🛑 በኢትዮጵያ የዘር ጭፍጨፋዎች ዙሪያ Genocide Watch ምን ይላል? | Ethio Teyim | Episode 57

በጣና እና እምቦጭ ዙሪያ አጠቃላይ ዳሰሳ! አጭር ቆይታ ከዶ/ር ሰለሞን ክብረት ጋር | | Ethio Teyim | Episode 33

ልዩ የኢድ በዓል ዝግጅት! አሚን በይ በቃሉ | የረመዳን ጾም | ልጅነትና የረመዳን ጾም ትዝታ | የጁምአ ጀነት | Ethio Teyim | Episode 30

አካውንቶቻችንን ከሳይበር ጥቃት ለመጠበቅ ምን ጥናቃቄ ማድረግ አለብን? | ልዩ ዝግጅት | Ethio Teyim

ካለ ሰው…

DS1j6ZEX0AAcrwwከነድህነቱ ወዘናው ፊቱ ላይ ጨፍ ያለ ምስኪን፤ ዘሩ ምን ሆነ ምን፥ ፈገግታው ከልቡ ፈልቆ ፊቱ ላይ፣ ጥርሱ ላይ፣ ዐይኑ ላይ፣ ግንባሩ ላይ ሁሉ የሚከለበስ ድሃ። ቂጡ ሁላ የሚስቅለት ዕድለኛ፥ ምንም የሌለው፣ ሁሉም ያለው። የአዲስ አባ ሰው፣ የአገር ሰው!
 
ገመድ እና አንድ ሁለት የተሳሉ ማረጃ ቢላዋዎችን ይዞ አሳራጅ የሚቃርም በሬ አራጅ። የበግ ቆዳ ያሌው። በአዲስ ልብስ ያሸበረቁ፣ በአዲስ ልብስ እና በጸዴ ምግብ ተስፋ በቀብድ የሚቦርቁ ሕጻናት።
 
እዚህ እና እዚያ በወዳደቀ ቀጤማ፣ መንገዱም የበዓል ይመስላል። የሚነሳለት ቆሻሻ ባይኖርም፣ ሁሉም የበዓል መልኩን ይይዛል። በፍቅር ዐይን እንደሚያዩት ሁሉ፣ ያምራል! በዋዜማ እና በእለቱ ፀሐዩዋም ትለያለች። የቅዳሜ ፀሐይ ተሞሽራ ተኳኩላ ማለት ነው!
 
ከየቤቱ፣ ከየግሮሰሪው፣ ከየሱቁ፣ ከየመደብሩ የሚወጣው የ”ስንት ገባ ዶሮ” …”ቅቤ እና ሽንኩርቱ እንዴት ነው?” …”ሰንጋው ስንት ተገዛ?” …”ቅርጫ ተሟላችሁ?”… ጥያቄው፥
 
“እኔማ ቀን አቁላላቼ ጣጣዬን ጨርሻለሁ” …”ጠላው አልፈላ አለኝ” …”ሸቀበኝ። ቀላጭ ዱቄት ሆነብኝና ዳቦው ማስቲካ ሆኗል።” …”ትንሽ ቂጡ አረረብኝ ባክሽ” …”ኤጭ! መብራቱን አስሬ ሲያበሩ ሲያጠፉት ዳቦውን አበላሹብኝ” …”ሊጥ ታቅፌ ቀረሁ። መብራቱ ሚመጣም አልመሰለኝ። ማዕድቤት ገብቼ ልጋግር እንጂ” የሚሉ የሚራገሙ፣ የሞኮሩ ድምጾች፥
 
እና፣ ሙዚቃ… የበዓሉን ጠረን ይዞ በየመንገዱ ላይ፣ በየቅያሱ ላይ ይደፋዋል። ሁሉም የራሱን ቅባት ከሌላው ቅባት እየቀየጠ ፊቱን ይደባበሰዋል። በጠረኑ ጦዞ ከፍ ይላል። በዓል አልወድም የሚል ዘበናይ እንኳን ከሁሉም አይጎልም። የግዱን እንኳን አደረሰህ/ሽ ተባብሎ ይተቃቀፋል።
 
ሻኛቸው ብቻውን፣ ከእሱ በቀር ያለው ሰውነታቸው ብቻውን የሚንጎማለሉ የእርድ ከብቶች፣ ከዚህም ከዚያም ድምጻቸው የሚሰማ በግና ዶሮዎች እንደ ቅርብ ዘመድ ትዝ ይላሉ።
 
የላቱ ሙቀት በህጻናት የተለካ፣ ቆለጥ እና ፊኛው በቁም እያለ ህጻናቱ የእኔ ነው የእኔ ብለው እጣ የተጣጣሉበት፣ ደግሞ ከታረደ በኋላ ሰባ አልሰባ የሚባልለት፣ ከታረደ በኋላ የተመገበው ሳር ዓይነት እና የመጣበት ቦታ ሳይቀር እየተጣጣመ የሚተረክለት፣ በግ። ቀዥቃዣ ባህርይው ከእድገቱ ጋ ተዳምሮ የሚወሳለት ፍየል።
 
