‘ከስሜት ባሻገር’

ቅዱስ ላሊበላ፥ ከአንድ ወጥ ድንጋይ፣ መሰረቱ ከጣራው የተጣለ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን በሚያስደንቅና የሰው ልጅ ሊያስበው በማይችለው ጥበብ አንጾ አበረከተልን። ዓለም ዛሬም ድረስ በኪነ ህንጻው ይደመማል። ያየው ሰው ሁሉ ይደነቃል። “ላሊበላና ሞት ሁልጊዜ አዲስ ነው” እስኪባል ድረስ በታየ ቁጥር አዲስ ነው።

ምን ያህል የተጻፈ ቢነበብ፣ የተቀረጸ ቪዲዮ ቢታይ፣ ነገር አዋቂ ሰው ሲተርክ ቢሰማ፥ ደርሰው ሲያዩት ስሜቱ ከቃላት በላይ ነው። ልክ ልጅ መውለድን በሉት። (በዚሁ አጋጣሚ ያላያችሁት እዩት።) የራስን ልጅ ወልደው እስኪያቅፉ ድረስ፥ ምን ለልጅ ቢንሰፈሰፉ፣ የስሜቱን ከፍታ ያውቁት ዘንድ ከባድ ይመስለኛል። እንዲህ ያለውን ድንቅ ነገር ላሊበላ አበረከተልን።

እኛ ደግሞ፥ ለላሊበላ አድናቆት ይሁን ተብሎ፣ እጅግ በረቀቀ ቋንቋና ምስክርነት ከተጻፈ ወስዋሽና ቀስቃሽ ውዳሴ ጽሁፍ ውስጥ “አዳራሽ” የሚል ቃል መዘን፥ የነገርንና የክርክርን ድንጋይ ስንፈለፍልና፣ ጥላቻንና ፍረጃን ስናንጽ እንውላለን። ውዳሴ አጻጻፉ ላይ ስህተት ቢኖር እንኳን፥ ስለብዙው ጥሩ ነገር አድንቀን መጀመር እንችል ነበር። (በጣም የደነቀኝ ደግሞ፥ ላሊበላን አይቶት የማያውቅ ሰው ሁሉ በጉዳዩ ላይ አስተያየት ሲሰጥ ነበር።)

ላሊበላ አካባቢ የነበሩት ድንጋያት ወደ ድንቅ አብያተ ክርስቲያናት ሲፈለፈሉ፥ በሌላ ቦታ ድንጋይ አልነበረም ማለት አይደለም። ቅዱስ ላሊበላ ድንጋያቱን ለህንጻ ቤተክርስቲያን አልሞ፣ ጥበብን ከፈጣሪ ጠይቆ ሲያገኝና ሀሳቡን ሲያሳካ፣ ሌሎች ድንጋያት ግን ለሌሎች ተግባራት ውለው ነው። ልክ እንደዚሁ፥ ነገርን ሁሉ በበጎም በጠማማም መልኩ መመልከት ሊፈጠር ይችላል።

ፋሲካን ለመብላት ቦታ እንዲያሰናዱ ጴጥሮስንና ዮሐንስን ሲልካቸው “ወዴት እናዘጋጅ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲሉት፥ “እነሆ፥ ወደ ከተማ ስትገቡ ማድጋ ውኃ የተሸከመ ሰው ይገናኛችኋል፤ ወደ ሚገባበት ቤት ተከተሉት፤ ለባለቤቱም። መምህሩ። ከደቀ መዛሙርቴ ጋር ፋሲካን የምበላበት የእንግዳ ቤት ክፍል ወዴት ነው? ይልሃል በሉት፤ ያም በደርብ ላይ ያለውን የተነጠፈ ታላቅ አዳራሽ ያሳያችኋል፤ በዚያም አሰናዱልን። ሄደውም እንዳላቸው አገኙና ፋሲካን አሰናዱ።” እንዳላቸው በመጽሐፍ ተነግሮናል። (የሉቃስ ወንጌል 22: 1-12; የማርቆስ ወንጌል 14:1-15) በመዝሙረ ዳዊት 47: 12 -13ም “ጽዮንን ክበቡአት፥ በዙሪያዋም ተመላለሱ፥ ግንቦችዋንም ቍጠሩ፣ በብርታትዋ ልባችሁን አኑሩ አዳራሽዋን አስቡ ለሚመጣው ትውልድ ትነግሩ ዘንድ።” ተብሎ ተጽፏል።

