“ዐይኔ ዓለም አየ”፤ የላሊበላ ልጅነት እና የቦታ ፍልስፍና (አጭር ቆይታ ከዶ/ር ይርጋ ገላው ጋር) | Ethio Teyim | Episode 14

ለአገሬ የህክምና ባለሞያዎች

በአስተዳደር በደል ምክንያት እጀ ሰባራ ለምትደረጉ፣
 
በsterilization መሳሪያ እጥረት ወይም በመብራት መቆራረጥ ምክንያት ጉልቻ ጥዳችሁ መሳሪያ ትቀቅሉ ዘንድ ለተፈረደባችሁ
 
ደም ለግሳችሁ ነፍስ ለማትረፍ ለምትተጉ
 
በላቦራቶሪ እና በዘመናዊ ዶክመንቴሽን ችግር ምክንያት የምርመራ ውጤት ለሚዘበራረቅባችሁ
 
የሀሰት ሪፖርት እንድትልኩ ለምትጠየቁ
 
በምንም ውስጥ ብዙ ተስፋ ለምትሰጡን፣ ስናያችሁ ብቻ ቀለል ለሚለን
 
ግራ ቢገባችሁ እና ምታደርጉት ብታጡ በእጃችሁ ዳብሳችሁ አይዞህ ለምትሉ
 
ችሎታ ሳያንሳችሁ፣ በስራ ቦታ አለመመቻቸት እና የህክምና ቁሳቁስ እጥረት የተነሳ አቅመ ቢስ ለምትሆኑ፣
 
አቅመ ቢሱን ካርድ አውጥታችሁ ለምታክሙ፣ መድኃኒት መግዣ ለምትሰጡ (ከፋርማሲ ጓንት ስትገዙም አይቼ አውቃለሁ)
 
በሙስና እና ብልሹ አሰራር ባለሀብቶች ባቆሙት የግል ሆስፒታል ውስጥ ይህን አርጉ ይህን አታርጉ ትንሽ ብላችሁ ለምትሰቃዩ
 
እኛ ሰው ለመጠየቅ ወይ ለህክምና ገብተን እስክንወጣ በሚጨንቀን የሚሸት ሆስፒታል/ጤና ጣቢያ ውስጥ ውላችሁ ለምታድሩ
 
በውሃና መብራት መቆራረጥ ምክንያት ትንፋሻችሁ አብሮ ለሚቆራረጥ
 
ቾክ እንደ መድኃኒት እየታሸገ እና ጊዜው ያለፈበት መድኃኒት በኮንትሮባንድ ይገባ ዘንድ በየእርከኑ ያሉ ባለጊዜዎች ተባብረው፣ የምታዙት መድኃኒት ታማሚውን ሳያሽል ሲቀር ለምትዘለፉ
 
በተፈጥሮ በሆነ ችግር በተከሰተ ጉዳይ ነፍስ ለማትረፍ ስትረባረቡ ባለጊዜ፣ ሽጉጥ ለሚመዝባችሁ (ከአንድም ሶስት ታሪክ አውቃለሁ። አንዱ በዐይኔ ያየሁት ነው) እልህ በማጋባት ወይም በማስደንበር ሊፈጥር ስለሚችለው ችግር ሳይጨነቅ፣ እያሳየ ሚያስፈራራም አለ።
 
በሽታው በየቅያሱ በሰው እጅ ለሚፈጠርባችሁ። (ጀሶ እና ሳጋቱራ ከመብላት ይጀምራል)
 
በተለይ ከመዲናዋ ከአዲስ አበባ ውጭ ለምትሰሩ፣ ሰርታችሁ ለምታውቁ!
 
ክብር ለእናንተ!
 
በበረሀ ላይ እንዳለ ዛፍ፥ ጥላና ተስፋ ናችሁ።
 
ሕይወት እንደነበር፣ ሕይወት እንደሚቀጥል ማሳያ ምልክቶች ናችሁ።
 
በተለይ የአሜሪካ ሀኪሞችን እና የህክምናውን ሁኔታ ባየሁ ቁጥር ልቤ ስለአገሬ ነዋሪ እና ስለ እናንተ ትደማለች። በእናንተ ሁኔታ ውስጥ ቢሆኑ፣ ግማሾቻቸውም survive ማድረግ ይችላሉ ብዬ አላስብም። የድሀ አገር ሰው መሆን ደግነቱ ጠንካራ ቆዳ ይሰጣል።
 
በምንም ውስጥ ሁሉንም ሆናችሁ የመኖራችሁ ነገርም እየደነቀኝ፣ ለእናንተ ያለኝ አክብሮት እና ፍቅር ይጨምራል። ልታከም የሄድኩበትን ጉዳይ ድኜ፣ ድብርት እና የጥፋተኝነት ስሜትን እታመማለሁ።
 
የእውቀት ችግር አለባችሁ እንዳይባል፣ ከማንም እንደምትሻሉ በየሰው አገሩ የወጡ የሞያ አጋሮቻችሁ ምስክር ናቸው። እንኳን ሀኪም፣ በየትኛውም ዘርፍ ላይ ኢትዮጵያዊያን ከማንም አያንስም። አንገት አያስደፋም።
 
ይህንን ስል የግል የጠባይ ችግር ያለባቸውን ሁሉ አካትቼ አይደለም። ዳሩ ግን መልካም ስርዓት ቢኖር ኖሮ፣ በወል ከመጠራት ይልቅ እነሱንም ተጠያቂ ማድረግ ይቻል ነበር።
 
አቅም ካገኘሁ ከሀኪም ጓደኞቼ ጋር በነበረኝ ውሎ የታዘብኩ የሰማኋቸውን፣ በአንድ ዓመት የሆስፒታል ሥራ (በፐብሊክ ኸልዝ) ቆይታዬ ያየሁ፣ የሰማሁ የታዘብኳቸውን፣ የማስታውሰቸውን ጥቂት ታሪኮች ለመጻፍ እሞክራለሁ።
 
ዛሬ ግን ይኽችን መጫሬ፥ አይዟችሁ፣ በርቱ፣ ሀሳቤ ከእናንተ ጋር ነው ለማለት ነው!
 