በየቅያሱ የተገዛላቸውን አልባሳት በኩራት እያወሩ በደስታ አፕዴት የሚደራረጉ፣ ኮሜንት የሚሰጣጡ፣ ላይክ የሚገጫጩ ህጻናት (አንዳንዶቹም ለናሙና ለብሰው የሚወጡ)፣ ያገኙትን በጊጩ እና ወጋሁ አጀባ ሼር የሚደራረቁ ንጽሀን፥ ለዓመት በዓል ብቻ ከፊት የሚጸዳ ንፍጥ ያለባቸው ህጻናት፣ ፊታቸው እንደ እርጥብ መሬት ሙትክ ሙትክ የሚል እንኳን ንፍጥ ሊታይባቸው ሲያስብ ተሯሩጦ አናፋጭ ያላቸው ብርቱካን መሳይ ፊቶች፥ ግን ደግሞ ዝርክርኩም ንጽሁሁም እኩል የሚያምሩ ህጻናት፥ ሁሉም የሚያወጡት ልዩ የበዓል መልክ አለ።
 
የበዓሉን ዋና ቀንበር የሚሸከሙት፣ እረፍት የሚናፍቃቸው፣ ኋላ እግሩን ዘርግቶ የቴሌቪዥን ጣቢያ በሚቀያይር ወጠምሻ “አሳረርሽው” “ቅባት ሞጀርሽበት” “ጨው አሳነስሽው” “አላበሰልሽው” የሚል ወቀሳ ሁሉ ሊደርሳቸው የሚችል፣ ቤቱ ሙሉ መሆኑን የሚያረጋግጡት ሴቶች።
 
በዓል ደርሶባቸው ልጆቻቸው ከሰው እንዳያንሱ የሚሳቀቁ ወላጆች ከርታታ ዐይን፥ ቢያምም የራሱ መልክ አለው። ለበዓል በተለየ መልኩ የተፈታ፥ ሀምሳ ሳንቲም ከመስጠት አስር ብር ወደ መስጠት የተሸጋገረ ለጋስ እጅ። ያለውን ቤት ያፈራውን አጥፎ ለጎረቤቱ የሚያቃምስ ደግ። የለው እንዳይባል ለዓመል ሰርቶ፣ አለው እንዳይባልና በደግነት እንዳይሰጥ ያለውም አንስቶበት በፀፀት አንጀቱን የሚበላው ምስኪን።
 
ጥርስ ውስጥ ስጋ ገብታ ሰላም ነስታ ስታስጨንቅ ጊዜ ከመሬት አንስተዋት ሰላም ያገኙባት የስንደዶ ስንጣሪ እንኳን እንደ ትልቅ ቁም ነገር ከነመልኳ እና ሁኔታዋ በዐይን ትዞራለች።
 
ሁሉም ይናፍቃል።
 
የትም ቢሄዱ፣ እንዴትም ባለ ስሜት ውስጥ ቢሆኑ፥ በዓል ጠረኑን አያጣም።
 
የመርካቶን ደጃፍ ካልረገጡ ግን አይሞላም!
 
በሽንኩርት ተራ ተሽሎክሉከው፣ ሳህን ተራ ጎራ ብለው ዱኙን፣ ቀበሪቾውን፣ ሀደሱን፣ ቀስሉን፣ እጣኑን፣ ከርቤውን፣ ጭሳጭሱን በያይነቱ ዘረጋግተው የሚሸጡት እናቶች ጠረን ካልታከለበት ይጎላል።
 
በበርበሬ በረንዳ በኩል አልፈው አንድ ሁለቴ ካላነጠሱ ምኑን በዓል ሆነ? ሰባተኛ ወርደው ቀጤማውን፣ ጠጅሳሩን፣ አሪቲውን እጅ ካልነሱ ምኑን ደመቀ?
 
ክንዴ ቡቲክ፣ እልል በል ሀበሻ፣ አላየሁም አልሰማሁም እንዳትል፥ ለየት ያለ የበዓል ቅላጼውን ካልለቀቀ ምኑን ዋዜማ ሆነ?
 
ታታሪው በያይነቱ፣ ፌሽታው በየቤቱ ነው። ሁሉም በያይነቱ ይሸጣል። መርካቶ የሰው ሰፈር!
 
