መንግስት ቢኖር…

የምር መንግስት ቢኖረን ኖሮ፥ ይህኔ በሬድዮና በቴሌቪዥን የሚታጀብ፣ ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ የሚደረግበት ብሔራዊ ኀዘን ላይ ነበርን። ግን ያው፣ ሕዝቡ ራሱ ብሔራዊ ሐዘን ተጠራርቶ ቁጭ ብሏል።
 
“የገደለው ባልሽ
የሞተው ወንድምሽ፣
ሐዘንሽ ቅጥ አጣ
ከቤትሽ አልወጣ” ሆኖ አላመች አላቸው እንጂ፥ ለራሳቸው ፍጆታ ሲሉ እንደከዚህ በፊቱ ሁሉ እኛ የጠራነውን ብሔራዊ ሐዘን ያዳምቁ ነበር።
 
አሁን እንደው የመለስ ሞት በምን ሚዛን ተሰፍሮ ነበር፣ “በመንግስት ጥበቃ ስር ናቸው።” ተብሎ ሲታሰብ፣ በጥይት እና በእሳት ተጠባብሰው ከሞቱ ወገኖች ልቆ በዋሽንት ስንደነቁር የነበረው? ሲሆንስ አዲስ ዓመትን ጠብቆ እስረኞችን መፍታት የሚጠበቅ ነበር።
 
እሺ እሱም ቅንጦት ሆኖ ይቅር። የቤተሰብን ልብ ሰቅሎ ማሰቃየት ምን ይባላል? ባገራችን ደንብ እንደው የሰው ክቡርነት በሞት ደምቆ ይገለጻል። እርም ሳይወጣ ምግብ አይበላም። የከፋ ቅያሜ ቢኖር እንኳን አስከሬን ቆመው ያሳልፏል።
 
የሟች ወገኖች እናቶች እንዴት ሆነው ይኾን? የእናት እና የልጅ ተፈጥሯዊ ትስስር ጥልቅ ስለሆነ፥ የሞቱት እስረኞች እናቶች ይኽኔ ቁርጡን ሆዳቸው ይነግራቸዋል። (እናቴ በሌለሁበት ጠንከር ያለ እንቅፋት ቢመታኝ ታውቃለች።)
 
ታዲያ ግን ምን ብለው “ልጄ ሞቷል” ብለው ለቅሶ ይቀመጡ? ስሜቱን የማያውቅ ሰው እንደአሟራች ቢቆጥራቸውስ ይፈረድበታል። ምን ብለውስ “ልጄ ደህና ነው” ብለው ይረጋጉ። ስሜቱን የማያውቅ ሰው እንደግብዝ ቢቆጥራቸውስ ይፈረድበታል? ልጆቻቸው ሞቱ/ኖሩ ቁርጡን ሳያውቁ እንዴት ያንቀላፋሉ? ወዳጅ ዘመድ ጓደኛስ እንዴት እህል ይወርድለታል?
 
ሕዝብ በመንግስት በዚህ ልክ ይጠላል? “የድሃ ድሃዎች” አሉ ቃል ሲያሳምሩ እና ወሬ ለመቀሸር ሲሯሯጡ።
 
የክፉ ክፉዎች!!
 
ሕዝብ
——-
የእምቧይ ድርድር ካብ፥ እሾህ የማያጣ፣
ንጉሥ ሲደብረው፣
¬ ጭቃ ሹም ሲከፋ፣ ባለሟል ሲቆጣ፣
እንኳን ወሬው ቀርቶ፥ ዝምታው ‘ሚያስቀጣ፤
 
ኩራቱ ‘ሚያስጨንቅ — እንደ እመቤት ኩርፊያ፣
መቻሉ ‘ሚያስገፋ፣ ‘ሚያስደምር ከትቢያ፤
 
ወንበር ‘ሚያነቃንቅ፥ — የሰላሙ ዜና፣
መንግሥት የሚያሸብር፥ — የነፍሱ ጽሞና፤
 
ሳቁ ‘ሚያጠራጥር፤ ትንፋሹ ‘ሚያስገምት፣
እርምጃው ‘ሚለካ፤ ሩጫው ‘ሚያስፎትት፤
 
ሕዝብነት—
— ከንቱነት!
 
/ዮሐንስ ሞላ (2005) የብርሃን ልክፍት/

የቂሊንጦ እስር ቤት እሳት

ቂሊንጦ እስር ቤት ውስጥ እሳት ተነስቶ እንደነበር እና፣ የእስር ቤቱ በሮች ተዘግተው ለረጅም ደቂቃዎች የቆየ ተኩስ ሲሰማ እንደነበረ ሰማን። መቼም ሴት ጠያቂ እንኳን እስከሞዴስ ድረስ ተፈትሾ በሚገባበት እስር ቤት ውስጥ ማን ማን ላይ ተኮሰ? ማን እሳት ለኮሰ? የሚል ጥያቄ ውስጥ አይገባም። (በድንገት የተነሳ የእሳት አደጋ ከሆነ፥ ምን ተኩስ አስከተለው? ብዬ ነው።)
ደግሞ እነ Daniel Berhane “ግርግሮች እየተቀዛቀዙ በመሄዳቸው የተደናገጡት የግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች የሀገሪቱን እስር ቤቶች በእሳት መለኮስ ስራዬ ብለው ተያይዘውታል።” በማለት ተናግረዋል። እንዲህ ያለው “ሳያጣሩ ወሬ እና ውንጀላ” እሳቱ የሴራ መሆኑን ያመለክታል። (ከልምድ እንደምናውቀው፥ ምናልባት ጩኸት ለመቀማት እና ነገሩን ሁሉ ‘የአሸባሪዎች ዓላማ’ ለማለት? ምን ጣጣ አለው ለነሱ… በየታክሲው እና በየሆቴሉ ቦምብ እየጠመዱ ‘ፀረ ሰላም ኃይሎች’ ሲሉ እናውቅም የለ?)
 
