘንድ ራሴን የታዘብኩበት ነገር አለ። መኪናው ፍጥነቱን ሲጨምር መንፈሳዊነቴ ይጨምራል። አላግባብ ፀሎተኛ እሆናለሁ። ነጠላ ማንጠላፋትና የፀሎት መዝገብ መግለጥ ያምረኛል። (ያልያዝኩትን) የማውቀውን ፀሎት ሁሉ እደረድራለሁ። በተማፅኖ እቀባጥራለሁ። “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝና ወራት ፈጣሪህን አስብ።” (መፅሀፈ መክብብ 12፥1) የምትለዋ ትምህርት ነገርም ይበልጥ ይገለጥልኛል። በዚያም እስቃለሁ። በሰቀቀን። – እያነቡ እስክስታ!

ከዚህ በፊት ‘ሰላም መጣችሁ እንጂ ቶሎ መጣችሁ የሚለን የለምና ቀስ ብለን እንንዳ።’ የምትል የረሳኋትን ምንጭ ጠቅሶ የፃፋት መልእክት አንድ ወዳጄ ፅፏት አንብቤ ልቤ ሰርፃ ነበር። እናም ዛሬ ልደግማት ወደድኩ። — ‘ሰላም መጣችሁ እንጂ ቶሎ መጣችሁ የሚለን የለ’! ምን ያጣድፈናል? ታላቅ ወንድሜ ደግሞ ‘በአላስፈላጊ ጥድፊያ ውስጥ ሆነንና ቶሎ ለመድረስ ፍጥነት ጨምረን ተጉዘን የምናተርፋቸው ጊዜያት ተመዝግበው ቢደመሩ በዓመት አንድ ቀንም አይሞሉም። በዓመት አንድ ቀን ላላተርፍ አልሯሯጥም።’ ይላል።

ገበያን የሚያሰፋው የተጠቃሚ ፍላጎት ሁኔታ ነውና ተረጋግተን ሄደን በሰላም ለመግባት (ለመድረስ) በመፈለግ አደጋን እንቀንስ። ለፍላጎታችን የሚሆነውን መኪና መምረጥ ስንጀምር መጓጓዣዎቹ ፍላጎታችንን ለማርካትና ገበያ ለማግኘት በምንፈልገው መስመር ይገቡልናል። ‘እንደወጣ ቀረ’ ከመባል ያድነን።

የልደት ወግ: 125 vs. . .

አንተዬ በማለዳው ልቤን አንድ ነገር ቢያስጨንቀው ጊዜ፥ ልጠይቅህ ረፋዱ ላይ ብቅ አልኩኝ። እንዲያው የትናንት የልደት ሻማ ገበያ እንዴት አዋለህ? — ድካሙ? ዋጋው?… ‘እድሜ ሲገፋ ከኬኩ ዋጋ ይልቅ የሻማው ዋጋ ነው የሚወደደው’ ምናምን የሚባል ወሬ ሰምቼ እኮ. . . “ወይኔ ወንድሜን እንዴት ሆኖ ይሆን?” ብዬ ስጨነቅ ነው ያደርኩት። እንዴት አረገህ ባ’ያሌው? አዪዪ. . . የኬኩን ነገርማ ትናንት ጨረስነው እኮ። ቢረክስስ በምን ጥርስ ሊበላ?– ጥርስ ድሮ ቀርቶ! –አያ!. . . እድሜ በልቶት! ሀሀሀ. . .

እድሜው ለገፋበትና እርጅና ለተጫነውስ፥ ሻማው ሲረክስ ነበረ ጥሩ፤ እንዲያ ሲሆን የደከመ እይታንም ያግዛል ምናምን ይላሉ። መቼስ የእኛ ነገር በ‘ይላሉ’ ነው።. . . እንጂማ ምኑን አይተነው? ምኑን አውቀነው?. . . ብለህ?! — ስታየን! ሰታውቀው!… ኸረ ገና ብላቴኖች ነን!…ብቻ ግን ሻማው ቢረክስ ከሞት ወዲያ ሌጋሲውን አጠናክሮ ለማስቀጠልም ጠቃሚ ግብአት የሚሆንይመስለኛል። ህልምና ራዕይስ ቢሆን በሻማ ይበልጥ ደምቆ ይታይ የለ?!…መሰለኝ! ሁሁሁ. . .

ዝም ብዬ ሳስበውግን. . .“ኧከሌ. . . ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል በፀሀይና በሻማ ሲሰራ ኖሮ”…ምናምን ተብሎ፥ በሻማ የመድመቅ ታሪኩ ታክሎ ወሬ ቢጀመር ሌላ ነው የሚሆነው። ስንቱን ሰምተህ የለህ… ‘እንትን ተደግፎ መፅሀፍ ሲያነብ… ኖሮ… ኖሮ… ሞተ’ ተብሎ ገድሉ ሲወራ…. ሌላው ቀርቶ ሻማና ምግባሩን መዝዘን እንኳን. . . “እንደ ሻማ ቀልጦ” ብለን ጨዋታ ብንጀምር የስንቱን አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪ ጆሮ እንስበው ይሆን? አዪ. . . አዲስ አበባ ስል ደግሞ ልደቷ ብልጭ አይልብኝ መሰለህ?! – (ነገርን ነገርም አይደል የሚያነሳው?) ሙት! ከሆኑስ አይቀር ከተማ መሆን ነው ኧረ። ሂሂሂ. . .
ከዚያም ልደትን ዓመት ሙሉ ማስከበር። በዘልማዳዊ ዘይቤም ይባላልሀል — “የወዳጃችንን ልደት ለየት የሚያደርገው ከአዲስ አበባ ልደት ጋር አብሮ መዋሉ ነው።”. . . ልክ “የዘንድሮውን አዲስ ዓመት ለየት የሚያደርገው ከሚሊንየሙ ጋር አብሮ በመዋሉ ነው።” እንዳሉት. . . ሃሃሃ. . . ውይ አዲስ አበባ፣ ውይ አራዳ ሆይ… (ወይ አላልንም ልብ አርግ!) እንዲያው ጭርጭስ ብላ፣ በአልሞትባይነት ስትታገል – ስታታግል፣ ስታስወጣ – ስታስገባ፣ ስትወድቅ – ስትነሳ፣ ስትጥል – ስታነሳ፣ ስትፈርስ – ስትገነባ. . . 125 ዓመቷን ደፈነች። አይዞን አንተም እኮ ደርሰህባታል፣ ብዙም አልቀረህ! ሃሃሃ. . .