ግን የባሰም አለ።
 
የሰው አገር በዓል፥ ሁሉም ያለው፣ ሁሉም የጎደለው።
 
ቀጤማው ባይጎዘጎዝም፣ ጠጅ ሳር እና ሀደስ ባይሸቱም፣ ከሴው ከአየሩ ጋ በድሪያ ስሜት መጥቀው እኛንም ባያሳብዱን የአልሞት ባይ ተጋዳይ ትግል አይቋረጥም።
 
የአዲስ አባ ውሃ ያልነካው ከሰው ያልጠጡት ቡና ቡና ባይሆንም፣ እንዳቅሙ ኤክስፖርት ስታንዳርዱ ተመርጦ ፣ እንደነገሩ እጣኑም አብሮት ቢነግስም፣ ተቆልቶ በአፍንጫ ተምጎ፣ ይፈላል።
 
በጉ ደጃፍ ታስሮ ለሁለት ለሶስት ቀን ድምጹን እያሰማ፣ ሲወጡ ሲገቡ በዐይን እየቃኙት፣ ሳር ውሃውን ባይቀርቡለትም፥ ከቦታው ታርዶ ተበልቶ ይመጣል።
 
ቅርጫ ገብተው፣ ከብት አማርጠው አራጅ ጠርተው ከነሙሉ ክብሩ እና ማዕረጉ ባይከፋፈሉትም ስጋውም ከኪሎ እስከንቅል አለ።
 
አተላው ይደፋ፣ አምቡላው ይጣል ባይባልም፥ ጠጁም ጠላውም እንዳቂሚቲ አይጠፉም።
 
ካቴም በያይነቱ ተሞሽራ አለች።
 
ግን መንፈስ እና ጠረን ይርቁታል። ውሃ ውሃ ይላል።
 
ሞቅታውም በለሆሳስ ነው። እቃ እንደረሳ ሰው፣ በአሁን እነሳለሁ ዓይነት ዱቅ ብለው፣ በዜና እየበረዙ፣ በአገር ቤት ወቅታዊ ወሬ እያዋዙ ስለሚጠጡት አንጎል ጋ ሳይደርስ፣ ሆድ ሳያጠረቃ ይተናል።
 
እናት እናት የሚል ሽታ፣ አባት አባት የሚል ጠረን የለም። ዶሮ ዶሮ፣ ጓሮ ጓሮ የሚሰማ ቅያስ የለም። ሰክሮ የሚወላገድ የለም። ለድጋፍም ለበረከትም እጅ የሚዘረጉለት ምስኪን የለም።
አንዱም የሌለው፣ ምናልባት ስጋውን በፈረንጂ ካቴ የሚያወራርድ የባሰበትም ብዙ ነው።
 
ግን ምኑም ካለ ብዙ ሰው አይጣፍጥምና፣ የትም ሆኖ ሰው ያለው፣ ሁሉም ቦታ አለ!
ያለንን የምናካፍልበት፣ ከእኛ የባሱትን የምናስብበት በዓል ያድርግልን! ጌታችን መድኃኒታን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን ተወልዶ መከራውን ሁሉ እንደተቀበለ፣ እኛም እንዲሁ ሰውነትን አስቀድመን ወንድሜ እህቴ በመባባል ያኑረን!
 
መልካም በዓል ይሁንልን!

ስለሀሳብ ልዕልና ሲወራ…

ምርጫውን ፍትሀዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የተደረገው የቃል ተስፋ መልካም ነው። እግዚግዚአብሔር ፈቅዶ ምርጫው ነጻ ሆኖ ቢከናወን ግን፣ ኢህአዴግ በምን ቁመናው ሊቀጥል ይችላል? 🤔
 
በርግጥ “ከማያውቁት መልዐክ የሚያውቁት ሰይጣን” በሚል ብሂል የሚገብርላቸው ሊኖር ቢችልም ቅሉ፥ ለክፋታቸው ሲነዙት የኖሩት የብሄር አጀንዳ መልሶ እነሱኑ ሳይሰለቅጥ የሚመለስ በማይመስል መልኩ ተቀጣጥሏልና፥
 
“ምርጫው በነጻ እና ፍትሀዊ መንገድ እንዲደረግ ፈቃደኞች/ቁርጠኞች ነን” ማለታቸውን በራሱ፣ በሰላም እንደሚለቁ ቃል የገቡ ያህል እቆጥረዋለሁ።
 
(የሚነደው ግን፥ የነጻ እና ፍትሀዊ ምርጫ ወሬ እና ምኞት እንኳን ካለነሱ ፈቃድ የማይቻል የነበረ መሆኑ ነው። ይኽንንም ውለታ እንደዋሉ እንጂ መሆን እንዳለበት አይቆጥሩትም።)
 
ኢህአዴግ “ሀሳብ ሸጠን ነው የምናሸንፈው” ሲልና ስለሀሳብ ልዕልና ሲያወራ መስማት ይገርማል። እንደው ምናልባት በታምራት ደስታ (ነፍስ ይማር)
 
አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ
“አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ”
 
ብለው ይጀነጅኑን እንደው እንጂ ምን ቀራቸው?
 