ዛሬ ድንግዝግዝ ቢሆንም፣ ሲነጋ ብርሃን ይሆናል።
 
ትግላችሁ ለሰፊው ሕዝብ የተሻለ ህክምና ለማስገኘት እና፣ ለዘርፉ ተገቢው ትኩረት እንዲሰጠው በማስቻል ትውልድ የሚያጣጥመውን መልካም ፍሬ ያፈራልና ዛሬ በብዙ ብትደክሙ፣ ብትዘለፉ፣ የሚዲያ ዘመቻ ቢደረግባችሁም አይዟችሁ!
 
መንግስት ሰብስቧችሁ እናንተን አንኳሶ እና ‘ስለህክምና ቱሪዝም የማታስቡ’ ብሎ ተሳልቆ፣ ወላድ እናት ደም የነካው ጨርቋ እንዲታጠብላት መብራት እና ውሃ በሌሉበት ከተማ፣ አዲስ አበባን አስውባለሁ፣ “ወንዞቿን አጥባለሁ” የሚል የ”ቂጥ ገልቦ ክንብንብ” ስላቅ ቢያደርግም፣ አይዟችሁ።
 
እኛንም አትፍረዱብን! ስንመጣ የምናየው የእናንተን ፊት ነውና ስላለው ቁም ስቅል፣ ስለ ህክምና ቁሳቁስ እጥረት፣ ስለሙስናው፣ ስለሕይወታችሁ ባንድረዳ ይቅር በሉን።
 
ጂጂ እና ቴዲ አፍሮ ከጋሪሰን ሃውክ ጋር ከተጫወቱት ሙዚቃ ላይ፣ በእነዚህ የጂጂ መስመሮች ላብቃ!
 
“በቀን በቀን የሚያኖረኝ
ተስፋ ሳልቆርጥ የሚያውለኝ
ዕምነቴ ነው ያለኝ ብርታት
ተሥፋ አልቆርጥም
ተሥፋ አትቁረጥ
አይፈራም አይፈራም
ጎበዝ አይፈራም
ተሥፋ አይቆርጥም”
 
ቴዲም እንዳለው
 
“ሀሳብ አይሆንም አይባልም
ከሀሰብኩት እደርሳለሁ”
 
ካሰባችሁት ደርሳችሁ ለወገን የህክምናውን ዘርፍ ለወገን እና ለአገር እንዲጠቅም ታሻሽሉት ዘንድ ተስፋ አደርጋለሁ!

ያልተዘመረላቸው የኑሮ ወታደሮች

48422130_1979307308856959_8456443323358380032_n.jpgየተረሱ፣ የተዘነጉ ወታደሮች…. ያልተዘመረላቸው የሕይወት ጀግኖች፣ ከኑሮ ጋ ትንቅንቅ ገጥመው በየበረሀው የቀሩ፣ እና በየአረብ አገራቱ የሚንከራተቱ እህት ወንድሞች አሉ።
 
የእናታቸውን ነጠላ ለመቀየር የተለሙ፣ የመሶቧን ልምላሜ ለማስጠበቅ የተመሙ፣ የቤታቸውን ዳር ድንበር ለማስከበር ልጅነታቸውን የገበሩ ብዙ ወጥቶ አደር ወገኖች አሉ።
የቤተሰባቸውን የውሃ ጥም የመቁረጥ ህልም ሰንቀው ወጥተው በውሃ ተበልተው የቀሩ፤ ድህነትን ዐይኑን ለማጥፋት ሲጓጉ፣ በአረብ ዐይናቸው የጠፋ፤ ችግርን ድል ለመንሳት ሲፋለሙ ቀን የደፋቸው፣ እናታቸውን ቀና ለማድረግ ሲፍጨረጨሩ ተሰብረው የቀሩ ምስኪኖች…
 
ከኑሮ ፍላጻ ጋር ሽል ሽል እየተባባሉ የሚራኮቱ፣ ሕይወት ሰንኮፉን ሲያራግፍባቸው፣ ህመሙን ዋጥ አድርገው ጸንተው የሚቆሙ ነፍሶች ብዙ ናቸው።
 
የቤተሰባቸውን ህልውና እና የኑሯቸውን ሉአላዊነት፣ የቤተሰቡን የሆድ ዳር ድንበር ለማስጠበቅ የደከሙ፣ ከኑሮ ጋር ሲታገሉ የተረቱ እና ፀንቶ ለመቆም የሚንገዳገዱ በርካቶች አሉ።
 
በድል ተሯሩጠው መጥተው ሰንደቁን ሰቅለው፣ ከእናታቸው እግር ስር ተደፍተው ምርቃቱን ለመቀበል እና እሳት እየሞቁ ጸጉራቸውን ለመዳበስ እንደናፈቁ…. እናት አስከሬን እንዲላክላት የምትለምንላቸው ኢትዮጵያውያን ሞልተዋል።
 
የድሀ አገር ከርታቶች ሆነው ተፈጥረው፥ ኑሮ ሽምቅ እየተኮሰባቸው፣ ቁልቁል እያሳደዳቸው፣ ጥርሱን አውጥቶ ሊቀረጥፋቸው ሲታገል በእጃቸው መንጋጋውን ወደላይ ሰልቀው ይዘው የሞት የሽረት የቆሙ ከርታታ እህቶች በየአረብ አገራቱ አሉ።
 
የአናብስቱን አፍ በእምነታቸው አዘግተው፣ የአዞዎቹን መንጋጋ በእልህ ፈልቅቀው ይዘው የሚንቧቸሩ ምስኪኖች፤ የመርከብ ነጂው በባህር አውሬ የታጀበ ማዕበል ሲያስቸግረው ማስታገሻ ብሎ አንድ አምስቱን ቆንጥሮ ወርውሯቸው የቀሩ፤ ተርፈው አረብ አገር ገብተው የሚኖሩ፤ ደርሰው የተጉላሉ ብዙሀን….
 