ከዚህ የምንረዳው፥ “አዳራሽ” የሚለው ቃል፣ ሆን ተብሎ የተጣመመ አገባብ እንደሌለው ነው። መዝገበ ቃላት ብናገላብጥም፥ “አዳራሽ ማለት ታላቅ ቤት፣ ብዙ ሰው የሚያገባ፣ ይኸውም ክብ፣ ሰቀልኛ ነው።” ወይም “ወደ ታሰበበት ነገርና፣ ጉዳይ የሚያደርስና የሚያገናኝ አድራሽ፣ አቃራቢ።” ተብሎ ይተረጎማል። ለእኛ ግን፥ ለላሊበላ አድናቆት “ኢአማኒ ነኝ” ባለ ሰው በተጻፈ ጽሁፍ የተነሳ ቃል መዘን ለክርክር እናውለዋለን።

ቁጣ፣ ክርክር፣ ተሳዳቢነት፣ ዛቻና ፌዘኝነት በመጽሐፍ ቅዱስ አንዱም ጋር በአዎንታዊ መልኩ አልተጻፈም። እንዲህም አልተማርንም። ሆኖም ግን፥ የምናምነው አምላክ የማይወደውን ነገር ተጠቅመን፥ በሀይልና በማንኳሰስ፣ በትምክህትና በመመጻደቅ የእርሱን ቤት እንዳስከበርን እናስባለን። ነገር ግን “ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም አላቸው።” (የሉቃስ ወንጌል 5፥32) ተብሎ ተነግሮናልና እግዚአብሔር ማንን መቼ፣ እንዴት እንደሚጠራ ስለማናውቅ፥ “ኢአማኒ ነኝ” ላለ ሰው የማርያም መንገድ በሚከለክል መልኩ ሆ ብለን እንነሳለን። ከዚህም ባሻገር “እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል።” (የሉቃስ ወንጌል 15፥7) ተብሎም ተነግሮናልና ኢአማኒ ሰው ንስሐ ሊገቡ ከሚችሉ ሰዎች መደብ ነውና፥ ከጻድቃን ይልቅ በእርሱ መጠራት በሰማይ ደስታ ይሆናል።

የሆነው ሆኖ፥ ይሄ ሁሉ ሲሆንስ ምን ላይ ቆመን ነው ሌላውን ሰው የምንዘልፈው? እኛ “አማኝ” መስለንና በስሙ ክርስቲያን ተብለን በጓዳም ባደባባይም ስንት ዓይነት ጽድቅ ሰርተን ጣታችንን ለመጠቆምና ድንጋይ ለማንሳት እንረባረባለን?

“ነኝ እንዳልል፥

የት ቆሜ መሆኔን አየሁ” እንዳለው ነው ጋሽ ሰለሞን ደሬሳ።

“አሁንም ያ ቆሜአለሁ ብሎ በራሱ የሚታመን ሰው እርሱ እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ።” (1ኛ ቆሮንቶስ 10:12) ተብሎም ተነግረናልና ሁሉም ነገር እንደ እኛ ሳይሆን እንደቸርነቱ ይፈጸምልን ዘንድ እንማጸናለን።

————

ትናንት በዕውቀቱ ስዩም ላንዲት ሴትዮ አስተያየት ለጥፎ የነበረው ምላሽ ላይ “Don’t waste your time with explanations: people only hear what they want to hear.” የሚለውን የPaulo Coelho ንግግር አስተያየት መስጫው ላይ አስፍሬ ነበር። (አስተያየታቸውንም አንብቤው፥ ቁጣውና ተግሳጹ እንዲሁም ነገር ፈልፋይነቱንና የማጋጨት ፍላጎታቸውን ብቻ ነበር ለማየት የታደልኩት።) በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ እርስ በርስ ማብራሪያ መሰጣጠትና መማማር እንዳለብኝ ስለተሰማኝ ነው ይህን ሁሉ መዘብዘቤ።