እንዴት መታደል ነው ግን አንተዬ?… 125 ዓመት ሙሉ በግንባታ ላይ።125 ሙሉ መቀባባት። 125 ዓመት ሙሉ መኳኳል። 125 ዓመት ሙሉ መጊያጊያጥ። 125 ዓመት ሙሉ መሽሞንሞን፡፡ 125! — ግን እንዲያው በብላሽ! – አንዴም ሳያምርባት! በስሜት “ኧረ እሷን ባረገኝ’ እልና. . . ደግሞ ወዲያው ታሳዝነኛለች። ስታገባ፣ ስትፈታ በወጉ ለደህና ባል ሳትዳር እድሜዋ እብስ ማለቱ ፊቴ ይደቀንና አንጀቴን ትበላዋለች። ውይ ወላጅ እናቷ ጣይቱና አባቷ ምንሊክ የዛሬን ባላይዋት። መቼስ ከሄዱበት መንገድ መመለስ ቢፈቀድ “ውይ እንዳስቀመጥናት” ምናምን ሳይሉ ይቀሩ ብለህ? ኧረ ወዲያ ህንፃው መች ሆነና ቁምነገሩ?!… የእኔ መኳንንት – በዓሉ እኮ ሁሉን ጨርሶታል —-

ከጎራው ዘልቄ እስኪ ልነጋገር፣
ያለሰው ቢወዱት ምን ያደርጋል አገር፣
ህንፃው መች ሆነና የድንጋይ ክምር፣
መንገድ መች ሆነና የድንጋይ አጥር፣
ህንፃው ምን ቢረዝም ምን ቢፀዳ ቤቱ፣
መንገዱ ቢሰፋ ቢንጣለል አስፓልቱ፣
ሰው ሰው ካልሸተተ ምንድነው ውበቱ
የኔ ውብ ከተማ የኔ ውብ አገር፣
የሰው ለጅ ልብ ነው. . .
. . . የሌለው ዳርቻ፣ የሌለው ድንበር፡፡
/በዓሉ ግርማ/

ብቻ እልሃለሁ 125 ዓመቷን ፉት አድርጋ ለማክበር ደፋ ቀና ስትል፥ የኬኩን ጉዳይ በአንድ አንድ ድፎ ዳቦ ስትሸውደው የሻማው ነገር ግን ኪሷን ሲንጠው ነበር የከረመው አሉ።125 ሻማዎች? ዓመቱን ሙሉ –እግዚአብሄር ያሳይህ… በዚያ ላይ በየቦታው ነው የሚበራው።እኔስ ቀድሞ ያሰብኩት. . . ዓመቱን ሙሉ ከተማዋ ላይ መብራት በማብራት (የኤሌክትሪክ አገልግሎት ባለማቋረጥ)፣ ኗሪዎቿን በሙሉም ዓመቱን ሙሉ ኬኩ ቀርቶ ሽልጦ በማብላት ይከበርላታል ብዬ ነበር። አይጠብቁትን ነገር ጠብቄ ተገረምክብኝ? ውይ እሱስ. . . የማይሆን ጠይቆ ሲቀርስ ድርብ በደል ነው። ይሁና . . .

ትዝ ትልህ ዬል ባለፈው በጨዋታ. . . ‘ሄዋን ገጣሚ’ ምናምን ብለን የጫርናት? አዳምሄዋን፣ ያው በለው! ጠይቆ መከልከሉ ነው ጉዳዩ. . .

ዋ… ሄዋን መበደሏ፣ ሄዋን መታለሏ፣
የማይሆን ጠይቃ፣ አልችልም መባሏ፣
የማይችል ጠይቃ፣ አይሆንም መባሏ፣
ስድ ፅሁፍ ሆኖባት ሰንካለው እድሏ፣
ገጣ ስትፈልግ፣ ፍቺኝ ሲላት ባሏ፣

/ዮሐንስ ሞላ/

ውይ ሳልነግርህ?! ባለፈው ከወደ መርካቶ ምናለሽ ተራ እሳት ተነስቶ ወደ 40 ሱቆችን ቢያወድም ጊዜ የአካባቢው ቧልተኞች. . . ‘ለሸገሪና የሚለኮሱ አሮጌ ሻማዎች ስለሌሉን 125 ቤቶችን ለማቃጠል እቅድ ይዘን ገና 40 ገደማው ከመቃጠሉ የከተማዋ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከል ሰራተኞች እንደ አሞራ መጥተው እሳቱን ተቆጣጥረው፣ ራዕያችንን አደናቀፉት’ ብለው ሲያስቁን ነበር።’ አሮጌ ተራም አይደል? ነገር ካላረጀ አገልግሎት ላይ አይውልም። ታዲያ ማን አሮጌ ሻማ አውጥቶ ይሸጥ ብለህ? – ማንም ካልሸጠስ፣ ማን ሊገዛ? የመብራቱ ብልጭ ድርግም መላ ካላገኘ ግን በቅርቡ ቆራሊያዎች — ‘ቆራሌዮ… አሮጌ ሻማ አሌዮ…’ ይሉ ይሆን?! ህህህ. . .

እውነት ግን. . . ይሄኔ ለሌላ ነገር (ለሌላ ዓላማ) ቢሆን እኮ የተቃጠለው ከርመው ነበር የሚመጡት። –ተዘንቦ! ተባርቆ! ነፋስ መጥቶ አመዱን ቡን ማድረግ ሲጀምር! ምቀኞች. . . ምናል ለእናት አዲስ አበባ ክብር እንኳን 125 ሺ ቤት ቢቃጠል? ደግሞ ለሚፈርሱ ቤቶች፤ ተቃጥለው እሳቱን መሞቅ ሳያተርፍ ይቀር ነበር ብለህ? ሄሄሄ. . . አንተዬ ‘ድንገተኛ አደጋ’ ስል ደግሞ እንትን ትዝ አይለኝ መሰለህ ‘አዲስ አበባ እኮ በዚህ እድሜዋ የግሏ መኪና ማንሻ – ክሬን – የላትም’ አሉ። አይገርምም?. . . (አይኔን ‘ባላየሁም’ ስብር አድርጌያለሁ፡፡)

ውይ ሳልነግርህ?! ባለፈው ከወደ መርካቶ ምናለሽ ተራ እሳት ተነስቶ ወደ 40 ሱቆችን ቢያወድም ጊዜ የአካባቢው ቧልተኞች. . . ‘ለሸገሪና የሚለኮሱ አሮጌ ሻማዎች ስለሌሉን 125 ቤቶችን ለማቃጠል እቅድ ይዘን ገና 40 ገደማው ከመቃጠሉ የከተማዋ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከል ሰራተኞች እንደ አሞራ መጥተው እሳቱን ተቆጣጥረው፣ ራዕያችንን አደናቀፉት’ ብለው ሲያስቁን ነበር።’ አሮጌ ተራም አይደል? ነገር ካላረጀ አገልግሎት ላይ አይውልም። ታዲያ ማን አሮጌ ሻማ አውጥቶ ይሸጥ ብለህ? – ማንም ካልሸጠስ፣ ማን ሊገዛ? የመብራቱ ብልጭ ድርግም መላ ካላገኘ ግን በቅርቡ ቆራሊያዎች — ‘ቆራሌዮ… አሮጌ ሻማ አሌዮ…’ ይሉ ይሆን?! ህህህ. . .