ቤታቸው ውስጥ በቀን ሶስቴ የመብላት ተስፋን ለማስከበር ቆርጠው የተነሱ፣ ታናናሾቻቸውን ለማስተማር የሚንደፋደፉ የልማት አርበኞች፣ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች፣ አረንጓዴ ስደተኞች በየአረብ አገሩ አሉ።
 
እናታቸው ለልመና እንዳትወጣ ሙግት ገጥመው፣ ከአገር ወጥተው ለጥቃት የዋሉ፤ ከኑሮ ጋር ግብግብ፣ ግንባር ገጥመው የሚራኮቱ፣ የሚታኮሱ፤ የሚናከሱ እና የሚቧጨሩ ታታሪ እህቶች አሉ።
 
ኑሮ ያቆሰላቸው፣ ኑሮ ያሳበዳቸው፣ ኑሮ ያሳደዳቸው ብዙሀን ወገኖች ሰብሳቢ አጥተው በየበረሀው ተበትነዋል። ዕድላቸውን ለመሞከር ወጥተው ቀርተዋል።
 
“ምን ይዤ ልመለስ” ብለው ለሁለት ዓመት ሄደው፣ ግራ እንደተጋቡ ከዚያ ብዙ የቆዩ አሉ። ፓስፖርታቸው በአሰሪ ተደብቆባቸው ወደ እናታቸው ቤት መመለስ የሎተሪ ያህል የማይተነበይ የሆነባቸው ሞልተዋል።
 
ያደለው የቤት ቀለም ማስቀየሪያ፣ ጤፍ ማስፈጫ ልኮ እናቱን ደግፎ፣ ልጅን ትምህርት ቤት ለመላክ፣ የኑሮ እሾህ ከበጣው እምቧይ ድህነቷ ላይ የሚፈሰውን እንባ በላቡ ጠግኖ፥ በናፍቆት እና በሰቀቀን እሾህ ተወግቶ የሚወርድ እንባ ተክቶላት፣ በአንጻራዊነት ቀና ብሎ ያልፋል። ግማሹ ባፈቀረው ወዳጁ የሰበሰበው ብር ሁሉ ተበልቶበት ሌላ ጎጆ ቀልሰው ይኖሩበታል። ያልታደለው ደግሞ በወጣበት ይቀራል።
 
ጉዳይ ተደራረተብን እና የሚያስበውም የለ እንጂ፥ “የስደተኛ እናት ታጠቂ በገመድ…” ተብሎ መዘፈን ነበረበት።
 
በዚህ ሁሉ መሀል የሚያጽናናው ግን እርስበርስ በጣም ደጎች ናቸው። የብዙ አገር ስደተኛ ሰው አይቻለሁ። የአረብ አገራት ስደተኞችን ያህል እርስበርሱ የሚደጋገፍ፣ ለቁስ ግድ የሌለው፣ ሰው አፍቃሪ አይቼ አልውቅም። ኑሮም ያደቀቃቸው፣ ድህነት የደቆሳቸው ታታሪዎች ናቸውና ርህራሄ ሞልቶባቸዋል።
 
ነግ በእኔም አያጣውም፥ ሲንፈሰፈሰፉ እንደእናታቸው ነው። ዘር ሳይመራረጡ ነው የሚጠያየቁት። ዘር ሳይቆጣጠሩ ነው ጥቁር ለብሰው ፊታቸውን እየቧጠጡ የወዳጃቸውን ሀዘን የሚቀመጡት። ከየት ናት ሳይሉ ነው ያላቸውን አዋጥተው ለሟቾች እናት ለመላክ ተፍ ተፍ የሚሉት። አንጀት ይበላሉ!
 
ይህን የማወራው አንዷ ወጥቷደር ዘመዳችን የመሞቷን ነገር ከሰሞኑ ስለሰማሁ ነው።
 
ምስኪን፣ ቀና ብላ ሰው የማታይ፣ ታጋይ… የድካሟን ያህል ያልሆነላት፣ የገጠር ድህነት ያድቀቃትና ካለአባት ጥንቅቅ አድርጋ ያሳደገቻቸውን እናቷን ለመጠገን ወጥታ የቀረች ከርታታ ወታደር ነበረች።
 
አይቻለሁ! ኑሮ ሺህ ጊዜ ቢዘርራት፣ ሺህ ጊዜ ተንገዳግዳ ቆማ መክታዋለች። ታግላ ፀንታ ቆማ በጸሎት ስቃበታለች። ጠብ ባይልላትም፣ ከትግል እና ጥረት ቆማ አታውቅም። አገር ውስጥ የምትችለውን ነገር ሁሉ ሞክራለች። ግን አንዱም ምንም አላመጣላት።
 
እናቷን፥ እናት አገሯን ደግሞ በጣም ነው የምትወዳት። እናቴ እናቴ ስትል ውላ ነው የምታድረው። መቼም ሁሉም ሰው እናቱን ይወዳል። የሷ ይለያል፤ ለአንድ ቀን እንኳን የሚያውቋት ሁሉ የሚመሰክረው ሀቅ ነው። እናቴ እናቴ እንዳለች፣ የእናቷን ነጠላ ለመቀየር ጎኗን ለማሳረፍ እንደናፈቀች፣ ከእነእድፏ ከነጉጉቷ ከነናፍቆቷ ከነስስቷ ትታት ሄደች።
 
ከዚህ ቀደም ቤሩት ሄዳ ለፍታ፣ ታግላ፣ ደክማ ምንም ሳይሰጧት ነበር የተመለሰችው። የአንዳንድ ሰው እድል እንዲህ ነው።
 
አንዴ እኛ ቤት ለእንግድነት በነበረችበት ጊዜ፣ እህቴን “ፀጉሬን ስሪኝ” ትላታለች። እህቴ ስትሰራት ጭንቅላቷ ላይ ትልቅ ስፌት አይታ ጮኻ ትጠራኛለች።
 
“ምንድን ነው ይሄ?” እኔንም እሷንም ትጠይቀናለች።
 
“አይ እሙ ትንሽ ነው እኮ። ኸረ ትንሽ ነው” ትላታለች። ወታደር ህመሙን ቻል አርጎ ነው የሚታገለው።
 
“ምን ትንሽ ነው ትይኛለሽ እንዲህ ተሰንጥቆ የተሰፋን ቁስል? ታክመሻል?”
 