አብረው ተባብረው ዘረፉ፣ ገረፉ፣ ደፈሩ፣ አባረሩ፣ ጣት ቀሰሩ፣ ጣት እንቆርጣለን ብለው ፎከሩ፣ ከፋፍለው አባሉ፣ ቀለም ጠልተው ቀለም ደፍተው፣ የቀለም ቀንድ ሰባብረው፣ ሕዝቡን በድንቁርና አጥረው አኖሩት፣ (ከርሞ ማመናቸውም ተመስገን ነው)፣ ምኑ ቅጡ ተሰፍሮ ተዘርዝሮ ያልቅና?
 
በተጭበረበረ ምርጫ ገነው፣ አሁንም በየመሀሉ በሊቀመንበራቸው በኩል “ተፎካካሪ” ያሉትን ይወቅሳሉ። ያስጠነቅቃሉ። ላይ ላዩን ገር ሆነው፣ ውስጥ ውስጡን አሁንም በሚዛን ሲቀመጡ እነሱ እንደሚሻሉ ያስባሉ። ያሳስባሉ።
 
በምርጫ ምክንያት ለተፈጠሩ ቀውሶች በሙሉ ዋናው ድርሻ ኢህአዴግ እንጂ ማን ሆኖ፣ አሁን “ወደኋላ ሄዶ ያለፈውን ማንሳት እና በትናንት መኖር አያስፈልግም” ካሉ በኋላ፣ በጨው መታጠብ ካልሆነ በቀር፣ መለስ ቀለስ እያሉ ሌላውን ለመውቀስ እና አበክሮ ለመውቀስስ ምን አቅም ያገኛሉ?
 
የኢህአዴግ ነገርማ
ያልጠፋነው፣
ከእግዚአብሔር ምህረት የተንሳ ነው”ን
እያስዘመረን የሚኖር ጉዳይ ነው!
 
እግዜር ቸር ቸሩን ያድርግልንማ!

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ…

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ ነው ስንል በምክንያት ነው። የጥቅም እና ዝርፊያ ተካፋይነቱን ሕወሃት የበላይ ሆኖ ቢሰፍርበትም፥ ትናንት ሁሉም በተመቸው እና ጊዜው በፈቀደለት ልክ ዘግኗል፣ አንገላቷል፣ በየፈርጁ እና በየደረጃውም፥ የግፉም የዝርፊያውም ተካፋይ ነበር። የሚደርሰው ወንጀል እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሁሉ እንዳይታወቅ በመሸፋፈን ረገድም ሁሉም አባል ይኽ ነው የማይባል ሚና ተጫውቷል። ምንም እንኳን በሕወሃት የበላይነት ቢዘወርም፥ የሰብአዊ መብት ጥሰቱን እና ንጹሐንን የማፈኑን ሥራም በድርጅት ደረጃ አቋም እና አተገባበር ይዘው ሲያደርጉት የነበረው ነውና፣ የጭንቀት ቀን ሲመጣ ጣት መቀሳሰሩ በኅሊና ዳኝነት ፊት የትም አያደርስም። ማናቸውም አሸባሪውን ድርጅት ሲያገለግሉ እንጂ፣ ገዳም አልነበሩም።

ሁሉም ደርሶ በድል አጥቢያ አርበኝነት ስሜት እና በለውጠኝነት ሽፋን ጣት ቀሳሪ ይሁን እንጂ፣ ለመዛኝ እና ለፈራጅነት የሚያበቃ ንጽህና ያለው ያን ያህል አይደለም። ምንም አያውቅም የሚባለው አባል እንኳን፣ ቢያንስ ዝም በማለት እና ንጹሐን ሲንገላቱ ባለመከላከል፣ ድሀ ሕዝብ ሲመዘበር የምዝበራው አበል ተካፋይ በመሆን እያመሰገነ እና፤ አባል ያልሆኑና ያገባኛል ያሉ ሰዎችን በጠላትነት እየፈረጀ ኖሯል። የኢትዮጵያ አምላክ ራቁት እሲያስቀር፣ የጊዜ ፈረስ እንዲህ በአፍጢም እስኪፈጠፍጥ ድረስ!

በርግጥ፥ አንድም ይሁን ሁለት፣ ያጠፋ ሰው መጠየቅ መጀመሩ አግባብ ነው። ሆኖም ግን፥ የሌላው ነውረኝነት አለመጋለጥ፣ የተጋለጡትን እና በህግ ለመጠየቅ መንገድ የተጀመረላቸውን ሰዎች ጉዳይ ስህተት አያደርገውም። ዛሬ ጊዜው ፈቅዷል፣ ትናንት አልፏል በሚል ቀመር፥ አብረው ሲፈተፍቱ፣ የሕዝብ ደም ሲገብሩ እና ነውሩን ሲጋርዱለት፣ በታማኝነት እና ቁርጠኝነት ሲያገለግሉት የነበሩትን ድርጅት “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ” በሚል ጲላጦሳዊ ግብዝነት ሲነዛ ግን፥ አሁንም ህሊና ካለ ይፈርዳል።