የሆነው ሆኖ ሰው መርጦ ማንበብና መርጦ መረዳት ይችላል። መፍረድና መወገን ግን በፍላጎት እና በስሜት ብቻ የሚወሰን አይመስለኝም።

ሰላም!

 

ተስፋዬ ገብረአብ እና የበዕውቀቱ ስንኞች

ውብሸት ታደለ

ተስፋዬ ገ/አብ በዕውቀቱ በስም ዙሪያ የፃፈውን ፅሁፍ በማጣቀስ በዕውቀቱን የማንነት ቀውስ ውስጥ እንዳለ የሚገልፅ ፅሁፍ ፅፏል፡፡ከበዕውቀቱ ፅሁፍ ውስጥ በዕውቀቱ የግል ማንነቱን የፈታበትን መንገድ መመልከት እንደምንችል ፅሁፉም ከማንነት ጋር የሚያስተሳስረው ጉዳይ እንዳለ እኔም አምንበታለሁ፤ በቀደመው ፅሁፌም ገልጫለሁ፡፡

በመሰረቱ ማንኛውም ሰው የማንነት ጥያቄ አለበት፡፡ የማንነት ጥያቄ የሰው ልጆች ሁሉ የሚገጥማቸው የህይወት አንዱ ገፅታ ነው፡፡ ጥያቄው ያለው የማንነት ጥያቄህን እንዴት ትፈታዋለህ የሚለው ላይ ነው፡፡ አንዳንዱ ጥያቄውን በማፈን ለመፍታት ይሞክራል፡፡ አንዳንዱ ከአካባቢው አስተሳሰብ ጋር ራሱን በማላመድ በሌሎች መንገድ ማንነቱን ለመፍታት ይጥራል፡፡ አንዳንዱ የብሄር ፖለቲካ ራዲካሊስት መሆን ለመፍታት ይፍጨረጨራል፡፡ ወዘተርፈ፡፡

እንደበዕውቀቱ ያሉ ጥቂቶች ግን የማንነት ጥያቄን በዘልማድና በኋላቀር መንገድ ሳይሆን በሰለጠነ መንገድ ግለሰብ በመሆን (ሰው በመሆን ይፈቱታል)፡፡ የበዕውቀቱን ለዬት የሚያደርገው ይህን ግላዊ ጥያቄውን አደባባይ ላይ አውጥቶ መልካም ስራ ለመስራት ተጠቅሞበታል፡፡ አስቂኙ ነገር የበዕውቀቱ ግለሰብ መሆን ብዙ ብሔርተኞችን የማንነት ቀውስ ውስጥ ሳይከታቸው አልቀረም፡፡ የቆሙበትን መሰረት ንዶ እንደግለሰብ እንዲቆሙ ሲጠይቃቸው የሚያነበንቡት ተረት ሁሉ ባዶ ሆነባቸው፡፡ ማንነታቸው በቡድን ተረት ላይ የቆመ ነበርና፡፡