በግንቦት ሰባት ስም ያሰሯቸውን እስረኞች ለመወንጀል ነው ‘የግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች’ የሚባለው? ደግሞ ግንቦት ሰባት፥ ይኽን ያህል አቅም ያላቸው፣ ‘እስከሚኒስትር ዲኤታ ድረስ ሰርገው የገቡ’ የውስጥ አርበኞች እንዳለው እየገለጹ ከሆነ የመጠላትን ወሰን አያሳይም? (እንግዲህ ገና ትናንት ነው 100 ፐርሰንት የተመረጡት) ‘አሸባሪ’ ብሎ ስም ማውጣት ብቻውን ሰውን አሸባሪ ያደርገዋል እንዴ? ይኼን ያህል ኢህአዴግ በሊዝ አልገዛን። የምን ነገር ሲተበትቡ መኖር ነው?!
 
ለማንኛውም እርሱው ከየቤቱ እና ከማኅበረሰቡ ጉያ ፈልቅቆ ላሰራቸው ንጹሐን፣ ለያውም ገና በክርክር ላይ ያሉ፣ መንግስት ሙሉ ሀላፊነቱን ይወስዳል!!
 
ቸሩን ወሬ ያሰማን!
 
ቃጠሎውን በተመለከተ የዋዜማ ሬድዮን ዘገባ ቀጥሎ ያንብቡ። 

fire-on-Kilinto-presion.jpgዋዜማ ራዲዮ-ተቃዋሚ የፓለቲካ አመራሮችን እና ጋዜጠኞችን ጨምሮ ከሶስት ሺህ በላይ እስረኞችን የሚይዘው የአዲስ አበባ ቅሊንጦ ማረሚያ ቤት በእሳት ጋየ።

በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ስር የሚገኘው የቂሊንጦ ጊዜያዊ የእስረኞች ማቆያ ዛሬ ጠዋቱን በግቢው በተነሳ የእሳት አደጋ ቃጠሎ የደረሰበት ሲሆን ቁጥራቸው ያልታወቁ ታራሚዎች መጎዳታቸውን የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡

የእሳት አደጋው የተነሳው ጠዋት ሶስት ሰዓት ገደማ እንደነበር እና ቃጠሎውን ተከትሎም የተኩስ ድምፅ በተከታታይ መሰማት መቀጠሉን በአካባቢው የነበሩ እማኞች ለዋዜማ ተናግረዋል፡፡ እሳቱ የተቀሰቀሰው የቂሊንጦ እስር ቤትን ከሚጎራበተው የአዲስ አበባ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ አቅጣጫ እንደሆነም ያስረዳሉ፡፡ ጥቂት ቆይቶ የአስተዳደር ቢሮዎች እና አዳራሽ ወደሚገኙበት ቦታ እንደተዛመተም ያብራራሉ፡፡

ለዩኒቨርስቲው የሚቀርበው የእስረኞች ቦታ በእስር ቤቱ አጠራር ዞን አንድ ተብሎ የሚታወቀው ቦታ ነው፡፡ በተለምዶ ወደ ሶስት ሺህ ገደማ እስረኞችን በውስጡ የሚይዘው የቂሊንጦ እስር ቤት በሶስት ትልልቅ ዞኖች የተከፋፈለ ነው፡፡ ምርጫ 2007ን ተከትሎ አነስተኛ የሆነ እና በቆርቆሮ የተሰሩ ማረፊያ ቤቶችን የያዘ አራተኛ ዞን የተገነባ ሲሆን በፖለቲካ ሰበብ ለእስር የተዳረጉ እሰረኞችን ከሌሎች ለመለየት በሚል አንድ አነስተኛ ዞን በቅርቡ ተጨምሯል፡፡

ቃጠሎው በየቦታው መስፋፋቱን ተከትሎ የእስር ቤቱ ፖሊሶች ዙሪያውን ከበው መተኮስ መጀመራቸውን እና የእስረኞች የጩኸት ድምጽ ከርቀት ሁሉ ጎልቶ ይሰማ እንደነበር በቦታው የነበረ የዋዜማ ምንጭ ይናገራል፡፡ ተኩሱ ለ40 ደቂቃ ያህል ግድም መቆየቱንም ይገልጻል፡፡ የተኩሱን ድምጽ የሰሙ በአቅራቢያው የሚገኙ የፌደራል የፖሊስ ኃይሎች ከጥቂት ጊዜ በኋላ መድረሳቸውንም ያስረዳል፡፡

በአንድ ኤፍ ኤስ አር ሙሉ የተጫኑ ፖሊሶች ወደ ግቢው ሲገቡ ተመልክቻለሁ የሚለው የዋዜማ ምንጭ በትንሹ በአምስት ፒክ አፕ መኪኖች የተጫኑ ተጨማሪ ፖሊሶችም ወደ ቦታው ሲያመሩ ማየቱን ይገልጻል፡፡

የተኩስ ድምጽ መሰማት ሲጀመር ከእስር ቤቱ አጠገብ በመሆን ለእስረኞች የሚፈቀዱ ሸቀጣ ሸቀጦችን የሚሸጡ የመንገድ ዳር ነጋዴዎች በፍጥነት መበታተናቸውን ሌላ የዓይን እማኝ ትናገራለች፡፡ የእስረኛ ጠያቂዎች ጉዳዩን ለማጣራት ወደ ቦታው ሲጠጉ ፖሊሶች ይመልሷቸው እንደነበርም ታስረዳለች፡፡

እኩለቀን ሊሆን ግማሽ ስዓት እስኪቀረው ድረስ በእስር ቤቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ ከፍተኛ ተኩስ ይሰማ የነበረ ሲሆን ወደ እስር ቤቱ የሚያስኬዱ መንገዶች ሁሉ በፀጥታ ሃይሎች ተዘግተዋል።