“አይ ተስፋ በዛው ቀረ”
 
“እንዴት አትታከሚም?”
 
“ኽረ ትንሽ ነው እሙ”……
 
ይህ በሆነ በጥቂት ወራት ውስጥ ነው ተመልሳ ለመሄድ ጉድጉድ ማለቷ የተሰማው።
“ተዪ” ተብላ ብትለመን ብትሰራ፣ አንዴ ልቧ ተነስቷልና “ሞቼ ልገኝ። አንድ እድሌን ሞክሬ እናቴን ቀና ላድርጋት” አለች።
 
“ኸረ ተይ እዚህ እንደሆንሽው ሁኚ። እናትሽ ያንቺን ደህንነት ነው የምትፈልገው።” ብትባል
 
“በፊትም እንደሰው የሰራሁበትን አልሰጡኝም እንጂ ቢሰጡኝ ኖሮ እኮ ጥሩ ነበር ያገኘሁት። ህጋዊ ስለሆነ እድሌን ልሞክር። አሁን ይሰጡኛል። እግዚአብሔር ያውቃል። ፀልዩልኝ።”
 
ብላ በህጋዊ መንገድ በጀመረችው ፕሮሰስ ተነስታ ቤሩት ገባች።
 
አራት ዓመት ከምናምን ቆየች።
 
ከርሞ ከራርሞ ታማ አልጋ ስትይዝ እንደተሰማው፥ አሰሪዎቿ ፍራንኳን አይሰጧትም።
ለማመን ቢቸግርም፥ በአራት ዓመት ከምናምን ውስጥ አስራ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ብር ብቻ ነው የላከችው። ያ ደግሞ ለመሄድ የተበደረችውንም ኮርቶ አይከፍልም ነበር።
“አበድሩኝና ለእናቴ ስጡልኝ” ብላ ሁላ ታውቃለች። እስትንፋሷ የተያያዘው ከእናቷ ጋ ነው። ሌላ ምንም ዓለም የላትም። እሷን ብሎ የሚመጣ ሰው የለም። ከራሷ ጋ ተማምላ የእናቷን ኑሮ ለመለወጥ ተፍ ተፍ የምትል፣ ባተሌ የኑሮ ወታደር ነበረች።
 
ቤተክርስቲያን አታጓድልም። ሄዳ ጸልያ ተለማምና ትመጣለች።
 
አረብ አገርም ሆና “ፀልዩልኝ” እና “እናቴን አደራ” ነው የምትለው። ሌላ ንግግር የላትም።
ስትኖር ስትኖር የዛሬ ሁለት ወር ገደማ ሆስፒታል ገባች አሉ። አሰሪዎቿ ሆስፒታል ወርውረዋት በዛው ጠፉ።
 
ህጋዊ ስለሆነች ኢንሹራንስም ያስገድዳቸዋልና የህክምናዋን ይከፍላሉ ተብሎ ተጠብቆ ነበር። ግን ደህና ቆንጽላ የለንም። አስከሬን እንጂ ሰው ከነነፍሱ አገሩ እንዲገባ የሚያደርግ ቆንጽላ የለንም። ከአገር ውስጥ የሰዉን ሀብት መዝብረው፣ በጭቆና እና በድህነት ረግጠው ያባረሩትን ሲሞት ይመልሱታል።
 
ደወለች የሆነ ቀን “ሁለቱም ኩላሊቴ ከጥቅም ውጪ ሳይሆን አይቀርም” አለች
ህመማቸውንም በቀጥታ ለእነሱ አይነግሯቸውም። ስለዚህ ከሰሞኑ ያለውን በሽታ ስም ይዘው ነው የሚቀጥሉት አሉ። በሰው በሰው ሲጣራ፥ ኤምባሲው “ህመሟ ጉበት ነው” አለ። በደህና ሁኔታ በሕያወት እያለች፣ የሚደረገው ተደርጎ አገር ቤት እንድትገባ እና እናቷን እንድታያት ተሞክሮ፣ ኤምባሲው ሄዶም ለማየት ፈቃደኛ ባለመሆኑ፥ ማቅቃ ማቅቃ ሞተች። በወጣችበት ቀረች።
 
ልጄ ትመጣለች ብላ ደጅ ደጁን የምታይ ምስኪን እናት አለች። ምን ተብሎ እንዴት ተብሎ ይነገራታል? ማን ደፍሮ የወታደር ልጇን ሞት ያረዳታል? ወታደሯ ልጅሽ ላንቺ ስትሟገት፣ አንቺን ሉዋላዊ እናት ለማድረግ ስትታገል ሞተች። ተረታች። የባለጌ ጥይት አረፈባት። ተብሎ እንዴት ይነገራታል?
 