እንግዲህ ተስፋዬ በዕውቀቱ የማንነት ቀውስ እንደገጠመው በማሰብ የበዕውቀቱ ቀደምት የጥበብ ስራዎች ውስጥ የቡና አተላ እንደሚያነብ ሰው ሲወራጭ የነበረው ለምንድነው? የበዕውቀቱ አያት ስም ኦሮምኛ መሆኑ ብርቅና ለማንነት ቀውስ የሚዳርግ እንግዳ ነገር ስለሆነ ነው? ተስፋዬ የኢትዮጵያን ህዝብ ሁኔታ አልተረዳውም እንዳልል ቢያንስ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ስለሚከታተል የፖለቲከኞችን ስም ሳያውቅ የሚቀር አይመስለኝም፡፡ በነገራችን ላይ የማንነት ቀውሱ ተስፋዬ ገ/አብን ራሱን የሚመለከት ይመስለኛል፡፡ በትውልድ ቦታና በዘር ቆጠራ መካከል የተወጠረች ባተሌ ነፍሱን ተንኮል በመስራት የሚያሰቃያት ማንነቱን መፍታት አቅቶት ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ ተስፋዬ በዕውቀቱ የሰነዘረበትን በማስረጃ የተደገፈ ጡጫ ለመቋቋም እንዲህ ዓይነት ጭቃ ውስጥ መግባቱ በበኩሌ አቅመ ቢስነቱን ስለሚያሳዬኝ ቢያስቀኝም ያሳዝነኛል፡፡ አቅመ ቢስነቱን ለማወቅ ወደትንተናው ይዣችሁ ልግባ፡፡

በመጀመሪያ ተስፋዬ የበዕውቀቱን “ዳዊትና ጎልያድ” የተሰኘ ግጥሙን በመጥቀስ ግጥሙ ኃይማኖትን የሚያጣጥል እንደሆነ ለማሳዬት ይፍጨረጨራል፡፡ በሱ ቤት ከአክራሪ ኃይማኖተኞች ጋር ሊያጋጨው ነው፡፡ እስኪ ለዳኝነት እንዲረዳን ግጥሙን ልጥቀሰው፡-

እግዜርና ዳዊት አብረው ተቧደኑ
ብቻውን ታጠቀ ጎልያድ ምስኪኑ
አንዳንዱ ተገዶ ለሽንፈት ሲፈጠር
በጥቅሻ ይወድቃል እንኳንስ በጠጠር

ግጥም አንብባችሁ የምታውቁ ሁሉ እባካችሁ የዚህን ግጥም መልዕክት ንገሩኝ፡፡ ጎልያድን የጣለው ዕጣ ፈንታው እንጅ የዳዊት ጠጠር ኃይል ኖሮት አይደለም የሚል መልዕክት አይደለምን በዕውቀቱ ያስተላለፈው?

እንቀጥል…

ተስፋዬ እንዲህ ይላል፡ “ከሚስጥራዊ ስንኞቹ መካከል ጥቂት አገኘሁ” ይልና የሚከተለውን የበዕውቄን ግጥም ይጠቅሳል፡-

በነፍሴ ሰማይ ላይ
ቢሰርቅ ጣምራ ፀሃይ
አንዱን ጋርጃለሁ
ሌላው ደምቆ እንዲታይ

“ምን ማለቱ ነው ብዬ ሳስብ የአቶ በዳዳን ኦሮሞነት ሸሽጎ አያቱ ባልሆነ ስም እየተጠራ መቀጠሉን እየተቃወመ ይመስላል አልኩ” ይለናል ተስፍሽ ባተሌው (እዚህ ጋ እንድስቅ ይፈቀድልኝ ሃሃሃሃ… የምር ይህን ፅኁፍ ስፅፍ ሳቄ እያቋረጠኝ እንደነበር መደበቅ አልሻም)፡፡ እባካችሁ ነፍስ የስጋ ዘርን የምትወክልበትን ይህን በተቃርኖ የተሞላ የስነፅሁፍ ትንታኔ በመፃፍ ላዝናናችሁ ተስፋዬ አጨብጭቡ፡፡ ልጁ “ነፍስ” ብሎ ገጠመ፤ ተስፍሽ “ስጋ” ብሎ ተረጎመለት፡፡ ወይ ጉድ!