ቅሊንጦ ከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ በኦሮሚያ ክልል የተነሳውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ በርካታ የፓለቲካ አመራሮች ፣ የኢትዮጵያ የሙስሊሞች ጉዳይ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ከፊል አባላት እንዲሁም ጋዜጠኞች ለአመታት የፍርድ ሂደታቸውን ታጉረው የሚከታተሉበት ስፍራ ነው።

በእስር ቤቱ ደንብ መሰረት የቅዳሜ እና እሁድ የእስረኞች መጠየቂያ ሰዓት ለግማሽ ቀን የተገደበ ነው፡፡ ጠያቂዎች ሁለት ሰዓት ተኩል አከባቢ ስማቸው እና የሚጠይቁትን ሰው አስመዝግበው ወደ ግቢው እንዲገቡ ይፈቀድላቸው ነበር፡፡ ቀናቱ የዕረፍት ቀን እንደመሆናቸው መጠን እና በርካታ ጠያቂዎች የሚስተናግዱበት በመሆኑ ብዙዎች በእስር ቤቱ አካባቢ የሚገኙት ማልደው ነው፡፡

በጠያቂዎች በኩል በዛሬው ዕለትም ተመሳሳይ ሁኔታ እንደነበር የዓይን እማኞች ይናገራሉ፡፡ በፖሊሶች አማካኝነት ከቦታው እንዲርቁ የተደረጉት ጠያቂዎች እና የአካባቢው ሰዎች በአንድ በኩል ከጥሩነሽ ቤጂንግ ሆስፒታል እንዳያልፉ መደረጉን እና በሌላኛው አቅጣጫ ደግሞ ሄንከን ቢራ ፋብሪካ ጋር መንገድ መዘጋቱን ያብራራሉ፡፡

ከእስር ቤቱ የሚትጎለጎለውን ጭስ በርቀት ሆነው የሚያስተውሉት ጠያቂዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች አምቡላንሶች ወደ ቂሊንጦ እየተመላለሱ የተጉዱ ሰዎችን ጭነው በፍጥነት ወደ ህክምና መስጫ ቦታዎች ሲሄዱ መመልከታቸውን ያስረዳሉ፡፡ አምቡላንሶቹ መጀመሪያ ላይ በቂሊንጦ አቅራቢያ ወደሚገኘው ጥሩነሽ ቤጂንግ ሆስፒታል ሲገቡ ይታዩ የነበረ ሲሆን በስተኋላ ላይ ግን ሞልቷል በማባሉ ተጎጂዎችን ይዘው ወደ ቃሊቲ አቅጣጫ ሲሄዱ እንደነበር ይገልጻሉ፡፡

እስካሁን ድረስ ቁጥራቸው ያልታወቀ ታራሚዎች መጎዳታቸው ቢነገርም ትክክለኛ መረጃ ማግኘት ግን አዳጋች ሆኗል፡፡ አደጋው መከሰቱን ያመነው የአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከል እና መቆጣጠር መስሪያ ቤትም ሶስት የአደጋ ጊዜ ሰራተኞቹ ላይ ጉዳት መድረሱን ከመናገር ውጭ በእሰረኞች ላይ ስለደረሰው አደጋ ከመናገር ተቆጥቧል፡፡

በእስር ቤቶች ላይ የሚደርስ የእሳት ቃጠሎ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተደጋጋሚ ሲከሰት የሚስተዋል ጉዳይ ሆኗል፡፡ በዚህ ዓመት ብቻ በርካታ ሰዎች የተጎዱባቸው ተመሳሳይ አደጋዎች በጎንደር እና በደብረ ታቦር እስር ቤቶች ተከስቶ ነበር፡፡

ዋዜማ ሬድዮን የፌስቡክ ገጽ ይከተሉ። 

Governance and bullying steps – the Ethiopian (TPLF/EPRDF) way!

(Comment on Alula Solomon’s post)
 
1. Sing ‘developmental democracy’, and dance ‘federalism’ to cover the fascist and the racist in it.
 
2. Censor private medias, and force them to close if they won’t be submissive to the government. Persecution and imprisonment follow.
 
3. Spread consistently fabricated lies and propaganda, labeling every good initiative ‘terrorist and anti-development’ if it is not harmonious with the government’s mischievous and corrupt plans and deeds, terrify the people as if it is an angel and devil will takeover when it fall, using the state owned TV and Radios. Doing every possible thing, whatever it may cost: from the tax payer’s money to the lives of journalists, bloggers, activists and opposition party members, to close and/or slander other information doors.
 
4. Organize immoral thugs in the name of ministers, advisers, officers, and cadres; and gangs in the name of federal police.
 
5. Work evilly to brainwash education, culture, pride, and every good thing the people has accumulated out of penury; and scorn the oppressed majority.
 
6. Corrupt systems and resources, terrify steadily, call up the hard times they had as rebel group against the Derg regime, to implicitly induce that they deserve to oppress the people (bragging like the country is their colony), benefit selectively based on ethnic and political opinion in almost every other spot, and creating disparity between different nations of the country.
 
7. Gather, as their cadres, many optionless bootlickers that strive to support their daily subsistence with the money they get as an allowance for attendance of Kebele meetings. And use them for any public demonstrations called by the government, such as the late PM’s mass mourning ceremony.
 
8. Create feelings of second citizens and strangers in the people through their ruthless practice of nepotism, and merciless actions against the concerned citizens.
 
9. Violate the constitution. Ban peaceful demonstrations, and assemblies. Imprison and persecute concerned citizens. Murder the people for their peaceful protests.
 
10. Vandalize and destroy the people itself, not limited to it’s properties.
 
11. Spread hatred among the people that itself has worked hard to segregate in the name of federalism, to let them fight each one another to seek more ages of tyranny.
 
12. Disseminate fabricated stories about the protests, hijack the realities of the causalities in order to confuse as if there is attack against an ethnic group. Fabricate lies about damaged properties of one, while there are mass killings of the other by it’s own police officers.
 
13. Making low quality documentaries; while the people keep on suffering, and try to sign petitions in vain to international community, US government, EU, etc.
 