እንደማሳያ፥ ሰሞኑን በድፍረታቸው እና አጋላጭነታቸው ተደንቀን፣ አፋችንን ከፍተን ሀቀኝነታቸውን የመሰከርንላቸውን አምባሳደር ሱለይማን ደደፎን የትዊተር ገጽ በጊዜ ወደ ኋላ ተመልሰን በመቃኘት ነገሬን ልቀጥል።

አቶ ሱለይማን ዛሬ ፓርቲአቸው ኦህዴድ የበላይ ባይሆን እና ሕወሃት ቢቀጥል ኖሮ፣ ሰጥ ለጥ ብለው የሚገዙ እንጂ “ግፍ አንገፈገፈኝ” ብለው የሚለቁ አይነት ነበሩ የሚያስችል የጀርባ ታሪክ እንዳላቸው የሚያሳይ ማስረጃ የለም። በርግጥ እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ሌሎች አባላቶችም እንዲሁ ከመጣው ጋር ቀጥለው፣ በጥሎ ማለፍ ድርጅታቸውን እያሽሞነሞኑ ይቀጥሉ እንደነበር መገመትም ከባድ አይደለም። ድርጅታቸው ኢህአዴግን በታማኝነት ከማገልገል ባለፈ፥ ሲያደርግ የኖረውን ነገር በመሸፋፈን እና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በማሳጣት የተጫወቱት ሚና ብዙ ነው።

በኦክቶበር 2013 የአፍሪካ አገራት በኢትዮጵያ መንግስት አዘጋጅነት፣ እነ ኡሁሩ ኬኒያታ የሰው ልጆች ላይ ወንጀል በመፈጸማቸው  በሚል መከሰሳቸውን ለመከላከል፥ በአዲስ አበባ አስቸኳይ ስብሰባ አድርገው ነበር። አጀንዳቸውም የዓለማቀፉን የወንጀል ፍርድቤት International Criminal Court (ICC) ለመቃወም ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በተባበሩት መንግስታት ስብሰባ ተገኝተውም ፍርድቤቱን መተቸታቸውን ተከትሎ፥ የአፍሪካ መሪዎችን ስብሰባ ጠርተው ነበር። ነገሩ “ነግ በእኔ”፤ “አፍንጫ ሲመታ አይን ያለቅሳል” ነበር። በተለይ ደግሞ የነገሩ ጠንሳሽ ኢትዮጵያ መሆኗ “ፈስ ያለበት ዝላይ አይችልም” ዓይነት ነበር።

ታዲያ ያንን ተከትሎ፥ ከሁለት ወይም ከሶስት ሳምንታት በኋላ በኦክቶበር 28 ቀን፥ አቶ ሱለይማን

I am skeptical on the very intention to create the ICC. Why doesn’t it open its eyes on the whole globe than giving excess attention to Africa?

በማለት ለአምባገነኖቹ የአፍሪካ መሪዎች መቆርቆራቸውን ገልጸው ነበር።

1

ኖቬምበር 15 ቀን 2013፥ የሳውዲ አረቢያ መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ የነበረውን ስቃይ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት በማውገዝ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በሳውዲ አረቢያ ኤምባሲ ደጃፍ ላይ ለማካሄድ በጠራው የሰላማዊ ሰልፍ ላይ የወጡ ሰዎች፣ ላይ ፖሊስ የተቃውሞ ሰልፉን በመከልከል ሰዎችን ደብድቦ እና አስሮ ነበር።  ታዲያ በዚያን ቀን፥ አቶ ሱለይማን

Ethiopian Gov’t has allocated 50 million Birr to integrate Ethiopians deported from Saudi Arabia. But what do the opposition parties are doing? Ethiopian opposition parties are trying to benefit out of tears of Ethiopian migrants in Saudi Arabia as usual. Why?

ብለው በሁለት ትዊት ጽፈው ነበር።

2.jpg

በመጀመሪያ የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘቡን የመደበው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ንብረት ላይ መሆኑን ዘንግተውት እንደልግስና ቆጥረውት ተመጻድቀው ነበር። ገንዘቡ በአግባቡ ይዋል አይዋልም አይታወቅም። ሆኖም ግን፥ በወቅቱ ለወገን በመቆርቆር የተጠራን ሰልፍ ተከትሎ፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን በጅምላ ለመፈረጅ እና፣ እንደ ኢህአዴግ አባልነታቸው “ተቃዋሚዎች በሕዝብ እንባ ለማትረፍ የሚሞክሩ ናቸው” ብሎ ስም ለመለጠፍ እና፣ “መንግስት ይህን ሲያደርግ፣ እነሱ ግን ምንም እንዳላደረጉ” ለማጉላት ዳክረው እንደነበር እናያለን።

20131115163925420734_20

(እንደፓርቲ ከአባላት ከሚያገኙት መዋጮ ላይ መቋቋሚያ እንዲሰጡ ጠብቀው ነበር ማለት ነው። እንደተቃዋሚ ፓርቲነታቸውም ለዜጎች ጥቃት መቆርቆራቸውንም አቃለዋል።) ከዚህ በላይ ኢህአዴን መጋረድ እና የሰብአዊ መብት ጥሰቱን መደገፍ ከየት ይመጣል?