እውነት ግን. . . ይሄኔ ለሌላ ነገር (ለሌላ ዓላማ) ቢሆን እኮ የተቃጠለው ከርመው ነበር የሚመጡት። –ተዘንቦ! ተባርቆ! ነፋስ መጥቶ አመዱን ቡን ማድረግ ሲጀምር! ምቀኞች. . . ምናል ለእናት አዲስ አበባ ክብር እንኳን 125 ሺ ቤት ቢቃጠል? ደግሞ ለሚፈርሱ ቤቶች፤ ተቃጥለው እሳቱን መሞቅ ሳያተርፍ ይቀር ነበር ብለህ? ሄሄሄ. . . አንተዬ ‘ድንገተኛ አደጋ’ ስል ደግሞ እንትን ትዝ አይለኝ መሰለህ ‘አዲስ አበባ እኮ በዚህ እድሜዋ የግሏ መኪና ማንሻ – ክሬን – የላትም’ አሉ። አይገርምም?. . . (አይኔን ‘ባላየሁም’ ስብር አድርጌያለሁ፡፡)

ግን ምናለ ከገቢያችን ቢቀር፣ ጠግበን ሳንበላ… ከጎረስናት፣ ካየናት ሁሉ 15 መቶኛውን ‘ተጨማሪ ጃዝገለመሌ ግብር’ ብለው ሲሰበስቡ እንዲህ የሚያስፈልጋትን ነገር ቢገዙላት? ለአንድ ከተማ የድንገተኛ አደጋ መከላከያ መኪና የላትም ማለት እኮ አንዲት የደረሰች ልጃገረድ ግልገል ሱሪ የላትም እንደማለት ነው፡፡ ይሄ ቢቀር እንኳን. . . በአንድ ጊዜ ሁለት ሶስት ቦታ እሳት ቢነሳ በተራ በተራ ነው የሚያጠፉት። በጥቂት መኪናዎች የአደጋ መከላከል ድርጅት አቋቁመው የጉድ ቀን ሲመጣ. . . ‘ቆይ የያዝኩትን ጨርሼ መጣሁ ቢሉህ ምን ይሰማ ይሆን?’ በዚያ ላይ መንገዶቹ ሁሉ በልማት ሰበብ ተቆፋፍረው መኪናስ እንዴት ሊገባ? ብቅ ብለው ሲመሱም አይተናል። ብቻ ግን የሸገር ሰው ‘ተለያየ’ ሲሉት በእንዲህ ያለ ጊዜ ህብረቱ ያስቀናል። በምራቅና በእንባውም ያጠፋዋል። – እግዚአብሔር ይጠብቅ እንጂ!

የቆሻሻውን ነገርስ አለማንሳት ነው የሚሻለው። ሰዉ በማህበር – በጥቃቅንና አነስተኛ – ተደራጅቶ በየቅያሱ የሚሸና እና ቆሻሻ የሚጥል ነው እኮ የሚመስልህ። እንዲያውም ባለፈው ጎጃም በረንዳ ዋናው አስፓልት ላይ 10 ጎረምሶች በአንድ ቱቦ አፍ ላይ ሲሸኑ አይቼ ጉድ ነው ያልኩት። ኸረ እንዲያውም ሽንቴን አስመጡት፡፡ እንክት 10! ቆጥሬያቸው ነበር ስልህ። የሰዉን ሁኔታ ስታየው ሽንት ቤት ሆነው ሽንታቸው ቢመጣባቸው ራሱ ውጪ ወጥተው የሚሸኑ ነው የሚመስልህ። በየመንገዱ እንደዚያ ነው። ሰዉ ቆሻሻ የትም ይጥላል። መንገዱ ሁሉ ይሸታል።– 13 months of sunshine እንዲሉ 13 months of ጉንፋን! ያሰኝሀል፡፡ ቅቅቅ. . .

ሽታው ሲያማርረኝ ምነው የአፍሪካ ህብረት ስብሰባ በጠራና መንግስታቱ አዲስ አበባ መጥተው ባንቀላፉ ነው የሚያሰኘኝ። ፓ ያኔ እኮ አስባፓልት ሳይቀር ይታጠባል። ኧረ ምን እሱ ብቻ? የጎዳና ተዳዳሪም ይደበቃል። — ሰው እንደ ቆሻሻ። ኧረ እነሱስ በትንሽ በትልቁ ነው የሚደበቁት። ‘የምን ጎዳና ተዳዳሪ? አሉ ወይ?’ ኧረ. . . አንተ ደግሞ! ዛሬም ድረስ አሉ ስልህ። መኖሩንስ ይኑሩ። – ዋናው ቤት ቦታ ከታጣላቸው ጎዳናውም እኮ አንዱ ክፍሏ ነው።

ግን ቆሻሻ ለበሱ ብላ አፍራባቸው እንግዳ በመጣ ቁጥር መጋረጃ አበጅታ ከጀርባ ማስቀመጧ ሰርክ ያስተፋፍረናል እንጂ! – ግን ምናለ እንግዳ ሲመጣ አንድ አንድ ካናቴራ ብትገዛላቸው? ብትፈልግ እንግዶቹ ሲሄዱ መልሳ ተቀብላ ስቶር ታስቀምጠው፡፡ ደግሞ ምን… በኮንትሮባንድ ሰበብ በየጊዜው ከነቦንዳው ለሚቃጠል ካናቴራ. . .

አሁን አውንማ እናቶችም ወደ ጎዳናዎች ብቅ እያሉልህ ነው። – ነጠላ ለብሰው ሊለምኑ። ‘የሰው ፊት አያሳይህ’ ይሉት ምርቃት ትልቅነት የሚገባህ እነሱን ስታይ ነው። እንዲያው ሲያሳዝኑ። አይናይንህን ነው የሚያዩህ. . . አይናይንህን እያዩ አንጀት አንጀትህን ይበሉታል፡፡ ሲፈሩ ሲቸሩ በደንብ በማይከፈት አፍ ‘እርዳኝ ልጄ’ እያሉህ፡፡ እንደዚያ ዓይነት ሰው ይለምናል ብለህ ስለማታስብ ያስደነግጥሀል . . ግን ምን ታደርገዋለህ? – ከገባህ ሳንቲም መስጠት ነው።

ደግሞ ብዙዎቹ ስማቸው እንዳይጠፋ ፈርተው ከሰፈር ርቀው ነው የሚለምኑት። እና በታክሲ ስትመላለስም ያጋጥሙሀል። እንዲያው ጎንህ ቁጭ ያሉ ገራገር እናት ከወያላው ጋር ቀንስ አትቀንስ እንደሚከራከሩ እቅዳቸውን ቀድመው ያማክሩሃል። “ኧረ ወዲያ፣ ዝም ስንል አበዙት እኮ. . . ብር ከአርባ? ኧረ እኔስ ከ1 ብር በላይ አልሰጠውም። ታያለህ፡፡ መንግስት የሌለበት አገር አደረጉት እኮ፡፡” ምናምን ምናምን ይሉሀል. . .

አዲስ ሆኖባቸው አይደለም። ዋጋው ዛሬ ተወዶም አይደለም። ካንተ በላይ ያውቁታል፡፡ ለምደውታል። ስራ እንዳለበት ሰው ማልደው ወጥተው አምሽተው ይመለሳሉ። (ነገሩን ሳስበው፣ ለልጆቻቸው (ካሏቸው) እና ለጎረቤት “ስራ” ብለው ይሆን የሚወጡት? የሚል ጥያቄ ሁሌ ይጭርብኛል።) ለሆድ በሰው ፊት እሳቱ ተገርፈው የቃረሟትን ጨርሰው እንዳይከፍሏት አሳዝናቸው ነው። ከገባህ ትሞላላቸዋለህ። ከዚያም ትለምደዋለህ፡፡ ህምምም. . .

ግን ምናለ ‘ግብር’ ተብሎ ከገቢያችን የሚቆረጠውን ትተውት ቢያንስ ከአፋችን የቆጠብናትን 15 ፐርሰንት ግማሽ ያህሏን ምግብ ፍለጋ ጎዳና የወጡት ሰዎችን መቀለቢያ ቢያደርጉት? አዛውንቶቹን ቢጦሩበት? ተ.እ.ታ. ስንከፍል… ልክ መቶ ጉርሻ ስንጎርስ 15ቱን ለእነሱ እንዲያጎርሱልን ቀኝ እጃችንን እንደሰጠናቸው ቢያስቡት? እንዲያ ቢሆን ማን ፆሙን ያድር ነበር ጃል?!