14. So much more.
 
#Ethiopia #StopKillingCivilians #OromoProtests #AmharaProtests

ስለ ሁሉም!

“የማርያም መንገድ ስጠኝ። ዝቅ ብዬ ቁልቁለቱ ላይ ልቁምና ተራራዬን ላብዛው።” ብሎ ጨዋታ ምንም አይጠቅምም። ብሔር ተለይቶ ብቻ የተፈጸመ/የሚፈጸም ነገር ካለ፣ ወይም እንደዚያ የሚወሰውሱ ሰዎች ካሉ እነሱን አወግዛለሁ። አመንነውም ካድነው፣ አገሪቱ ላይ እንደ ሁለተኛ ዜጋ ሲሰማው የኖረ ብዙ ሰው አለ። ሀተታ እና ማስረጃ ሳያስፈልገው፥ ኢህአዴግ ይህን ማድረጉ ይታወቃል። ሀላፊነቱንም ራሱ ይወስዳል።
 
“የትግራይ ህዝብ ከመተማ ተለይቶ ተሰደደ፣ ቤቱ ተቃጠለ፣ ጥቃት ተፈጸመበት።” የተባለው ወሬ እውነት ከሆነ፥ በዋናነት ሀላፊነቱን የሚወስደው ኢህአዴግ ነው። “እውነት ከሆነ” ያልኩት፥ ተቃውሞዎች መሰማት ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ፣ ያለውን ጫና እና የጥቃት ልክ ስንሰማ የኖርንባቸው ሚዲያዎች፥ በዚህ ዙሪያ የዘገቡት ነገር ስለሌለ ነው። አገር ውስጥ ያለ ነጻ ሚዲያም የለምና እንዲህ ያለውን ወሬ የሚዘግብ አናገኝም። ሌላው ቀርቶ፥ “አመጽ ቀስቃሽ መጽሐፍ ይዘህ ዞረሃል” ብሎ መጽሐፍ አዟሪዎችን የማሰር ዜና ከሰማንም ሳምንት አልሆነውም።
 
የመንግስት ሚዲያ እንደው እንደከብት ዓይን አረንጓዴ እንጂ ራሱ የሚቀምመውን ቀይ ቀለም እንኳን አያሳይም። የሌለ ልማት እና ሰላም፣ እንጂ ሌላ ሌላ ነገር ሲወራ እንዳንሰማ ተፈርዶብናል። የተወራ ቀንም ለመግለጫ፣ ለዛቻ፣ ሕዝቡን በአንዳንድ የከተማ ነዋሪዎች ለማስመከር፣ እንዲሁም “ታድለው ምንም አይሰማቸውም” ለማስባል፣ እና ለስም መስጠት ነው። ስለዚህ ኢህአዴግ ሀላፊነቱን የሚወስደው፥ ሚዲያዎችን በማፈን፣ አገር ውስጥ የሚከናወኑ ጉዳዮች በእኩል መጠን የዜና ሽፋን እንዲያገኙ ስለማይፈቅድም ጭምር ነው። በፌስቡክ እንኳን ሰዉ በመረጃ ክፍተቱን ቢሞላ፥ እንዴት ጥርስ እንደነከሱባት በዶክመንተሪ እና በየስብሰባው እያነሱት አሳይተውናል።
 
የፈሰሰውን ደም እና ያለውን ተቃውሞ ከመዘገብ ይልቅ ያልዘራውን ማሳ፥ “አሸተ ጎመራ” ብሎ ማሳየት ነው የሚቀለው። ባለፈው ፈይሳ ሌሊሳ እጁን ቢያጣምር እና ተቃውሞውን ሲያሳይ ቀጥታ ቢታይ፥ መብራቱን ደረገሙት። እንግዲህ የኢህአዴግ ሚዲያ ከዚህ ከፍም ዝቅም የለውም። ስለዚህ ዜናዎች በአግባቡ እንዳይደርሱ እና እኩል ዘገባ እንዳያገኙ ከማድረግ ጀምሮ ለተጫወታቸው መሰሪ ሚናዎች ሁሉ ሀላፊነቱን ይወስዳል።
 
ስለዚህ፥ የትግራይ ሕዝብ ላይ ተለይቶ በሕዝብ ጥቃት ተፈጽሟል ብለው ያመኑ ሰዎች፥ ከሰፊው ሕዝብ ጋር ወግነው፣ መንግስትን የሚያወግዙበት እና “በቃህ” የሚሉበት ትክክለኛ ጊዜ ነው። ቢያንስ እሱን ሲያወግዙ ከስር ከስሩ ግድያውን እና ጅምላ ጨራሽ አዋጁን ማውገዝ ቀላል ነገር ሆኖ ተሰሚነትን ያስተርፋል። በዚያም ላይ፥ የዘረኝነትን ሴራ በመሸረብ ሲወጣ ሲወርድ የነበረውም ኢህአዴግ ስለሆነ እሱን በጋራ ማውገዝ እና አንድ ላይ በመሆን አምባገነንነት እንደማያሸንፍ ማሳወቅ ነው።
 
ተቃውሞ ስለማይረፍድ (መንግስትን መቃወም ማለት ሰፊው ሕዝብን መደገፍ ማለት መሆኑም እየታወቀ)፣ ከተጠቁት ወገን ሆኖ ኢህአዴግን በአደባባይ ስላወጀው ግድያ ማውገዝ ፈጣን መፍትሄ ይሆናል። አንዱ ቢጀምረው ሺ ምንተ ሺው ይከተላል። ሀበሻ ደግሞ በአንድ መፈክር ዞሮ ይገናኛል። Trust me, if it is heartfelt, unity is a slogan away!, and it will only terrify the bloody government.
 