ተስፍሽ በማስከተል የጠቀሰው የሚከተለውን የበዕውቄን ግጥም ነው፡-

ቀንድ አውጣ ሆይ!
ውብ ዛጎልህ አማለለኝ
ከጎጆህ ላስወጣህ ነው (ይቅር በለኝ)
‘በዝግ ዓለም ሰማይ ጣራ ነው’ ይባላል
ያለውበት ነው እንጅ ያለቤት መኖር ይቻላል

እንግዲህ ለመሳቅ ተዘጋጁ፤ ተስፍሽ ይህን ግጥም ሲተነትነው እንዲህ ይላል፡-

“እነዚህ ስንኞች ለኔ የሰጡኝ ትርጉም በዕውቀቱ አቶ በዳዳን ከተሸሸጉበት ዛጎል ጎትቶ ለማውጣት መወሰኑን ነበር፡፡ በርግጥም እንደፎከረው ፈፅሞታል፡፡ ያለውበት መኖር እንደሚቻል ለማሳየት ሞክሯል፡፡”

እና ይሄ ሰው አያሳዝንም? ሃሃሃ እስኪ ተመልከቱ… በዕውቀቱ “ያለቤት መኖር ይቻላል፤ የማይቻለው ያለውበት መኖር ነው እንጅ፡፡ ስለዚህ ቀንዳውጣ ሆይ ውብ ዛጎልህን ልዋብበት፤ ያለቤት መኖር ስለምትችል” በሚል ግልፅ ቋንቋ የሰው ልጅ ካለውበት መኖር እንደማይችል በመግለፅ በተለይም ውበትን የምታስሰውን ገጣሚ ነፍሱን ሊገልፃት ሲሞክር፣ ተስፋዬ ግን አማርኛውን ፍፁም ገልብጦ “ያለውበት መኖር ይቻላል” ብሎ ተረጎመው፡፡ ይህ ነገር ግጥም አንብቦ ለማያውቅ ማንኛውም አማርኛ ቋንቋን ለሚያውቅ ሰው ግልፅ ነው፡፡ ወይ ተስፍሽ!

ተስፍሽ ስለአባ ገብረሃና የተፃፈውን ግጥም ጠቅሶ የመተንተን ሙከራ እንኳን ሳያደርግ የልጅ ተንኮል ሞክሮ አልፎታል፡፡ እንዴት ለማያያዝ እንደሞከረ ለራሱ እንኳን የገባው አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ እዚህ ላይ ጊዜ አላጠፋም፡፡

ወደሌላው እንለፍ…

“በተለይ ገዢዎች ላይ ቅሬታና ቂም እየያዘ እንደመጣ የሚጠቁሙ ከጥቂት በላይ
ስንኞቹን ታዝቤያለሁ፡፡ አንዷ እንዲህ ትላለች፡”

አልወጣም ተራራ ደመናውን ላብስ
ቀስተ-ደመናውን ሽቅብ ልቀለብስ
አልዋስም እኔ ካቡነ ተክሌ ክንፍ ከያዕቆብ መሰላል
እኔ መውጣት ሳስብ ሰማዩ ዝቅ ይላል

… ዝቅ ይላል ያለው ሰማይ ስልጣን ነው”፡፡

ሃሃሃ… ይሄ ሰውዬ ግጥም ሊያስጠላኝ እኮ ነው፡፡ ይሄን የግጥም ግንዛቤውን ይዞ ነው በየመፅሃፎቹ ግጥም የሚደነጉር? ይህ ግጥም የሰው ልጆችን የምኞት ኃይልና የማድረግ አቅም የሚያሳይ ግጥም ነው፡፡ የእኛ ፍላጎትና ኮሚትመንት ካለ ሁሉን ነገር ማድረግ እንችላለን የሚለውን የምኞት ኃይል የሚገልፅ ግጥም ነው፡፡ ሌላ ነው ትርጉሙ የሚል ሰው ካለ ያስረዳኝ፡፡ ተስፍሽ ካለው ስልጣን ቅብጥርሶ ጋር የተያያዘ እንዳልሆነ ግን ከበዕውቀቱ በሚልቅ እርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፡፡ አለበለዚያ ግጥም ማንበብም ሆነ መፃፍ ባቆም ነው የሚሻለኝ፡፡