እነ ወ/ሮ ሚሚ ስብሀቱ፣ አቤል ተስፋዬ እና መርከብ ነጋሽ ተሳትፈውበት በነበረ “የቀለም አብዮት” ዶክመንተሪ ማግስት፥ የዞን 9 ስድስት ጦማርያን እና 3 ጋዜጠኞች ወዳጆቻችን በአፕሪል 2014 መታሰራቸውን ተከትሎ፥ አቶ ሱለይማን፣ በሜይ 1 2014፥

Zone Niners are messangers of color revolution hired by neo-liberal masters. They are instructed to create violence ahead of next election. Press Freedom is not systematic invasion or campaign to change regime by color revolution. That is what the west are trying in Ethiopia.

ብለው ንጹሀን ላይ ጣታቸውን ቀስረው፣ እና የመንግስትን ጭቆና ለመሸፈን ሞክረው እንደነበርም እናስታውሳለን።

4.jpg

የመንግስትን የተጋነኑ “የኢንቨስትመንት” ወጪዎችን በተመለከተም፥ በዲሴምበር 3፣ 2014

Where will huge state investments lead Ethiopia? Obviously to growth

ብለው ጽፈው ነበር።

6

እንግዲህ ወደ እድገት ያመራናል ያሏቸውን ወጪዎች በተመለከተ ነው፣ አሁን ያላየ፣ ያልሰማ ሆነው በጻድቅ ምስክርነት የቆሙት። ምስክርነት መቆማቸውን መንቀፌ አይደለም፣ ነገር ግን ትህትና የቀላቀለ ቢሆንና፣ ሁላቸውም መነካካታቸውን የማይክድ መንፈስ ያረበበት አነጋገር ቢሆን የሚል የከሸፈ ጉጉት እንጂ።

በሌላ ማሳያ፥ የአሁኑ የጠቅላይ አቃቤ ህግ፣ የያኔው የፍትህ ሚንስትሩ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ፥ በ2011

ያለ ፍርድቤት ትዕዛዝ አይታሰርም። ያለፍርድቤት ውሳኔ አይቀጣም። በምርመራ ወቅት ድብደባ የለም። ግርፋት የለም። ሕገመንግስታችን ይከለክላል። እነዚህን ነገሮች ማለት ነው። ስለዚህ እንደዚህ ተደርጓል፣ እንደዚህ ተደርጓል ተብሎ አሉባልታ ካልሆነ በስተቀር በተጨባጭ እንደዚህ አይደረግም። በማረሚያ ቤት የሚገኙ፣ በምርመራ ላይ የሚገኙ፣ በፍርድቤትም የሚገኙ ማየትም፣ መጎብኘትም ይቻላል። እየተደረገም ነው። በውስጥም በውጭም ባሉት አካላት ነው። በዋናነት ለነዚህ አካላት አይደለም መንግስት እነዚህን ስራ የሚሰራው።

በዋናነት፥ ቅድም እንዳልኩት፣ ህገመንግስቱ ላይ የተቀመጡትን መብቶች የማስከበር፣ የማክበር ኃላፊነት የመንግስት ነው። ይሄም ህግ የወጣው፣ [የዜጎችን] መንግስት ሌት ተቀን እየሰራ ያለው፣ የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር ነው እንጂ ሌሎች ሶስተኛ ወገን የውጭ አካላትን ለማስደሰት፣ ወይ ደሞ ለማስቀየም አይደለም። ለዜጎች፣ የዜጎችን መብት ለማስጠበቅ፣ በአገራችን ውስጥ የዴሞክራሲ ስርዓት ስር እንዲሰድ ለማድረግ ነው እየተሰራ ያለው እንጂ፤ ለነዛ አካላት ተብሎ የሚሰራ ነገር አይደለምና፣ ጣልቃ የሚገባበት ነገርም አይኖርም።

ባሉበት አንደበታቸው፣ ባለፈው ሳምንት በቁጥጥር ሥር የዋሉ ሰዎችን አስመልክቶ የሰጡት መግለጫ ላይ፥ ይደርስ የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት የገለጹበትን መንገድ እናስታውሳለን። ቪዲዮውን እዚህ ይመልከቱ።

የበፊት ንግግራቸው መታወሱ ሲወራ፣ ወዲያውኑ ዋልታ የያኔውን ቪዲዮ ከድረ ገጹ ላይ ወዲያው ያነሳው ቢሆንም፣ ቀድመው ያወረዱት ሰዎች እየተቀባበሉት ተመልክተነዋል። (ዋልታስ ቪዲዮውን ማንሳቱ ምን ይባላል?)