የዘረኝነት ድርጊት ካለ ቋቱ ኢህአዴግ ጉያ ስር ነው። ዋናው ጠላታችን ለራሳችን ያለን ስሜት (ego) ነው። ሌላው ጠላታችን ደግሞ ነገሩን ቆመን የምንመለከትበት ቦታ ነው። ዳገት ላይ ቢቆሙ ቁልቁለት ነው የሚታየው። ቁልቁለት ላይ ቢቆሙ ደግሞ ዳገት ነው የሚታየው። እና አቋቋምን ለማስተካከል በመጣር ቢያንስ ጥፋትን መቀነስ ይቻላል። ጨካኞች ቀጥለው ነው የሚያጠቁን።
 
የትግራይ ሆነ የአማራ፥ የሰው ልጆችን መጎሳቆል ማየት የማይፈልግ ሰው፣ በውስጡ ሰብዓዊነት ይኖራልና፥ “ትግራይ ተለይቶ ጉዳት ደረሰበት” ካለ፥ የሌላውንም ጉዳት እኩል ዘግቦ ማውገዝ አለበት። መሞት እጣ ፈንታ በሆነበት አገር ላይ፥ ወደ ሱዳን መሰደድ እንደ እድል ሲቆጠር ቢታይም ብዙ አያስፈርድም።
 
አምባገነኑን መንግስት በመቃወምና፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ሀማደ የታወጀውን ጅምላ ግድያ ለመቋቋም መከራውን እየበላ ያለ ሁሉም፥ ትግሉ ከስርዓቱ ጋር መሆኑን በማወቅ ጥቃት ያልፈጸመበት ሕዝብ ላይ ምንም እንዳያደርግ ሊጠነቀቅ ይገባል። የአምባገነኑ መንግስት አካላትም ቢሆኑ፥ የድርጅታቸውን እድሜ ለማራዘም ጥቃቱን ከሕዝብ ለሕዝብ የተፈጸመ በማስመሰል አድርገው ሊያደርጉ ይችላሉና እነሱንም ነቅቶ ማየት ያሻል።
 
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

ፈርኦናዊነት

Hailemariam-Desalegnሰው ከመጽሐፍ ቢቀር ከእድሜው፣ ከእድሜው ቢቀር ከወዳጆቹ/ጎረቤቶቹ፣ ከነሱ ቢቀር አለትን ወደ አፈር በሚለውጠው ጊዜ፣ ከእርሱም ቢቀር ጨለማና ብርሃን ከሚፈራረቁበት የጠፈጥሮ ዑደት… እንዴት አይማርም?
 
በእኔ እምነት ይሄ ስርዓት እንኳን አሁንና ድሮም ያልፈረሰ፣ በከባድ ችግር ውስጥ እንኳን ገብቶ የማይፈርስ ስርዓት ነው። ስለዚህ በአለት ላይ የተመሰረተ ስርዓት አለን ብሎ ማመን ጠቃሚ ይሆናል። ….በዚህ ሂደት ውስጥ የተሳተፉ አካላትን ያለምህረት ህግ የማስከበር ስራችንን ማከናወን የሚገባን ይሆናል። መንግስት የህግ የበላይነትን ለማስከበር ሁሉንም አቅሙን ይጠቀማል። በእኔ በኩል ይህ የህግ የበላይነት እንዲከበር ለማድረግ ሁሉም የጸጥታ አካሎቻችን ህግ የበላይነትን እንዲያስከብሩ አዝዣለሁ።
ብሏል (ጠ/ሚ?) ኃይለማርያም ደሳለኝ
እንግዲህ ትዕዛዝ ማንበብ ነበርና ስልጣኑ’አለሁ’ ለማለት ጊዜ ተራው ደርሶት መሆኑ ነው ሕዝብ ለመፍጀት ትዕዛዝ ያስተላለፈው፡፡ ይሄ መቼም የሚረሳ ጉዳይ አይደለም!
 
ቃል በቃል ገልብጬው ደጋግሜ አነበብኩት። ደጋግሜ ነፈርኩኝ። የሰው ልጅ አእምሮ እንዴት በዚህ ደረጃ ሊደነዝዝ ይችላል? መቼስ ያደገ አገር ሰዎች ብንሆን እንዲህ ያለውን ሰው ሰብስበው ጥናት መከናወኑ አይቀርም ነበር።
 
“ፀጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል” ነበር ተረቱ። “ፀጉራም ውሻ ሞቶም ሲታይ ጣረ ሞቱ ‘አለሁ’ ይላል” እንበለው ይሆን?!
.
.
ሰውዬው በሀይማኖተኛ ማሊያም እንደሚጫወት ትዝ ቢለን፥ ከመጽሐፍ ቅዱስ የፈርኦንን ታሪክ እናስታውሳለን….
 
“እግዚአብሔር እንደ ተናገረ፥ የፈርዖን ልብ ጸና፥ አልሰማቸውምም። እግዚአብሔርም ሙሴን አለው፦ የፈርዖን ልብ ደነደነ፥ ሕዝቡንም ለመልቀቅ እንቢ አለ።” (ኦሪት ዘጸአት 7፥ 13-14) “ግብፃውያንም፥ የፈርዖን ፈረሶችና ሰረገሎች ፈረሰኞቹም ሁሉ፥ እያሳደዱ በኋላቸው ወደ ባሕር መካከል ገቡ።” (ኦሪት ዘጸአት 14፥23)
 
“የሰው ልጅ ሆይ፥ ስለ ግብጽ ንጉሥ ስለ ፈርዖን ሙሾ አሙሽ፥ እንዲህም በለው። የአሕዛብን አንበሳ መስለህ ነበር፥ ነገር ግን እንደ ባሕር ዘንዶ ሆነሃል በወንዞችህም ወጥተሃል፥ ወኃውንም በእግርህ አደፍርሰሃል፥ ወንዞችህንም አሳድፈሃል።” (ትንቢተ ሕዝቅኤል 32፥2
 
“የመለስ መንፈስ ከኃይለማርያም ላይ ልቀቅ!” የምንልበት ጊዜ አልፏል። አሁን መንፈሱ ሙሉ ለሙሉ እንደተዋሃደው እያየን ነው። …እንግዲህ ሙሾ እያሞሸን ፍትህ ሲፈጸም የምናይበት ቀን ይመጣል! የሰው ልጅ ደም እንደው በከንቱ ፈሶ አይቀርም!
 