ኧረ የሸዋስ ጉድ መች ተወርቶ ያልቅ ብለህ? ደግሞ ከዚህ ሁሉ ኮተቷ ጋር ‘ከዐለም መታየት ካለባችው ከተሞች አንዷ ሆና ተመረጠች’ ይሉሀል ካስመረጧት ትሩፋቶቿ መሀል ዋናው የካፌዎቿ ብዛት መሆኑን ሲነግርህ ደግሞ ሳቅ ያፍንሀል…. (ስለሱ ሌላ ጊዜ አጫውት ህ ይሆናል) የስዋ ነገር ግን እንዲያው ጉንጭ አልፋ ነው። እኔም በወሬ ሰቅዤ በልደትህ ማግስት አደረቅሁህ አይደል?

ውይ ሳልነግርህ ደግሞ፥ ትናንትና እናቴን “ዛሬ እኮ የዮሐንስ ልደት ነው።” ስላት ምን እንዳለች ታውቃለህ? “ዮሐንስ፣ ዮሐንስ… ዮሐንስ የዐይን አባትህ?” ሃሃሃ… ዐይኔ እስኪጠፋ ነው የሳቅኩት። እኔ የታወቅሁልህ ታዲያ? ግን አዲስ አበባ የዓይን አባት አላት እንዴ? ማለቴ መጎሳቆሏን የሚያይላት የዐይን አባት። መውጣት መግባቷን በስስት የሚመለከት የዐይን አባት? አዪዪ. . . የዐይን አባት ትርጉሙ እንደዚያም አይደል ለካ? ሃሃሃ. . .

በል አንተዬ ንግስቲቱ መጥተው online ሳይፈነክቱኝ፣ እንተንም “አንበሳ ሲያረጅ”ን ለንጉስ ሳላስተርትህ በፊት ከትናንት በስቲያ ወዳጄ ያደረሰችኝን የበዕውቀቱ ስዩም “ወይ አዲስ አበባ” ግጥም ልልቀቅብህና ልሰናበትህ፡፡ ኧ ማነው ዝንብ አንተ?. . . ዝንብማ ከቆሻሻዋ አዲስ አበባ ማደሪያ ቦታ አታጣም። ሃሃሃ… ይብላኝ ለእኔ – ለ40/60 ተስፈኛ. . . ሆሆሆ. . .

ወይ አዲስ አበባ. . .
ወይ እመ ፊንፊኔ. . .
ንቅሳትሽን ስታሳይኝ፣ ጠባሳሽን አያለሁ እኔ፡፡
የሴቶችሽ ውበት – የገባኦን ጸሀይ
ሲወጣ ነው እንጂ፤ ሲጠልቅ የማይታይ፡፡

በረንዳ ላይ ሆኜ
ቁስል ለበስ ለማኝ. . .
ማየቱ ቢቀፈኝ፣ አይኖቼን ጨፍኜ
ስንት አንገት፣ ስንት ጡት. . .
ስንት ዳሌ አለፈኝ?!

ወይ አዲስ አበባ . . .
ወይ እመ ፊንፊኔ. . .
ሴቶችሽ እርጉሞች ሀሳባቸው ክፉ፣
ቀስተ ደመና ላይ ቡትቶ እየጣፉ፣
ውበት አስጠየፉ፡፡

ወይ አዲስ አበባ. . .
ወይ እመ ፊንፊኔ፤
የብረት አበባ – የማይረግፍ ፔታሉ፣
የሚዝግ ነው እንጂ የማይደርቅ ቅጠሉ፤
የአዱኛ ሽራፊ፣  የመከራ ግንጥል፣
አልኖርብሽ ባ’ማን፤ አልለይሽ በጥል፤
በዕንባ በሳቅ መሀል እንደተቸነከርኩ
. . . አብሬሽ ልቀጥል፡፡

/በዕውቀቱ ስዩም/

ጨዋታ ዘግንቦት

ክረምቱ ተገፋ፣ ፀሀዩ በረደ፣ ቀዘቀዘ ስንል… ወርሀ ፅጌ ከማለፉ፣ ፀሀዩ በህዳሩ እንደ ግንቦት ከርሮ ሲቀጠቅጠንና፣ ዝንቦቹም ሲፈለፈሉ ብናይ ጊዜ ባለፈው ያመጣናት ጨዋታ ትዝ ብላን ድጋሚ መዘዝናት፡፡  ግንቦት መጨረሻ ላይ እንዳለን ሁሉ በታሳቢ ይነበብ…

እሽሽ….ቆይ ….የት ትሄድ መስሎሃል? ….አገኝሃለሁ! …. (እዝዝዝ….እያለ ሄደ።…. ዝንብ መሰለኝ። በዝንብኛ እየሳቀባቸው። በዝንብኛ እያለመጠባቸው። በዝንብኛ ሙድ እየያዘባቸው….) ወቸው ጉድ! በግንቦት እንዲህ ተፈልፍለው መጫወቻቸው አረጉኝ እኮ።…. ወይስ እርጅና ይሆን?…. ኤድያ! ዝንብ ድሮ ቀረ እቴ! የዛሬ ዝንብ እንደው ዓይነ ደረቅ ነው። ሂድ ቢሉት አይሰማ፣ ቢያባርሩት ተመልሶ እዛው። አሳበዱኝ እኮ። ኧረ ጨርቄን ሊያስጥሉኝ ነው። እኔ ለነርሱ ስል ቆዳዬን አልገፍ ነገር፤ ምን ተሻለኝ ይሆን?…. (የልጅ እግር ሴት ልጅ ሳቅ ይሰማል)

ምን ያስቅሻል? ጥርስሽ ይርገፍ እቴ! ለነገሩ የዛሬ ልጅ ምን ቆዳ አለውና ምን ይሰማዋል ብለሽ? ቆዳ ድሮ ቀረ እቴ! ኧረ እንኳን ዝንብ አርፎብሽ ጅብ ግጦሽ እንኳን ህመሙ ከሰማሽ ልቀጣ! (ይሳሳቃሉ…) ተባብረው ሲበቀሉልሽማ ደስታሽ ነው። ሙች! እውነቴን እኮ ነው…እስኪ እያቸው አፈር ስሆን… ድሮ የበደልኳቸው ነገር እንዳለ ሁሉ ለበቀል የመጡ ነው የሚመስሉት። የማይሆኑት የለም እቴ…..እንደ ወይዘሮ – ኩሽና ነው….እንደ አባወራ – ሳሎን ነው…. እንደ ባለሞያ – ላብስል ነው…. እንደ ምኡር – ላንብብ ነው….እንደ ፈላስፋ – ልተንትን ነው…. እንደ ውሻ – ልንከስ ነው …እርጎው ሳይኖር በባዶ ሜዳ የማይጠልቁበት የለም …