እንግዲህ በደም የተጨማለቀ ስርዓትን በሀቀኝነት ማገልገል እና ሲደርስ የነበረውን ግፍ እና በደል ሁሉ፣ የሰብአዊ፣ የዴሞክራሲ እና የሕገመንግስት ሽፋን በመስጠት እንዳልነበሩ፥ አሁን ሌላው ላይ በሚናገሩት ነገር ህሊና ቢኖር ኖሮ አይሸመቅቅም ነበር ወይ?

ከላይም እንዳልኩት፥ ትናንት እንዲህ ተደርጎ ነበርና ዛሬ ዝም ይባል አይደለም። ቢያንስ ግን፥ ትናንት ተሳትፎ የነበራቸው፥ ከጋዜጠኛ እስከ ባለስልጣን፤ ከተራ አባል እስከ ፈላጭ ቆራጭ ድረስ፥ “ስላልተጋለጥን/ስለማንጋለጥ” በሚል ስሜት፥ ወይም በኖሩበት የአድርባይነት ስሜት፣ ነገሮችን ሲተርኩ፣ ፍጹም ከደሙ ንጹህ መስለው ለመታየት የሚያደርጉትን ነገር በልኩ ቢያደርጉት የሚል ነው። አሁንም ተጠያቂነት ድንበር አይኑረው!

እንግዲህ መመዘዝ የተጀመረው የሙስና እና የሰብዓዊ ጥቃት ክር የት ጋ እንደሚቆም በጉጉት እና በሌሎች በራሪ እንስሳዎች እናያለን! 😉

ዕድሜና ጤና ይስጠን እንጂ ከጊዜ ዳኝነት ማንም አያመልጥም!

ሰላም!

ስለ24 ዓመቷ ሌንሴ ኔሜ ሹመት

 

43371204_2460431533973313_7357390166161358848_n

የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስኪያጅ (CEO) ተደርጋ የተሾመችውን፣ የ24 ዓመቷን ሌሊሴ ኔሜ በተመለከተ መረጃውን ማጋራታችንን እና ነገሩን ማውገዛችንን ተከትሎ፣ በግራም በቀኝ ወዳጆች አስተያየት ሰጥተዋል።

 
ነገሩ ያስቆጣቸው በርካቶች የመኖራቸውን ያህል፣ በገራገርነት ተመልክተው “ከቻለች ምን ችግር አለው? ወጣት ወደ ሀላፊነት ሲመጣ ማበረታት ነው ያለብን” ዓይነት ሀሳብ የሰጡም አሉ።
 
ከዚያም አልፈው፣ ጽሁፉ ኦሮሞ ስለመሆኗ በማይገልጽበት ሁኔታ፥ “ገና ለገና ኦሮሞ ስለሆነች፤ የኦሮሞ ስም ስላላት” ብለው በልባቸው የሚያስቡትን (ምናልባትም እየሆነ ያለውን ስለሚታዘቡ) የተናገሩም አሉ።
 
ባረጀ ባፈጀ ማሸማቀቂያ “ኦሮሞፎቢያ” ያሉም አሉ። እንደዚህ እያልን እውነትን የምናፍንበት እና የምናሳቅቅበት ጊዜ ሳያልፍ አልቀረም። ስለኦሮሞነቷ ነው ብሎ ከማሰብ ይልቅ፣ “ከእሷ የተሻለ ለቦታው የሚበቃ ኦሮሞ ስለሌለ ነው ወይ?” ብሎ መጠየቅስ አይቀልም ነበረ? 
 
አሁን ማንሳት የፈለግኩት ግን ነገሩን በበጎ ተመልክተው “ምን ችግር አለው? ዋናው ብቃት ነው እንጂ ዕድሜ አይደለም። እስከቻለች ድረስ ትሁና።” ያሉትን ነው።
 
በመጀመሪያ እንደዚህ ያለ አገር አቀፍ ዋና ፕሮጀክት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሀላፊ (CEO)
መሆን ከልምድም ከእውቀትም አንጻር የሚጠይቀው ብዙ ነገር አለ። የነገሩን ትርጓሜ፣ የሚሰጠውን ሀላፊነት እና ዓለም ላይ እንዴት ነው የሚስራበት የሚለውን መፈተሽ ተገቢ ነው።
 
ብስለት እና አመራር ጋር ሲመጣ፣ ዕድሜ ቁጥር ብቻ አይደለም። የሚያሸክመው ልምድ፣ እውቀትና ብስለትም አለው። 24 ዓመት ተለዋዋጭ ፍላጎት እንኳን ጠርቶ ቦታ ይዣለሁ የማይልበት፣ ከራስ ጋር ተስማምተው የማይጨርሱበት ዕድሜ ነው።
 
እንደዚያ ባይሆን እንኳን፣ ከተመረቀች 2 ዓመት የሆናትን ወጣት ለዚህ ቦታ ለመሾም፣ መስፈርቱ እሷ የምታሟላውን ያህል ብቻ ሲሆን ነው። ካልሆነ ግን ቢያንስ ያስተማሯትም አሉና፣ የት ባሳየችው የአመራር ብቃት ነው ተመራጭ ሆና ለሹመት የምትበቃው?
 