“ፈርዖንንና ሠራዊቱን በኤርትራ ባሕር የጣለ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና!” (መዝሙረ ዳዊት 136፥15)
 

ፈይሳን አትንኩት!

14067671_1461358120547331_7833434000898986507_nI can’t keep the brave #FeyisaLelisa out of my mind, I can’t keep him out of my soul. It needs an altruist soul to forgo comfort zone to help the helpless, and to be voice to the voiceless majority. He could have lived in a selective ignorance, and act as if ‘nothing is wrong in the country’ as many have chosen.
 
In fact, he knew that it may cost him career, friends, families, and even breath; as even simple trial of exercising freedom of speech may cost career, freedom of movement, close friends (that play ‘I hate politics’ and/or ‘I am neutral’), neighbors, and life. But he has loved the people, and choose to submit for his own conscience.
 
It is just one of the simplified and contemporary forms of Walk of Jesus. His courageous selfless act is an ever inspirational deed to a generation in general. This is what ‘living well’ means!, what ‘living to the fullest’ means. ‘Thank You’ is an understatement. May his kinds of souls multiply in all sectors. May God be with him and his loved ones throughout.
አትንኩት!
——
ሚዛን ነው – ለክብር
መስፈሪያ – ለፍቅር፣
ፈዋሽ – ከበሽታ፥
አበባ – ለደስታ፤
ምውት – ለእምነቱ፣
ታዛዥ – ለስሜቱ፤
 
ይልቅ ተንጋግታችሁ፥
ቅሰሙ፣ ተማሩ፣
በእጁ ይዳብሳችሁ፣
ተሰለፉ ከእግሩ፤
 
በየቦታው ይኑር፥
ሁሉም በየግብሩ፣
የተከሉት ይመር፣
ይታከም አገሩ፤
 
ስለሕዝብ ማቃሰት፣
ዓለም ደስታን ትቶ፥
ስለአገር መዋተት፣
ቤት ንብረት ረስቶ፥
 
ማሰማት እሮሮ
ባልጠነከረ ልብ
ባልሰላ አእምሮ፥
አይገኝም ከቶ!
ደርሶ ካላሳየን፥
ድንገት ሰው ተነስቶ!
 
“ሃምሳ ሰው ቢወለድ
ሃምሳ ጉድ ይመጣል”
 
ሃምሳ ጀግና ቢወድቅ
ሃምሳ ሺህ ይነሳል፤
 
ሃምሳ ዘር ቢበተን
ማሳ ሰብሎ ያምራል፤
 
ይኸው በዚህ ጊዜም
በአንዱ ሰው ፈይሳ
ሺ ልሳን ተነሳ፣
 
በደልን ምለሳ፣
ግድያን ወቀሳ፣
አፈናን ፍወሳ፣
ጭቆናን ምየሳ።
 
/ዮሐንስ ሞላ/

“ሳይቃጠል…”

13939360_1032565160197850_3393683655956488976_nእንግዲህ ጫፍ ጫፉን እንዳየነው፥ ቢችሉ ኖሮ ፌስቡክም ላይም አጋዚ በትነው የንጹሐንን ደም ያፈሱ ነበር። ስጋን ይገድላል እንጂ፥ ነፍስን እንደው ማንም አያገኛትም! ይኸው ከያዙት መሳሪያ ብዛት የሚያርዳቸውም የመረጃ እና የሀሳብ ልውውጡ ነው።
 
መቼም ከዛሬው “ሳይቃጠል በቅጠል” እና ከሰሞኑ የኢንተርኔትና ማኅበራዊ ድረገጾች አፈና የምንማረው፥ ማኅበራዊ ድረ ገጾች (በተለይም ፌስቡክ) እንደሚያጣጥሉት፣ ከቁብ የማይቆጥሩት ሳይሆን፣ በጣም የሚፈሩትና ሕዝብ በማንቃት እነሱ የፈጠሩትን የመረጃ እና የመማማር ክፍተት የሚሞላ መሆኑን… ያም በጣም የሚያስጨንቃቸው እንደሆነ… እኛም ብንሆን ስለብዙ ነገር ብዙ የምንልበትና፣ ብዙ ነገሮችን ለማየት የምናጮልቅበት መስኮታችን በመሆኑ፥ ከምንግዜውም በላይ፣ በሀላፊነት እና በጥንቃቄ በመጠቀም ጋንጩራቱን በቀላሉ ማንጨርጨር እንደምንችል ነው። በተለይ በዚህ የግል ፕሬስ ድርቀት ባለበት ወቅት የፌስቡክ አስተዋጽኦ ጉልህ መሆኑን ትኩረት ማድረግ እንደሚገባን ነው።
 
የለበጣ ተጠቅመን እንዲህ ያራድናቸውማ፣ ቅርጽ ቅርጽ ስንይዝ፣ ወሬያችንም ደርዝ ደርዝ ሲያበጅ፣ ቃላቶቻችን የተመረጡ ሲሆኑ፣ የውይይት ባህሉም ሲደረጅማ ጨርቃቸውን ጥለው ያብዳሉ። ዩኒቨርስቲ እያለን የተማሪ አመጾች ሲኖሩ ከማይረሱ የተማሪ ድምጾች መካከል ይህቺ ዝማሬ ነበረች። (ሀዋሳ የተማራችሁ ታውቋታላችሁ።)
 
ጥያቄያችን ኦሆ… ይመለሳል ኦሆ፣
ይመለሳል… ኦሆ!
ባይመለስ ኦሆ… ጉድ ይፈላል ኦሆ፣
ጉድ ይፈላል ኦሆ
እኛ ያለን ኦሆ… ወረቀት ነው ኦሆ፣
ኦሆ ወረቀት ነው!
የእናንተ ግን ኦሆ… መሳሪያ ነው ኦሆ
መሳሪያ ነው!
እንግዲህ ከቻሉ የንጹሐኑን ስጋ ትተው ሀሳቦችን ይቀጥቅጡ። ሀሳቦችን ይግደሉ። ጥያቄዎችን ያሰቃዩ። የንጹሕ ሰው ደም እንደው አንዱ ቢነካ ሺውን ይቀሰቅሳል! አንዱ ቢወድቅ እልፍ ሆኖ ያፈራል! ሰማየ ሰማያትን ሰንጥቆ ያስተጋባና አማልክቱን ያስቆጣል!
 