እርጎስ በእኛ ጊዜ ቀረ እቴ። ወተቱ ከጓዳ… ልግዛህም ቢሉት የት ጠፍቶ? ሁሉ በእጅ ሁሉ በደጅ። አዪዪ….ይብላኝ ለዛሬ ልጅ፣ ለወተት ብርቁ!….ግን ዝም ብዬ ሳስበው እናንተ የምትወልዷቸው ልጆች ወተትን በአማርኛ ትምህርት ክፍለ ጊዜ ‘ለምሳሌ’ ቢያውቁት ነው። ኧረ ወዲያ…እርሱስ አማርኛው ከኖረ  አይደል? አማርኛ በእኛ ጊዜ ቀረ እቴ….! ነገሩን ሁሉ በምሳሌ እያወራርድን፣ ጠጁን ሁሉ በብርሌ እየኮመኮምን ባንድ ‘ዝም ባለ አፍ ዝንብ አይገባም!’ ምሳሌ ብቻ የስንቱን የጨዋ ልጅ አፍ እንዘጋው ነበረ መሰለሽ?! ቢሻን ደግሞ ‘ካለመናገር ደጃዝማችነት ይቀራል’ን መዝዘን እናናግረው ነበር፡፡ ዛሬ ግን ይኧው ዝንብ እንኳን ጊዜ ሰጥቶት፣ አፋችንን ፈልቅቆ ሊገባ ይጠብቃል… ደጃዝማችነቱንም ጠቅልለው ይዘውታል ስልሽ….

መቼስ ታምር አያልቅም!…. ‘ሰው ከጦጣ መጣ’ ሲባል ሰምተው፣ ምናልባት ከዝንብነት ወደ አውሬነት ለማደግ ሲታገሉ ይሆን እንዲህ ድርቅ የሚሉት? ሆሆሆ…. (ሳቅ ይሰማል…) ኡኡቴ….አሁን በእኔ ድንቁርና መሳቁ ነው? ወግ ነው!… የናንተ እውቀት እንደው ነገር ማጣመምና ቦታ ማገላባበጥ ነው። የዝንቡን ፍሊት ከኔ ደብቀሽ ለገላሽ ስታርከፈክፊ አንድ ቀን እዚያው እንዳትደፊ እንጂ….(‘ዶዶራንቱን ነው እኮ’ እያለች ትስቃለች) ድንቄም! ከፈረንጅ ሴጣን ጋር አማሽኝ ማለት ነው? አማርኛማ ዳገትሽ ነው… ነገሩን ሁሉ እያደባለቀሽ በእግሩ እያስኬድሽው…. የኔታው ብርቅ ሆኖ አስኳላ የማንም መጫወቻ ሆና ቀረች! ቱቱቱ….

(የረሱት ነገር ድንገት ትዝ እንዳላቸው ሁሉ መንጨቅ ብለው) እስኪ የዝንቡን ብዛት እዪማ! አቆናጠጣቸው ብትይስ? እንደ ሆነ ነገር አይደል ሚመዘልጉት እንዴ? ሆሆ… እኔማ ድንጋይ ይዞ ከነሱ ጋር መሯሯጥ ነው የቀረኝ። ዱላውንማ ቆየ ከጀመርኩት። ታዲያ ምን ያደርጋል?! እቃ ብሰባብር እንጂ ዝንቦቹ ከኔ ጋር አባሮሹን ለምደውታል። ‘የባሰ አታምጣ!’ ማለት ነው የሚሻለው….እንጂማ የመጪውን ማን ያውቃል?  ምናልባት ዝንብ መግደል ከጀግንነት ተቆጥሮ ያሸልም ይሆናል። (አሁንም ሳቅ ይሰማል…) ሙች ስልሽ… (ሳቁ ይቀጥላል…)

ኤድያ! ለነገሩ ጊዜ ሰጥቶሻል….በደንብ ሳቂ! ጊዜ እንጂ ብርቱ፣ ሰውማ ደካማ ነው። ምኑንም ችዬ አላሳይሽ። ጊዜ ያሳይሻል….አንሙት ብቻ! ሰው ዛሬ የያዘው የመሰለው ነገር ሁሉ ከእጁ እየተፈተለከበት ሰዶ ሊያሳድድ ይሰደድም ይሆናል።… ደግሞስ ማን ያውቃል? በዝንብ ተማርረን ጫካ የምንገባበት ጊዜም ይመጣ ይሆናል። (አሁንም ይሳቃል…) ሥራ መፍታት እንዲያ ነው! ታየኝ መቼስ…. ለዝንብ ቦምብ ሲጠመድ….. ለዝንብ ምሽግ ቆፍሮ ሰው ተሸሽጎ  ሲዋጋ…..ግን ምን ያተርፈኝ ተብሎ? ለነገሩ ሰውስ ምን ያተርፈኝ ብሎ ነው ከሰው ጦር የሚማዘዝ? እንዲያው ቢፈርድበት  እንጂ… ‘በዚህ ብላ! ላብ ይሁንህ’ ቢባል እንጂ!… ይሁና! ነገ ሰኔም አይደል?… የወቅቱስ ዝንብ ያልፋል!… ብቻ የባሰ አታምጣ! ተመስገን!….

ትናንት ጠዋት አልጋዬ ላይ ሆኜ በሰመመን የሰማሁት ነው። በህልሜ ይሁን በእውኔ እንጃ። ሴትዮዋም ማን እንደ ሆኑ በትክክል አልለይም። …አንድ ነገር ግን አውቃለሁ….ዛሬ ሰኔ ነው….ግንቦት አልፏል….ዝንቦቹም ቀስ እያሉ ይሄዳሉ። እኛን ለብርድና ለቁር አቀብለውን.። ዞምቢዎቹስ?

(ማስታወሻ፡ ሰኔ 1/2004 የተፃፈ)

አዪዪ…

☞ ORION BANANA ማስቲካ ከ1996 ዓ/ም ጀምሮ (በግምት) ጥቂት ከሚባሉ ጊዜያት በቀር ከኪሴ ተለይቶኝ አያውቅም ነበር። ተመሳስሎ ሲሰራም ከአስመጪው ከአልሳም ትሬዲንግ ሁሉ ቀድሜ የማውቀው እኔ ነኝ ብል ማጋነን አይሆንም። ሃሃሃ… ስንቱን እንደከተብኩለት ቢያውቅ ኖሮ ተቆራጭ ያስብልኝ ነበር። (ተቆራጭ ኬክ ነው? ብሎ መቀለድ አይቻልም። ሄሄሄ…) ባለፈው የሀዘኑ ጊዜ ‘በየመንገዱ ማስቲካ ማኘክ አይቻልም።’ የሚል ተባራሪ ወሬ ሰምቼ የተውኩት፥ ይሄው እስከዛሬ አፌ ገብቶ አያውቅም።

Oh my Orion, I missed u so much!:D

 

☞ በ1993 ዓ/ም የ11ኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ በ1 ብር ከስሙኒ (1:25) የገዛሁትን ጥፍር መቁረጫ ነው እስከዛሬ ድረስ የምጠቀመው። ውይ ደጉ ዘመን… ብር ከስሙኒ የሚባል…እቃ የሚገዛ ብር ነበረን። ምናምን ብለን እናማር እንዴ? ሃሃሃ… የምር ግን በየመሀሉ ለአፍታ ከዐይኔ እየተሰወረች ሳጣት ሌላ ብገዛም ሳይቆይ ይሰበርብኛል። ያኔም ጥንካሬና አለመሰልቸቷን ውለታ እየቆጠርኩ እወለውላታለሁ። ምናልባት ለልጄ አወርሳት ይሆናል እያልኩ።…ሃሃሃ (ሰው ጠብመንጃ ሲወለውል፣ ቤት ሲያወርስ አይተሀል።’ ብሎ መቀለድ አይቻልም።) ተመስገን! እነሆ እኛም ድሮ ቀረ እያልን ያለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡

Oh my nail cutter, I owed a lot to you! :p

 

☞ በ1997 ዓ/ም የ3ኛ ዓመት ተማሪ ሳለሁ በ35 ብር የገዛኋት አንዲት የምታምር ነጭ ቲሸርት አለችኝ። በጣም ስለምወዳት ብዙ ጊዜ እለብሳታለሁ። እርሷ ግን ለመጣል ፈቃደኛ አይደለችምና ዛሬም ያኔ በነበረችበት ይዞታ ላይ ሆና ታባብለኛለች። ሰሞኑን (ከ3 ወር ወዲህ) ባመጣሁት ክብደት የመጨመር ፕሮግራም መሰረት ያቀድኩትን ያህል በመጨመሬ ምክንያት እርሷም እንደሌሎቹ ልብሶቼ እየጠበበችኝ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። እንዴት ነው እናጫርታት? ወይስ መልሰን ክብደት የመቀነስ ስራ (z other way round) እንጀምር?:) (ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ’ ብሎ መተረት ከቅናት ይቆጠራል። ሄሄሄ…)

Oh my t-shirt, I don’t wanna lose you!;)

 

☞ በ1992 ዓ/ም የአስረኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ ጋሽ ዓለሙ የሚባሉ ባዮሎጂ መምህራችን (አዲስ ከተማ የተማሩ ያውቋቸዋል። ወይም ደግሞ በትርፍ ጊዜያቸው የመስመር ዳኝነት (አራጋቢነት) ስራ ስለሚሰሩ ምናልባት ስታዲየም የሚያዘወትሩ ወዳጆች ያውቋቸው ይሆናል።) በትምህርት መሀል ‘ጉንፋን ሊጀምር ሲል (ስሜቱ ሲመጣ) አፍንጫን በቀዝቃዛ ውሀ በመታጠብ ጉንፋኑን ሳይመጣ በፊት ድራሹን ማጥፋት ይቻላል፡፡ ያው ክትባት በሉት።’ ብለው ነገሩን። እነሆ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ እኔም ምክራቸውን ተግባር ላይ እያዋልኩ (ለሰውም እየመከርኩ) ጉንፋንን እከላከላለሁ።:) በመሆኑም ከዚያ ወዲህ ጉንፋን ይዞኝ የሚያውቀው በጣም ጥቂት ጊዜ ነው። እርሱም ክትባቴን ስረሳት! (‘ውሀ በመንደሩ ሲጠፋ ሲጠፋ…’ በል እንጂ ብሎ ማላገጥማ አይቻልም። ሃሃሃ…)

Oh common cold, where are you?:-/

ወይ ትምህርት…

‘የብቁ ባለሞያ ያለ’ vs ‘የስራ ያለ’…

የአገራችን የትምህርት ጥራት ጉዳይ ብዙ የተባለለትና፣ እንደማስቲካ ዘወትር በየሰዉ አፍ የሚላመጥ ነገር ነው። – ላይዋጥ፣ ላይተፋ በአፍ የሚንከባለል። የሚያሳሳ። ተሰልችቶ የሚያስጠላ። ጣእሙን ይቀይር ዘንድ ተአምር የሚናፍቁለት። እንደነገሩ ችግሩ በየጊዜው እየተነሳ ቢደከምለትም እስከዛሬ ይህ ነው የሚባል ጉልህ ለውጥ አላሳየም። እንዲያውም አንዳንዴ ለመፍትሄ የታሰበው ጥረት ዘርፉን ለሌላ ድካም አቀብሎት ያልፋል።….ምናልባትም ትግበራ ላይ ያለ የለውጥ ዘዴ (strategy) መጨረሻው ሳይታይ በአናቱ ሌላ እያስነደፈ።

የጥራት ማነሱን ጉዳይ ባለማመን ፀንቶ (አንዳንድ ጊዜም በስሱ እያመነና ከትናንት የተሻለ መሆኑን ለማስረዳት ላይ ታች እያለ) የሚታገለው መንግስትም ጥራቱን ለማሻሻል (ወይም ለመሸፋፈን) በተለያዩ  ጊዜያት የተለያዩ  እንቅስቃሴዎችን ያደርጋል። “የአንዳንድ ፀረ – ልማት ሀይሎች…” ወሬ ነው፥ ብሎ የሚፈርጀውና “የለም” ብሎ የሚከራከርለት የትምህርት ጥራት ማነስ ጉዳይ… በአሳሳቢ ደረጃ ላይ መሆኑን በመከላከልና (defence) ለመለወጥ (ለመሸፋፈን) ሰርክ መኳተኑን በመመልከት መረዳት ቀላል ነው። – ከራሱ ውጪ ሌላ አስረጂ ሳያሻ!

በተለያዩ  ጊዜያትም የትምህርት ፖሊሲውን በማደስ፣ የትምህርት አሰጣጥና የተማሪዎች የምዘና መንገዶችን በመከለስ፣ የመማሪያ መፃህፍትን በመቀየር፣ ለግል ተቋማት የማስተማር እውቅናና ፈቃድ በመስጠት፣ አንዳንዴም ባልታሰበ ሁኔታ የሰጠውን ፈቃድ በመንጠቅ፣ አዳዲስ ተቋማትን በመክፈት፣ የተቋማቱን የአገልግሎት መዋቅር በመለወጥ፣ ለመምህራን ስልጠናዎችንና ስብሰባዎችን በማዘጋጀት፣ እንዲሁም በሌሎች በብዙ መንገዶች ቢሞክረውም ውጤቱ እንኳን ለጥጋብ፥ ለአቅመ ረሀብ ማስታገስም አልደረሰም። ዛሬም ሞያዎች ‘የብቁ ባለሞያ ያለ’ ብለው ይጮሃሉ። በአንፃሩም ብቁ ተብለው ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተመረቁትም ‘የሥራ ያለ’ እያሉ ይባክናሉ።…ያላሰቡትንና ሰዎች የማይመርጡላቸውን ስራ እየሰሩ።

የተውኩትን ነገር ተመክሬ… (ኮብልስቶን እንደምሳሌ….)