(በርግጥ የሌንሴ የሹመት ሙስና እና ፖለቲካዊ አድልዎ የጀመረው ከዩኒቨርስቲ ከመመረቋ በተሰጣት ሹመት ነው። እንደዚያም ሆኖ እንኳን፣ ዩኒቨርስቲ ውስጥ የማስተማር ስራዋን ሳትተው፣ ዋና ስራ አስኪያጅነቱን ደርባ መስራት መቻሏም ሌላ አነጋጋሪ ጉዳይ ነው። ካልተሳሳትኩ፣ የስራ አጡ ቁጥር ባሻቀበበት አገራችን ላይ፣ ሁለት የመንግስት መስሪያ ቤት ተቀጥሮ መስራት በህግ የተከለከለ ነው። በዚያም ላይ በእንደዚህ ያለ ከፈተኛ የአመራር ስራ ላይ ያለ ሰው፣ መኪና የመንዳትን ስራ እንኳን ደርቦ እንዳይሰራ ጥንቃቄ ይደረግለታል።)
 
ቦታው የተሰጣት በሹመት ነው እንጂ፣ ማስታወቂያ ወጥቶ ሰዎች አመልክተው፣ በነጻ ተወዳድረው እና በገለልተኝነት ተመዝነው አለመሆኑ ነገሩን ከብቃት እና ከእውቀት ጋር እንዳናያይዘው ያደርገናል። ምናልባት እርሷ የትምህርት ቤት ጓደኞች መካከል (የዛሬ 2 ዓመት የተመረቁ) የመጀመሪያ ስራ እንኳን ይዘው የማያውቁ ይኖሩ ይሆናል። በጣም ችሎታ እያላቸው፣ በፓርቲ ተሳትፎ እና ትውውቅ የተነሳ ስራ አጥተው ባክነው የቀሩ ብዙ ሰዎች እንዳሉም ይታወቃል።
 
ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ “ከቻለችው ምን ችግር አለው? ዋናው መስራቷ ነው” የሚሉት አስተያየቶች ናቸው፣ ሌላ ትኩረቴን የሳቡት።
 
ታዲያ ትናንትና “የትግራይ የበላይነት ነገሰ” ያልነው ለምን ነበር?
 
አንድ መስሪያ ቤት ውስጥ ከጥበቃ እስከ ሀላፊ ድረስ ትግሬዎች ናቸው የሚቀጠሩት እና ቦታ ቦታ የያዙት የተባለው ለምንድን ነው?
 
ኮንዶሚነም ቤት እስከከፈሉ ድረስ ቢሰጣቸው ምን ችግር ነበረው?
 
የጥበቃ ሰራተኛው እስከጠበቀ ድረስ ትግሬ ሆነ ምን ሆነ ለምን ደነቀን?
 
የመከላከያ ሰራዊቱ ብሔር ስብጥር ለምን አሳሰበን?
 
የአውሮፕላን አስተናጋጇ እስካስተናገደች እና አውሮፕላኑ ስራ እስካላቆመ ድረስ፣ ትግሬ ሆነች ምን ሆነች ምን አገባን?
 
መርካቶ ንግዱ እስካልታጎለ ድረስ፣ ጉራጌዎችን አፈናቅለው በግብር እና በኮንትሮባንድ ደግፈው ትግሬዎችን ቢያስፋፉ ምን አስጨነቀን?
 
የተለያዩ ሀላፊነት ቦታዎች ላይ የተሾሙትስ አለመቻላቸው በምን ታወቀና ነው ትግሬ መሆናቸው ያስከፋን?
 
ታዲያ ድካማችን ሁሉ ለምን ነበር?
 
አገሪቱ ላይ ሁሉም ዜጋ እኩል ተጠቃሚ ይሁን ከሚል ቅንነት አይደለምን? ፍትህ እና ተጠያቂነት እንዲነግሱ፣ የዘመድ እና የካድሬ አሰራር እንዲወገድ አይደለምን?
 
“አዲስ ንጉስ እንጂ ለውጥ መቼ መጣ” የሚለው ሙዚቃ ትዝታ ይሁንልን! የትናንቱን የጠላነውን፣ በአዲስ ዛሬ ለመተካት አይደለም ተስፋ እና ጉጉቱ!
 
ኢፍትሀዊ አሰራር ይውደም!