#EBC: Thank you for stressing on the fact that our cyber existence is stressful to the brutal government; and our proper usage matters towards the different kinds and levels of changes we seek. ሰሞኑን በተሰራው ማስታወቂያ መሰረት ብዙ አዳድዲስ የፌስቡክ አባላት እንደሚመጡ እናምናለን። (ልማት ቅብርጥሶ ለማለት የሚበተኑትንም ጭምር) I hate you tho. #IHateEtv!
 
#Bullies: come, try the ideas! Fight with the minds of the oppressed majority!
 
#Friends: ከአብዮተኛው ፌስቡክ ጋር ወደ ፊት (Y) (Y) Let’s socialize in a way that we can sustainably desocialize violence and oppression from our beloved country!
 
#Ethiopia #StopKillingCivilians

የሀይማኖት ነጻነት ይከበር!

ህግ እንዳከበረ ሰው ለመመጻደቅ አይደለም መቼም። ግን ሌሎች ትዕዛዛቱን ሲጥስ ስለኖረ፣ ከምዕመኑ እኩል “ንስሀ ግባ” ብሎ መወትወት ቢቀር፣ በዘርና በሀይማኖት ለያይቶ ሊደላደል እየዳከረ፣ በጠራራ ፀሐይ ሕዝብን እንደጤፍ ሲቆላና እንደምንም ሲያራግፍ፣ ክቡር ሰውነትን ባለቤት እንደሌለው ሲያንገላታ ባላየ ባልሰማ ኖረው (ለእግዚዮታ እንኳን ጥሪ ማድረግ አንድ ነገር ነበር)….
 
“ለቀደሙት አትግደል እንደተባለ ሰምታችኋል፤ የገደለም ሁሉ ፍርድ ይገባዋል እኔ ግን እላችኋለሁ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፡፡” ማቴ. 5፡ 21-22 የሚለውን ትዕዛዝ ጠቅሰው ያላወገዙትና ጠብመንጃውን እንዲዘቀዝቅ ስለነፍስ ያልወተወቱት አካል፣ ሲጨንቀው “ኑ አማልዱኝ… ሕዝብን ዐይኑን ያዙልኝና ማሞኘቴን ካቆምኩበት ልቀጥል።” ሲል…
 
“ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።” ~ 1.ቆሮ.6: 19-20
 
“በዋጋ ተገዝታችኋልና የሰዎች ባርያ አትሁኑ” ~ 1ቆሮ.7፡23
 
“እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” ~ ቆላ.1፤13-14
 
“ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።” ~ ገላ.4:7
 
እና ሌላም ተብሎ የተነገረውን፣ ‘በክርስቶስ ክርስቲያን ተብለሀልና ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ’ እያሉ ሲሰብኩት የኖሩትን ሕዝብ፣ ለመሸምገል ማሰቡ እንደምን ቀለላቸው?
 
ለነገሩ፣ ጥላሁን ገሰሰ ሞቶ ያኔ የነበሩት ጳጳስ ለቅሶ ቤት ሊያጽናኑ ሄዱ ተብሎ ወሬ ሲነገር፣ ጥሌን ብንወደውም፣ ስለዘላለማዊ ሕይወት ለመስበክ ሜዳና ፈረሱ ገጠሙላቸው ብለን ኢቲቪው ላይ ቸክለን ስንሰማ “ጥላሁን አልሞተም። ቤተክርስቲያናችን ሞተ የምትለው ምንም ሳይሰራ ያለፈን ሰው ነው…” ምናምን ብለው ያሸማቀቁንንም አንረሳውም።
 
እንደአቡነ ጴጥሮስ ‘ጽአ እርኩስ መንፈስ!… ሕዝቤን ልቅቅ’ ብሎ ጋንጩራቱን ጭራ የሚያስበቅል አባት እንናፍቃለን። ምህረቱ ለዘላለም ይሁን!!
 
የሀይማኖት ነፃነት ይከበር!
 
!
 
#Ethiopia #StopKillingCivilians

ሀገሬን ከነኗሪዎቿ…

13925175_1450435844972892_1002811786806231956_nበስፖርቱም ሆነ በሌላው ጉዳይ አገሬን ከነኗሪዎቿ እንደ ሮቤል ኪሮስ ያስተዋወቀልኝ የለም። እንደሱ፥ በደልና ግፉን ሁሉ ባንድ ላይ ሸክፎ ለዓለም ያሳየልኝ የለም። ሙስናውን፣ ውጥንቅጡን፣ የወጣቱን ጉስቁልናና መገፋት፣ የስራ ማጣቱን፣ ሞያ ማቃለሉን፣ የሆድ ስፋቱን፣ የፖለቲካና የዘር መድልዎውን፣ የኑሮ ልዩነቱን (‘ሰላም ውሎ መግባት’ን ካለማወቅና ‘የጠሉትን የመቃወምን ዋጋ’ ካለመተመን፣ እስከ ‘የፈለጉትን ልዩ ነገር መሞከር’ መቻል ድረስ)… “መተዋወቅ” ላይ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የሆነ መጭበርበር ደርሶባታል። ሀቀኛ ኗሪዎቿም ተበድለዋል።
 