እንደምንም! አዎ እንደምንም ተነገራት።
 
ግን “አስከሬኗን ካላየሁ አላምንም። እሷ አልሞተችም። አስከሬኗ ካልመጣ አልሞተችም። አንድ ቀን ትመጣለች።” አለች አሉ።
 
ለይስሙላ የተሰየመው ቆንጽላው ደግሞ የተካነበትን አስከሬን የመላክ ሚናም የተወው ይመስላል።
 
በጣም አስቀያሚ በሆነ ገጠመኝ ደግሞ፥ በአንድ ቀን የተረዳችው የሁለት ልጆቿን ሞት ነው። እሷ አረብ አገር በሞተች በሶስተኛው ቀን፣ ታናሽ ወንድሟ አዲስ አበባ ውስጥ ተከራይቶ ይኖር ከነበረበት ቤት ደጃፍ ላይ ተገድሎ ተገኘ አሉ።
 
እሱም የኑሮ ወታደር ነበር። እናቱን ሊጠግን የከተማ መብራት ተከትሎ አዲስ አበባ ውስጥ የከተመ ታታሪ ምስኪን! እሱን እናት ቀብራዋለች እና አምና ህመሟን ዋጥ አድርጋለች። የአረብ አገሯ ግን አስከሬኗ ካልመጣ አላምንም ብላለች። የትኛው ደህና ቆንጽላ ነው የሚደርስላት?
 
ነፍስ ይማር!

የጉዞ ነገር…

images.jpgሁሉም የአፍሪካ አገራት ነዋሪዎች ወደኢትዮጵያ ለመግባት፣ በደረሱ ጊዜ ቪዛ ማግኘት የሚችሉበት አሠራር፣ ከኖቬምበር 10 ይጀምራል ተብሎ ነበር። (እንዴት ሆነ እንኳን “እንኳንስ ዘንቦብሽ እንዲሁም ጤዛ ነሽ” ይላሉ። የደህንነት ሁኔታው እንዲህ በሆነበት ጊዜ ጣጣው ብዙ ነው።
 
እሱን ባሉ በ20 ስንተኛ ቀኑ፥ አሁን ደግሞ ፓስፖርት ለማውጣት ቁም ስቅል ሆኗል ተብሏል። ወዳጆች ነገሩን ሲያወሩት ይኽን ያህል የተጋነነ ችግር አልመሰለኝም ነበር። ሰው እንዴት ፓስፖርት ለማውጣት መከራውን ያያል?
 
የሚሄድበት አገር ይጭነቀው እንጂ፣ እንዴት እና በምን ተለይቶ ይስተናገዳል?
 
ማን ነው አንቺ ቱሪስት ትመስያለሽ፣ አንቺ አትመስዪም ማለት የሚችለው?
 
በምንስ መስፈርት ነው?
 
ለምንስ እንደዚያ ይደረጋል?
 
በር ዘግቶ ስደት አስቀርተናል ለሚል ሪፖርት ነው?
 
ማንኛውም ሰው ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት አለው።
የሚሄድበት አገር አልቀበል ካላለው በስተቀርም፣ የፈለገበት ቦታ ሄዶ የመስራት እና የመኖር መብት አለው።
 
መብት የሆነውን ነፍገው፥ ምን ሸፍጥ እንዳሰቡ እንጃ… በጎን ለጎዳና ተዳዳሪዎች እና ለረጅም ጊዜ አዲስ አበባ ውስጥ ለኖሩ ሰዎች ጊዜያዊ መታወቂያ እንሰጣለን ይላሉ። ለምን አስፈለገ?
 
በዚህ በግርግር የቀበሌ ቤቶች ከድሃ ተነጥቀው ለባለጊዜ እየተሰጡ ነው ተብሎ በሚወራበት እና ምርጫና፣ ሕዝብ እና ቤት ቆጠራ በደረሰበት ጊዜ መታወቂያ መስጠቱ ለምን አስፈለገ?
 
መታወቂያው ቀርቶ ፓስፖርት ይሰጣቸውና እንደኢዮጵያዊ ይቆጠሩ።
 
#የጉድአገር

የምናፍቃቸው ዜናዎች…

06-Bidens macroptera - Adey abeba - 10-Verso Gimma-05-Mascàl-DSC01754
– መንግስት ከሕዝብ የሚሰበስበውን ግብር ገንዘብ አወጣጥ በተመለከተ ግልጽ የሆነ አሰራር መዘርጋቱን አስታወቀ። በዚህም መሰረት በመንግስት ጥሪ ተደርጎላቸው አገር ውስጥ ገብተው ለነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እና ግለሰቦች ይደረግ የነበረው የእለት እና የማረፊያ ወጪ እንዲቋረጥ እና፣ ግለሰቦቹ/ቡድኖቹ ራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ ተወሰነ።
 
– ዘር እና ጎጥን መሰረት አድርገው ፓሪዎች እንዳይመሰረቱ፣ ጥብቅ አዋጅ ተላለፈ።
 
– ተቃዋሚ ፓርቲዎች መከባበር የተሞላበት ውይይት አደረጉ። ፓርቲዎቹ በየልሳኖቻቸው ያደረጓቸው ውይይቶች እና ክርክሮችም፣ ፍጹም መከባበር እና ለአገር በሚጠቅም መልኩ መተጋገዝ የታየባቸው ነበሩ።
 
– አድማጭ ተመልካቾቻቸውን ለማስፋት እና ስርጭቶቻቸውን በሰፊው ለማዳረስ በጋራ በነደፉት እቅድ መሰረት፣ ኦኤምኤን እና ኢሳት የ30 ደቂቃ የዜና ሽፋን ሰዓት በቅይይር ተሰጣጡ። በወቅቱ ሚዲያ ከሚዲያ ጋር ተደጋግፎ፣ ሀሳብን የመግለጽ መብትን ለማስረጽ መስራት እንደሚያስፈልግ ተገለጸ።
 
– አገሪቱ ላይ ባለው የመልካም አስተዳደር ጉድለት እና ፖለቲካዊ እና ወገናዊ ጥቅመኝነት የተቆጡ የአዲስ አበባ ወጣቶች መስቀል አደባባይ ፍጹም ሰላማዊ የሆነ የተቃውሞ ሰልፍ አድርገው፣ እስር እና ወከባ ሳይገጥማቸው በሰላም ወደየቤታቸው ተመለሱ። ፖሊስም ለሰልፉ በሰላም መጠናቀቅ ከፍተኛ ጥበቃ አድርጎ ሕዝባዊነቱን አስመስክሯል።
 