የስራ ትንሽ የለውም። አርቀን ሳናስበው እንኳን ማንኛውም ዓይነት ስራ የሆድን ገመና ሸፍኖ  ቀጥ አርጎ ከሰው እኩል ያውላል።  ብዙ ነገር ሳንጎትት በዚህ ብቻ ስራ ክቡር መሆኑን አምነን እንናገራለን። አግባብ የሆነ የስራ ክፍፍል (rational division of labor) መኖሩም ለእድገትና ለስራው ጥራት የሚኖረው አስተዋፅኦም ጉልህ መሆኑን እናውቃለን። ያ ሳይሆን ቀርቶ ግን ማንኛውም ስራ ለደረጃው በሚመጥን ባለሞያ ካልተሰራ፥ ስራው በሌላ ተሰርቶበታልና የሚመጥነው ባለሞያው ስራ ከመፍታቱ ባሻገር ትልቅ የሰው ሀብት ብክነትም ያስከትላል።

ለዚህም ነው ከላይ ‘ያላሰቡትንና ሰዎች የማይመርጡላቸውን ስራ እየሰሩ’ ያልኩት። እንደ ምሳሌ እንደ ትልቅ የገቢ ማስገኛ ተቆጥረው ዝናቸው በአገሩ ከናኘ ስራዎች መሀል ኮብልስቶን አንዱ ነው። በእርግጥ ወጣቶችን አሰባስቦ፣ ስራን ያለመናቅ ስነልቦናን ገንብቶ ማሰራትና፣ ራሳቸውን እንዲረዱ ማድረግ ጠቃሚነቱ አያጠያይቅምና በራሱ ትልቅ ስኬት ነው። ለሰራተኞቹ የገቢ ምንጭ፣ ለከተማዎቹም ውበት ነውና፥ በአገሪቱ ላይ የኮብልስቶን ንጣፍ ስራ በሰፊው መሰራቱ ማንንም አይሳዝንም። አያበሳጭም።

በድንጋይ ማንጠፍ ስራው ላይ የተሰማሩ የከፍተኛ ትምህርት ምሩቃን መኖራቸውን መስማት (ለዚያውም በመንግስት የመገናኛ አውታሮች በኩል) ግን ያማል። ሲሆን ሲሆን በዚህ የስራ ዘርፍ ላይ መሰማራት የነበረባቸው ትምህርታቸውን ከተለያዩ  የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጨረሱት ወጣቶች ሳይሆኑ ሌሎች (እነሱ ትምህርታቸው ላይ ውጤት ለማምጣት ደፋ ቀና ሲሉ ስራ ፈት የነበሩ አሊያም በተለያየ ምክንያት ትምህርታቸውን መቀጠል ያልቻሉ) ወጣቶች ነበሩ።

እንዲያም ሳይሆን ቀርቶ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው የወጡ ወጣቶች ስራውን እየሰሩ ቢገኙ (መርጠውትም ሆነ ምርጫ አጥተው) ኑሮአቸውን ለማሻሻል ክብሬን፣ ማቄን ጨርቄን ሳይሉ፣ ስራ ሳይንቁ ተገኝተዋልና በማህበረሰብ ደረጃ አድናቆት ይቸራቸው ይሆናል። ከዚያ ባለፈ ግን እንደ ጥሩ ነገር ታይቶ ለመንግስት የፕሮፖጋንዳ ፍጆታ ሲውሉ መመልከት ትዝብት ነው ትርፉ። – አንድም ላስተማራቸው ዜጋዎቹ የሚመጥን የስራ ዘርፍ ቀድሞ አላመቻቸምና፤ ሌላም በድንጋይ ንጣፍ ስራ ላይ መሰማራት የሚችሉ ወጣቶችን በቅናሽ ወጪ ማምረት ሲችል ያን አላደረገምና እንደ ኪሳራ እንጂ እንደ ትልቅ ስኬት ሊወሰድ አይችልም።

በወቅቱ የነበረው የሰዉም አፀፋ ይህን ድርጊቱን የሚያወግዝ እንደነበር ለብዙዎቻችን ትኩስ ትዝታ ነው።  ዛሬም ድረስ እየገረብን የምንታዘበው። በዚህም “ዓሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል” ይሉት ተረት ለመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ ተተርቷል። ምናልባት ትርፍና ኪሳራውን ቀድሞ ሳያሰላ አምልጦት ያደረገው ነገር ነበር፤ ብንል እንኳን የትምህርት ጥራቱን በተመለከተ ማጣፊያው እንዳጠረው የኮብልስቶን ስራ በግልፅ የሚያሳየን አንድ የአደባባይ ምሳሌ ሊሆን ይችላል። (ትምህርታቸውን ጨርሰው በበሬ አረሱ ስለተባሉ ወጣቶችም ትዝብቱ ከዚህ አይለይም።)

‘ቄሱም ዝም! መፅሀፉም ዝም!’

ዛሬም በዘርፉ የሚያጠኑ ምሁራን ስለ ትምህርት ጥራቱ አሳሳቢነት ይጮሃሉ። ችግሮቹን መዝዘው ስለመፍትሄው ይባክናሉ። ከወረቀት በዘለለ መፍትሄ ሲሆኑ ግን አንመለከትም። እንደ ምድረበዳ ጩኧቶች ናቸው። ጯሂውና አድማጩ በአንድ ዓይነት መስመር ውስጥ አይደሉምና ትርፉ ከግለሰብ እርካታ ባለፈ ስምና ድካም ነው። መንግስትም ቢሆን በአንድ ጎን የችግሩን መኖር ላለመቀበል እየተከላከለ፣ በሌላው ደግሞ ነገሩን ለማሻሻል (ወይም ገፅታውን ለመቀየር) ይረዳል ያለውን መንገድ ሁሉ ይሞክራል።

ከነዚህ መሀል ግን ተማሪዎችን በፓርቲ አባልነት መመልመልና በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንዲሰበሰቡ ማመቻቸት፣ ተማሪዎቹን የገመናው ተካፋይ ቤተሰቦች በማድረግ ጥረታቸውን ሁሉ የራስን ገመና በመደበቅ ትርምስ ውስጥ ጥሎት፣ ነገሩን በማይደፈር ማእቀፍ ውስጥ እንዲቀመጥ አድርጎታል። ተማሪዎችም ስለጥራቱ እና ችግሮቹ ከማሰብና ከመጠየቅ ይልቅ ገፅታውን በመሸፈን ስራ ላይ ተጠምደው ስለነገ የፓርቲያቸው ህልውና ይብሰከሰካሉ። – ገፁ ገፃቸው መሆኑን አምነው ተቀብለዋልና።

ባለፈው ወዳጃችን ማህሌት ፋንታሁን  “የፍርሀት ዘመን” በሚል ርእስ እንዳስነበበችን የዘመናችን የፍርሀት ዛር በከፍተኛ ተቋማት ተማሪዎች ላይ ልዩ መልክና ገፅ ይዞ፣ እንዲሁም በነገ ጥቅም (job security) ሰበብ ዳብሮ የተንሰራፋ ነው። ተማሪዎች በችሎታቸውና በራሳቸው ጥረት ካለመተማመናቸው ወይም ደግሞ የስራ ዓለሙን አሰራር ቀድመው በማወቃቸው የተነሳ የነገ እንጀራቸውን ለማብሰል ይረዳቸው ዘንድ ማገዶአቸውን የሚያቀራርቡት ገና ስራቸው ሳይጠነክር ከመነሻው ነው። – በፓርቲ አባልነት! ከቀናቸው እና የነቁ ታላላቆች ካላቸው ደግሞ ከበሶ ጋር አደራ ተቋጥሮላቸው። – ‘Green ካርዷን…!’ በምትል ለዛ ባላት ቀጭን ሀረግ።

ይሄም በተማሪዎች ዘንድ የሚኖረውን የፉክክርና የመበላለጥ ስሜት ያቀጭጨዋል። በከንቱ የራስ መተማመን (ጉራ) እና ትእቢት እንዲታነፁም ያደርጋል። ልቡን በትዕቢት ቀድሞ የሞላ ተማሪ ደግሞ ትምህርት የመቀበል ፍላጎቱም ሆነ አቅሙ አናሳ ነው የሚሆነው። በዚያም እንደነገሩ ካለምንም ማማረርና ማንጎራጎር ቆይተው ወደየመጡበት ይመለሳሉ። – ተመርቀው።