ከትናንት በስቲያ ግን በሮቤል ቀፈት በኩል ሁሉም ነገር ታየ። በእርሱ ከአቅም በታች በሆነ ችሎታ ኦሎምፒክ ላይ መሳተፍ ሁሉም ነገር ፍጥጥ ብሎ ተነገረ። ሮቤልም አባቱም ያውቃሉ ብዙ ችሎታ እያላቸው ቤት የቀሩ ድንቅ ዋናተኞች እንዳሉ… ሌላ ሰው ተወክሎ ቢወዳደር የማሸነፍ እድል እንደነበረን… የሰውነት አቋሙን ዝርክርክነት (ፎቶው ላይ ወላ ተሰብስቦ ነው)… በምን መስፈርት እንደተመለመለና ባንዲራ ተሸካሚ እንደሆነ… እንዲህ ያሉ ትልልቅ ጉዳዮች ላይ አገርን ለመወከል ቀርቶ ለተራ የቀበሌ ሥራ፣ ሚኒማውን ማሟላት ማለት ዝምድና ወይም የፖለቲካ ትስስር መፍጠር ማለት እንደሆነ… ሌሎችም ብዙ ባለጊዜያት ያውቃሉ። ግን በቃ ሮቤል መሞከር የሚፈልገውን ነገር እንዲሞክርና “ለየት” ማለት እንዲችል፥ የአገሪቷን መስፈርት ያሟላል። እንደአባትና ልጅ ሊያሳፍር የሚገባ ጉዳይ ሳይቀር፥ እንደባለጊዜ ሲታይ አእምሮን ይደፍንና ያኮራል።
 
ከነኅሊና ከሆኑ ምን እውቀትና ጉጉት ቢሰንቁ፣ ሰተት አድርጎ የማያስገባውን የሥራና የሞያ ዓለም አሳየልኝ። በየትኛውም ዘርፍ፣ ሰው ምን ያህል ያሸበረቀ ሲቪ ቢኖረው፥ በልኩ የተሰራ ስራ ላይ ተወዳድሮ አገሩን ማገልገል ቀላል እንደማይሆንለት… በአንጻሩ፥ የሚፈለገውን ሞያዊ አቋም ያላሟላ ቦርጫም፥ ላዩ ላይ ተጣብቆ በሚያስጨንቀውም ሆነ፣ ሰፍቶት በሚወላለቅበት፥ የስራ ዓለም ላይ ገብቶ አገሩ ላይ መገልገልና ሕዝቧን መበደል መቻሉን አሳየልኝ። የራበውና ቤተሰብ ማስተዳደር ያለበት ሰው ህሊናውን ሸጦ፣ የማያምንበትን ሀሳብ እያራመደ ዳቦ ይገዛ ዘንድ የሚያስገድደውን የተጨማለቀ ሲስተም ፍንትው አደረገልኝ።
 
የተማሩና አገር ውስጥ መስራት ያልቻሉ ብዙ ሰዎች ለስደት ወጥተው በየበረሀው ቀርተዋል። የቀናቸውም በየሰው አገሩ ተበትነዋል። እንኳን የማይችሉትን ልዩ ነገር ለመሞከር ቀርቶ፣ የሚችሉትን ልዩ ነገር መስራት እንዳይችሉ በሀሳብ ልዩነታቸውና በፖለቲካ ተሳትፎአቸው የተነሳ ከየእስር ቤቱ ፍርግርግ ጀርባ የተወረወሩም ሞልተዋል። መንግስትን የሚቃወም መፈክር ያዛችሁ ተብለው ከዩኒቨርስቲ ትምህርት ገበታቸው ሳይቀር ተፈናቅለው ጥቃት የተፈጸመባቸውም አሉ። በየጎዳናው ለሰላማዊ ሰልፍ ወጥተው በግፍ ደማቸው የሚንዠቀዠቅ ወጣቶችም አይቆጠሩም። በአንጻሩ ደግሞ፥ የፖለቲካ ታማኝነትንና ዝምድናን ተገን አድርገው፥ ሳያንኳኩ፣ በተኙበት በሮች ተከፍተውላቸው ከቤት የሚጠሩ ቦርጫሞች አሉ። ይኼን ይኼን ሁሉ ሮቤል አሳየልኝ።
 
በአትሌቲክሱ እንኳን ብንመለከት፥ ብዙ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ለሌላ አገር ባንዲራ እየሮጡ ነው። ከአገር ቤት የሚገፉት፥ እንዲህ እንደሮቤልና አባቱ ያሉ የኅሊና ቦርጫሞች እየተመረጡባቸው ነው። ይህኔ፥ እሱ ቀፈቱን ለዓለም ባሳየበት ቅጽበት ቅስማቸው ተሰብሮ የስደት በርን ያማተሩ ብዙ ዋናተኞች ይኖራሉ። በሌላውም ዘርፍ እንዲሁ። ….እንጦጦ ሄደሽ ብትወድቂ ብትነሺ፣ አገር እቅፉን በሚደንቅ ብቃት ብትሮጪ፥ አትሌቲክስ ማኅበሩ ዙሪያ ዘመድ ከሌለሽ ማንም አያይሽም። ብለሽ ብለሽ ሲመርሽ፥ እዚያ ለሚሮጡት ጀላቲና ቀዝቃዛ ውሀ በመሸጥ ራስሽን ለማስተዳደር ትሞክሪ ይሆናል። …ይኼን ይኼን ሁሉ ብዙ ሳያወራ አሳየልኝ።
 
ሮቤል አገራችንን በዋና ለመወከል ወጥቶ፥ በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ወክሎን ለዓለም አሳይቶልናል፣ እዚሁ እያለንም ለተጋረደብን ሰዎች ነገሮችን ገላልጦልናልና፥ ከእርሱ ይልቅ ፈልቅቆ ባሳየን አገር ላይ ዐይናችንን እንጣል።
 
የእርሱ ቦርጩን ማዝረክረክ የማሳፈሩን ያህል፣ የብዙ ቀልዶች መፈጠር ምክንያት ቢሆንም፥ እሱ እሱ እንዳያዘናጋንና መብታችንን ከመጠየቅ (ቢያንስ መበደላችንን በቅጡ ከመገንዘብ) እንዳያዘናጋን።
 
#Ethiopia #StopKillingCivilians