– አገሪቱ ውስጥ እየመጣ ባለው ለውጥ አማካኝነት 3 እስር ቤቶች ተዘግተው ረዳት የሌላቸው አረጋውያን መቆያ ተደረጉ።
 
– በስልጣን ዘመናቸው የሕዝብን ሀብት በመበዝበዝ እና ሰዎች ላይ ኢሰብአዊ ጥቃት በማስፈጸም የተሳተፉ ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው በወንጀለኛ መቅጫ ህጉ መሰረት ቅጣት የተበየነባቸው ሲሆን፣ በወቅቱ ያፈሩት ሀብትም ተወርሶ ለሕዝብ ጥቅም ገቢ ሆኗል።
 
– ሰዎች ሀሳባቸውን ያለገደብ መግለጽ በነበራቸው ፍላጎት የተነሳ፣ በየማህበራዊ ድረ ገጹ ፌስቡክ ላይ የነበረው ትርምስ እና መሰዳደብ በመጥፋቱ፣ ወጣቶች ሀሳብን መሰረት ያደረገ ውይይት ላይ እንዲያተኩሩ እንዳገዛቸው ተናገሩ።
 
– ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ሁለቱ ብቸኛ ፓርቲዎች በቀጣዩ ምርጫ ላይ ከፍተኛ ፉክክር ያደርጋሉ። ከወዲሁ የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን የጀመሩ ሲሆን፣ ምርጫ ቦርድም ለነጻ እና ገለልተኛ ምርጫ ዝግጅቱን ጨርሶ እየጠበቀ ነው።
 
– ጾታዊ ጥቃት እና ትንኮሳ የፈጸሙ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ለተጠቂዎቹ ፍትህ በመሆኑ ደስታ የተሰማቸው ሰዎች ገለጹ።
 
– ኢትዮጵያ ውስጥ በተፈጠረው የስራ እድል እና ሞያን መሰረት ያደረገ ውድድር መሰረት ወደውጭ የሚሰደዱ ምሁራን ቁጥር ቀነሰ። ውጪ የሚገኙ ምሁራንም ወደ አገር ተመልሰው የተለያዩ የስራ መስኮች ላይ እየተሰማሩ ነው።
 
– ህብረት ለእድገት በተባለ የወጣቶች ማህበር ውስጥ ወጣቶች በተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች ላይ ተሰማርተው አስተሳሰብን የመቀየር ስራዎችን እየሰሩ ነው። በተለይም አገሪቱ ላይ ለረጅም ዓመታት ተንሰራፍቶ የቆየውን የት/ት እጥረት ለመቅረፍ፣ በክረምት እና በእረፍት ቀናቸው የማስተማር ስራዎችን ያከናውናሉ።
ወዳጄ ጋዜጠኛ ሀብታሙ ስዩም በጋበዘኝ መሰረት፥ የምናፍቀውን ዜና በስስ፣ ድፍርሱ እንዲህ አስፍሬያለሁ። እስኪ ደግሞ የምትናፍቃቸውን ዜናዎች እንድታጋራን ወዳጄ Emebet Lakewን ልጋብዝ።
Join the #mydreamnews campaign
23434779_1710343645673534_1845674905758295091_nእንደ ቀልድም እንደቁምነገርም “ኧረ ውጪ መብላት ገደለኝ ሚስት ፈልጉልኝ” የሚል ገልቱ ሞልቷል።
 
ቤቱ ሲዝረከረክ “ለምን አንዷን አትጠቀልልም?” ብሎ መካሪም አለ።
 
ወንድ ልጅ ራሱን የጎዳ፣ ውጭ ውጭ ያበዛ እንደው “ኧረ በዚህ ኑሮ ላይ ትችለዋለህ? አንዷን ባለሞያ ፈላልገህ ማታገባ?” ይባላል።
 
ሸሚዙ የተወቀጠ የመሰለ እንደው “ኧረ ግድ የለህም አንዷን አግባ።” ተብሎ ይመከራል። ብዙ ነው ዐውዱ። ግን ያው ሁሉም “የምትገባው ሴት ሚስት ናት? ወይስ ሰራተኛ?” የሚል ጥያቄን የሚያጭሩ ናቸው።
 
ለዝርክርክ ወንዶች እንደ መድኃኒት የምትታዘዘው ሴት፣ ስትገባ አያያዟ የሚታወቅበት አይመስልም መበዳደሉ ለጉድ ነው።
 
በርግጥ “ለአንድ ብርቱ ሁለት መድሃኒቱ” ነው። የሴቶችን የማደራጀት እና የማዘጋጀት አቅምና ችሎታ ማጣጣልም አይቻልም። (ሆኖም ያ ችሎታቸው በተፈጥሮ ብቻ የሆነ ነው ብዬ አላስብም። የኑሮ ጣጣ እና ማኅበራዊ ሁኔታችን የጫነባቸው ይመስለኛል። አብዛኞቻችን፥ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ በሴቶች ትከሻ ላይ ነው ቆመን የምንሄደው። አሁን አሁን የሰለጠኑ አባቶች እየመጡ ነው እንጂ፥ ለልጅ የሽንት ጨርቅ መቀየር አንስቶ ምግቡን እስከማሰናዳት ድረስ የእናቶች ድርሻ መሆኑን እናውቃለን። እናቶቻችንና እህቶቻችን ካልሲዎቻችንን ሳይቀር አጥበውልን፣ ልብሶቻችንን ፈትገው ቦታ ቦታ አድርገውልን ነው ያሳደጉን። እኛ ቀና ብለን አምረን እንድንጓዝ፥ እነሱ ጎንበስ ብለው ኖረዋል። አመስግነናቸው አናባራም!!)
 