ዋቸሞ ዩኒቨርስቲ

ዋቸሞ ዩኒቨርስቲ ከዚህ በፊት ሆሳህና ዩኒቨርስቲ ተብሎ የመሰረት ድንጋይ ተጥሎለት አዲስ የተገነባ (በግንባታ ላይ ያለ) ዩኒቨርስቲ ነው። አዲሱ ስያሜ በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ አልተወደደም የሚል ነገርም ከተለያዩ  ምንጮች ሰምቼአለሁ። አሁን ግን ዋቸሞ ዩኒቨርስቲን ላስተዋውቅ አይደለምና ስለስሙ ለውጥ አግባብነትና ኢ-አግባብነት አልጫወትም። ግን እንዲያው ለዚህ ፅሁፍ መነሻ የሆነኝ ይሄ ዩኒቨርስቲ ነውና ከርሱ ጋር የተያያዘውን ላጫውታችሁ።

ባለፈው ረቡእ (ጥቅምት 20) በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ እግር ጥሎኝ (ጉዳይ ገጥሞኝ) ተገኝቼ ነበር። የሄድኩበት ጉዳይ ፈፃሚዎች ስብሰባ ላይ ነበሩና እስኪወጡ ድረስ ዐይኔን ግድግዳ ለግድግዳ እያንከራተትኩ ያገኘሁትን ሳነብ ቆየሁ። በመሀል….

እኔ ኧከሌ…በህክምና ትምህርት ዘርፍ በዋቸሞ ዩኒቨርስቲ የተመደብኩ ሲሆን፣ ወደ ጥቁር አንበሳ የሚቀይረኝ ሰው ካለ ወሮታውን እከፍላለሁ።

ስልክ…..

ምናምን የሚል የተማሪ የቅያሪ ማስታወቂያ አንብቤ በጣም ተገረምኩኝ። በርግጥ ስሙን ከዚህ በፊት አዲስ ከተገነቡ ዩኒቨርስቲዎች ዝርዝር ውስጥ አይቼዋለሁ። የሆሳህና ዩኒቨርስቲ አዲስ ስም መሆኑንን ግን እስኪነገረኝ ድረስ አላውቅም ነበር። ለአቅመ ህክምና ትምህርት ማስተማር መድረሱንማ ጠርጥሬም አላውቅ። እርሱም ነበር አግራሞቱን የጫረብኝ። (ምናልባት ማስታወቂያው በተማሪዎች ለፌዝ የተለጠፈ እንደሆነ እንጃ….ተገንብቶ ያላለቀው ድህረ-ገፁ ላይ ግን ህክምናን ትምህርት የለም።)

እስከጊዜው ድረስ… – ‘ለምን?’!

በእለቱ ቤቴ ስመለስ፥ ነገሬን ቅደም ተከተል አስይዤ ጨዋታውን ለማዋዛት በማሰብ፥ በመፅሀፈ ፊት (facebook) ግድግዳዬ ላይ

ኢትዮጵያ ‘ወቻሞ’ (or something like that) የሚባል ዩኒቨርስቲ እንደተሰራላት ሰምቶ የሚያውቅ እጁን ያውጣ!!! :)) የምር…

ብዬ ለጠፍኩኝ። ብዙ ጊዜ FB ላይ የሆነ ነገር ስፅፍ በጨዋታ ደንብ ነው። ያኔም ነገሩን ሳነሳው ከጨዋታ ባለፈ ቁም ነገር… ምን ያህሉ ሰው ዩኒቨርስቲውን ያውቀው ይሆን? ከሚል ሀሳብ በቀር ሌላ ምንም ዓይነት ፍላጎት ኖሮኝ አልነበረም።

ከአስተያየቶቹ መሀል ግን አንድ ወዳጅ ነገሩን ከፌዝ (በቃሉ ላይ ከማላገጥና ቃሉ የሚመለከተው ብሄርን ከመናቅ) ወስዶት ተበሳጨ። እኔም ነገሬን ለማስረዳት ላይ ታች አልኩኝ። – ከነ ስሜቴና ብስጭቴ! ግን መግባባት አልቻልንም። ሀሳቤን በመጠየቅ ለመረዳት ከመሞከር ይልቅ ቃሉ ላይ እንደተሳለቅሁኝ ደግሞ ደጋግሞ ነገረኝ። እኔን መኮነኑ ውሀ ያነሳለት ዘንድም የጠቀሰው “ዋቸሞ” በማለት ፈንታ “ወቻሞ” ብዬ መፃፌን ነቅሶ በማውጣት ነበር።

በእርግጥ ስሙን ስፅፈው ተሳስቼያለሁ። እንዲህ ያለ የቃል አፃፃፍ ስህተት ግን እኔም ስሰራው ወዳጄም ሲታዘበው የመጀመሪያችን ሊሆን አይችልምና ነገሩ ከማስተካከያ ባለፈ ለዘለፋ አያበቃም ነበር ባይ ነኝ። በቅንፍ ውስጥ (or something like that) ስል… ስሙን በትክክል መጥራቴን ከመጠራጠሬ የመጣ መሆኑን በግልፅ አስቀምጦ ለሚፈጠረውም ማንኛውም ዓይነት ስህተት እንደ ቅድመ-ይቅርታ ያገለግለኛል ብዬ አስቤም ነበር። ይሄንንም አብራርቼም መግባባት ሊታሰብ አልቻለም። እንግዲህ ይሄ ንትርክም የትምህርታችን አንድ ውጤት ሊሆን ይችላል። ላይሆንም ይችላል።

ያም ሆነ ይህ ግን የማይጠይቅ ዜጋን ማፍራት ተጠያቂነትን ከማጥፋቱ ባሻገር የሚጠይቁ ዜጎችን ለማሸማቀቅና ለመዝለፍ ዓይነተኛ መንገድ ነው። ሀሳቡን በነፃነት መግለፅ የማይችልም ሀሳባቸውን በነፃነት ለመግለፅ የሚጥሩ ምስኪን ነፍሶችን በሀሳባቸው ለመናቅ ሲጥር ይስተዋላል። “ለምን?” ተብሎ ሳይጠየቅ ያደገ ሰው “ለምን?” ብሎ ይጠይቅ ዘንድ አይማርም። “ለምን?” ብሎ የማይጠይቅ ሰውም ለሰዎች ምክንያታዊነትና ማብራሪያ ቦታ የለውም። ይህም ጉዳቱ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ለአገር እና ለኗሪዎቿ ነው። ለመጪው ትውልድ የሚያስተርፈው ርዝራዥም ብዙ ነው።

ጨዋታዬን ስጠቀልለውም ትምህርትን የትም እና ከማንም ይማሩታልና የትምህርት ጥራታችን እንዲጠበቅልን እየተማፀንንና እየፀለይን እስከ ጊዜው ድረስ ከአገኘነው ነገር ሁሉ እንማር። በፍርሀት እና በራስ ከመተማመን ማነስ የተነሳ፥ የጎደሉንን እውቀቶችም በመጠየቅና በንባብ እንሙላ። ታናናሾቻችን “ለምን?” ብለን እየጠየቅናቸው “ለምን?” ብለው የሚጠይቁ ተቆርቋሪ ዜጎች እንዲሆኑ እናግዛቸው።