“የበዕውቀቱ ቀደምት ግጥሞች ከአሜን ባሻገር ላይ ከተጠቀሱት አቶ በዳዳ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማዬት ሞክሬያለሁ” ይላል ተስፍሽ ተንትኖት ልቡ ውልቅ ብሏል፡፡ አንድ ጤነኛ ፊደል የቆጠረ ሰው እንዴት ይሄን ሁሉ የአንድ ገጣሚ ግጥም ከአያቱ ስም ጋር ለማያያዝ ይሞክራል? እንደዛ ማሰቡ ራሱ የጤንነት ምልክት ነው?
“በዕውቀቱ የመፅሃፉን ርዕስ ለምን ‘ከአሜን ባሻገር’ ሲል እንደሰዬመው ምስጢር አልነበረም፡፡ በቀጥታ ከአያቱ ከአቶ በዳዳ ጋር ይያያዛል”

ይሄ ሰው አቶ በዳዳን ምን አድርጉ ነው እሚላቸው? አሁን ከአሜን ባሻገርና አቶ በዳዳን ምን አገናኛቸው? ተስፋዬ ይቀጥላል፡- “እሱም (በዕውቀቱም) በዚያው ምዕራፍ ላይ የሚከተለውን ገልፆ ነበር” ይልና በዕውቀቱን እንደሚከተለው ይጠቅሳል፡- “የተለያዩ ባህሎችን በአንድ በገና ውስጥ እንደተወጠሩ አውታሮች ማስተናገድ በማይታወቅበት ጥንታዊ ማህበረሰብ ውስጥ ግለሰቦች የገናና ባህሎችን ምልክት አሜን ብለው ከመቀበል ያለፈ ምርጫ አልነበራቸውም” ይሄ ምን ማለት ነው? መልቲ-ካልቸራሊዝም ስለማይታወቅበት ዘመን በማስታወስ ያን ዘመን በአሁኑ ዘመን ዕይታ እንዳናዬው ከመናገር ውጭ ሌላ ምን ትርጉም አለው?

ተገርማችሁ ሙቱ ብሎን ተስፋዬ የበዕውቀቱን አንድ ግጥም እንደሚከተለው ይጠቅሳል፡፡ የግጥሙ ርዕስ ‘ሉላዊነት’ ሲሆን ተስፍሽ ግን ለአተላ ንባቡ እንዲጠቅመው ርዕሱን ‘ሉአላዊነት’ በሚል አቅርቧታል፡፡ ተስፋዬ ብሶት ያዘለ ነው ብሎ የገለፀው ግጥም ይሄው፡-

የጋራችን ዓለም የጋራችን ሰማይ
የብቻችን ህመም የብቻችን ስቃይ

ትንታኔው፡- “በአንድ አገር ስር ዜጎች አብረው እየኖሩ፣ አንደኛው ወገን ስቃይ እንደሆነበት ሲነግረን አልገባ ብሎን ይሆን?” ይላል የገ/አብ ልጅ፡፡ ግጥሙ የሚያወራው ስለሉላዊነት (ግሎባላይዜሽን) ሆኖ ሳለ ተስፋዬ ግን ርዕሱን ቀይሮ ጠለፈው፡፡ በዕውቄ ግሎባላይዜሽንን ሊሳለቅበት የሞከረውን ግጥም ሰውዬው በቡና አተላ ስልት አነበበው፡፡

ደከመኝ፡፡ እስኪ በቀጣይ ክፍል ልጨርሰው እሞክራለሁ፡፡ እስከዚያው ተስፋዬ እንዲህ ጭቃ ውስጥ የገባው ለተንኮል ብሎ ነው ወይስ ተስፋዬ ይህን እንኳን መረዳት የማይችል ተራ የወሬ አሰናዳኢ ነበር የሚለውን ጥያቄ አስቡበት፡፡ እኔ ደግሞ የዚህን በሽተኛ ሰውዬ ፅሁፍ ከቁምነገር ቆጥሬ ጊዜዬን የማጠፋው ለምንደነው የሚለውን ጨምሬ በቀጣይ ክፍል እመለሳለሁ፡፡

ሰናይ ጊዜ!