ከኑሮ ጫና የተነሳ የሚያድርብን የማግባት ሀሳብ ቤቱን ቤት ያደርገዋል? ለልጃችን “እናትህን ያገባኋት ኑሮ ከብዶኝ እንድታስተካክልልኝ፣ ቤቱን መላ መላ እንድትለው ነው።” የማለት አቅም ይኖረናል? ልጆቻችንን ጊዜያቸው ደርሶ ስንድር፥ የተወቀጠ ሸሚዙን እንድትተኩስ የታሰበችበት ቤት እንድትገባ እንፈቅዳለን? የዘመመ አጥሬን ያቃናልኛል ብላ የትዳር ጓደኛ የምትፈልግ ሴት ብትኖርስ ሳይጎረብጥ ይዋጥልናል?
 
ይኽን ይኽን ሳስብ፥ ወዳጃችን ጋዜጠኛ እና ደራሲ Tewodros Teklearegay “የእኔ ሳሎን!” ብሎ በራሱ አንደበት ጭምር “ግራ የሚያጋባውን” ያለውን እጅግ የተዝረከረከ ሳሎኑን አስጎብኝቶን ነበር። በወቅቱ ስድብም ጭምር ለመቀበል ዝግጁነቱን ገልጾ ስለነበር፥ እኔም ፈቃዱን ተገን አድርጌ የበኩሌን ተንፍሼ ነበር። የማከብረው ወዳጄ እና የማደንቀው ባለሞያ ነውና አስተያየቴ ፎቶው የጫረው ነው እንጂ ሌላ አልነበረም። የሚያዝናኑ አስተያየቶችም ጭምር ሰፍረው ነበርና፣ ዝርዝሩን ለመዝናኛ ለመመልከት እነሆ ማስፈንጠሪያው። በዚያው ወዳጁ ሆናችሁ ቤቱን ተቀላቀሉ።
 
የእኔን ትኩረት የሳበው ግን ከአስተያየቶቹ መካከል በርከት ያለው ጎራ ውስጥ የሚመደበው ከላይ ያነሳሁት የ“ለምን አታገባም?” ዓይነት መሆኑ ነው። የተጀመረውም “ርዕሱን ሚስት የሻትን (ተኪላ ሳንል) ለት ቢባል ቴዲ” ከሚል ፈገግታ አጫሪ አስተያየት ነው።
 
“ሳሎንህ የሚስት ያለህ እያለ ይመስላል”
 
“You need to have a decent Habesha woman!”
 
“የምታገባህ ፈረደባት። ይብላኝ ለእሷ”
 
“አግባ ግድ የለህም”
 
“ቺኳ የታለች?”
 
“አይ የሠው ነገር እኔ የምመክርህ አግባ ብዬ ነው”
 
“አግባ አግባ”
 
“…ቶሎ ብለህ አግባ ግን ያው ከከተማ ፅዳትና ውበት ቢሮ እንደሚሆን ላንተ አይመከርም”
 
“ቴዲ ይሄ ሁሉ የሆነው አነተ ያዝረከረከውን ወጣ ስተል የምትሰበስብልህ በለማዘጋጀትህ ነው…”
 
“….ከትዳር በፊትና በሆላ ብለህ ደሞ ትዳር ስትይዝ የቤትህን ሁኔታ ብታሳየን ደስ ይለኛል።”
 
“የባለትዳር ቤት አይመስልም”
 
“አለማግባትህን ወደድኩት”
 
“ሴትዮዋ ብትኖር እንዲህ አይሆንም ነበር፤ አስብበት።”
 
“ምንድን ነው መዝረክረክ? አንዷን አስገባ እንጂ…”
 
“…አየህ ሚስት እንኳን የለህም…”
 
“ሚስትህስ የለችም ወይስ….”
“ሚስት የለህም ማለት ነው?” ብሎ የጠየቀና፥ ማርከሻውን “የእሷ የሆነ ነገር ስላልጻፍክ ነው” ብሎ ያስከተለም አለ።
 
“ሚስት የቤት ሰራተኛ ነች??” ብሎ የጠየቀ እና “ለማለት የፈለገችው ብታገባ እንድትዝረከረክ እድል አትሰጥህም፤ ቆማ አንድ በአንድ ታስለቅምሀለች ለማለት ነው እንጂ እሱ ያዝረከረከውን እሷ ታስተካክላለች ለማለት አይደለም፡፡” ብሎ ያስተባበለ አዎንታዊ አስተያየት ሰጪዎችም አሉ።
 
እንዲሁም “ሚስት የለኝም ለማለት ነው በጣም ሚገርመው ኮሜንቶችህ ላይ አግባ ያሉ ብዙዎች ናቸው ለሰራተኝነት ነው ምትመጣው ወይስ ለሚስትነት? ደሞ ቤት ሲዝረከረክ ነው ሚስት ምትታወሰው” ያለ ሌላ አያዎ አስተያየትም አለ። “ሚስት የለኝም ለማለት ነው” አባባሉ ያው ሚስቶች ሚናቸው ቤት ማስተካከል እንደሆነም ጭምር ማውሳቱ ይመስላል። ቀጥሎ ደግሞ “ለሰራተኝነት ነው የምትመጣው ወይስ ለሚስትነት?” ብሎ ይጠይቃል።
 
“…በጊዜ አግብተህ ቢሆን እንዱህ አትሆንም ነበር ጓደኛዬ አሁንም አረፈደም ግን እንዲህ አዝረክርከህ እንዳትጠብቃት” ያለ አስተያየት ሰጪም አለ። ይኼም ያው አያዎ ነው።
በመሀል ቴዲም “ኧረ ጎበዝ ሰው እንዴት ተጨካክኗል? ወንዶቹስ ግድ የለም የራሳቸውን ቤት ደብቀው ይሳደቡ። ከሴቶቹ ግን እንዴት አንድ እንኳን “ልምጣና እናስተካክለው” የምትል ትጠፋለች ? ትዝብት ነው።” ብሎ እንደ ቀልድ ጽፏል።
 
እንዴት ነው ነገሩ?
 
ሚስቶቻችንን የምናገባው ለምንድን ነው? ለተዝረከረከ ቤታችንን እንዲያስተካክሉ የምናምናቸው እና እነሱን የምንጠብቅ ከሆነ፣ በሌሎች ጉዳዮቻችን ላይስ ላለማሳተፍ (to be inclusive) ምንድን ነው የሚያግደን? ማኅበረሰቡ ግማሽ በግማሽ ጎራ ለይቶ የሚበዳደልበት ጉዳይ ነውና ያሳስባል።
 
ሰላም!
 
#Ethiopia

Adwa_Menelik

ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ በ፲፱፻ ዓ/ም የዠመራቸው በሽታ እየጸና ሔዶ በመጨረሻ ሰውነታቸው ዝሎ፣ አንደበታቸው ተዘግቶ እንደቆየ በታኅሣሥ ፫ ቀን ፲፱፻፮ ዓ/ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። የሸዋ ንጉሥ (፲፰፻፶፯-፲፰፻፹፩) በኋላም፣ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት (፲፰፻፹፪-፲፱፻፮) በነበሩበት ዘመን ሁሉ ክፉውን በክፉ ሳይሆን፣ ክፉውን በደግነት እየመለሱ ጥፋትን ሁሉ በትዕግሥት እያሸነፉ፣ አገር የሚሰፋበትን ልማት የሚዳብርበትን፣ ሕዝብ ዕረፍትና ሰላም የሚያገኝበትን ከማሰብና ከመፈጸም አልተቆጠቡም። የአውሮፓን ኃያል መንግሥት በጦር ሜዳ በማሸነፍ ኢትዮጵያን በዓለም እንድትደነቅ አድርገዋል።

የዳግማዊ አፄ ምኒልክን ዜና ዕረፍት በወቅቱ ለመደበቅ ቢሞከርም ወሬው ካንዱ ወደሌላው እየተላለፈ ነገሩን የተረዳው ሁሉ፣ «እምዬ ጌታዬ፣ እምዬ አባቴ» እያለ በየቤቱ ያለቅስ ነበር። ከአልቃሾቹ አንዱ፣

ፈረስ በቅሎ ስጠኝ ብዬ አለምንህም
አምና ነበር እንጂ ዘንድሮ የለህም፤

አለ ይባላል። በንጉሠ ነገሥቱም ሞት ዋናዎቹ ሐዘንተኞች ባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ፣ ልጃቸው ወይዘሮ ዘውዲቱና ብዙ መኳንንት አሉ። በልቅሶውም ጊዜ እቴጌ ጣይቱ፣

ነጋሪት ማስመታት፣ እምቢልታ ማስነፋት ነበረ ሥራችን፣
ሰው መሆን አይቀርም ደረሰ ተራችን›› ብለው ገጠሙ ይባላል።

ከልጅ ኢያሱ ቀጥለው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ወለቱ ለምኒልክ ተብለው የነገሡት ልጃቸው ወይዘሮ ዘውዲቱ የሚከተለውን ሙሾ አወረዱ።

እልፍ ነፍጥ በኋላው፣ እልፍ ነፍጥ በፊት፣ ባለወርቅ መጣብር አያሌው ፈረስ፣
ይመስለኝ ነበረ ይኼ የማይፈርስ።
ሠላሳ ሦስት ዘመን የበላንበቱ የጠጣንበቱ፣
የትሣሥ ባታ ለት ተፈታ ወይ ቤቱ።
ብትታመም ልጅህ እጅግ ጨነቀኝ፣ ብትሞትስ አልሞትም እኔ ብልጥ ነኝ።
ወልደውኛል እንጂ እኔ አልወለድሁዎ፣ አንዠቴን ተብትበው ምነው መሔድዎ።
አሳዳጊ አላንተ አላውቅም እናት፣ ምነዋ ሞግዚቴ እንዲህ ያል ክዳት።
ቀድሞ የምናየው የለመድነው ቀርቶ፣ እንግዳ ሞት አየሁ ካባቴ ቤት ገብቶ።
እጅግ አዝኛለሁ አላቅሽኝ አገሬ፣ የሁሉ አባት ሞቶ ተጐዳችሁ ዛሬ።
ትንሽ ትልቅ አይል ለሁሉ መስጠት፣ ከጧት እስከ ማታ ያለመሰልቸት።
ድርቅ ሆኗል አሉ ዘንድሮ አገራችሁ፣ ዝናሙ ሲጠፋ ምነው ዝም አላችሁ።
አሻግሬ ሳየው እንዲያ በሰው ላይ
መከራም እንደሰው ይለመዳል ወይ።

/አቶ ተክለጻድቅ መኩርያ፥ «ዐፄ ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት» ውክፔዲያ ላይ እንደተጠቀሰው።/

ኢትዮጲያ: በግራ መጋባት ወደ እርስ-በእርስ ግጭት!      — Ethiopian Think Tank Group

አሁን ባለው የኢትዮጲያ ፖለቲካዊ ሁኔታ ላይ ከፍተኛ ግራ-መጋባት ይታየኛል። ግራ መጋባቱ በዋናነት “ሀገሪቱ ወደየት እያመራች ነው?” በሚለው ጥያቄ ላይ የተመሰረተ ነው። ይህ ግራ መጋባት ታዲያ በአንዱ ወይም በሌላኛው ወገን ላይ ሳይሆን በሁሉም ወገኖች ላይ የሚስተዋል ነው። የገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች እና ደጋፊዎች፣ በብሔርተኝነት እና በአንድነት ጎራ በተሰለፉት ተቃዋሚ የፖለቲካ መሪዎችና ደጋፊዎች ላይ በግልፅ ይስተዋላል። […]

via ኢትዮጲያ: በግራ መጋባት ወደ እርስ-በእርስ ግጭት!      — Ethiopian Think Tank Group